Tuesday, October 13, 2015

ኢህዴግ በሚጠራው መድረክ አለመገኘት ማንን ይጠቅማል? ግርማ ሠይፉ ማሩ



girmaseifu32@yahoo.com, www:girmaseifu.blogspot.com
ቅጥ አንባሩ የጠፋው የኢትዮጵያችን ፖለቲካ በዋነኝነት የሚጎድለው ልክ ያልሆነን ነገር ልክ አይደለም ማለት ያለመቻል ነው፡፡ በግል አስተያየት ልክ አይደለም ብሎ መቆም ደግሞ ዋጋ ያስከፍላል፡፡ የተሳሳተ ውሳኔ ባለቤቶች በድጋሚ ጥፋታቸውን በጥፋት ለማረም ሌላ ስህተት ይደግማሉ፡፡ አሰተያየትን በአሰተያየት ለመመለስ ይከብዳቸዋል፡፡ የዚህ ደግሞ ዋነኛው ሰለባ የተቃዋሚው ጎራ ነው፡፡ ለነገሩ አሁን ይህ ነው የሚባል ተቃዋሚ አለ ባይባልም፤ ያሉትም ቢሆኑ ከልምድ የሚማሩ ዓይነት ሆነው አልተገኙም፡፡
ለዛሬ ፅሁፌ መነሻ የሆነኝ አንድ ሰሙ “የአንዳርጋቸው ፅጌ ብርሃን” በሚል የብዕር ሰም የሚከተለውን መልዕክት በፌስ ቡክ ገፄ የውስጥ መልዕክት ማስቀመጫ
“ግርማ ካሳ (ልብ በሉ እኔ ግርማ ሠይፉ ነኝ) ወረድክብኝ በጣም። ተፈጭቶ ተቦክቶ ተጋግሮ ሊበላ የቀረበውን ነገር ድጋሚ ወፍጮ ቤት ይሂድ ብለክ እየተከራከርክ ነው። 24 አመት ሲያታልል የኖርን መንግስት ዛሬ 25ኛው አመት ላይ ሆነክም እንዴት አልገባክም? ስንት አመት ነውሚፈጀው እንዳንት አይነት ሰዎችን ለማብሰል? ተወያየተክ ምን ታተርፋለክ ? ወያኔ ተቃዋሚዎችን  ሚፈልገው ለተራ ፕሮፖጋንዳው ሊጠቀምባቸው እንጂ ለነሱ ሀሳብ ጆሮ ለመስጠት አደለም። መንግስት እራሱ ያወጣውን ህግ ጥሶ ያሰራቸውን የፓርቲ አባሎችን ለማስፈታት ከወያኔ ጋር ስብሰባ መቀመጥ አያስፈልግም። እንዲምታስብ ከሆነ ከአልም ሁሉ ተለይተክ ከሀይለማርያም ደሳለኝ ብቻ የተሻልክ ጅላጅል ነክ ማለት ነው። ወያኔ ተቃዋሚ ፓርቲዎች የተጻፈውን ድብዳቤ ልብ ብለክ አንብበከዋል ? እንዲ የሚል አርፍተ ነገር አለበት። "በሀገራችን የሚገኙ ሀገር አቀፍ ፓርቲዎች "እንደ መላው የሀገራችን ህዝቦች " እያለ ይቀጥላል። ሲጀመር ወያኔ እነዚ ፓርቲ ብሎ የሚያውቃቸው ድርጅቶች ከህዝብ ተለይተው ያሉ እና የህዝብ ድጋፍ የሌላቸው አርጎ ነው የጠራቸው። ፀረ ህዝብ አርጎ ነውሚስላቸው። አንደ ህዝብ አካል አርጎ አይቆጥራቸውም አያከብራቸውም። አንዳንተ ዓይነት አሟሟቂ ሰው ነው ወያኔሚፈልገው።ኢቢሲን አሟሟቂ”
የሚል መልዕክት አስቀመጠልኝ፡፡
መልዕክቱ የተፃፋው በዚህ ጉዳይ አስተያየት ለሰጠው ወዳጄ ግርማ ካሣ ይመስላል ነገር ግን  የተላከው ለእኔ በእኔ አድርሻ እና እኔን በዓይነ ልቦናው እየሳለ እንደሆነ ያስታውቃል፡፡ በእኔ እይታ ደግሞ የግርማ ካሣን ሃሳብ መደገፍ ብቻ ሳይሆን በግል ለደወሉሉኝ አቋሜን ገልጬ ነበር፡፡ በዚህ ጉዳይ  ግን ሚዲያ ላይ ወጥቶ አስተያየት መስጠት ብፈልግም፤ ብዙ ምቾት አልተሰማኝም ነበር፡፡ ለማነኛው የዚህ አሰተያየት ሰጪን ሃሳብ መነሻ አድርጌ የግሌን አስተያየት ላቅርብ፡፡
በመጀመሪያ ማነኛውም ግብዣ ላይ የተጠራ ሰው ግብዣ የሚሄደው በመከባበር ሰሜት መሆን አለበት፡፡ ጠሪ አክባሪ በሚል እንጂ ግብዣው ላይ ምን ድግስ አለ በሚል መሆን የለበትም፡፡ በእኔ እምነት ለመጀመሪያ ጊዜ በሀገራዊ አጀንዳ ላይ ከዚህ በፊት ጥሪ ተደርጎላቸው የማያውቁ የፖለቲካ ፓርቲውች መድረክ፣ ሰማያዊ እና መኢህአድ ግብዣ ተደርጎላቸዋል፡፡ ለምሳሌ በመጀመሪያው የአምስት ዓመት ዕድገትና ትራንሰፎርሜሸን ዕቅድ እና በአባይ ግድብ ወቅት ጥሪ ስለ አልተደረገላቸው አልተጠራንም ሃሳባችንን መስጠት እና የጋራ ማድረግ አልቻልንም ሲባል ነበር፡፡ በዚህ ወቅት የፖለቲካ ምዕዳሩም ሆነ አጠቃላይ ሀገሪቱ ያለችበት ሁኔታ ተመሳሳይ ነበር፡፡ በዛን ጊዜ ተቃዋሚዎች አልተጠራንም ሲሉ የነበረው ተጠርተው ለመቅረት አይመስለኝም፡፡ ተገኝተው ሃሳባቸውን ለማካፈል ይመስለኛል፡፡
በእኔ እምነት አሁን በተደረገው ጥሪ መስረት ከላይ ሰማቸውን የጠቀስኩት ፓርቲዎች ተገኝተው የሚከተለውን ማከናወን ይችሉ ነበር፡፡ መጀመሪያ ያለፈው አምስት ዓመት ክንውን ሲቀርብ ከመነሻው ጀምሮ በጋራ ከተቃዋሚዎች ጋር በጋራ ለመስራት መንግሰት እርምጃ ባለመውሰዱ የእቅዱ ዋና ዋና ምሶሶ የሆኑት ተግባራት ያለመሳካታቸውን በተጨባጭ ማስረጃ ለማስረዳት እድሉን ሊጠቀሙበት ይችሉ ነበር፡፡ ለምሳሌ የባቡር ዝርጋታ ከታቀደው 30 ከመቶ ያለመሰራቱ፣ በኤሌትሪክ ሀይል በተመሳሳይ 20 ከመቶ እንኳን ያለመሳካቱ፤ በመንገድ በውጭ ንግድ፣ በዋጋ ማረጋጋት፣ በግብርና በተለይ በሰፋፊ እርሻ ወዘተ.. ያሉትን መሰረታዊ ችግሮች በማሳየት ለዚህ ዋነኛው ችግር በጋራ በመስራት ሊገኝ የሚችለውን ሀገራዊ ሀይል ወደ ጎን ማድረጋቸውን ለህዝብ ይፋ ማድረጊያ መድረክ ይሆን ነበር፡፡ በተለይ የአባይ ግድብን ገዢው ፓርቲ የፖለቲካ መጠቀሚያ እንዲሆን በማድረጉ በውጭ የሚኖሩ ኢትዮጵያዊያን እና ትውልደ ኢትዮጵያዊያን ሊያደርጉ የሚችሉት ከፍተኛ አሰተዋፅኦ መገደቡን ለመናገር ከዚህ የተሻለ ትክክለኛ መድረክ የሚያገኙ አይመስለኝም፡፡ ይህንን መድረክ ለመጠቀም ባለመቻላቸው ትልቅ የፖለቲካ ኪሣራ ይመስለኛል፡፡
በሌላ በኩል ደግሞ ገዢው ፓርቲ እራሱ ያመነውን የመልካም አስተዳደር መፍቻው ቁልፍ መንገድ የመድበለ ፓርቲ ስርዓት ግንባታ እና በተለይ ደግሞ የሚዲያዎች ተሳትፎ መኖር ተዓማኒነት የሚጣልባቸው የፍትህ ስርዓት መሆኑን በሰብሰባው በሚፈጠሩ አጋጣሚዎች ሁሉ በማንሳት ዕቅዱ ያልተሳካው ይልቁንም ሙስና የተንሰራፋው ስርዓቱን የሚተቹ ጋዜጠኘኞችና አምደኞች በመታሰራቸው፣ እምነት የሚጣልበት የፍትህ ስርዓት ባለመኖሩ እንደሆነ አጋጣሚውን መጠቅም ይቻል ነበር፡፡ ለዚህ ደግሞ ተመሳሳይ አቋም ያላቸው ተቃዋሚ ፓርቲዎች ዝግጅት አድርገው መሳተፍ እንጂ አድማ አድርጎ ከግብዣ በመቅረት ውጤት የሚገኝ አይመስለኝም፡፡ ይህ ትልቅ ሰህተት ይመስለኛል፡፡
ከዚህ ውይይት በማስከተል “የፈሰሰ ውሃ አይታፈስም” በሚል ተረት ከገዢው ፓርቲ ጋር ተመራርቆ ለመውጣት ሳይሆን በቀጣይ ዕቅድ ተቃዋሚ ፓርቲዎች በተለያዩ ሀገራዊ አጀንዳዎች በምን መልክና ደረጃ ስንሳተፍ ይህ ዕቅድ ተግባራዊ ይሆናል በሚል መነሻነት የድርጊት መርዓ ግብር በመንደፍ የጋራ ኮሚቴ አቋቈሞ መውጣት፣ በተለይ የፖለቲካ ምዕዳሩ ለማስፋት የሚቻልበት መንገድ መቀየስ ሊሞከር የሚገባው ትልቅ ስራ ነበር፡፡ ይህ ከገዢው ፓርቲ ባህሪ አንፃር ተቀባይነት ባያገኝ እንኳን እንቢተኝነቱን ለማጋለጥ ይረዳ ነበር፡፡ እንደ ፓርቲ ሰርተፊኬት ይዞ ዓመት ከመቁጠር በዘለለ መንግሰት በተገኘበት ሁሉ እየተገኙ ድምፅ ማሰማት (ባይሰሙም መጮኽ) ግዴታቸው ነበር የሚል የግል አቋም አለኝ፡፡
እውነቱን ለመናገር በቁጥር እስከ ሃያ የሚደርሱ የፓርቲ አባላትን (ለምሳሌ ሶስቱ ፓርቲዎች 60 አባላትን) በአንድ መድረክ ላይ እንዲገኙ የተሰጠን እድል ያለመጠቀምን ያክል ደካማ ውሳኔ አይታየኝም፡፡ እያንዳንዳቸው ሁለት ደቂቃ መልእክት ቢያስተላልፉ የሁለት ሰዓት መልዕክት በመንግሰት ጆሮ ላይ ማስቀመጥ ይቻል ነበር፡፡ እነዚህን አጋጣሚዎች በእስር የሚማቅቁ ጓዶቻችንን በማንሳት ልንዘክራቸው ይገባ ነበር፡፡ አሸባሪ ያሏቸውን “ጀግኖች” ብለን ልናወደስ የምንችልበት መድረክ ያለመጠቀም በምን መመዘኛ ልክ እንደሚሆን አይታየኝም፡፡
ገዢው ፓርቲ ከአሁን በኋላ ለማነኛውም ዓይነት ውይይት ሳይጠራ ዳተኛ ቢሆን ሰበብ አግኝቷል፡፡ ቢጠሩም አይገኙም ይልቁንም በሚጠሩበት መድረክ ከመገኘት ይልቅ ውጪ ሆነው መግለጫ በማውጣት ላይ ይገኛሉ ብሎ ለሀጋሮቹ ማስረጃ ያቀርባል፡፡ በአሁኑ ወቅት ከኢህዴግ መንግስት ባልተናነሰ ካድሬ የሆኑ የአሜሪካን እና አውሮፓ ህብረት ድጋፍ ሰጪዎች ይህን ለመስማት እና ለማመን ብዙ አይቸገሩም፡፡
በእኔ አረዳድ ፓርቲዎቹ በግብዣው ላይ ተገኝተው በምን ጉዳይ አተኩረው እንደሚናገሩ እንዴት አድርገው የፖለቲካ ጥቅም እንደሚያገኙበት መካሪ አላገኙም፣ በውስጥም በቅጡ አልመከሩበትም፡፡ የሚያሳዝነው እነዚህ ፓርቲዎች የአሜሪካ ኤምባሲ ለስዕል ኤግዚቢሽን ምረቃ ቢጠራቸው በግብዣው ላይ ይገኛሉ፡፡ የአውሮፓ ህብረት ፓርላማ አባል ሊያነጋግራችሁ ይፈልጋል ቢባሉ ይገኛሉ፡፡ መገኘት ብቻ ሳይሆን አነጋገሩን ብለው ዜና ይሰራሉ፡፡ እንግዲህ አንባገነኑ ኢህአዴግ ዲሞክራት እሰኪሆን ጠብቀው ለመወያየት ከሆነ ወደፊት የሚታይ ይሆናል፡፡ ባለፈው ፕሬዝዳንት ኦባማ ጉብኝት ሲያደርጉ ለግንኙነት በሚመቸው የእራት ግብዣ ላይ ላለመገኝት ወስነው በብዙ ሜትር ርቀት በቴሌቪዥን በተሻለ ለመከታተል በሚቻልበት የአዳራሽ ስብሰባ ላይ ለመገኘት ሲወስኑ ዝም ማለታችን አበጃችሁ ያልን የመሰላቸው መሪዎች፤ ይህንንም ግብዣ ለፖለቲካ ጥቅም ማዋል አለመቻላቸውን ዝም ማለት ተገቢ አይደለም ለማለት ሲባል የቀረበ አስተያየት ነው፡፡ በእኔ እምነት በሰላማዊ ትግል በሀገር ውስጥ ለመንቀሳቀስ የወሰነ ማንኛውም አካል መንግሰትን በተገኘው አጋጣሚ ሁሉ እያገኙ መልዕክት ማስተላለፍ ተገቢ ብቻ ሳይሆን ግዴታም ጭምር ነው፡፡ ገዢው ፓርቲ እና መንግሰት በሚጠሩት ማንኛውም ስብሰባ ላይ ላለመገኘት መወሰን የሚጠቅመው ገዢውን ፓርቲ ብቻ ነው፡፡ ከዚህ በተቃራኒ ሃሣብ ያለው በመቅረት የሚገኘውን ጥቅም ቢያስረዳኝ፣ በተለይ አሁን በተደረገው የሁለተኛው የእድገት እና ትራነስፎርሜሽን እቅድ ለመወያየት በተደረገው ጥሪ ላይ ያለመሳተፍ ያስገኘውን ጥቅም ለሚያስረዳኝ ለመማር ዝግጁ መሆኔን እገልፃለሁ፡፡ በደፈናው ገዢውን ፓርቲ እውቅና መንፈግ የሚል መልስ ግን አልቀበልም፡፡ በሀገር ውስጥ ሆኖ በዚሁ መንግሰት ስር እየተዳደሩ እውቅና መንፈግ የሚባል ፖለቲካ አይገባኝም፡፡
ቸር ይግጠመን!!!!