Saturday, December 27, 2014

አንድነትና ምርጫ ቦርድ


ዛሬ በምርጫ ቦርድ ጉዳይ ለመፃፍ ያነሳሳኝ ነገር ማንም ይረዳዋል ብዬ አምናለሁ፡፡ ፀረ አንድነት ዘመቻ ከተጀመረ ቢቆይም እያለፈ እያለፈ ብቅ ማለቱ ብዥታ ስለፈጠረብኝ ነው፡፡ ምርጫ ቦርድ ከአንድነት ጋር የሚያድርግ ያለውን ዝርዝር ከማውራቴ በፊት ግን ለአንባቢ ማስጨበጥ ያለብኝ ነገር አለ፡፡ አንድነት ፓርቲ ምርጫ እሳተፋለሁ ሲል ምን ማለቱ ነው? የሚለውን ብዙዎች እነደፈለጉ ይልቁንም እነሱ ለመረጡት የሰነፍ መንገድ በሚመቻቸው መንገድ እየተረጎሙት ይገኛል፡፡
አንድነት ፓርቲ ምርጫ እገባለሁ ብሎ ሲወስን አንድነት በምንም መመዘኛ ከገዢው ፓርቲም ሆነ ከመንግሰት መዋቅሮች የተለየ ድጋፍ አገኛለሁ ብሎ በማሰብ አይደለም፡፡ ምርጫ ቦርድን ጨምሮ ማለት ነው፡፡ ይልቁንም አሁን ባለው ሁኔታ ማለትም ከዋና አዛዣቸው የቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትር እልፈት በኋላ ለመጀሚረያ ጊዜ የሚያካሂዱትን ሀገራዊ ምርጫ ከቀድሞ በተለየ ለመሸነፍ ዝግጁ ይሆናሉ ብሎ ማሰብ አይቻልም፡፡ ማለትም በ1997 እንዳደረጉት ለሙከራም ቢሆን የጫወታ ሜዳውን ሊከፍቱት አይችሉም፡፡ ባጠቃላይ የአንድነት ፓርቲ ግምገማ ገዢው ፓርቲ ከምን ጊዜውም በላይ ዘግቶ መጫወት እንደሚፈልግ ከግንዛቤ ያሰገባ ነው፡፡ ሰለዚህ መድረኮች በቅርቡ እንዳሉት እንዲሁም አንድ እንድ ፓርቲዎች ሲሉት እንደነበረው ኢህአዴግ በሩን ለውይይት የዘጋው እንደ አንድነት ፓርቲ ምርጫ እንገባለን ስለአልን አይደለም፡፡ ኢህአዴግ አሁን ካለበት ነባራዊ ሁኔታ ተነስቶ ምንም ክፍተት እንደማይሰጥ በመረዳት ከወዲሁ መላውን ህዝብ አንቀሳቅሰን ለማስከፍት የወሰንን መሆኑን ማውቅ ይኖርባቸዋል፡፡
አንድነት ምርጫ እሳተፋለሁ ሲል ደግሞ ለተሳትፎ እንዳልሆነ ደግሞ ሁሉም ያውቀዋል፡፡ የመጀመሪያው በር ማስከፈቻው ደግሞ ህዝቡ አማራጭ የለም ከሚል ፕሮፓጋንዳ እንዲላቀቅ በማድረግ አማራጭ ማሳየት ዋነኛው ሲሆን፣ አማራጭ መኖሩን ከተረዳ ደግሞ በነቂስ ወጥቶ ለመራጭነት እንዲመዘገበ፣ እንዲመርጥ እና ድምፁን እንዲያስከብር ማስተማር ነው፡፡ ይህ ደግሞ በሩን ክፈቱ ከሚል ጉንጭ አልፋ ጭቅጭቅ ተላቀን እንዴት እንክፈተው ላይ ማተኮር የሚል ስትራቴጂ ነው፡፡ ሚሊዮኖች በዚህ መስመር ከተሰለፉ ደግሞ ማንም ውሳኔያቸውን እንደማይቀለብስ እርግጠኞች ነን፡፡ ይህ ደግሞ በህዝብ ኃያልነት መተማመን ነው፡፡ ህዝቡ ከተባበረ ይህን በመንግሰት መዋቅሮች የሚደርሰውን አፈና ሊበጥሰው እንደሚችል ማመን ይኖርብናል፡፡ ከሌሎች ፓርቲዎች ጋር የምንለየው በዚህ ነው፡፡ ሌሎች ኢህአዴግ በሩን ይክፈትና እንግባ ሲሉ እኛ ደግሞ ከፍተን እንግባ ብለናል፡፡ ኢህአዴግ ልብ ቢገዛና ሜዳውን ለሁሉም እኩል እንዲሆን ቢያደርገው ምርጫው ፍጥጫ ሳይኖርበት ሊጠናቀቅ እንደሚችል የሁላችንም እምነት ነው፡፡ በነገራችን ላይ በሩን ከፍተን እንግባ ያልነው እኛ ብቻ አይደለንምን የሀይል አማራጭ የሚከተሉትም ይህን ከፍቶ መግባት ይስማሙበታል፡፡ ልዩነታችን እኛ በሰላማዊ መንገድ ህዝብን አስተባብሮ ማሰከፈት እና መግባት ይቻላል ማለታችን ነው፡፡
ወደ ምርጫ ቦርድ ጉዳይ ስንመለስ፣ ምርጫ ቦርድ አንድነትን ምን አድርግ እያለው እንደሆነ ለሁላችን ግልፅ አይደለም፡፡ ከምርጫ ቦርድ ሰዎች ጋር በግንባር ቀርበን ስንወያይ በአክብሮት እንደሚያስተናግዱን መካድ ተገቢ አይደለም፡፡ ይሁን እንጂ በተለያየ ጊዜ በሚዲያ ብቅ እያሉ የሚሰጡት መግለጫ ስንመለከት አንድነት ፓርቲን ለምን በዚህ ደረጃ እንደሚፈታተኑት ለመረዳት ይከብዳል፡፡ በቅርቡ በአንድነት ውስጥ በአመራር አሰያየም ችግር እንዳለ አስመስለው ያቀረቡት ነገር በጣሙን አሳኝ ብቻ ሳይሆን በተለይ አንድነት ፓርቲ የህዝብ ታዛቢዎች ምርጫን በንቃት ለመሳተፍ በቂ ዝግጅት አድርጎ መንቀሳቀስ በጀመረበት ወቅት መሆኑ ጋር ተራ ግጥምጥሞሽ ነው ለማለት አያስደፍርም፡፡ ከዚህ ጋር ተያይዞ የምርጫ ቦርድ ከዚህ ቀደም እንደሚያደርገው በሚዲያ ምንም ዓይነት ቅስቀሳ ሳያካሂድ፣ በየሰፈሩም የህዝብ ታዛቢ ምርጫ እንደሚካሄድ በይፋ ጥሪ ሳይደረግ፣ በሚስጥር በደብዳቤ በተጠሩ የቀበሌ ነዋሪዎች የህዝብ ታዛቢ ምርጫ ማድረጉን ስንታዘብ፣ ምርጫው ፕሮፌስር መርጊያ በቃና በተደጋጋሚ ምርጫን በተሻለ ሁኔታ ለማካሄድ አቅም ፈጥረናል ይበሉ እንጂ ሁሉንም እኩል ለማጫወት ዝግጁ ናቸው ብለን ለማለት አቅም እያነሰን፣ እነሱም እምነታችንን እየሸረሸሩት ይገኛል፡፡
ምርጫ ቦርድ አንድነት ፓርቲን ከሌሎች ፓርቲ በተለየ ሁኔታ የጠቅላላ ጉባዔ አባላትን ብዛት አሰገቡ ይህም በደንባችሁ ውስጥ ይካተት ብሎ ሲል በግልፅ ባይሆንም በገደምዳሜ ጠቅላላ ጉባዔ ካልጠራችሁ ይህን ማድረግ አትችሉም ማለቱ ነበር፡፡ አንድ ዓመት ባልሞላ ጊዜ ደግሞ አንድ ተቃዋሚ ፓርቲ ይህን ማድረግ አይችልም የሚል ታሳቢ ያደረጉ ይመስላል፡፡ አንድነት ግን ይህን ግምት መና ባስቀረ መልኩ ጠቅላላ ጉባዔ ጠርቶ በደመቀ ሁኔታ ለ2007 ምርጫ መሰረት ጥሎ ሲለያይ ምርጫ ቦርድ እሰይ ተፎካካሪ የሚሆን ፓርቲ መጣ ብሎ መደሰት ሲገባው በተራ የአስተዳድር ስራዎች መሰረት አድርጎ ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥቶ በሳምንት ጊዜ እንድታስታውቁ የሚል ማስጠንቀቂያ አዘል መልዕክት በማስተላለፍ ህዝቡን ግራ ማጋባት ተገቢ እንቅስቃሴ አይደለም፡፡ ይህን ጉልበታቸውን ለፓርቲዎች አቅም ግንባታ ቢያውሉት የሚጠቀሙ ይመስለኛል፡፡ ሀገርም ከዚህ ይጠቀማል፡፡
አንባቢ እንዲረዳ የምንፈልገው ዋና ቁምነገር አንድነት ፓርቲ እንደ ፓርቲ ሁሉንም ህጋዊ መስመሮች አሟልቶ በተደጋጋሚ በሆደ ሰፊነትና በቅንነት በህግ ከሚጠበቅብን በላይ በመሄድ ከግብግብ ግንኙነት ወደ ውይይት ለማምረት ሙካራ እያደረግን መሆኑን አውቆ አንድም የህግ ክፍተት ፈጥረን ከጫወታ ለመውጣት ሰበብ እንደማንሰጣቸው ነው፡፡ ይህ ማለት ግን እንዲያንበረክኩን እድል እንሰጣለን ማለት አይደለም፡፡ ለማነኛውም ምርጫ ቦርድ ህዳር 19 ቀን በፃፈልን ደብዳቤ መሰረት የሚጠበቅብን የጠቅላላ ጉባዔ ቁጥር በደንብ አካታችሁ አምጡ የሚል ሲሆን ይህን ደግሞ ታህሳስ 3 የተሰበሰበው ጠቅላላ ጉባዔ እንዲካተት አድርጎ ሪፖርቱ ታህሳስ 10 2007 ለቦርዱ ፅ/ቤት ገቢ ተደርጎዋል፡፡ ታህሳስ 10 ማለት ቦርድ ስብሰባ ያደረገበት ዕለት እና በሚዲያ የቀረበበት ቀን ስለሆነ ሪፖርቱን ከማየቱ በፊት ያሳለፈው ውሳኔ ነው ብለን በቅን ልቦና በመውሰድ በህዝቡ ዘንድ የፈጠሩት ብዥታ በሚያጠራ መልኩ የፈለጉት ሪፖርት በአንድነት በኩል የቀረበ መሆኑን በሚዲያ ይገልፃሉ ብለን አሁንም በቅንነት እንጠብቃልን፡፡
አንድነት ፓርቲ ላይ ምርጫ ቦርድ ከዚህም የከፋ ጫና ሊያደርስብን እንደሚችል መጠበቅ ትጥቃችንን ጠበቅ ለማድረግ እንደሚረዳን መገንዘብ አለብን፡፡ በቀጣይ በሚኖሩት ተደጋጋሚ ምርጫ ተኮር እንቅስቃሴዎች በቁጥር ብዙ የሚባሉ ለውጤት ሳይሆን ለተሳትፎ የሚገቡ ፓርቲዎች ይህን ጫና ለማድረግ አብረው መሰለፋቸውም የግድ ነው፡፡ ለለውጥ የተነሳው ህዝብ ግን ትኩረቱን ማን ላይ ማድረግ እንዳለበት ግን ጠንቅቶ ያውቃል፡፡ በቅርቡ በምርጫ ቦርድ በተሰጠው የሚዲያ መግለጫም አብዛኛው ሕዝብ ይህ ዘመቻ አንድነት ላይ ለምን በዛ? ብሎ ጠይቆዋል፡፡ መልሱም ግልፅ ነው፡፡ አንድነት ፓርቲ ቁርጥ አቋም ይዞዋል፣ በቀጣይ ምርጫ ሚሊዮኖች ተንቀሳቅሰው ድምፃቸውን ይስጣሉ፣ የሰጡትን ድምፅ ደግሞ ያስከብራሉ ብሎ ያምናል፡፡ አምሳ ሎሚ ለአንድ ሰው ሸክሙ ለአምሳ ሰው ጌጡ እንደሚባለው፣ አንድነት ፓርቲ እያንዳንዱ ዜጋ ነፃነቱን ለማስከበር ዘብ ከቆመ የሚሊዮኖች ድምፅ ይከበራል ብሎ በማመን የኢትዮጵያ ህዝብ ታሪክ እንዲሰራ ምቹ ሁኔታ እየፈጠረ ይገኛል፡፡
ቀኝ ኋላ ዙር ሊሉ የሚፈልጉትን በሙሉ ወደፊት በማለት ለማሸነፍ የስነ ልቦና ዝግጅት እናድርግ እላለሁ፡፡ ምርጫ የገባ ነው ምርጫ ቦርድን አምነን ሳይሆን የህዝብን ሀያልነት ተገንዝበን ስለሆነ ማሸነፋችን ሳይታልም የተፈታ ነው፡፡ መንገዱ ምንም ያህል ጎርባጣ ቢሆንም ለድል የተነሳን መንፈስ ማሸነፍ ይከብዳል፡፡ ይቻላል ብለን እንደጀመርነው ከግብ ለማድረስ ቀበቶዋችንን ጠበቅ ነው፡፡ ቀላል ነው፣ የመጀመሪያው ሰራ ለመራጭነት መመዝገብ ነው፡፡ ቀዳሚ ይሁኑ ካርዶን በእጆ ያስገቡ!!!
ቸር ይግጠመን!!!!


Saturday, December 20, 2014

ጀግኖቻችን እና የፍርድ ቤት ነፃነት!!!

ግርማ ሠይፉ ማሩ
girmaseifu32@yahoo.com; girmaseifu.blogspot,com
በቅርቡ የሚካሄደውን የ2007 ምርጫን  አስመልክቶ የፓርቲዎችን ዝግጅት ምን እንደሚመስል ለመረዳት ኢህአዴግ፣ አንድነት እና ኢዴፓ የወከሉ ሰዎች በፋና ሬዲዮ ባለፈው እሁድ ውይይት አድርገው ነበር፡፡ መኖሩ ትርጉም ስለአልነበረው ነው እንጂ ሌላም አንድ ፓርቲ ወክያለሁ ያለ ሰው እንደነበር ዘንግቼው አይደለም፡፡ የኢህአዴጉ ወኪል በመጨረሻ ላይ ያቀረቡትን ሃሳብ ሳደምጥ የኢህአዴግ ፓርቲ ወኪል ማንም ቢሆን ተመሳሳይ እንደሆነ መረዳት የምንችለው ነገር አንዳቸውም በተነገራቸው እንጂ በራሳቸው መርምረው ሊደርሱበት የሚፈልጉት ሀቅ ያለ አይመስለኝም፡፡ በፓርቲው ስብሰባ ከሚሰበካቸው ውጭ ዋነኛ የመረጃ ምንጫቸው የኢትዮጰያ ሬዲዮና ቴሌቪዥን ገፋ ሲል ደግሞ ፋና ናቸው፡፡ እንደዚህ ዓይነት መደምደሚያ ላይ እንድደርስ ያደረገኝ ነጥብ ደግሞ የአንድነት ምክትል ፕሬዝዳንት እና የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ ሆኖ ሲሰራ የነበረው አንዱዓም አራጌ እና ሌሎች የህሊና እሰረኞች ላይ የተፈረደውን የፍርድ ቤት ውሳኔ መቀበልና አለመቀበል ከፍርድ ቤት ነፃነትና ለፍርድ ቤት እውቅና ከመስጠት ጋር ማያያዛቸው ነው፡፡ በፍርድ ቤት ውሳኔ ባለመስማማት የምንይዘውን አቋም መረጃ የሌለው ነው ብለው የሚያቀርቡት ጉንጭ አልፋ  ክርክር እጅግ አስገራሚ ነው፡፡
ከዚህ ቀደም አንዱዓለም አራጌ ይፈታ በሚል አንድ ፅሁፍ ፅፌ ነበር አንዱዓለም የታሰረው በ “አሸባሪነት” ነው ለሚሉን መስሚያ የሌለን መሆኑን ብቻ አይደለም የታሰረው የኢህአዴግ ጉምቱ ባለስልጣናት ከእቅዳቸው በፊት ከስልጣን የሚነቀንቃቸው ሰላማዊ ታጋይ መሆኑን በመጠርጠራቸው ነው የሚል ነበር፡፡ ብዙዎች እንደሚስማሙት ደግሞ በምርጫ ሁለት ሺ ሁለት ክርክር ወቅት ተናዳፊ ተከራካሪ ሆኖ በመቅረቡ ነው፡፡ በብዙዎች ዘንድ አንዱዓለም ንቢቱን አስንቆ በስልጣን ሲናገሩ የነበሩትን በመረጃ አስደግፉ ሲያጋልጣቸው ቂም ይዘው እንደሆነ ይታመናል፡፡ ይህን እንድንገምት ያደረገን ደግሞ አንዱዓለም በተከሰሰበት ወንጀል ለዕድሜ ልክ እስር አይደለም ለምክር የሚገብዝ ጥፋት ማጥፋቱን የሚያስረዳ ማስረጃም አልቀረበበትም ምስክርም አልተሰማበትም፡፡ አዳፍኔ ምስክሮችም ቢሆኑ ከእስር ቤት ለመውጣት ቃል የሰጡ ቢሆንም በፍርድ ቤት ገብተው ግን አንዱዓለም ለሸብር ተግባር ወጣት ሲያደረጅ ነበር ብለው ሊመስክሩ አልቻሉም፡፡ የኢህአዴግ ሹሞች በቦታው አልነበሩም፤ እኛ ግን በቦታው ነበርን፡፡
ፍርድ ቤት ውሳኔ የሰጠበት መዝገብ በአሁኑ ወቅት ማንም ሰው ሊያገኘው እንደሚችል ግልፅ ነው፡፡ የኢህአዴግ አባላትና ሹማምንት ደግሞ ይህን መረጃ ለማግኘት ከማነኛችንም በላይ እድሉ አላቸው፡፡ እነዚህ የኢህአዴግ አባላትና ባለስልጣናት ይህን የምናቀርበውን ጩኽት ልክ መሆኑን ለማጣራት ለምን ይህን የፍርድ ቤት መዝገብ መርምረው አቋም አይዙም? የሚል ብርቱ ጥያቄ ማቅረብ እፈልጋለሁ፡፡ እነዚህ ሹሞች ከላይ እንደገለፅኩት በኢህአዴግ ስብሰባ ወቅት ከሚሰሙት ማብራሪያ እና በመንግሰት ሚዲያ ከሚሰሙት ውጭ ሌላ ነገር አንብበው ለመረዳት ዝግጁ አይደሉም፡፡ የኢህአዴግ ደጋፊዎች ቢሆኑም ከዚህ ጭፍን መስመር ውጭ አይደሉም፡፡ አንዱዓለም ይፈታ በሚል በፃፍኩት ፅሁፍ እንዲ ብዬ ነበር፤
“መደበቅ የሌለብኝ ዕውነት ግን ከአንዱዓለም ጋር ከምናደርገው የሠላማዊ ትግል ውይይት (አንዳንዴም ጭቅጭቅ የሚባል ቦታ ሊደርስ የሚችል) በተቃራኒ አንድ የሆነ ሠይጣን አሳስቶት - ይህ ሠይጣን ኢህአዴግ ሊሆን ይችላል፤ ማለትም የሠላማዊ መንገዱን ሁሉ እያጠበበ ያለ ከመሆኑ ጋር ተያይዞ - አንዱዓለም ተገዶ ሌላ አማራጭ ፍለጋ ሄዶ ይሆን በሚል የመረጃ ፍለጋ ጉጉቴ አልጨመረም ልላችሁ አልችልም፡፡”
ይህ የሚያሳየው አንዱዓለም ጓደኛ የትግል ጓዴ ቢሆንም ሊሳሳት ይችላል ብዬ መጠራጠሬ አልቀረም ነበር፡፡ ሟቹ ጠቅላይ ሚኒስትርም ክምር ማስረጃ አለ ብለውን ነበር፡፡ ፍርድ ቤት ከቀረበው ማስረጃ እና ከቀረቡት ምስክሮች ግን አንድም ውሃ የሚቋጥር ነገር ስናጣ፤ ክምር ቀርቶ አንድ ገፅ ወረቀት ሲጠፋ ፍርድ ቤት ወስኖዋል ብለን ከህሊናችን ጋር ተጋጭተን እንደ ኢህአዴጎቹ አንዱዓለም አሽባሪ ነው እንድንል መፈለጋቸው አስገራሚ ብቻ ሳይሆን እነዚህ የኢህአዴግ ሹሞች እንዴት አድርገው እንደሚሰሯቸው መረዳት አስቸጋሪ ነው፡፡
ይህን ሁሉ በድጋሚ እንድል ያስባለኝ ኢህአዴግን ወክሎ የቀረበው የውይየት ተሳታፊ “በእስር ቤት የሚገኙትን አመራሮችና አባሎች ጅግኖቻችን ማለታችሁ አሁንም በሁለት ሺ ሰባት ምርጫ ህጋዊና ህገወጥ መስመር እያጣቀሳችሁ ለመሄድ ያላችሁን ዝግጅት የሚያሳይ ነው፡፡” የሚል አስተያየት ሲሰጡ መስማቴ ነው፡፡ የሁለት ሺ ሰባት ምርጫ ሰላማዊ ሊሆን የሚችለው ሀቅን በመደፍጠጥ እና ፍርድ ገምድል ውሳኔን አሜን ብሎ በመቀበል ሳይሆን ኢህአዴግ በስልጣኑ የመጡበትን ያለምንም ይልኝታ እድሜ ልክም ቢሆን እስር ቤት ለመጎር ደንታ የሌለው መሆኑን በማጋለጥ ነው፡፡ ይህንን ሀቅ ለመመርመር ድፍረት ያገኙ የኢህአዴግ አባላትም ሆኖ ሹሞች በዚህ አይነት ስርዓት ማንም ተጠቃሚ እንደማይሆን ለመረዳት አይቸገሩም፡፡ ይህን ስርዓት በመለወጥ የሚገኘው ትንሳኤ ማንም በግፍና በፍርደ ገምድል ውሳኔ ሰጋት ላይ እንዳይወድቅ የሚያድርግ ነው፡፡ የዚህ ደግሞ ትሩፋት ለኢህአዴግ አባላትም የሚሆን ነው፡፡
የኢህአደግ ሹሞች በዚህ ዓይነት ውይይት ወቅት ከፓርቲያቸው በተቃራኒ መስመር ይቁሙ የምል የዋሃ አይደለሁም፡፡ ይልቁንም እነዚህን ነጥቦች መከራከሪያ ሆኖ ቢመጣ እንኳን ችላ ብለው በማለፍ ከትዝብት ሊተርፉ ይቻላሉ የሚል እምነት ስለ አለኝ ነው፡፡ በሀገራችን ያሉትን ተቋሞች የምናከብራቸው በህንፃቸው ግዝፈት ወይም በቀጠሩት የስው ሀይል ብዛት ሊሆን አይችልም፡፡ ፍርድ ቤቶች ሊከበሩ የሚችሉት በሚያሰፍኑት ፍትህ ነው፡፡ ዜጎች መብቴ ፍርድ ቤት ሄጁ አስከብራለሁ የሚል ደረጃ ሲደርሱ ነው፡፡ በሀገራችን ያለው የፍትህ ስርዓት ፖለቲካ ነክ በሆኑ ጉዳዮች ብቻ ሳይሆን በቤተስብ ውርስ ጉዳይ እንኳን አፋጣኝ ፍትህ የሚሰጥ አይደለም፡፡ በፍትሃብሔር ጉዳይም ቢሆን በዓለም አቀፍ ደረጃ የሚሰጠው ደረጃ የወረደ ነው፡፡ ይህ እንዲሻሻል ማሳሰብ እና መታገል ፍርድ ቤቶቸን እውቅና እንደመንፈግ መቁጠር ተገቢ ነው ለማለት አይቻለም፡፡ በተመሳሳይ ፍርድ ገምድል ውሳኔዎችን እንድንቀበል መገደድም የለብንም፤ ብንገደድም ሊሳካ የሚችል አይደለም፡፡ ለዚህ ነው የህሊና እስረኞችን ጅግኖቻችን የምንለው፡፡
እኔም እላለሁ የአንድነት ፓርቲ አባላት ላይ እየተለጠፈ ያለው “የአሸባሪነት” ታፔላ በፍጹም ተቀባይነት እንደሌለው ደግመን ደጋግመን ማሳሰብ እንፈልጋልን፤ መፍተሔውም ፖለቲካዊ ውሳኔ በመስጠት መፍታት እና ለሰላማዊ ትግል የፖለቲካ ምዕዳሩን ማስፋት ነው፡፡ የሰላማዊ ትግል መድረኩ በጠበበ ቁጥር ደግሞ ዜጎች አማራጭ የትግል ስልት መፈለጋቸው የግድ ነው፡፡ በጠረጴዛ ላይ ያለው ሌላኛው አማራጭ ሀገርን ህዝብን ከመጉዳት ውጭ ገዢዎችንም ሊጠቅማቸው የሚችልበት አንድም መንገድ አይታይም፡፡ ሁሉም አሽናፊ ሆኖ የሚወጣበት ስርዓት መዘርጋት ለፍትህ ስርዓቱም ትንሳኤ ስለሚሆን ጅግኖቻችንን በመፍታት ለፍትህ ስርዓቱ ትንሳኤ በጋራ እንድንቆም መንግሰት ኃላፊነት አለበት፡፡
ምርጫ ሁለት ሺ ሰባት ለለውጥ!!!
ቸር ይግጠመን



Sunday, December 14, 2014

ህገ መንግሰቱን የሚንደው ማን ነው?




ግርማ ሠይፉ ማሩ
girmaseifu32@yahoo.com; girmaseifu.blogspot.com
በአገባደድነው ሳምንት መጀመሪያ ህዳር 29 ቀን በከፍተኛ የገንዘብ ወጪ ብቻ ሳይሆን በከፍተኛ የፕሮፓጋንዳ ዘመቻ የ “ብሔር ፣ብሔረሰቦች እና ህዝቦች”  ቀን ተክብሮ ውሎዋል፡፡ “ብሔር፣ ብሔረሰቦች፣ ህዝቦች” የሚሉት ሶሰት ቃላቶች ቢሆኑም በህገ መንግስት ውስጥ አንድ ትርጉም የተሰጣቸው ቢሆንም ባለቤቶች ነን የሚሉትም ቢሆኑ በውል ያልተረዷቸው ተምኔታዊ ነገሮች ናቸው፡፡ ወጣም ወረደ ግን እነዚህ ቃላቶች በኢትዮጵያ ፖለቲካ ውስጥ ጉልዕ ቦታ ያላቸው እንዲሆኑ ተደርገዋል፡፡ እኛም እነዚህን ቃላቶች በኢትዮጵያ ፖለቲካ ጉልዕ ቦታ የያዞ መሆናቸውን አምነን ተቀብለናል፡፡ ይህ ማለት ግን ገብቶናል ማለት አይደለም፡፡ ይህ በየክልሉ በዙር የሚከበረው ባህል ታስቦበት ህገ መንግሰት ከጸደቀበት እለት ጋር የተገናኘ ስለሆነ እለቱን ከህገ መንግሰት ጋር የተያያዙ ጉዳዮች የሚነሱበት ብናደርገው ክፋት የለውም፡፡ ስለዚህ ባለፉት 20 ዓመታት ይህ ህገ መንግሰት ምን ሰጠን ምንስ ነፈገን ብለን መጠየቅ እና የተወሰኑ ማሳያዎች ማቅረብ ተገቢነት ያለው ይመስለኛል፡፡
ጠበቃ ተማም አባቡልጉ ባለፈው ሳምንት ዕትም በሰጠው ቃለ ምልልስ ላይ እንዳስቀመጠው ህገ መንግሰታችን ተገቢ ባልሆነ ሁኔታ የህግ ግዴታ ለማይጣልባቸው “ብሔር፣ ብሔረሰቦችና ህዝቦች” ለሚባል ሃሳባዊ ስብስብ ተሰጥቶ ህገ መንግሰቱ የናንተ ነው ተብለዋል፡፡ በዚህም የተነሳ ህገመንግሰቱ የማንም እንዳይሆን ተደርጎዋል ብሎናል፡፡ ይህ የሆነው ግን በስህተት የሚመስለው ካለ ተሳስቶዋል፡፡ የማንም ያልሆነን ማለትም ባለቤት የሌለወን ነገር በአደራ ለመጠበቅ በሚል ለረዥም ጊዜ በስልጣን ለመቆየት የተደረገ ደባ እንደሆነ መረዳት ተገቢ ይመስለኛል፡፡ የዚህን ሴራ ማሳያ የሚሆን ምሳሌ ከዚህ በታች ማቅረብ ጉዳዩን ግልፅ ያደርገዋል፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ በፕሬዝዳንትነት የጀመሩትን በታሪክ አጋጣሚ የተገኘ ሀገር የመምራት ተልዕኮ ወደ ጠቅላይ ሚኒስትርነት ሲያወርዱት በፕሬዘደንታዊ ስርዓት (በቀጥታ የህዝብ ምርጫ ስልጣን የሚይዝ) ፕሬዝዳንት መሆን ጠልተው አይደለም፡፡ በዛን ጊዜ በነበረው ነባራዊ ሁኔታ አቶ መለስ ዜናዊን ማንም ሀገር ወዳድ ተነስቶ ዕጩ ሆኖ ቢቀርብ ሊያሸንፋቻው እንደሚችል ስለሚያውቁ ከዚህ የተለየ አደረጃጀት መከተል ነበረባቸው፡፡ ይህም በድርጅታዊ አሰራር በሚስጥር ጠቅላይ ሚኒስትር መሆን የሚያሰችል ዘዴ መከተል ነው፡፡ ይህ ህውሃት እንደ ቡድን አቶ መለስ ዜናዊ በግል ያለባቸውን ያለመመረጥ ስጋት ካነሱት ነጥቦች አንዱ በ1987 አይደለም ዛሬ ከሃያ ዓመት በኋላ ኢትዮጵያዊያን የባህር በር አጥተው መታነቃቸውን ለመዘንጋት አልተቻላቸውም፡፡
ከዓለም የባህር በር ከሌላቸው ሀገሮች በህዝብ ብዛት አንደኛ መሆናችን ብቻ ሳይሆን በቅርብ ርቀት በባሕር በር ላይ ተገኝተን የበይ ተመልካች መሆናችን ታሪክ ይቅር የሚለው ስህተት አይደለም፡፡ የዚህ ታሪካዊ ስህተት መሃንዲስ ደግሞ ሟቹ ጠቅላይ ሚኒስትር ናቸው፡፡ ሌላው የቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትር የኢትዮ-ኤርትራ የወንድማማቾች ጦርነት ተከትሎ ህዝቡ ለባንዲራ ያሳየውን ፍቅር ተመልክተው የባንዲራ ቀን እንዲከበር አረንጓዴ መብራት ቢያሳዩም፤ እራሳቸው በስታዲየም ተገኝተው “ጨርቅ” ነው ብለው ያጣጣሉትን ባንዲራ በክብር ቢሰቅሉትም ህዝቡ ባንዲራ “ጨርቅ” ነው የሚለውን የአፍ ወለምታ ሊዘነጋው አልተቻለውም፡፡ በእነዚ እና ሌሎች ብዙ ምክንያቶች የኢትዮጵያ ህገ መንግሰት ዜጎች በቀጥታ የሚመራቸውን መሪ እንዳይመርጡ ያደረገ ህገ መንግስት ነው፡፡
ባንዲራን በሚመለከት የኢትዮጵያ ህገ መንግሰት በግልፅ የኢትዮጵያ ባንዲራ አረንጓዴ፣ ቢጫና ቀይ ነው ብሎ ደንግጓል፡፡ በተጨማሪም አርማ እንደሚኖረው ይደነግጋል፡፡ አርማው ላይ ካልተስማማን በሚያስማማን የባንዲራው ይዘት ላይ አብረን መቆም እንችላለን፡፡ በግሌ ከዚህ ቀደም ከነበሩት አርማዎች የአሁኑ የተሻለ ነው የሚል እምነት ቢኖረኝም ሁሉም ዜጋ ይህ አርማ የሌለበት ባንዲራ መያዝ አለበት የሚለውን ህገ ወጥ የህግ ድንጋጌ ግን ለመቀበል እቸገራለሁ፡፡ መንግሰት በኤምባሴዎች፣ በመንግሰት ተቋማት አርማዬ ያለውን የማድረግ ግዴታ ቢጥል ግድ የለኝም፡፡ በግል አርማ ካላደረጋችሁ የሚል አስገዳጅ ህግ ማውጣት ግን መንግሰት ጉልበተኛነቱን ለማሳየት ካልሆነ በስተቀር ይህ አርማ ከልብ የሚፃፍ እና በፍቅር ሊወደቅለት የሚችል ሊያደርገው አይችልም፡፡
በሌላ በኩል የኢትዮጵያ ህገ መንግሰት ከማነኛውም ጊዜ እና ምን አልባትም በፅሁፍ ደረጃ ከማንም ሀገር በተለየ የሰብዓዊ መብት ድንጋጌዎች ህገ መንግስታዊ ዕውቅና የሰጠ ነው ቢባል ማገነን አይሆንም፡፡ ምን ያደርጋል እነዚህ ድንጋጌዎች በወረቀት ላይ የቀሩ ናቸው፡፡ በደም የተፃፈ የሚባለው ህገ መንግሰት በቾክ እንደተፃፈ መቁጠር የተሳናቸው የመንግስት ሹሞች እንደ አፈተታቸው ሲደፈጥጡት ይታያሉ፡፡ ዜጎችን በአደባባይ ከመደብደብ ጀምሮ በዓለም ላይ የቀረ ቶርች የሚደረግባት ሀገር ኢትዮጵያ ነች፡፡ በህገ መንግሰት እውቅና ያገኘን የሰብዓዊ መብት ድንጋጌዎች በ “ፀረ ሽብር ህግ” ተደምስሶዋል፡፡ የሰው ልጅ ክቡርነት ዋጋ አጥቶ በህዝብ ስም ስልጣን ለማቆየት ምንም ዓይነት እርምጃ የሚወሰድባት ሀገር ሆናለች፡፡ ይህ ደግሞ ባለበቤት የሌለው ህገ መንግሰት ያመጣው ትሩፋት ነው፡፡ የህገ መንግሰት ባለቤት የተባሉት “ብሔር፣ ብሔረሰቦችና ህዝቦች” የህግ ተጠያቂነት የሌለባቸው ብቻ ሳይሆኑ ሰብዓዊነትም የሌላቸው ስለሆኑ መብታችን ተነካ ሊሉ አይችሉም፡፡ እስር ቤት አይገቡም፡፡ የሚታሰረው ሰው ነው፤ ሰብዓዊ መብቱ የሚጣሰውም ሰው ነው፡፡ ዜጋው የህገ መንግስት ባለቤት ለመሆን በቡድን ውስጥ መገኘት የግድ ይለዋል፡፡ እኔ ለምሳሌ እነዚህ ቡድኖች ውስጥ ለመገኘት ፍላጎትም ምኞትም ስለሌለኝ ይህ ህገ መንግሰት የእኔ ነው ብዬ በግድ የራሴ ለማድረግ ከመታገል ውጭ ሌላ አማራጭ የለኝም፡፡
ገዢው ፓርቲ በቡድናዊ አስተሳሰቡ በመወጠሩ የእኔ ዓይነት አመለካከት ያላቸውን ሰዎች ህገ መንግሰቱ የእኛ እንዲሆን የምናደርገውን ጥረት ህገ መንግሰት መናድ ነው ብሎ የቡድን ጠብ ለማስነሳት ይታትራል፡፡ በዚህ ዓይነት የቡድን አስተሳሰብ ውስጥ ለሚገኙ የኢህአዴግ አባላትም ሆነ አጋሮች ማረጋገጥ የምፈልገው አንድ ቁም ነገር አለ፡፡ ይህም ቁም ነገር፤
“ይህ ህገ መንግሰት ከነ እንከኑም ቢሆን እንዲከበር የምንፈልግ መሆኑን ብቻ ሳይሆን   ለማሻሻል የተቀመጡት ድንጋጌዎች ምንም ዓይነት አስቸጋሪ ቢሆኑም በዚሁ መስመር ብቻ እንዲሰተካከል እንደምንታገል ማወቅ አለባቸው፡፡”
ይህ ማለት ግን በህገ መንግሰቱ በተቀመጠው መሰረት እንዳይሻሻል ሊሆን የሚችልበት ሁኔታ የለም ማለት አይደለም፡፡ ለዚህም ዋነኛው ተጠያቂ ገዢው ፓርቲና መንግሰት ብቻ ናቸው የሚሆኑት፡፡ ገዢው ፓርቲ እና መንግሰት በዚህች ሀገር ሰላማዊ የስልጣን ሽግግር ሊኖር የሚችልበት እድል ዘግተው በነውጥ ወይም በጠመንጃ ለውጥ ከመጣ ይህ ህገ መንግሰት ከዚህ ቀደም እንደነበሩት ህገ መንግሰቶች ታሪክ ሊሆን ይቸላል፡፡ ይህ እንዲሆን ፍላጎት የሌለን ሰዎች ህገ መንግስቱ ያሉበትን ችግሮች በህግ ስርዓት ብቻ እንዲሻሻል እንፈልጋለን፡፡ ይህ ባልተሟለበት ሁኔታ አንድ ፊደል በፍሉድ ሳይጠፋ ህገ መንግሰቱ እንዲከበር እንፈልጋለን፡፡
ከዚህ በተቃራኒው ግን መንግሰት ህገ መንግሰቱ እንዲናድ እና ወደ መቃብር እንዲወርድ ተግቶ እየሰራ ነው፡፡ ይህን ስንታዘብ  ህገ መንግሰቱ እንዲናድ የሚሰሩት ተቃዋሚ ፓርቲዎች ናቸው ማለት አይቻልም፡፡ ተቃዋሚ ፓርቲዎች በአሁኑ ሰዓት እየጠየቁ ያሉት በህገ መንግስት በግልፅ የተቀመጡት ሰብዓዊና ዲሞክራሲ መብቶች ይከበሩ ነው፡፡ መብቱ የተከበረለት ዜጋ ለልማት ግብዓት እንጂ ዕዳ ሊሆን አይችልም፡፡ በቁስ በሚገለፁ እድገቶች መብታችንን አሳልፈን አንሰጥም ማለት ህገ መንግሰቱን ማስከበር እንጂ መናድ ሊሆን አይችልም፡፡ ዜጎች ህገ መንግሰታዊ መብታችንን ለማስከበር ነቅተን በምርጫ እንሳተፍ የመዝጊያ መልዕክቴ ነው፡፡
ቸር ይግጠመን




Saturday, December 6, 2014

የምርጫ ስትራቴጂ እንዴት ይሁን?



የምርጫ ስትራቴጂ እንዴት ይሁን?
ግርማ ሠይፉ ማሩ
girmaseifu32@yahoo.com; www.girmaseifu.blogspot.com
በስታራቴጂክ ዕቅድ ዝግጅት ወቅት ከተለመዱት የአካባቢ ሁኔታ ትንታና መሳሪያዎች አንዱ የውጭ እና የውስጥ ሁኔታን የምተነትንበት በእንግሊዘኛ ስዎት/ (SWOT/SLOT Analysis) የሚባለው ነው፡፡ ወደ ውስጣችን ስንመለከት አንዱ ጥንካሪያችን ምንድነው የሚለው ጥያቄ መመለስ ሲሆን ሌላኛው ደግሞ ያሉብን ድክመቶች ወይም ውስኑነቶች ምንድናቸው የሚለው ነው፡፡ ወደ ውጭ ስንመለከት ደግሞ ምን ምቹ ሁኔታ አለ አንዱ ሲሆን ሌላኛው ደግሞ ተግዳሮቶቹ ምንድናቸው ብለን በዝርዝር ማየት ይኖርብናል፡፡
አንድ ስትራቴጂክ ዕቅድ የውስጥና የውጭ ትንተና ሰርቶ የሚከተሉትን ማድረግ የግድ ይለዋል፤
·         በውስጣዊ ጥንካሬ ላይ ያተኮሩ እና በውጭ ያሉትን ምቹ ሁኔታዎችን ለመጠቀም ላይ ያተኮረ፤
·          በውጭ ያሉ መልካም አጋጣሚዎች ለመጠቀም  እና የውስጥ ድከመቶችን በማስወገድ ላይ ያተኮረ፤
·         በውስጥ ጥንካሬዎችን በመጠቀም የውጭ ተግዳሮቶችን በማሸነፍ ላይ ያተኮረ፤ አና
·         የውስጥ ድክመቶች እና የውጭ ተግዳሮቶች የሚያደርሱትን ጉዳቶች በመቀነስ ላይ ያተኮሩ
ስልቶችን መንደፍ የግድ ይላል፡፡ አነዚህን በዝርዝር ከሰለማዊና ህጋዊ ትግል በተለይም ከምርጫ ስትራቴጂ ዕቅድ ዝግጅት ጋር እንዴት ማየት እንዳለብን መረዳት ተገቢ ነው፡፡ እነዚህን ስልቶች አንድ አንድ ምሳሌ እያነሳን ማየት እስከ ዛሬ የሄድንበትን መንገድ ከመፈተሸ በዘለለ ወደፊት እንዴት መሄድ እንዳለብን የመወያያ ርዕስ ይከፍታል የሚል እምነት አለኝ፡፡ ከላይ የተቀመጡትን ስልቶች የተገኙት በዚህ መልክ ከተቀመጠ ሰንጠረዥ ውስጥ ነው፡፡
                                             
ውስጣዊ ሁኔታዎች
ውጫዊ

ሁኔታዎች

ጥንካሬ
ድክመት/ውሱንነት
መልካም አጋጣሚዎች/
ዕድሎች

በውስጣዊ ጥንካሬ ላይ ያተኮሩ እና በውጭ ያሉትን ምቹ ሁኔታዎችን ለመጠቀም ላይ ያተኮረ


በውጭ ያሉ መልካም አጋጣሚዎች ለመጠቀም  እና የውስጥ ድከመቶችን በማስወገድ ላይ ያተኮረ



ተግዳሮቶች

በውስጥ ጥንካሬዎችን በመጠቀም የውጭ ተግዳሮቶችን በማሸነፍ ላይ ያተኮረ

የውስጥ ድክመቶች እና የውጭ ተግዳሮቶች የሚያደርሱትን ጉዳቶች በመቀነስ ላይ ያተኮሩ

ከላይ የተዘረዘሩትን ስልቶች ከታች ወደ ላይ እንመልከታው፡፡
እሰከ አሁን ባለው ነባራዊ ሁኔታ በተቃዋሚ ጎራ የምንገኝ አካላት ትኩረት ሰጥተን ስንሰራ የነበረው የውስጥ ድክመቶቻችንን እና የውጭ ተግዳሮቶች የሚያደርሱብንን ጫናዎቸና ጉዳቶች በማጉላት ላይ ነበር፡፡ ከውስጥም ሆነ ከውጭ ያሉትን ችግሮች ማወቅ ተገቢ ቢሆንም እነርሱም ደጋግሞ ማንሳት መፍትሔ ሊያመጣ እንደማይችል አልተረዳንም፡፡ በስትራቴጅክ እቅድ ዝግጅት እነዚህ ጉዳታ የሚያደርሱ ውስጣዊና ውጫዊ ሁኔታዎች እንዳሉ ተረድቶ እነርሱን ለመቀነስ የምነወስዳቸው እርምጃዎች ቅድሚያ ማግኘት ይኖርባቸዋል፡፡ በተለይ ምንም ማድረግ የማንችላቸው ለውጫዊ ሁኔታዎች ትኩረት ስጥቶ እነርሱን ማግዘፍ ከጥቅሙ ጉዳቱ ነው የሚበልጠው፡፡ ከዚህ አንፃር ከምርጫ ጋር የተገናኙ ውስጣዊ ችግሮች ከምንላቸው አንዱ ለምርጫ ለመወዳደር ያለብን የፋይናንስ ችግር ሲሆን ይህን ችግር ማሰቀረት ባይቻል እንኳን ለመቀነስ ስልት ነድፈን ከመንቀሳቀስ ይልቅ የገዢው ፓርቲ ድጋፍን እንደ አማራጭ እንወስደዋለን፡፡ ገዢው ፓርቲ ከዚህ አኳይ ሊረዳን ሳይሆን እንዴት ችግራችን ተባብሶ እንድንወድቅ እንደሚሰራ አንረዳም፡፡ ገዢው ፓርቲ የሚያደርሰውን ጫና ከመቀነሻ መንገዶች አንዱ ከመንግሰት የሚጠበቅን የገንዘብ ድጋፍ መብትም ቢሆን ትኩረት አለመስጠት ነው፡፡
ይልቁንም ከመንግሰት የሚመጣን የዚህን ዓይነት ተግዳሮት ትንሸም ብትሆን ካለችን የውስጥ ጥንካሬ በመጠቀም እነዚህን ተግዳሮቶች ማሸነፍ ይኖርብናል፡፡ ከፋይናንስ አንፃር ባነሳነው ምሳሌ ብንቀጥል ተቃዋሚ ፓርቲ አባላትና ደጋፊዎች አምሰት መቶ አርባ ሰባት ምርጫ ክልል ለማሸነፍ የሚያስችል የፋይናንሲንግ ሰትራቴጂ ልንጠቀም እንችላለን፡፡ ይህም እያንዳንዱን ዕጩ ሰፖንሰር የሚያደርግ አንድ ደጋፊ መመልመል ሲሆን፤ ድጋፉ ለአንድ ሰው ይበዛል ከተባለ ለአስር ማካፈል ይቻላል፡፡ አንድ ዕጩ አሸናፊ ሆኖ እንዲወጣ አስር ደጋፊዎች ሰፖንሰር ሊያደርጉት ይችላሉ፡፡ አንድ ፓርቲ አምስት ሺ ደጋፊዎች ያስፈልጉታል ማለት ነው፡፡ ከዚህ በተጓዳኝ ተቃዋሚ ፓርቲዎች ካላቸው የውስጥ ጥንካሬ አንዱ ገንዘብን በቁጠባና መጠቀም፣ ይልቁንም በነፃ የሚያገለግሉ ሰፍር ቁጥር የሌላቸው ወጣቶች መኖራቸው ትልቅ ውስጣዊ ጥንካሬ ነው፡፡ ይህንን አጠንክሮ መሄድ ያለብንን የፋይናንስ ችግረ ለመፍታት ይረዳናል፡፡
በአሁኑ ሰዓት ከተቃዋሚ ፓርቲዎች ውጭ ያሉ አመቺ ሁኔታዎች እጅግ ብዙ ናቸው፡፡ ለምሳሌ መንግሰት በሚወስዳቸው የተለያዩ የተሳሳቱ ፖሊሲዎች እና አፈፃፀም ዙሪያ ያሉትን ችግሮች በመገንዘብ ህዝቡ ተቃዋሚ ፓርቲዎችን ለመደገፍ ዝግጅቱን እያሳየ ይገኛል፡፡ ይህንን የህዝብ ዝግጁነት ወደተግባር ለመለውጥ በውስጥ ያሉብንን ወደ ህዝብ የመቅረብ ችግር አሰወግደን ለውጤት ማብቃት ይኖርብናል፡፡ እኛ ወደ ህዝቡ በመቅረብ ያሉንን አማራጮች ካላቀረብን እና ከህዝቡ ምን እንደምንጠብቅ ካላስረዳነው ፓርቲዎች ከህዝቡ ጋር ሳይገናኙ ይቀራሉ፡፡ ገዢው ፓርቲ በአንድም በሌላም የሚሰራቸው ስህተቶች ለተቃዋሚዎች የተዘጋጁ ዕድሎች ሲሆኑ ተቃዋሚዎች ደግሞ ወደ ህዝቡ ለመቅረብ ያለባቸውን ችግር በማሰወገድ ለድል የሚያበቃ ሰልት መንደፍ የግድ ይላቸዋል፡፡ እዚህ ነጥብ ላይ ሊነሳ የሚችለው ወደ ህዝብ መቅረቢያውን መንገድ ኢህአዴግ ዘግቶታል የሚለው ነው፡፡ ትክክል ነው ተቃዋሚ ፓርቲ አባላት ህዝቡን ማግኘት ያለብን ሰብሰበን በአዳራሽና በአደባባይ ብቻ ነው ከሚለው አቋም ወጥትን የአንድ ለአንድ የሰው ለሰው ግንኙነት በየሰፈራችን መጀመር ይኖርብናል፡፡ ማህበራዊ ሚዲያዎች እንደተጠበቁ ሆነው ማለት ነው፡፡
ዋነኛውና አውራ/ግራንድ የሚባለው ስትራቴጅ ግን መሆን ያለበት ጥንካሬዎቻችን ላይ መሰረት ማድረግና በውጭ ያሉ ምቹ ሁኔታዎችን አሟጦ መጠቀሙ ላይ ነው፡፡ ላለፉት 23 ዓመታት ችግሮችን እና ተግዳሮቶችን ከበቂ በላይ ተናግረናል እነርሱ የሚያደርሱትን ጉዳት ለመቀነስ ከመስራት ይልቅ መኖራቸው እንዲታወቅ ጩኽናል፡፡ አሁን ጊዚው መለወጥ አለበት ያሉትን እድሎች ለመጠቀም ቆርጦ መነሳት መሆን ይኖርበታል፡፡ ምንም ትንሽ ቢሆኑ በውሰጣችን የሚገኙትን ጥንካሬዎች መፈተሸ እና ዕድሎችን የምንጠቀምበት እድል ማድረግ ይኖርብናል፡፡ ለምሳሌ አሁን በሀገራችን ያሉት ወጣቶች ከሞላ ጎደል ፊደል የቆጠሩ ናቸው እነዚህ ወጣቶች በእውቀት ላይ የተመሰረተ አማራጭ ከቀረበላቸው ያለምንም ፍርሃት በመራጭነት ለመሳተፍ አያቅማሙም፡፡ ይህ ትልቅ ዕድል ነው፡፡ በተቃዋሚ በኩል የበለጠ የሰራ እድል መፍጠር የሚያስችሉ የፖሊሲ አማራጮች ወጣቶችን ከመንግሰት ጥገኝነት የሚያላቅቅ የመኖሪያ ቤት ፖሊሲ፣ ወጣቶችን የመሬት ባለቤት ሊያድርግ የሚችል የመሬት ፖሊሲዎች እንዳሉን ግልፅ ነው፡፡ ይህ ወጣቱን ከፍተኛ የምርጫ ሀይል ሊያደርግ የሚችል በውጭ ያለ ዕድል እና በፓርቲዎች ውስጥ ያለ ጥንካሬ ነው፡፡
ሌላው ለምሳሌ በከተማ ውስጥ ያለው ከፍተኛ የመኖሪያ ቤት ችግር ለመፍታት የሚችል አማራጭ ፖሊሲ ብቻ ሳይሆን አሁን በተገነቡ ኮንዶሚኒየም ቤት አግኝተው የሚኖሩ ዜጎች የገጠሩን ህዝብ በመሬት እንደያዘው ሁሉ የከተሜውን የኮንዶሚኒየም ጠርንፎታል፡፡ የኮንዶሚንየትም ቤቱን ለአምስት ዓመት እንዳይሽጥ፤ እንዳይለውጥ፤ በባንክ እንዳያሲዝ የሚያደርግ ፖሊሲ አለው፡፡ ይህ በእርግጠኝነት የአንድነት ዓይነት ፓርቲ ስልጣን ቢይዝ በወራት ውስጥ ቀይሮ ሁሉንም የቤቱ ባለቤት የሚያደርግ ነው፡፡ የዚህ ዓይነት የሚታይና የሚጨበጥ እርምጃዎችን የሚያሳዩ እንቅስቃሴዎች ማድረግ ይኖርብናል፡፡ አንድነት ከዩኒቨርሲቲ ስትመረቁ ኮብል ሰቶን /ድንጋይ ፈለጣ/ ትገባላችሁ አይልም፡፡ ድንጋይ ለመፍለጥ አራት ዓመት ዩኒቨርሲቲ መቆየት አያስፈልግም፡፡ እንደ አማራጭ የስራ መስክ ሆኖ ለሌሎች ይቆያል፡፡ የተማሩ ዜጎች ስራ እንዲይዙ ምቹ ሁኔታ የሚፈጥሩ የግል ባለሀብቶች ግልፅ በሆነ አስራር እንዲሰፋፉ ድጋፍ ማድረግ ነው፡፡ ሀገር ማለት ህዝብ ነው ስንል ዜጎች ለዜጎች የስራ እድል የሚፈጥሩበት ማለታችን ጭምር ነው፡፡
ለዛሬ በዚሁ ይብቃኝ!!!!! ቸር ይግጠመን!!!!



Sunday, November 30, 2014

ምርጫ መሳተፍ በመርዕ ላይ የተመሰረተ ውሳኔ ወይስ ኢህአዴግን ማጀብ?

 ሰዎች በማንኛውም መንገድ ሸብረክ ሸብረክ የሚሉ ከሆነ መርህ አልባ መሆናቸውን ከማሳየት ውጭ ሌላ ምንም ሊሆን አይችልም፡፡ ባለፈው ሳምነት ፍኖተ ነፃነት ላይ ወጣቱ ፀሃፊ ኢዮኤል ፍስሃ ዳምጤ ለምን እንደምንፈራ ቁልጭ አድርጎ አሳይቶን ነበር፡፡ የገዢዎቻችን በትር የበረታብን በእነርሱ ጥንካሬ ሳይሆን ከፍርሃት በመጣ ዝምታችን እንደሆነ አስምሮበታል፡፡ መፍትሔውም ከፍርሃት መላቀቅና ዝምታውን ማፍረስ ነው፡፡ በዛሬው ፅሁፌ ማንሳት የፈለኩት ደግሞ ለምን ሸብረክ ሸብረክ እንደምንል ነው፡፡
ለምንድነው ኮሽ ሲል ደንግጠን ከቆምንበት “መርዕ” ከምንለው አስተሳሰብ የምንሸራተት? እንዲህ ከሆነ ቀድሞውንም መርዕ አልነበረንም ማለት ነው፡፡ መርዕ ብለን የምንይዘው አሰተሳሰብ በእኔ እምነት ለምናደርገው እንቅስቃሴ የማዕዘን ድንጋይ መሆን አለበት፡፡ ከዚህ መርዕ ሸርተት ስንል ቀጥሎ የምናገኝው ሌላ የተሻለ ማዕዘን የሚሆን ድንጋይ ሳይሆን ድጥ ወይመ ማጥ ነው የሚሆነው፡፡ ብዙዎች መርዕ የሚመስላቸው በአቋራጭ የሚፈልጉትን ግብ የሚያሳካ አጭር መንገድ አድርገው ይወስዱታል፡፡ ይህ አቋራጭ መንገድ ግን ብዙን ጊዜ ወደ ሌላ ውጥንቅጥ ከመውሰድ አልፎ ለስኬት ሲያበቃ አይታይም፡፡
ግልፅ ያልሆነ የህይወት ግብ ያለን ሰዎች የምንሄድበትን ስለማናውቅ ሌሎች በሄዱበት ተከትለን እንነጉዳለን፣ ሌሎች ግባቸውን ሲያሳኩ እኛ የበይ ተመልካች መሆናችን አይቀርም፡፡ ግባችን ግልፅ ያለመሆኑ መድረሻችንን ብቻ ሳይሆን መነሻችንንም ስሚያዛባው ከየት ተነስተን የት እንደምንደርስ፣ እንዴት እንደምንደርስ እንዳናውቅ ያደርገናል፡፡ መርዕ ማለት አሁን ካለንብት ቦታ ተነስተን ወደምንፈልገው ቦታ ለመድረስ የምንጓዝበት ፍኖተ ካርታ ነው፡፡ ይህ ደግሞ በአሰተሳሰብ ብቻ ሳይሆን በተግባርም ልክ መሆን ያለበት ነው፡፡ አንድ አንድ ሰዎች የምንፈልገውን ግብ ለማሳካት ማነኛውንም መንገድ መጠቀም ችግር የለውም ይላሉ፡፡ ይህ የትም ፍጪው ዱቄቱን አምጭው /the end justify the means/ የሚባለው ዓይነት መሆኑ ሲሆን፡፡ ከዚህ በተቃራኒው ደግሞ ሌሎች የምንሄድበት መንገድ እንደ ወጤቱ ሁሉ መርዕ ላይ መመስረት አለበት የሚሉ ናቸው /The means is equally important as the end/:: በግሌ የማምነውም የምከተለውም የኋለኛውን አማራጭ ነው፡፡ የትም ፍጪው ዱቄቱን አምጭው የስግብግቦች መንገድ ነው ብዬ በፅኑ ስለማምን፡፡
ሰሞነኛ ወደ ሆነው የምርጫ አጀንዳ እና በመርዕ ላይ የተመሰረተው የአንድነት ፓርቲ ምርጫ እሳተፋለሁ ውሳኔ እንዴት መታየት እንዳለበት በአጭሩ ይህን አቋም ለደገፉም ሆነ ለተቃወሙ ማሰረዳት ተገቢ ይመስለኛል፡፡ አንድነት ፓርቲ ስልጣን የሚገኘው በህዝብ ድምፅ ነው የሚል መርዕ አለው፡፡ የህዝብ ድምፅ የሚገኘው ደግሞ በምርጫ ወቅት መራጩ ህዝብ በሚሰጠው ካርድ ነው፡፡ ይህ ማለት ደግሞ በምርጫ የህዝብ ድምፅ ይገኛል ማለት ነው፡፡ ብዙዎች ምርጫ ለመሳተፍ እኩል ሜዳ ያሰፈልጋል ይላሉ፡፡ ትክክል ነው እኔም አምንበታለሁ፡፡ ሜዳውን ትክክል ከሚያደርገው አንዱ ጉዳይ የምርጫ ቦርድ ገለልተኝነት እንደሆነ ይታወቃል፡፡ የምርጫ ቦርድ ገለልተኛ ካልሆነ ማለትም ሜዳው ትክክል ካልሆነ ስልጣን በሌላም መንገድ መያዝ ተቀባይነት አለው የሚል መከራከሪያ ለማቅረብም ሰበብ ይሆናል፡፡
ስልጣን በተለያየ መንገድ ለመያዝ እንደሚቻል አማራጭ ማሳየት አንድ ጉዳይ ሆኖ እኛ የመረጥነው ብቻ ልክ ነው ማለትም ተገቢ አይደለም፡፡ በተገኘው መንገድ ለመያዝ መሞከር ግን መርዕ አልባ ያደርገናል፡፡ ሰላማዊ ትግል እከተላለሁ ብሎ በሰላማዊ ትግል መርዕዎች አምናለሁ የሚል ማታ-ማታ ወይም ቅዳሜና-እሁድ በሌላ መንገድ ልሞክር የሚል ከሆነ መርዕ አልባነት ነው፡፡ በእኔ እምነት ችግር ያለው የምርጫ ሜዳ ላይ ከሆነ የምርጫው ሜዳው ለማስተካከል ምን አድርገናል? ከሚለው መነሳት አለበት፡፡ ስልጣን የመያዣው መንግድ ኮሮኮንች በዝቶበታል ማለት ኮሮኮንቹን እንዴት እናሻሽል ወደሚል ሊገፋን ይገባል፡፡
ሁሉም ሰው መረዳት ያለበት ገዢው ፓርቲ የምርጫ ሜዳውን ያጠበበው ወይም ኮሮኮንች እንዲበዛበት ያደረገው አውቆ ነው፡፡ ሜዳው ደግሞ የጠበበን ደግሞ አማራጭ አለን የምንል ፓርቲዎች ነን፡፡ አማርጭ ለማቅረብ እድል ስንነፈግ መጠየቅ ያለብን አንድ መስረታዊ ጥያቄ አማራጭ የተከለከለው ህዝብ ምንም ማድረግ አለበት የሚለው ነው? አማራጭ የሚፈልግ ህዝብ ድንጋይ ወይም ጠብመንጃ ይዞ አማራጭ አትከልክሉን ቢል ነው የሚሻለው ወይስ የምርጫ ካርድ ይዞ? አንድነት የመረጠው መስመር የምርጫ ካርድ ይዞ ቢሆን ይሻላል የሚለውን ነው፡፡ ይህ በምንም ዓይነት ሌሎች የመረጡት መስመር አይሰራም ማለት አይደለም፡፡ የትም ፍጪው ዱቄቱን አምጭውን እንደ መርዕ የተቀበለ ብዙ ሌላ አማራጭ ሊያስብ፣ ሊተገብር ይችላል፡፡ ችግሩ የእኛ ካልሆነ ብሎ የሌሎችን ምርጫ ለማክበር አለመፈለጉ ላይ ነው፡፡
በሀገራችን ኢትዮጵያ በ1997 ከተደረገው ምርጫ ውጭ ህዝቡ በምርጫ እንዲሳተፍ የምርጫ ካርድ እንዲወስድ በተቃዋሚ ፓርቲዎች በተገቢው መልኩና ደረጃ ተቀስቅሶዋል የሚል እምነት የለኝ፡፡ ከ1997 በፊት ምርጫ መወዳድር ወያኔን ማጀብ ነው እያልን ምርጫ የሚወዳደሩትን ብቻ ሳይሆን መራጩንም ተሰፋ እያስቆረጥን ኖረናል፡፡ ይህን ምርጫ የማጣጣል ስትራቴጂያችንን በደንብ የተረዳው ገዢው ፓርቲ የራሱን መራጮችና ተመራጮች እያዘጋጀ ውድድር ሲያድርግ ነበር፡፡ እንደዚያም ሆኖ ህዝቡ በምርጫ ካርዱ ቅሬታውን ሲገልፅ እንደ ነበር የገዢው ፓርቲ የኮሚኒኬሽን ሚኒስትር ዴእታ የነበሩት አቶ ኤርሚያስ ለገሠ “የመለስ ትሩፋቶች” በሚለው መፅሃፍ አስነብቦናል፡፡ ስለዚህ የአንድነት ቤተሰቦች ምርጫ እንሳተፋለን ስንል መራጮቻችን እንዲመዘገቡ እናደርጋለን ማለት ነው፡፡ የእኛ መራጮች ሲመዘገቡ፣ ገዢው ፓርቲ የእኔ ብሎ ያስመዘገባቸውም ቢሆኑ እኛን ለመምረጥ እንዲችሉ መሸሸጊያ እንሰጣቸዋለን፡፡
ብዙ ሰው መረዳት ያለበት የምርጫ ቅስቀሳ የሚጀመርበት ወቅት መራጮች ምዝገባ ሊጠናቀቅ ሳምንት ሲቀረው ነው (በ1997 ቀድሞ የምርጫ ቅስቀሳ ተጀምሮ ነበር)፡፡ ለዚህ ነው ገዢው ፓርቲ ሁል ጊዜ የሚጮሁት ካርድ ያልያዙ ናቸው የሚለው፡፡ ያስመዘገባቸውን ስለሚያውቅ ነው፡፡ የእኛ መራጮች ካርድ ባልያዙበት ሁኔታ የፈለገ አማላይ የሆነ ለሀገር የሚጠቅም አማራጭ ብናቀርብ ለማሸነፍ ያለን እድል አነስተኛ ነው፡፡
ማስተላለፍ የፈለኩት ነጥብ ምርጫ እገባለሁ-አልገባም በሚል ዥዋዝዌ ስንጫወት ደጋፊዎቻችን በመራጭነት ሳይመዘገቡ እንዳይቀሩ በአንድነት በኩል የተወሰደው እርምጃ ትልቅ ፖለቲካ ውሳኔ ነው፡፡ የምርጫ ፓርቲ መሆናችን የሚታወቅ ቢሆንም እስከ አሁን በተቃዋሚ ፓርቲዎች መስመር ምርጫ መግባትና አለመግባት በቁርጥ ቀድሞ ስለማይወሰን መራጮች ሁለት ልብ እየሆኑ ከጫወታ ውጭ ሲደረጉ ከርመዋል፡፡ ይህ እንዳይደግም መራጮች እንዲመዘገቡ እና በምርጫው ሙሉ ሂደት በንቃት እንዲሳተፉ ይህን አቋም መያዝ እጅግ አስፈላጊ እና ጠቃሚ ነበር፡፡ ሁሉም እንደሚረዳው ያልተመዘገበ ደግሞ አይመርጥም፣ ያልመረጠ ደግሞ ድምፁ እንዲከበር ዘብ ሊቆም አይችለም፡፡ ድምፃችን ይከበር የሚለው እንቅስቃሴ የሚጀምረው ከህዝብ ታዛቢዎች ምርጫ እሰከ ድምፅ ቆጠራ ድረስ ይዘልቃል፡፡
ጎበዝ ሰላማዊና ህጋዊ ትግል እናደርጋልን ስንል የሰላማዊና ህጋዊ ትግል መርዖዎችን ጠንቅቀን መረዳት የግድ ይለናል፡፡ በስላማዊ ትግል ዋናው ግብ የህዝብን የስልጣን ባለቤትነት ማረጋገጥ ሲሆን፣ ስልጣን መያዝ የሚፈልግ ፓርቲ የህዝብ ይሁንታ ማግኘት የግድ ይለዋል፡፡ ይህ ደግሞ በምርጫ የሚገኝ ነው፡፡ ምርጫውን የህዝብ ፖለቲካ ተሳትፎ መለኪያ አድርገን ለመውስድ ቁርጠኞች መሆን የግድ ይለናል፡፡

ቸር ይግጠመን

Wednesday, November 26, 2014

ህዝቡ የሚለው …..


ዛሬ በርዕስነት የመረጥኩት ጉዳይ ለመፃፍ ካሰብኩ ቆይቻለሁ፡፡ መልዕክት ማስተላለፊያው መንገድ ሲዘጋ በጅምር ትቼው ነበር፡፡ ለዛሬ የ “ፍኖተ ነፃነት” ጋዜጣ እንዲሆን ብዬ ሳዘጋጀው የቱን አንስቼ የቱን እንደምጥል ግራ ገብቶኝ ለ “ህዝብ ጥቅም” ሲባል ከሚወሰዱት ህገ ወጥ እርምጃዎች የቅርብ የቅርቦቹን ብቻ ለማንሳት ወሰንኩ፡፡
የ “የፀረ ሽብር ህግ” ከምንጊዜውም በላይ ተግባራዊ እየተደረገ ያለበት ወቅት ላይ እንደምንገኝ ማንም ሰው ይረዳዋል ብለን እናምናለን፡፡ ሀገራት ሽብርን ለመከላከል የሚያስችላቸውን የህግ ማዕቀፍን ጨምሮ ሌሎች አወቃቀራቸውን በማደረጀት ህዝብን ከአደጋ ለመጠበቅ ዝግጁ መሆ እንዳለባቸው ዓለም አቀፍ ጥሪ ከቀረበላቸው ቆየት ቢልም ኢትዮጵያ ሀገራችን ዘግየት ብላም ቢሆን ከዓለም አቀፍ ማዕቀፉ ውጭ የዜጎችን ስብዓዊና ዲሞክራሲያዊ መብቶች ለማፈን የሚረዳ ህግ አውጥታ ተግባራዊ ማድረግ ጀምራለች፡፡ ለ “ህዝብ ጥቅም” ሲባል በሚል ማስመሰያ ብዙ ኢትዮጵያዊያን የ “ፀረ ሽብር” ህጉ ሰለባ እየሆኑ ይገኛሉ፡፡ በመላው ዓለም ፍተሻ ቢደረግ ዜጎቹን በሽብርተኝነት  በ“ፀረ ሽብር” ህግ የሚያንገላታ መንግሰት የሚገኘው እዚህ ኢትዮጵያ የምትባል ሀገር ብቻ ነው፡፡ የሌሎች ሀገሮች የፀረ ሽብር ህግ ትኩረቱና ግብ ሀገርን ከውጭ ሀገር ከሚመጣ የተደራጀ አሸባሪ ቡድን መጠበቅ ነው፡፡
በ “ፀረ ሽብር ህግ” ተከሰው ቅጣት ከተጣለባቸው ውስጥ ቅጣት የሚገባቸው ተከሳሾች የሉም የሚል ጭፍን ዕየታ የለኝም፡፡ እነዚህ ሰዎች በወንጀል ህጉ ሊቀጡ የሚችሉ እንደሆነ ግን መቶ በመቶ እርግጠኛ መሆን ይቻላል፡፡ ፖለቲከኞች እና ጋዜጠኞች እየታደኑ “በፀረ ሽብር” ህግ ስም የሚታጎሩት ግን ለህዝብ ደህንነትና ሰላም ሳይሆን በገዢዎች ወንበር ላይ በሚፈጥሩት ሽብር ነው፡፡ እነ አንዱዓም አረጌ፣ ናትናኤል መኮንን፣ እስክንድር ነጋ፣ ርዕዮት ዓለሙ፣ ሽብር የነዙት በአራት ኪሎ ወንበር ላይ ነው፡፡ የእነርሱ ድምፅ ለህዝቡ የነፃነት ድምፅ ነው፡፡ የተሰፋ ድምፅ ነው፡፡ አሁንም በብዞዎች የሚዘመር እና ወደፊትም ለክብር የሚበቃ የነፃነት ድምፅ፡፡

ሌላ የሰሞኑ ወሬ የግል ሚዲያዎች ህዝቡን ለብጥብጥ ህገመንግሰታዊ ሰርዓቱን በሀይል ለመናድ እየተንቀሳቀሱ እንዴት ዝም ተባሉ የሚለው ነው፡፡ የመንግሰት የፖሮፓጋንዳ ሚዲያዎች የህዝብ ጥያቄ እነዚህ ሚዲያዎች ለፍርድ ይቀረቡ የሚል ነው፡፡ ይህ በእውነት የህዝብ ጥያቄ ከሆነ ይህን ጥያቄ ያቀረበ ህዝብ ለምን አዲስ ዘመን ተሯሩጦ አይገዛም? ለኢቲቪም ያለምንም ውትወታ፣ ማስታወቂያና ማስፈራሪያ ዓመታዊ ኪራይ አይከፍልም? ለምን የግል ሚዲያ ህትመቶችን ተሻምቶ ይገዛል? ነገሩ ግን አንዲህ አይደለም፡፡ አንድ ቅምጥል የንጉስ ዘር የህዝብ ብዛት 20 ሚሊዮን ደርሶዋል ብትባል ምናምንቴውን ቆጥረው ይሆናል እንጂ እኛ ከአምሰት መቶ አንበልጥም ብላለች ተብሎ የሚበላ ወሬ አለ፡፡ ሕዝብ ለዚህች ቅምጥል ትርጉሙ የተለየ ነው፡፡ ለእኛዎቹ ቅምጥሎች ደግሞ ህዝብ የሚባለው ሌላ ትርጉም ካልተሰጠው እና አሁን በብዛት የግል ሚዲያ ሰርጭት ያለበት አዲስ አበባ ከሆነ እኛ ነን ህዝብ የምንባለው ካላሉን በስተቀር ነገሩ ለየቅል ነው፡፡ ህዝቡ እያለ ያለው ቅዳሜ ምን ልናደርግ እንውጣ? ነው፡፡ ቅዳሜ ተወዳጇ ፋክት መፅሔትን ጨምሮ ሌሎች ብዛት ያላቸው ህትመቶች ለገበያ ቀርበው የሚያነብበት ቀን ስለነበር ነው፡፡ በዚህ እለት አዲስ ዘመን በገበያ ላይ ብትውልም የሚመለከታት እንደሌለ እርግጠኛ ነኝ፡፡ ለጨረታ ማስታወቂያ ከሚፈልጉት ውጭ ማለቴ ነው፡፡
ሌላው የህዝብ ጥያቄ በእሰር ላይ የሚገኙትን ፍቱልን የሚል እንደሆነ ለመረዳት ፈላስፋ መሆን አያስፈልግም፡፡ በቅርቡ ቂሊንጡ እስር ቤት ሄጄ የታዘብኩት አንድ ነገር እጅግ ብዛት ያለው እስረኛ መኖሩን ነው፡፡ ተቃዋሚዎች እስር ቤት የሌለው መንግስት እንደማይመሰርቱ የታወቀ ቢሆንም በአሁኑ ሰርዓት ከህግ ውጭ ታስሮ መንገላታት ግን በግልፅ የሚታይ ሀቅ ሆኖዋል፡፡ ህዝቡ በግፍ የታሰሩትን ፍቱልን ሲል የቅምጥሎቹ ወገን የሆኑት ደግሞ እነዚህ ታሳሪዎች አሸባሪዎች ናቸው ይሉናል፡፡ እውነት እነዚህ ሰዎች አሸባሪ ከሆኑ ሰፍር ቁጥር የሌለው ህዝብ በየፍርድ አደባበዩ እና በየማጎሪያ ሰፍራ ለምን ይገኛል? እነዚህ በመንግሰት አሸባሪ የተባሉ ሰዎች ህዝቡ ለምን በፈቃዱ ይጎበኛቸዋል? እነዚህ ታሳሪዎች መጎብኘት የሚፈልግ ሁሉ በነፃነት እንዳይጎበኝ ለምን የተጠና እገዳ ይጣልባቸዋል? እዚህ ጋ ምፀት የሚሆነው ጉብኝት እግድ የሚጣለው “አሸባሪ” ብለው ያሰሯቸው እስረኞች ላይ ጉዳት እንዳይደርስ ነው የሚለው ነው፡፡ የሚያገላቱዋቸውም ለእነርሱ ደህንነት ብለው ነው፡፡
ከዚህ ጋር ተያይዞ ህዝቡ እያለ ያለው መሰረት የሌላቸው ሲከፋም ህገወጥ የሆነ የአቃቢ ህግ ክስና ይህን መሰረት አድርጎ የሚሰጥ የፍርድ ቤቶች ውሳኔ ይቁም ነው የሚለው፡፡ በመንግሰት በተጠና ጥናት እምነት የማይጣልባቸው ተቋማት የተባሉት እነዚህ ተቋማት በዚህ ድርጊት አሁን ባለው ጥልቀት መሳተፋቸው የተዓማኒነት ጉድለታቸውን ከማሳደግ ውጭ የህዝብ ጥያቄን አይመልስም የጊዜ ጉዳይ እንጂ የገዢዎችንም ወንበር አያፀናም፡፡
ሕዝቡ እያለ ያለው በየአምሰት ዓመት ምርጫ ቢመጣም አማራጭ አሳጣችሁን፡፡ አፈናውን አቁሙና ፍላጎት ያለው ተደራጅቶ አማራጭ ያምጣ ነው፡፡ የመደራጅት መብት ያለምንም ገደብ ይከበር!! ሕገመንግሰት ላይ በተቀመጠው መሰረት ተግባራዊ ይሁን!!! ነው፡፡ ከዚህ ቀደም ህዝቡ ያለው አሁንም የሚለው፡፡ እዚህ ላይ ገዢው ፓርቲም የመንግሰት መዋቅርን ተጠቅሞ የሚያደርገው አፈና አማራጭ አሳጣን እንጂ ደግ አደረጋችሁ የሚል ድምፅ አይሰማም፡፡ በቅርቡ በመንግሰት ድጋፍ በገዢው ፓርቲ አብዮታዊ ዲሞክራሲያዊ መስመርና ልማታዊ መንግሰት ፍልስፍና ዙሪያ የተደረጉት ከ-እሰከ የማይገልፃቸው ስብሰባዎች ያረጋገጡት ሀቅ ኢትዮጵያዊያን አማራጭ እንደሚፈልጉ እና የመንግሰት ህገወጥ አካሄድ እንዲቆም ነው፡፡ ኢትዮጵያዊያን እንደ ህዝብ ያቀረቡት ጥያቄ ከልማት እኩል ነፃነት ይገባናል ነው፡፡ ነፃነት ልማትን ያሳልጣል እንጂ የልማት ደንቃራ የሚሆንበት አንድም በቂ ምክንያት እንደሌለ ህዝቡ ተገንዝቦዋል፡፡ ህዝቡ የሚለው ነፃነታችንን አትንኩ ነው፡፡
ህዝቡ አሁንም እያለ ያለው የእምነት ነፃነት ይከበር የመንግሰት ጣልቃ ገብነት ይቁም ነው፡፡ ባለፈው ሰሞን ኢሳት የሚባል ለኢህአዴግ እሣት የሆነ ሚዲያ በቅርቡ ይፋ ያደረገው የሰብሰባ ውስጥ ውይይት መንግሰት በምን ያህል ጥልቀት በሙስሊሞች ጉዳይ ጣልቃ እንደሚገባ ብቻ ሳይሆን የሙስሊሙን ማህበረሰብ ለመምራት በሚል የአመራር ቦታ “የቀሙት” ሰዎች ግብ ምን እንደሆነ አጋልጧቸዋል፡፡ ህዝበ ሙስሊሙ እያለ ያለው እምነታችን በካድሬ አይመራም ነው፡፡ የኢሳትን ተደማጭነት ያጎላው የሀገር ውስጥ አፈና መሆኑን ለመረዳት ነብይ መሆን ያስፈልግ ይሆን? ህዝቡ እያለ ያለው አፈና ይቁም!!! ሀሳብ በነፃነት ማንሸራሸር የሚፈቅደው ህገመንግሰታዊ ድንጋጌ ይከበር ነው፡፡
ለማጠቃለል መንግሰት በህዝብ የመደራጀትና ሃሳብን በነፃነት የማንሸራሸር መብት ላይ በህዝብ ስም ገደብ እያደረገ ቢሆንም ህዝቡ ግን በተቃራኒ እየጠየቀ ያለው እነዚህ መብቶች ያለምንም ገደብ ይከበሩ ነው፡፡ እነዚህን መብቶች ተጠቅሞ በህዝብ ጥቅም ላይ ጉዳት የሚያድርስ ቡድንም ሆነ ግለሰብ ቢመጣ ህዝብ ለመቅጣት የሚያስችለው አቅም አለው እያለ ነው፡፡ የህዝብ ድምፅ ይሰማ፡፡
ቸር ይግጠመን!!!!


Saturday, November 22, 2014

የነፃነቴ ዋጋ ነብሴ ነው!!!


 መረጃ በሃያ አንደኛው ክፍለ ዘመን ጠቃሚ ነው ብሎ መንገር ለቀባሪ እንደማርዳት ነው፡፡ የተሟላ መረጃ የሰውን ልጅ ሙሉ ያደርገዋል፡፡ መረጃን አጣሞ ማቅረብ ደግሞ የሰውን ልጅ ውሳኔ ለማጣመም ካልሆነ በስተቀር ግቡ ምን ሊሆን እንደሚችል አይገባኝም፡፡ በሰሞኑ ሰው በላው የኢትዮጵያ ፖለቲካ በጥርሱም በጥፍሩም ዘመቻ የጀመረው እኔ ላይ ነው፡፡ ዓላማው ግልፅ ነው፡፡ በነፃነት የማሰብ መብቴን ለድርድር እንዳቀርብ ነው፡፡ ለነፃነቴ ያለኝን ዋጋ የማያውቁ ሰዎችን ይህንን ለማድረግ ቢሞክር ካላቸው የመረጃ እጥረት ወይም ማወቅ ባለመፈለጋቸው ነው፡፡ አንዳንድ ቅን ሰዎች ሰህተት እንደሰራው አድርገው ይቅርታ እንድጠይቅ፤ ይቅርም እንድባል አስተያየት ሰጥተዋል፡፡ በቅን ልቦና ላደረጋችሁት ምስጋናዬ ይድረሳችሁ፡፡ ነገር ግን በሰጠሁት አስተያየት ያልተስማማ ሰው በሃሰብ ልዮነት መለያየት እያለ ይቅርታ ጠይቄ፤ ይቅርታም ተደርጎልኝ ወደ እነሱ ሃሳብ እንድገበ መፈለጉ ምን ዓይነት ከፍተኛ ችግር ያለበት አስተሳሰብ እንደሆነ የተረዱት አይመሰለኝም፡፡ ይህ ደግሞ በጣም አስገራሚ የሚሆነው የመድበለ ፓርቲ ስርዓት ደጋፊ፣ ለግለሰብ ነፃነት እንቆማለን የሚሉ ወገኖች መሆናቸው ነው፡፡ ለሃሳብ ነፃነት የማይቆም እንዴት አድርጎ ለመድበላ ፓርቲ ስርዓት ግንባታና የግለሰብ ነፃነት እንደሚያከብር አይገባኝም፡፡
ጫጫታ ወደ ፈጠረው አጃንዳ ስገባ፡፡ አንድነት ፓርቲ የምርጫ ግብረ ሀይል ማቋቋሙን ለህዝብ በይፋ ለማሳወቅ እና በቀጣይ ሳምንት ስለሚያደርገው የህሊና እስረኞች ስለሚታሰብበት ፕሮግራም መግለጫ በሰጠንበት ወቅት በፍፁም ጠቃሚ ያልሆነ የተቃዋሚ ጎራውን በተለይ በሀገር ውስጥ ለምንገኝ ሰዎች የማይጠቅም (በኢቲቪ ቢቀርብ የማይገርም) ጥያቄ ቀረበ፡፡ ጥያቄው በእስር ላይ የሚገኙ የቀድሞ አንድነት አባል የነበሩ ታሳሪ ስም ጠርቶ በአንድነት አቋም እኝህ ሰው የህሊና እስረኛ ናቸው ብላችሁ ታምናላችሁ ወይ? የሚል ነበር፡፡ የሰጠሁት መልስ የማንንም ታሳሪ ስም ማንሳት ሳያስፈልግ የአንድነት ፓርቲ አባል ሆኖ የሌላ ፓርቲ አባል መሆን ትክክል እንዳልሆነ፣ ከአንድነት ጋር በትግል ስትራቴጂ ከማይመሳሰሉት ጋር ብቻ ሳይሆን በትግል ከሚመሳሰሉትም ጋር ቢሆን የተሻለ ወደሚለው መጠቃለል እንጂ ሁለት ቦታ መሆን ትክክል እንዳልሆነ አስረድቻለሁ፡፡ በማስከተልም “በፀረ ሽብር” ህግ መንግሰት እየከሰሰ የሚያስራቸው ሰዎች አንዳንዶቹ በወንጀል ህግ ሊያስጠይቅ የሚችል ሰህተት አልሰሩም የሚል ድምዳሜ እንደሌለኝ አሰረግጬ ተናግሬያለሁ፡፡ ለምሳሌ በፈንጂ ስው የገደለ ሰው በወንጀለኛ ህግ መጠየቅ እና መቀጣት አለበት ብዬ አምናለሁ፡፡ ይህ እምቴ አሁን ፅኑ ነው፡፡ የ “ፀረ ሽብር” የሚባለውን ህግ በይፋ አሸባሪ ህግ ነው፡፡ ፖለቲከኞች እና ጋዜጠኞች አሸባሪ እየተባሉ የሚታሰሩ ያሉት የአራት ኪሎን ወንበር ስለሚያሸብሩ ነው የሚል አቋሜን ከብዙዎቹ ተችዎቼ በላይ እና ከማንም በማያንስ መልኩ ሃሳቤን በነፃነት አራምጃለሁ፡፡ ይህን ሳራምድ ማንንም ለማስደስት ሳይሆን አምኜበት ነው፡፡ አንድነት የ “ፀረ ሽብር” የሚባለው ህግ እንዲሰረዝ የተገበረውን “የሚሊዮኖች ድምፅ ለነፃነት” ዘመቻ በቁርጠኝነት ከመሩት አንዱ ስሆን፤ በተለይ በደሴ ከተማ የተደረገውን የሚሊዮኖች ድምፅ ዘመቻ በቦታው ተገኝቼ የመራሁት እኔ ነኝ፡፡ ይህን ሁሉ የምዘበዝበው በዚህ ህግ ላይ ያለኝን ግልፅ አቋም በድጋሚ ለማረጋገጥ ነው፡፡
በእኔ በኩል የአቋም ለውጥ ሳይኖር እሳት ጭረው ቤንዝን እያርከፈከፉ ያሉት ግለሰቦችና ቡድኖች ለምን ተፈጠሩ?  የሚለው ነው፡፡ በእኔ እምነት የአንድነት በምርጫው የመሳተፍ ውሳኔ በትግል ስልታቸው ላይ የሚፈጥረው ጫና ስለሚያስጨንቃቸው ነው ብዬ ነው የማምነው፡፡ ምርጫ መሳተፍ ትክክል አይደለም ብሎ መሟገት ሲያቅታቸው የፈጠሯት ስልት ነች፡፡ አንድነት ምርጫ መሳተፍ ሲወስን በምንም መመዘኛ የመወዳደሪያው ሜዳ ምቹ ነው የሚል ግምገማ ላይ ደርሶ አይደለም፡፡ የፖለተካ ምዕዳሩ ጠበበ ብቻ ሳይሆን ዝግ ነው የሚል ግምገማ ላይ ደርሶዋል፡፡ ልዩነቱ ማስከፈቻ መንገዱ ምን ይሁን የሚለው ነው፡፡ በህዝብ ድምፅ የተዘጋው የፖለተኪ በር ይከፈታል ነው አንድነት ያለው፡፡ በዚህ ውሳኔ የማይስማማ ሊኖር እንደሚችል ይገመታል፡፡ በዚህ ደረጃ ወርዶ ግን በጥርስና በጥፍር ለመናከስና ለመቧጨር መሞከር ግን ያስተዛዝባል፡፡

የግል ሰሜቴን ለመግለፅ እሰከ ዛሬ ድረስ ለሚቀርብልኝ ሙገሳና የማጀገኛ ቃለቶችን ተመርኩዥ ልቤ አላበጠም፡፡ አንድ ቀን ያለአግባብ ከፍ አድርገው ከሰቀሉ ቦታ ላይ አውርዶ የሚከሰክስ ማህበረሰብ አባል መሆኔን አውቃለሁ፡፡ ያለ አግባብ በእራሳቸው ስሜት ሊወስዱኝ የፈለጉት ከፍታ ላይ ስለአልሄድኩኝ አሁን ሊያወርዱኝ አይችሉም፡፡ እደግመዋለሁ ለነፃነቴ የምሰጠውን ዋጋ የማያውቁ ሰዎች ምንም ሊሞክሩ ቢችሉም ነፃነቴን ለኢህአዴግ አሳልፌ አልሰጥም ስል በተቃዋሚ ጎራ ለተሰለፈ አሳልፌ እሰጣለሁ ማለት አይደለም፡፡ ለነፃነቴ የመደብኩት ዋጋ ነብሴን ነው፡፡ ስም፣ ዝና፣ ክብር፣ ገንዘብ፣ ወዘተ እንዳይመስላችሁ!!!!! ነብሴን ነው፡፡

Monday, November 17, 2014

በኢትዮጵያችን በጥርስና በጥፍር የሚደረግ ትግል እንዴት ይቁም?


አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ/አንድነት አሳዛኙን የ2002 ምርጫ ውጤት ተከትሎ ፍራሽ አንጥፎ ኢህአዴግን ምርጫ ዘረፈ ከሚል መደበኛ ለቅሶ መውጣት አለብኝ ብሎ ቁርጠኛ ውሳኔ በመወሰን ውስጣችንን መፈተሸ ተገቢ አቅጣጫ ነው ብሎ በማመን በእኛ በኩልስ የነበረው ችግር ምንድነው? የሚለውን ጥያቄ አንስቶ ለመመለስ ከፍተኛ ጥረት አድርጎዋል፡፡ ይህ ነገሮች ወደ ውጭ ከማላከክ በዘለለ ሙሉ ቁጥጥር ባለን በራሳቸን ላይ የውስጥ ፍተሻ ማድረግ ጠቃሚና ተገቢ ነው ከሚል እምነት የመነጨ ነበር፡፡ ይህ ማለት ግን የውጭ ጫናዎች በተለይም የኢህአዴግ አፈና የነበራቸውን ተፅዕኖ አሳንሶ ማየት እና የኢህዴግን አፋኝነትን ዝቅ አድርጎ መመልከት አድርገው የሚውስዱ ሰዎች አይጠፉም፡፡ ዋናው ጉዳይ እና ቅድሚያ መሰጠት ያለበት የውሰጥ ጥንካሬና ድክመትን ማወቁ ነው የሚለው ነበር፡፡ በዚህም መነሻ አንድነት በተቃዋሚ ፓርቲዎች ታሪክ የመጀመሪያ የሆነውን የአምስት ዓመት ሰትራቴጂና ዕቅድ አዘጋጅቶ ለህዝብ ይፋ አድርጓል፡፡ ይህም ሆኖ ግን ሪፖርተርን የመሰሉ ጋዜጦች ተቃዋሚዎችን በጅምላ የሚመሩበት አቅጣጫ የሌላቸው አድርገው መፈረጃቸወን አላቆሙም፡፡ ሌሎችም ቢሆኑ ይህን ተከትለው ከማሰተጋባትና ተቃዋሚዎችን በጅምላ ከመክሰስ ወደኋላ አላሉም፡፡ ለማነኛውም ፍረጃው እንደተጠበቀ ሆኖ አንድነት ያለፉትን አራት ዓመታት ጎዞዉን ባስቀመጠው ሰትራቴጅና አምስት ዓመት ዕቅድ መሰረት አድርጎ ቀጥሏል፡፡ የእቅዱ ማጠቃለያ ዘመንም ከምርጫ ሁለት ሺ ሰባት ምርጫ ጋር የሚገጣጠም ነው፡፡
ይህ የአምስት ዓመት ዕቅድ አፈፃፀም ግምገማ ወደፊት እንደሚካሄድ ታሳቢ ተደርጎ የመጨረሻው ዓመት ሊኖረን የሚገባው ዋነኛ ሰራ ምርጫን መሰረት ያደረገ እንደሚሆን ይታወቃል፡፡ ከዚህ አንፃር ገዢው ፓርቲ በጥርሱም በጥፍሩም ምርጫን ለማሸነፍ እየተንቀሳቀሰ ሲሆን እግረ መንገዱን ደግሞ የተቃዋሚዎችን በተለይም ደግም የአንድነትን ጥርስ ማውለቅና ጥፍር ማዶልደሙን ተያይዞታል፡፡ የጫወታው ህግ በጥርስም በጥፍርም መጫወት የሚፈቅድ ከሆነ ተወዳደሪዎች በተመጣጣኝ ጥርስም ጥፍርም ሊኖራቸው ይገባል፡፡ በቦክስ ጫወታ ደረጃ የሚወጣው በኪሎ ነው፡፡  አጫዋቹም/ዳኛውም ጫወታው ከመጀመሩ በፊት ቅድሚያ ሰጥቶ ማረጋገጥ ያለበት ይህን ጉዳይ ሁሉም ተወዳዳሪዎች ማሟላታቸውን ነው፡፡

አንድነት በዚህ ዓይነት የጥርስና የጥፍር ጫወታ ውስጥ ገዢው ፓርቲ ለማድረግ እንደሚፈልገው የተወዳደሪን ጥርስ ማርገፍና ጥፍር ማዶልዶም ተመጣጣኝ ምላሹ የገዢውን ፓርቲ ኢህአዴግ ጥርስ ማርገፍና ጥፍር ማዶልዶም መፍትሔ ይሆናል ብሎ አያምንም፡፡ ለውድድሩ ጥርስም ጥፍርም አስፈላጊ ከሆነ የአንድነት ፓርቲ ጥርስና ጥፍር እንዳይጎዳ መጠበቅ ቅድሚያ ይሰጠው ነው፡፡ ይህ ነው በቁጥጥራችን ስር የሚገኘው እና ዋና ትኩረታችን ሊወስድ የሚገባ እንዲሁም ተገቢ ጊዜ መስጠት አለብን የምንለው፡፡ የገዢውን ፓርቲ ጥርስ ለማርገፍና ጥፍርሩን ለማዶልዶም የምናባክነው ጊዜ የራሳችን በመጠበቅ ብሎም በቁርጠኝነት ባለማስደፈር ቢሆን የበለጠ አዋጭ ነው ብለን እናምናለን፡፡
በገዢው ፓርቲ መንገድ የምንሄድ ከሆነ ግን ወደፊት ለሚደረግ ውድድር በሁለቱም ወገን የሚኖሩ ተወዳደሪዎች በድድ እና በዱልዱም ጥፍር የሚወዳደሩ ይሆናሉ ማለት ነው፡፡ ይህ ደግሞ የጫወታውን ህግ መለወጥ የሚጠይቅ ይሆናል፡፡ በዛሬው የጥርስና ጥፍር ተምሳሌት ዋነኛ ወካይ ባህሪዎች በሁለቱም ጎራ የተሰለፉ ኢትዮጵያዊያን መሆናቸውን ነው፡፡ ኢህአዴግ የተቃዋሚዎችን በተለይ የአንድነትን ጥርስና ጥፍር ላይ አደጋ አደረሰ ማለት በየደረጃው ያሉ የአንድነት አባላትና ደጋፊዎች ላይ የሚወስዳቸው ቅጥ ያጡ ህገወጥ እርምጃዎች ማለታቸን ነው፡፡ በአፀፋው አንድነት ይህን ያድርግ ሲባል ደግሞ በኢህአዴግ አባላትና ደጋፊዎች ላይ ቅጥ ያጡ ሕገ ወጥ እርምጃዎች እንውሰድ ማለት ነው፡፡ የእነዚህ ድምር ውጤት ኢትዮጵያዊያንን በፖለቲካ አቋማቸው ከመጉዳት የሚተናነስ አይደለም፡፡ በዚህ ሁኔታ በተጎዳ ህዝብ ውስጥ ወደፊትም ቢሆን የተሸለ እና የሰለጠነ አማራጭ ይዞ በፖለቲካ መወዳደር ይቻላል የሚል እምነት አይኖርም፡፡ ለዚህም ነው ጉልበታችንን የኢህአዴግ አባላትን ለመጉዳት ወይም ለመበቀል ሳይሆን የአንድነት አባላትና ደጋፊዎችን አቅም በማሳደግ የአይደፈሬነት ሰነልቦና ማዳበር መሆን ይኖርበታል የምንለው፡፡
በአንድነት በኩል የአባላቶቻችንን አቅም እናሳድጋለን ብለን ስንነሳ በዋነኝነት በፖለቲካ ፓርቲዎች መካከል የሚደረግ ውድድር የሚመነጨው አንዱ ሀገር ወዳድ ሌላው ጠላት ነው ከሚል መንፈስ፣ ወይም በግል በደረሰብን በደል በቁጭትና ለበቀል መሆን እንደሌለበት በማሰተማር ነው፡፡ የፖለቲካ ፓርቲዎች የሚለያዩት በሚመርጡት የርዕዮተ ዓለም፣ ይህን ለመተግበር በሚያወጡት ፖሊሲና የማስፈፀሚያ ስትራቴጂዎች መሆኑን በማስረዳት በማስከተለም እነዚህ ልዩነቶች ሀገርን ሊጎዱ እንደሚችሉ ለህዝብ በማሰየት ህዝብ ለሚሰጠው ብይን ተገዢ ለመሆን ዝግጁ ሲኮን ነው፡፡ ይህን ልዩነታችንን ከጠባብ ቡድናዊ/የፓርቲ ወይም ሌላ ስብስብ ፍላጎት ከመነሳት “ሀገር ወዳድ እና የሀገር ጠላት” በሚል እንድንፈራረጅ ምክንያት ከሆነ የጋራ ሀገር እንዲኖረን እየሰራን ነው ማለት አይቻልም፡፡ ኢትዮጵያ ሀገራችን ለሁሉም ፓርቲዎች የጋራ መኖሪያ ከመሆን በዘለለ የሁሉም ፓርቲዎች አባላት የሚኖሩባት ብቻ ሳትሆን ለልጅ ልጆች በተሻለ ደረጃ ልናስተላልፋት ትልቅ ራዕይ ሰንቀን የምንቀሳቀስ መሆኑ በሁሉም ዘንድ መታወቅ አለበት፡፡ ኢትዮጵያችን እንድትኖር እኛም በእርሷ እንድንኮራ በሁሉም ጎራ የተሰለፍን ኢትዮጵያዊያን ሁሉ ከፍተኛ ሀገራዊ ኃላፊነት እንዳለብን አውቀን መንቀሳቀስ ይኖርብናል፡፡
በኢህአዴግ በኩል የሚገኙ አባላት ብሎም ከፍተኛ አመራሮች ጭምር የተቃዋሚ ፓርቲዎችን “ኪራይ ሰብሳቢ” ከሚል ቅጥ አንባሩ ከጠፋው ፍረጃ በላይ ግልፅ ሆኖ በወጣ መልኩ በተቃዋሚ ጎራ የተሰለፍን ዜጎች በፍፁም ለሀገር ደንታ የሌለን አድርገው መሳል የተለመደና አስልቺ ፕሮፓጋንዳ ከሆነ ቆይቶዋል፡፡ ይህ በእውነቱ የኢህአዴግ በጥርስም በጥፍርም ለመጫወታ እንዲመቸው የሌላውን ጥርስ ማርገፍና ጥፍር ማዶልዶሚያ ስትራቴጂው ነው፡፡ ይህ መንገድ ግን ብዙ ርቀት የማያስኬድ ብቻ ሳይሆን ለሀገራችን ዘላቂ ሰላም የሚበጅ ነው የሚል እምነት የለንም፡፡
በተቃዋሚ መስመር የተሰለፍን ሰዎች መካከልም ኢህአዴግን መሳደብ እንደ ዋና የትግል ሰልት የተያዘ እስኪመስ ድረስ ጥግ እንደምንሄድ አምኖ መቀበል ስህተታችንን ለማረም ጉልዕ ድርሻ አለው፡፡ አንዳንዴም የሃሳብ ልዩነትን በሰለጠነ መንገድ ከመግለፅ ይልቅ ሰነምግባር በጎደለው ሁኔታ በተለይ የግለሰቦችን ስብዕና የሚነኩ አላስፈላጊ የቃላት ጫወታዎች እንዳሉ እንረዳለን፡፡ “ቅኔው ሲጣፋበት ቀረርቶ ሞላበት” የሚለው አባባል በሁለቱም ጎራ የመከራከሪያ ሃሰብ ድርቀት ምልክት ሊሆን ይቻላል፡፡ ይህንን ከመሰረቱ ለመቅረፍ ከላይ እንደተገለፀው አባላትን በስነምግባር መኮትኮት እና ዋነኛው የፓርቲዎች ልዩነት መሰረት መሆን የሚገባው የፖሊሲና የስትራቴጂ ጉዳዮች ላይ እንዲያተኩሩ ማድረግ ነው፡፡ ይህ ሲሆን በከፍተኛ ሀገራዊ መግባባት ሰሜት መንቀሳቀስ ይቻላል የሚል ፅኑ እምነት ይዳብራል፡፡


Monday, October 27, 2014

የ “ካዛንችሱ መንግሰት በአዲሰ አበባ ማዘጋጃ ቤት”


ዛሬ ጥቅምት 17/ 2007 እግር ጥሎኝ አዲሰ አበባ ማዘጋጃ ቤት ጎራ ብዬ ነበር፡፡ የታዘብኩት ነገር ያስታወኝ ኤርሚያስ ለገስ “የመለስ ትሩፋቶች” በሚል ባወጣው መፅሃፍ ውስጥ “የካዛንችስ መንግሰት” ብሎ ያስነበበንን በገሃድ ከካዛንችስ ቦታ ቀይሮ አዲስ አበባ መስተዳደር ግቢ ውስጥ መኖሩን ነው፡፡ የካዛንችሱ መንግሰት ምን እንደሚሰራ እዚህ መዘርዘር አይጠበቅብኝም፤ በጥቅሉ ግን የአዲስ አበባ ህዝብ “መርጦ” ወይም ቀጥሮ ያስቀመጣቸው ሰዎች ሳይሆን ውሳኔ የሚስጡት ሌሎች በስውር በደህንነት ስም በኢህአዴግ የተቀመጡ ሰውር እጆች መሆናቸውን የሚያሳይ ነው፡፡
እነዚህ ሰውር እጆች ለእኛ ለተቃዋሚዎች አዲስ አይደሉም ለምሳሌ፤
  • ·         በሆቴሎች አዳራሽ ለማከራየት አንችልም ምንም ጠቃሚ ገንዘብ ቢሆን ሆቴሎች ፈቃደኞች አይደለም፤
  • ·         ማተሚያ ቤቶች የተቃዋሚ ፓርቲዎች ወይም እነርሱን ይደግፋሉ የሚባሉ የግል ጋዜጦችና መፅሄቶች አያትሙም፤
  • ·         መብራት ኃይል ለአንድነት የማተሚያ ማሽን ሊያንቀሳቅስ የሚችል የኤሌትሪክ ሀይል (ሰሪ ፌዝ የሚባል ሀይል) ለፓርቲ ለማስገባት ፈቃደኛ አይደለም፤
  • ·         ቤት አከራዮች ቤታቸውን ለማከራየት ይፈራሉ፤
  • ·         በቅስቀሳ ጊዜ መኪና እና የድምፅ መሳሪያዎች ማግኘት ፈተና ነው፤
  • ·         ለቅስቀሳ የወጡ ሰዎች እንደ በግ በየጣቢያው ሲታሰሩ የሚያስሩት ሰዎች በግልፅ ዩኒፎርም የለበሱት ፖሊሶች ሳይሆኑ በሬዲዮ የሚያዙ ማን እንደሆኑ የማይታወቁ ናቸው፤ ወዘተ

ይህ ሁሉ የሚሆነው በህግ አግባብ ሳይሆን በሰውር መንግስት ውስጥ ያሉ ሰውር እጆች የሚሰሩት ነው፡፡
ለዛሬ ፅሁፌ መነሻ የሆነኝ ግን በአዲስ አበባ ከተማ  መስተዳድር የህዝባዊ ስብሰባና ሰላማዊ ሰልፍ ማሳወቂያ ክፍል ኦፌሰር የሆኑት አቶ ማርቆስ ብዙነህ የሰጡን ምላሽ ነው፡፡ አንድነት ፓርቲ በቀጣይ ፓርቲው በሚያደርገው እንቅስቃሴዎች የፓርቲ አባላትን በስነ ምግባር የታነፁ እና ሰላማዊ ትግል በሰለጠነ መንገድ የሚደረግና በግብግብ ሳይሆን በሃሳብ የበላይነት የተመሰረተ እንዲሆን ለማድረግ ለሚያካሂደው ስልጠና ለማካሄድ አዳራሽ ለመከራየት ባቀረብነው ጥያቄ በጎ ምላሽ እንደሌለ ከውስጥ ሰምተን ምክንያቱን በግንባር ለማወቅ ሄጄ የሰማሁት ምላሽ በአንድ መንግሰታዊ ተቋም ውስጥ ተቀጥሮ ደሞዝ ከሚበላ ሲቪል ሰራተኛ የሚጠበቅ ሆኖ አላገኘሁትም፡፡ የሰጡን ምላሽ “አራት ሰዎች መጥተው ፍቃዱ እንዳይስጥ ጠይቀው አለቃይ እንዳትሰጥ ስለአለኝ ነው የሚል ነው፡፡” በቃ ይህ ነው ምክንያቱ፡፡ አንድነት ፓርቲ ይህን ፈቃዳ ላለማግኘት አንድም ያጎደለው መስፈርት የለም፡፡ አቶ ማርቆስ አለቃቸው ይህን መልስ ሲሰጣቸው ለምን? እንዴት ብዬ? ከመመሪያ አንጻር ልክ  አይደለም ብለው አይጠይቁም፡፡ አለቃቸውንም አይሞግቱም፡፡ እርሳቸውም የሚያውቁት አለቃቸውም ቢሆን እራሳቸው እንደማይወስኑ፡፡ የሚወስነው ይህ ስውር እጅ ያለው ካዛንችስ የነበረው አሁን በመስተዳድር ቅፅር ግቢ የሚገኘው መንግሰት እንደሆነ፡፡
አንድ መስሪያ ቤት ሰራውን የሚሰራው በአዋጅ በተሰጠው ስልጣን በደንብ እና መመሪያ እንደሆነ ይታወቃል፡፡ ኦፊሰሮች ተግባራቸውን ሲያከናውኑ ደግሞ እነዚህ የህግ ማዕቀፎች መሰረት አድረገው ነው ብለን እንጠብቃለን፡፡ በዚህች ምስኪን ሀገር ግን ይህ ምፀት ነው፡፡ በህግ ማዕቀፍ የሚሰራ ኦፊስር ማግኘት ዘበት እየሆነ መጥቶዋል፡፡ አለቃው በቃል አድርግ ያለውን የሚያደርግ የማርቆስ ዓይነት ኦፊሰር ሞልቶ ተርፎዋል፡፡ በጣም የሚገርመኝ የዚህ ዓይነት ኦፊሰሮች ለልጆቻቸው ሰራ ሄጃላሁ የሚሉ ከሆነ ብቻ ነው፡፡ ባይሉዋቸው ደግ ነው፡፡ ይህን ሊያደርጉ መሄዳቸውን ሲያውቁ ያፍሩባቸዋል ብዬ ስለማስብ ነው፡፡ ለምን ለልጆቻችን ማፈሪያ እንደምንሆን አይገባኝም፡፡
መልካም አስተዳደር አስፍናለሁ የሚል መንግሰት መልካም አሰተዳደር የሚሰፍነው በአዳራሽ ኮፍያና ቲ ሸርት ለብሶ በሚደረግ ዲስኩር እንዳልሆነ የገባው አይመስለም፡፡ መልካም አስተዳደር የሚሰፍነው በህግ ማዕቀፍ አገልግሎት የሚሰጥ ሲቪል ሰርቪስ ሰራተኛ አገልግሎት ሲሰጥ እንጂ በስውር በቃል በሚሰጥ ትዕዛዝ እንዳለሆነ መረዳት ይኖርብናል፡፡ ማርቆስ በሚሰጠው  መልስ እየተበሳጨ፣ እያዘነ ሲከፋውም እየተሳደበ የሚሄድ ተገልጋይ መዘዝ እንደሚያመጠ ግን የገባቸው አይመስለኝም፡፡ ይህ ሁሉ የሚሆነው ደግሞ በስውር መንግሰት በዚህ መንገድ እንዲሆን ስለሚፈልግ ነው፡፡
ዛሬ በግልፅ የተረዳሁት በአዲስ አበባ ከተማ መስተዳድር ብሎም በሀገር አቀፍ ደረጃ መልካም አስተዳደር የማሰፈን ችግር ምንጭ በደህንነት ስም በስውር ያለው መንግሰት የሚሰጠው ትዕዛዝ ሲሆን፣ ሲቀጥልም አድርግ ያሉትን ለማድረግ በተጠንቀቅ ዝግጁ የሆነው የማርቆስ ዓይነት ደሞዝ እየበሉ ያሉ ሲቪል ሰራተኞች ናቸው፡፡ አለቃዬ እንዲህ አድርግ ብሎኝ ነው በሚል መመሪያን መሰረት ያላደረግ ትዕዛዝ የሚሰፈፅሙ የማርቆስ ዓይነት ኦፊሰሮች የዚህች ሀገር መከራ እንዲረዝም፣ ህዝቡ የመልካም አስተዳደር ትሩፋት እንዳያገኝ ተባባሪ እንደሆኑ አበክረን መንገር ይኖርብናል፡፡ ይህንን አሜን ብሎ የተቀበለ ህዝብ መከራውና ግፉ ተስማምቶኛል እንዳለ ይቆጠራል፡፡ የዚህ ዓይነት ህዝብ ደግሞ ምንም ዓይነት አንባገነን መንግስት ቢመጣ የሚገባው ነው ማለት ተገቢ ነው ብዬ አምናለሁ፡፡ ኢህአዴግ አይመጥነንም ያለ ህዝብ በቃ!!!! ሊለው ይገባል፡፡ ኢህአዴግ በቃ ሊባል ይገባል!!!!

ቸር ይግጠምን

Saturday, October 18, 2014

የማሻሻያ ሞሽን

ጥቅምት 3/2007
ክቡር የኢፌዴሪ ፕሬዝደንት በምክር ቤቱ ደንብ መሰረት መሰከረም 26/2007 ዓ.ም ለሁለቱ ምክር ቤቶች የመክፈቻ ንግግር በማቅረባቸው ምሰጋናዬን አቀርባለሁ፡፡ በተለይ ባልተለመደ ሁኔታ የተሟላ ባይሆንም በመብራት መቆራረጥ ለተፈጠረው ችግር ይቅርታ ለመጠየቅ ድፍረት በማሳየታቸው ምስጋናዬ የላቀ ነው፡፡ ይህን ስናበረታታ ከፍ ወዳለው ተጠያቂነትን ወደ መውሰድ ያድጋል የሚል ተሰፋ ስለአለን ነው፡፡
ክቡር ፕሬዝዳንቱ ባቀረቡት የመክፈቻ ንግግር ላይ የተካተቱ እና ተገቢ ያልሆኑ ወይም ያልተሟሉ እና መሻሻል የሚገባቸው ያልኳቸውን ነጥቦች አቀርባለሁ፣
F በየዘርፉ በቀረበው ሪፖርት ያለፈውን አራት ዓመት አፈፃፀም ያካተተ ነው፡፡ ይሁን እንጂ በአብዛኛው የቀረበው መንግሰት ተሳክቶልኛል ብሎ በሚያምነው አካባቢ ነው/ ያለመሳካታቸው የታመነው ከወጪ ንግድና ከውሃ አቅርቦት የመሳሰሉት በስተቀር/፡፡ በሪፖርቱ መግቢያ ላይ ባለፉት አራት ዓመታት ሁለት አሀዝ እድገት እንደተመዘገበ በያዝነው ዓመትም 11.4 እንደሚሆን ይገልፃል፡፡ ይህም ማለት በእድገትና ትራንሰፎርሜሽን ዕቅድ ላይ የተቀመጠው 11.2 ግብ አሳክተናል እንደማለት ነው፡፡ አሁን በመሬት ላይ ያለው ሀቅ ግን፣
o   የባቡር መስመር ከታቀደው 2395 ኪሎሜትር100 ኪሎ ሜትርም አይጠናቀቅም (ሁላችንም እንድናተኩር የሚፈለገው በአዲስ አበባ 34 ኪሎ ሜትር ላይ ብቻ ነው)፤
o   662 ሚሊዮን ዶላር በዓመት የውጭ ምንዛሪ ያስገባል የተባለለቻው የሰኳር ፋብሪካዎች፣ ወደ ውጭ መላኩ ቀርቶ ለሀገር ውስጥ ፍጆታ ከውጭ ግዥ እየተከናወነ ነው፤
o   የማንፋክቸሪን ሴክተር እየተሰፋፋ አይደለም፣በዚህ ዘርፍ ለመሳተፍ የሚመጣ ባለሀብት ቢኖር እንኳን ሊያስተናግደው የሚችል የሀይል አቅርቦት የለም (8000 ሜጋ ዋት ይኖረናል ተብሎ የነበረው በዕቅድ ዘመኑ መጨረሻ 3500 መድረስ ከተቻለ ትልቅ ስኬት ነው)፤
o   የመንገድ ግንባታ ከታቀደው ግማሽ መሰራት የሚቻል አይመስለንም፤
o   የትላልቅ ዘመናዊ እርሻዎች ታቅደው የነበረው 3ሚሊዮን ሄክታር ለአልሚዎች ለመስጠት አስር በመቶ እንኳን የተሳካ አይደለለም፣ የተሰጣቸውም ቢሆኑ በአግባቡ እየሰሩ እንዳልሆነ ይታወቃል፤
o   በምግብ እህል እራሳችንን ጭለናል የሚል ፕሮፓጋንዳ ቢኖርም ሰንዴ አሁን ከውጭ እየገዛን ለዋጋ ማረጋጋት በሚል እየቀረበ ነው እየቀረበ ነው፤
እነዚህን ዋና ዋና የልማት ግቦች ማሳካት ባልተቻለበት ሁኔታ በዕቅዱ የመጀመሪያ ሶስት ዓመታት የነበረውን እጅግ አሳሳቢ የዋጋ ንረት ጋር ተደምሮ  የእድገቱ ቁጥር ለዕቅዱ ሊቀንስ ያልቻለው ምን የተለየ እነዚህን ጉድለቶች ማካካሻ ተገኝቶ ነው? የሚል አጠቃላይ አሰተያየት አለኝ፡፡ የእነዚህ ጉድለቶች ለእድገት ምጣኔ ትርጉም የላቸውም አንባልም ብዬ ነው፡፡

F በሪፖርቱ ገፅ 4 ቁጠባ በእድገትና ትራንሰፎሜሽን ከታቀደው በላይ መድረሱን ነገር ግን ከዚህ በላይ መስራት የሚያስችል አቅም እንዳለ ይገልፃል፡፡ አሁን የተገኘውም ውጤት በከተማ የቤቶች ግንባታ እና በቦንድ ሸያጭ የተገኘው ከፍተኛ ነው፡፡ ሪፖርቱ የግብርናው ሴክተር የኤኮኖሚው የጀርባ አጥንት ሆኖ ቀጥሎዋል በተለይም አነሰተኛ ማሳ በሚያካሄደው የአርሶ አደር ሚና ከፍተኛ እንደሆነ አሰቀምጦዋል፡፡ ከዚህ ሴክተር ቁጠባን በተገቢ ሁኔታ ማግኘት ያልተቻለው እና ለሀገር ውስጥ ገቢም ይህ ነው የሚባል ድርሻ ያልታየበት ምክንያት በሪፖርቱ ውስጥ አልተገለፀም፡፡ አሰተያየቴን ግልፅ ለማድረግ ሚሊየነር አርሶ ሀደሮች በቁጠባና በግብር ከፋይነት ያላቸው ሚና ምን ያህል እንዲሆነ አይታወቅም ለማለት ነው፡፡ ሁሌም ሲሸለሙ እንጂ ግብር ከፈሉ ሲባል ሰለማንሰማ ነው፡፡

F በሪፖርቱ ገፅ 4 ላይ “… ሀገራቸን ምንም እንኳን በመንግሰት ዋስትናም ሆነ ከዚያ ውጭ የምትወስደው የብድር መጠን ከጊዜ ወደጊዜ እየጨመረ የመጣ ቢሆንም በተለያዩ የዕዳ ጫና መለኪያዎች መሰረት ዝቅተኛ የዕዳ ጫና ካላቸው ሀገሮች ተርታ ትገኛለች፡፡….. ይህም ተጠብቆ ይቀጥል፡፡” ይላል፡፡ በቅርቡ የኢንተርሸናል ሞነተሪ ፈንድ ያቀረበው ሪፖርት እንዲሁም የዓለም ባንክ የሚያወጣቸው ፅሁፎች ከዚህ በተቃራኒ መንግስት ለመሰረተ ልማት ግንባታዎች የሚወሰዳቸውን ብድሮች ተጠቃለው የማይታዩ በመሆናቸው እነዚህ ብድሮች ጫናቸው ከፍተኛ ነው ብሎዋል፡፡ በዚህ ጉዳይ ላይ ሰምምነት መድረስ አለመቻሉም ተዘግቦዋል፡፡ መንግሰት የሚገነባቸው የመሰረተ ልማት አውታሮች ከመንግሰት በጀትም ሆነ የብድር ዕዳ ውስጥ ለማሳየት ያልተፈለገበት ምክንያት ተቀባይነት ያለው አይመስለኝም፡፡ ሪፖርቱም ከዚህ አኳያ ሙሉ ነው ማለት አይቻለም፡፡

F በሪፖርቱ ገፅ 6 “… ሀገራዊ ባለሀብቱ አሁንም በኢንዱስትሪው ዘርፍ ያለው ተሳትፎ አነሰተኛ ነው፡፡ በያዝነው ዓመት ማነቆዎችን ለመፍታት ተዋናዮችን ያሳተፈ ጥረት ይደረጋል፡፡” ይላል፡፡ ከዚህ አንፃር እጅግ ተሰፋ ሰጪ የሆነ የሀገር ውስጥ ቁጠባና ኢንቨሰትመንት በሚያበረታታ መልኩ በአክሲዮን ተቋቁመው ወደ ሰራ ለመግባት በጅምር ላይ የነበሩ ለምሳሌ ሀበሻ ሲሚንቶ፤ ከዚህ በፊት ጠቅላይ ሚኒስትሩ በስም የጠቀሱት ህብር ስኳር ለመሳሰሉት ትላልቅ የግል ባለሀብት ለሚመጡ ተነሳሸነቶች በቂ ትኩረትና ድጋፍ አለመስጠቱን ስናይ ሪፖርቱ በተግባር ካለው ጋር የሚጋጭ ነው የሚል አስተያየት አለን፡፡ አሁንም በዚህ ዓይነት ከመንግሰት ውጭ ለሚመጡ ተነሳሽነቶች ምንም ዝግጅት አይታይም፡፡

F በቤቶች ልማት በሪፖርቱ የቀረበው ቁጥር እና በሚሊዮን ከሚቆጠረው ቤት ፈላጊ ጋር ሲነፃፀር አሁንም ተመጣጣኝ ነው የሚል እምነት የለኝም፡፡ ባለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት እንዳልኩት መንግሰት የተመዝጋቢዎቹን ፍላጎት በማርካት ተሰፋቸውን ያለመልማል ብዬ አላምንም፡፡ ይህ ፕሮግራም መንግሰት ባለው አቅምና ቁርጠኝነት ላይ የሚፈተንበት እንደሚሆን አሁንም እምነቴ ነው፡፡ በሪፖርቱ ውስጥ “ በማህበር ተደራጅተው የሚሰሩ ዜጎች በተያዘው አቅጣጫ መሰረት የሚሰተናገዱ ይሆናል፡፡” ይላል፡፡ ይህ አቅጣጫ ምንድነው? ዜጎች ተበድረው ገንዘብ ባንክ ካሰገቡ በኋላ የመንግሰት የአቅጣጫ ለውጥ እና የአዳዲስ መመሪያና አቅጣጫ ፍለጋ የገባበት ምክንያት መታወቅ ይኖርበታል የሚል እምነት አለኝ፡፡ ከዚህ ጋር ተያይዞ በውጭ ለሚኖሩ ኢትዮጵያዊያን እና ትውልደ ኢትዮጵያዊያን የተያዘው አቅጣጫ ግብር ከፋዩ ዜጋ በግልፅ ሊያውቀው ስለሚገባ ግልፅ መሆን ይኖርበታል ብዬ አምናለሁ፡፡

F በሪፖርቱ ገፅ 11 “…. የሰኳር ልማት እና የማዳበሪያ ፋብሪካ ግንባታዎች በከፍተኛ ትኩረት እና ክትትል በተያዘላቸው ጊዜ እንዲጠናቀቁ ርብርብ ይደረጋል፡፡” ይላል፡፡ ለምንድነው ልክ የህዳሴ ግድቡ የደረሰበት ደረጃ እንደሚነገረው እነዚህ ሜጋ ፕሮጀክቶች የደረሱበት ደረጃ በግልፅ የማይገለፀው? በዚሁ ገፅ ላይ የመጠጥ ውሃ በተመለከተ በዕቅድ የተቀመጠው እንደማይደረስ ታምኖዋል፡፡ ስንት ለማድረስ ነው ክለሳ የተደረገው፣ ከዚህ ጋር በተያያዘ የተሳሳተ መረጃ ሲያቀርቡ የነበሩ ተጠያቂ ሆነዋል ወይ? የሚለውን ሪፖርቱ ማካተት አልቻለም፡፡

F በሪፖርቱ ገፅ 15 “በ2007 በሀገራችን የሚካሄደው ሃገራዊ ምርጫ ነፃና ዲሞክራሲያዊ እንዲሆን አስፈላጊው የቅድመ ዝግጅት ሥራዎች እንዲሰሩ መንግሰት የሚጠበቅበትን ሁሉ ያደርጋል፡፡ ሁሉም ተዋናይ ወገኖች ዋናው ፈራጁና ወሳኙ ህዝብ በሀገራቸን  የተፈጠረውን ሰፊ የሃሳብ ግብይት ዕድል በመጠቀም ደረጃ በደረጃ እየጎለበተ የመጣውን ዲሞክራሲያዊ ስርዓታችንን ኃላፊነት በተሞላበት መንፈስ ወደሌላ ከፍታ ማሸጋገር ይጠበቅብናል፡፡” የሚል ነው፡፡ በእኛ እይታ

o   ኢህአዴግ አስፈላጊውን ቅድመ ዝግጅት እንዲያደርግ መንግሰት የሚጠበቅበትን ሁሉ እያደረገ እንደሆነ እንረዳለን፡፡ ለምሳሌ የኢህአዴግን ፖሊሲ ለማስረፅ በመንግሰት ተቋማት፣ በዩኒቨርሲቲዎች ረጅም ጊዜ የወሰደ ውይይት ሲያደርግ ነበር፡፡ እኛም ያለንን አማራጭ ለመግለፅ ለአንድ ቀን ፈቃደኛ የሆኑ ተማሪዎችና መመህራን የሚገኙበት ሁኔታ ሊያመቻችልን ይችላል፡፡ በዚህ አጋጣሚ በተደረጉት ውይይቶች ለህዝቡ ከሰብሰባው ምን እንደተማራችሁ መግለፅ ቢችሉ የሚል ሀሳብ አለኝ፡፡
o   በምርጫ መቼም ዋናው ተዋናይ ፓርቲዎች ናቸው፡፡ ኢህአዴግ እንደ አንድ ፓርቲ በአዲስ አበባ ከተማ በየወረዳው ከመንግሰት ያገኘው ፅ/ቤት አለው፡፡ አንድነት እንደ ፓርቲ ቢሮ ለመከራየት ችግር ላይ ነው፡፡ የገንዘብ አይደለም በህዝቡ ላይ ካድሬዎች በሚፈጥሩት ስጋት ነው፡፡ ይህን እንደ መንግሰት አንድ ቢሮ ለመስጠት ፈቃደኛ ነው ብለው ያምናሉ፡፡ ወይም ባዶ ቦታ ቢሰጠን ደረጃውን የጠበቀ ቢሮ ልንገነባበት የምንችል እንደሆነ ላረጋግጥሎት እችላለሁ፡፡
o   “ሰፊ የሃሰብ ግብይት ዕድል መጠቀም” ማለትስ ምን ማለት ነው? የግል ሚዲያ እንዳይኖር ተግቶ የሚሰራ መንግሰት፣ ብሎገሮችን የሚያስር መንግሰት፣ የመንግሰትን ሚዲያ ለገዢው ፓርቲ መጠቀሚያነት ብቻ እንዲውል ለወሰነ መንግሰት ሰፊ የሃሳብ ግብይት ተፈጥሮዋል ለማለት ድፍረቱ ከየት እንደመጠ ግልፅ አይደለም፡፡
ሰለሆነም እነዚህ አገላለፆች ከሪፖርቱ ውስጥ እንዲወጡ ወይም እንዲሻሻሉ ቢደረግ መልካም ነው እላለሁ፡፡
ክቡር ፕሬዝዳንቱ ባደረጉት የመክፈቻ ንግግር ላይ ያልተካተቱና እንዲካተት ወይም ተገቢው ትኩረት እንዲሰጣቸው የምንፈልጋቸው ጉዳዮችን በዋና ዋና ርዕስ በማድረግ አቅርባለሁ፡፡
ፖለቲካዊ ጉዳዮች፤
F የ “ፀረ ሽብር ህግ” ሲወጣ እንደ ምክንያት ቀርቦ የነበረው ምርመራን ለማቀላጠፍ እንደሆነ ሲገለፅ ነበር፡፡ ነገር ግን አሁን ባለው ሁኔታ በፓርቲ ውስጥ ንቁ ተሳትፎ የሚያደርጉ ወጣቶችን እነ ሀብታሙን፤ ለሰላማዊ ለውጥ የሚተጉ ብሎገሮችን፤ አሰሮ ምርመራ እያደረኩ ነው ብሎ ማንገላትት ለዚህች ሀገር የሚጠቅም አይደለም፤ከዚህ ቀደም በወህኒ ቤት የሚገኙ ጓዶቻችን እነ አንዱዓለም ናትናኤል በቀለ ገርባ እንዲሁም  ጋዜጠኞች እስክንድር፣ ርዕዮት የመሳሰሉት የህሊና እስረኞች ናቸው ብለን ስለምናምን አሁንም ፖለቲካው መፍትሔ የሚሻ ጉዳይ ነው ብለን እናምናል፤

F በአሁኑ ሰዓት መንግሰት በውጭ ከሚኖሩ ኢትዮጵያዊያን ጋር የገጠመው አላስፈላጊ ግብ ግብ ለልማት ልናውለው የምንችለውን አቅም ከማባከን ያለፈ አንድም ፋይዳ ስለማይኖረው በሁለቱም ወገን ስክነት በተሞላበት ሁኔታ በውይይት እንዲፈታ ማድረግ ይገባል ብለን እናምናለን፡፡ ይህ በግንባር ቀደምነት መውሰድ ያለበትም መንግሰት ነው የሚል እምነት አለን፡፡ ይህ ሲሆን በውጭ የሚኖሩ ኢትዮጵያዊያን እና ትውልደ ኢትዮጵያዊያን ለሀገራቸው የሚያደርጉትን አስተዋፆ አሁን በሪፖርቱ ከተገለፀው በላይ ማድረግ ይቻላል የሚል እምነት ስለአለን ነው፡፡


F ባለፈው ዓመት ሪፖርት “የመድበለ ፓርቲ ሰርዓቱን ለማጠናከር ይቻል ዘንድም መንግሰት በህገ መንግሰታዊ ሰርዓት በተበጁ ህጋዊና ሰላማዊ ስልቶች ዓላማቸውን የሚያራምዱ የፖለቲካ ፓርቲዎች ለሚያደርጓቸው ፖለቲካዊ እንቅስቃሴዎች ምቹ ሁኔታዎችን ለመፍጠር የሚያደርገውን እንቅስቃሴ አጠናክሮ ይቀጥላል፡፡”የሚለው በዝርዝር ተቀምጦ ለክትትል/ለመጠየቅም በሚመች መልኩ ቢቀመጥ መፍትሄ ይሆናል፡፡ የሚል አስተያየት የሰጠሁ ቢሆንም ተቀባይነት አላገኝም እንደዛ ሆኖም አንድም ነገር ሳይከናወን ዓመቱ ተጠናቆዋል፡፡ አሁንም ቢሆን በሰላማዊ መንገድ በሀገር ውስጥ ለሚደረግ እንቅስቃሴ መንግሰት የሚፈጥረው ምቹ ሁኔታ እጅግ አስፈላጊ መሆኑን በመገንዘብ ግልፅ የሆነ እርምጃ እንዲወሰድ እንጠይቃለን፡፡

F ዛሬም እንደ ሁልጊዜው በድጋሚ መግለፅ የምፈልገው ተቃዋሚዎች እና ገዢው ፓርቲ በማንስማማባቸው የርዕዮት ዓለምና ፖሊሲ ዙሪያ በግልፅ ልዩነታችን እንደተጠበቀ ሆኖ፣ በጋራ የሀገር ጉዳይ እስከአሁን የሄድንበት ቅጥ ያጣ ፍረጃ እንዲቆም ማድረግ፤ ልዩነታችንን የምናራምድበት መድረክ በእኩልነት ማግኘት (በአስተዳደራዊና በፀጥታ ሀይሎች በኩል የሚደርስብን በደል እንግልት ያለምንም ቅድመ ሁኔታ ማስቀረት)፤የቅድሚያ ቅድሚያ የሚሰጠው ተግባር መሆን ይኖርበታል፡፡ በተለይ በዚህ የምርጫ ዓመት ለምርጫ በሚደረግ ቅስቀሳ ከፍተኛ ጥንቃቄ ማድረግ ይኖርብናል ብለን እናምናለን፡፡


F የፖለቲካ ምዕዳሩን መሰፋትና መጥበብ ለዲሞክራሲያዊ ስርዓት ግንባታ ያለውን ሁኔታ በመረዳት፤በጋዜጦችና መፅሄቶች ላይ ከህግ ውጭ ማተሚያ ቤቶች እንዳያትሙ የሚያስፈራሩ ካድሬዎችን፤ ከህግ አግባብ ውጭ የሚደረጉ እንቅስቃሴዎች በሙሉ ከውንብድና የሚለዩ ባለመሆናቸው ማሰቆም የማይችል እንዲሁም ይህንን ድርጊት ደግ አደረጉ የሚሉ የመንግሰት ሹሞችን አደብ የማያስገዛ መንግሰት  ጠመንጃ ካነሱበት ይልቅ በሃሳብ ሊታገሉት የተነሱትን እንዲመፈራ ማሳያ ብቻ ሳይሆን በሃሳብ ለመፋለም ዝግጁ ያለመሆኑን የሚያሳይ ነው፡፡

F ምርጫ በሚመለከት ምርጫ መወዳደር ለፓርቲዎች መደበኛ ተግባር እንደሆነ ይታወቃል፤ ለህዝብ ምርጫ እንዲሳተፍ ሲጋበዝም አማራጭ መኖሩን እርግጠኛ መሆን ያስፈልጋል፤ ከዚህ አንፃር መንግሰት አማራጭ የሌላቸው ተቃዋሚዎች የሚለውን በመተው አማራጫችንን ልናቀርብ የምንችልባቸውን በህግ የተፈቀዱትን ስርዓቶች እንዲያሰከብርልን በድጋሚ እንጠይቃለን፤በዲሞክራሲያዊ መንገድ የሚመጣ ማነኛውንም ውጤት ለመቀበል ግን ገዢው ፓርቲ ዝግጁ መሆኑን ማረጋገጥ ይኖርበታል፡፡


F በሀገራችን ኢትዮጵያ በተለያዩ ቦታዎች ዜጎች በብሔራቸውና የሚናገሩትን ቋንቋ መሰረት በማድረግ እንዲፈናቀሉ እየተደረገ ነው፡፡ ይህ ጉዳይ የፌዴራል መንግሰትን ጣልቃ ገብነት እስከ መጠየቅ ደርሶዋል፡፡ ማነኛውም ኢትዮጵያዊ በፈለገው ቦታ የመኖር ህገ መንግሰታዊ መብት ከመቼውም በላይ አደጋ ላይ እየወደቀ ነው፡፡ ይህ ደግሞ በህገ መንግሰት እውቅና ያገኘውን አንድ የፖለቲካ ማህበረስብ ምስረታ አደጋ ላይ የሚጥል ነው፡፡ ከዚህ አንፃር መንግሰት ችግሩን ከሰሩ ለመፍታት አቅም እንዳነሰው ማሳያ ነው፡፡ መንግሰት የችግሩ ምንጭ ከላሆነ ማለት ነው፡፡
ኤኮኖሚያዊ ጉዳዮች በተመለከተ
F አዲስ አበባ ከተማ ላይ እየቀረበ ያለ የሊዝ ዋጋ ከፍተኛ መሆኑ ምንጩ አሁንም በቁጥ ቁጥ እየቀረበ ያለ የመሬት አቅርቦት ሲሆን፣ በእኛ እምነት ይህን ቦታ በዚህ ዓይነት ዋጋ እየገዙ ያሉ ሰዎች ልማታዊ ባለሀብቶች ናቸው ብለን ለመውሰድ እንቸገራለን፡ይህ ሁኔታ በመኖሪያ ቤትም ሆነ በአገልግሎቶች ላይ የዋጋ ንረት እንደሚፈጥር ግልፅ ነው፡፡ ከዚህ ውጭ በህገ ወጥ መንገድ የተገኙ ገንዘቦች መመሸጊያ እንዳይሆን ሰጋት አለን፡፡ 65 ሺ ብር በካሬ ገዝቶ ምን ሊነግድበት እንደሆነ ማወቅ ከባድ ነው፡፡ መንግስት በአዲስ አበባ የሊዝ ሰርዓት ላይ ተገቢውን ማስተካከያ ማድረግ እንደሚችል ካላረጋገጥ ይህች ከተማ ለመካከለኛ እና ዝቅተኛ ገቢ ላላቸው ዜጎች መኖሪያ አይደለችም ብሎ እንደማወጅ ይቆጠራል፡፡

F ሀገራችን ኢትዮጵያ ንግድ ለመጀመር 2013 ከ 185 ሀገሮች 163 ከነበረችበት በ2014 ወደ 166 ዝቅ ብላለች፣ የሚገርመው ታክስ ለመክፈል ከነበረችበት 103 ወደ 109 ዝቅ ብላለች ይህን መንግሰት የኒዎ ሊብራል ሪፖርት ሊለውና ችላ ሊለው ቢችልም ለኢንቨሰትምንት የሚመጡ ባለሀብቶች ግን እምነት የሚጥሉበት ሪፖርት እንደሆነ ግልፅ ነው፡፡ ኢንቨሰትመንት ለመሳብ እየሰራን ነው እየተባለ ውጤታችን ዝቅ የሚልበት ምክንያት ማወቅ መፍተሔውን ለማግኘት ይረዳል ተብሎ ይታመናል፡፡ ታክስ ለመክፍል መቸገር ማለት ምን ማለት እንደሆነ ታክስ የምንከፍል ሰዎች እናውቀዋለን፡፡


ማሕበራዊ ጉዳዮች
F ወደ ተለያዩ ሀገሮች ለስራ በተለይ ወደ ሀረብ ሀገራት የሚሄዱ ሰዎች ህግድ ሳይነሳ በመቆየቱ ህገወጥ ዝውውሮች እየተበራከቱ መሀኑን ብዙዎች ይናገራሉ፡፡ በሀገራችን ያለው እድገት ዜጎችን ከሰደት መታደግ እስኪችል በህጋዊ መስመር እንዲሄዱና ለዜጎች ተገቢው ጥበቃ ማድረግ የሚችል መንግስት መሻታችን ይቀጥላል፡፡ በዚህ ጉዳይ ክፍተት ያለበት ሪፖርት ነው ብዬ ነው የምወሰደው፡፡

F አሁንም ዜጎች ለህክምና ወደ ውጭ እየሄዱ ከፍተኛ ወጪ እንደሚዳረጉ ይታወቃል፡፡ ከዚህ አንፃር በእድገትና ትራንሰፎርሜሽን ዕቅድ በተቀመጠው መሰረት ውጤት ማምጣት አልተቻለም፡፡ ይህ ጉዳይ አሁንም ይህች ሀገር የግል ባለሀብት በዚህ መስክ ለመሳብ ካለብን ችግር ጋር የተያያዘ መሆኑን ሪፖርቱ መግለፅ የቻለ አይደለም፡፡

በመጨረሻም
መንግሰት/በተለይም ገዢው ፓርቲ በቀጣይ ምርጫ ከግል ቡዳናዊ አስተሳሰብ ወጥቶ ለሀገር በሚበጅ መልኩ ለመድበለ ፓርቲ ስርዓት ግንባት የበኩሉን ድርሻ እንዲወጣ እየጠየቅን፤ በእኛ በኩል በኃላፊነት ሰሜት እንደምንንቀሳቀስ እና የኢትዮጵያ ህዝብ ግልፅ አማራጭ እንዳለን የምናሳይበት እንደሚሆን ለኢትዮጵያ ህዝብ ማረጋገጥ እፈልጋለሁ፡፡ 
ፈጣሪ ኢትዮጵያ ሀገራችንን እና ህዝቧን ይባርክ!!!!!!
አመሰግናለሁ
ግርማ ሠይፉ ማሩ