Saturday, March 31, 2018

ዶክተር አብይ አህመድ እንደ ጠቅላይ ሚኒሰትር እና የጦር ኃይሎች ጠቅላይ አዛዥ



ተሰፈኞች ተሰፋ የምናደርገው ሞኞች ስለሆንን አይደለም፡፡ ይልቁንም ጮሌዎች፣ በልጣ ብልጦች ሳንሆን አንቀርም፡፡ ይህም በሠላም የመኖራቸን የጤንነታችን መሠረት እንደሆነን እምነቴ ነው፡፡ ተስፋ ቢስነት ምን ያደርጋል? ተስፋ ቢስነት (Negative Energy) ኃይል ጨራሻ ነው፡፡ በሆነው ባልሆነው ተስፋ እየቆረጥን ኃይላችንን መጨረስ ያለብን አይመስለኝም፡፡ ተስፋ የምትቆርጡ ሁሉ የተሰፈኞችን ቡድን ብትቀላቀሉ ምክሬ ነው፡፡ መፅሃፉ እንደሚለው ለራስህ እንዲሆን የምትወደውን፤ ለባልንጀራህም አድርግ እንደሚለው ማለት ነው፡፡ ባለፈው አቶ ሀይለማሪያም ደሳለኝ በወንበር ገፍ ሥልጣን ሲይዙ “ማወከብ ሳይሆን ማገዝ አለብን” ብዬ ስሟገት ነበር፡፡ ይህን በማለቴ ከፓርቲዬ (ነብሱን ይማርና አንድነት ድንክ ሳይሆን) ጭምር ከፍተኛ ውግዘት ደርሶብኛል፡፡ አይቼ አይቼ ሲበቃኝ ደግሞ ከሁለት ዓመት በፊት መሆኑ ነው፤ እባኮትን ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር ሥልጣን ይልቀቁ ብዬ ፃፍኩ፡፡ ሁለቱም ጊዜ ልክ ነበርኩ፡፡ በእርግጥ ከእኔ በተቃራኒ የቆሙትም ቢሆኑ በራሳች መለኪያ ልክ ናቸው፡፡ ብለን ነበር፤ ይኽው ለውጥ የሚባል ነገር አላመጡም፣ ብለው ሊሟገቱ ይችላሉ፡፡ ልዩነቱ የእኔ ብጤዎች ለተወሰነ ጊዜም ቢሆን በተስፋ ዳቦ ኖረናል፡፡ በእኔ እምነት አቶ ሀይለማሪያም ደሣለኝ ላይ ተሰፋ እንድጥል ያደረጉኝ ነገሮች ሁሉ ተሰፋ ለማድረግ ከበቂ በላይ ነበሩ፡፡ እሳቸው ይህን ሊጠቀሙበት አልቻሉም፡፡ ይህ በወርቅ ሳሕን ታሪክ የሰጣቸውን እድል ባለመጠቀማቸው ጥፋቱ የእርሳቸው እንጂ የእኔ እና የእኔ ቢጤ ተስፈኞች ሊሆን አይችልም፡፡ ዶክተር አብይ አህመድ በአቶ ሀይለማረያም ደሣለኝ ላይ ተስፋ እንዳደርግ ያደረጉኝ ምክንያቶች በሙሉ ያሏቸው ሲሆን ሌሎች ተጨማሪ ችሎታዎችም አይቼባቸዋለሁ፡፡ ሰለዚህ ተሰፋ ማድረጌን እቀጥላለሁ፡፡ ተሰፋዬ እውን ባይሆን አሁንም ጥፈቱ የእኔ ሳይሆን የዶክተር አብይ አህመድ ብቻ ነው ሊሆን የሚችለው፡፡ ዶክተር አብይ አህመድ ለኢህአዴግ ሊቀመንበርነት ሲመረጡ በፌስ ቡክ ገፄ ላይ እንዲህ ብዬ ከትቤ ነበር፡፡ “ለታሪክ የተፃፈን ሰው ከታሪክ መዝገብ መፋቅ አይቻልም፡፡ ከአሁን በኋላ አብይ አህመድ በታሪክ መዝገብ ተፅፏል በደግ ይሁን በክፉ ወሳኙ እርሱና እርሱ ብቻ ናቸው፡፡”
በዚህ መነሻ ዶክተር አብይ በመጪው ለምክር ቤቱ ወይም ደግሞ ለመላው ኢትዮጵያ ሕዝብ በሚያደርጉት ንግግር በምንም መመዛኛ ዝም ብሎ ለሕዝብ ግንኙነት ፍጆታ ተብሎ የሚደረግ የፖለቲካ ቃላት ድረቶ መሆን የለበት፡፡ የጠቅላይ ሚኒስትሩ ንግግር ኢህአዴግን እንደ ፓርቲ ከዘመኑ ጋር ሊያቀራርቡት መስራት እንደሚፈልጉ ሊነግሩን ሙከራ ባያደርጉ እመክራለሁ፡፡ ይህ የድርጅት የቤት ሥራቸው ስለሚሆን የሚያደርጉት ንግግር በሙሉ መቃኘት የሚኖርበት በጠቅላይ ሚኒስትርነት እና የጦር ኃይሎች ጠቅላይ አዛዥ በመሆናቸው የሚያደርጉት ንግግር መሆን ይኖርበታል፡፡ ይህን ካልተረዱት የውድቀታቸው መጀመሪያ ይሆናል፡፡ ጠቅላይ ሚኒሰትር ሀይለማሪያም መውደቅ የጀመሩት “የመለስን ራዕይ አስቀጥላለሁ”፣ “ዘላለማዊ ክብርና ሞገስ ለታላቁ መሪ”፣ ወዘተ ማለት ሲጀምሩ ነው፡፡ ተሰፋ ሳንቆርጥ አሻራዎን ያኑሩ ክቡር ጠቅላይ ሚኒሰትር ብንልም አልሰሙን፡፡ መጨረሻቸው ይህ ሊሆን፡፡
ዶክተር አብይ ኢህአዴግን ለሃያ አንደኛው ክፍለ ዘመን የሚሆን ፓርቲ ማድረግ ለእኔ እና ለእኔ መሰል ዜጎች አንድም የሚፈይደው ነገር እንደሌለው መረዳት አለባቸው፡፡ ይህ ለፓርቲ አባሎቻቸው ማድረግ የሚገባቸው ንግግር ነው፡፡ በፓርቲያቸው ጠቅላላ ጉባዔ ላይ ይህን ንግግር ማቅረብ ተገቢ ቦታ ነው፡፡ እኛ ክቡር ጠቅላይ ሚኒሰትር በንግግራቸው ውስጥ እንዲያካትቱት የምንፈልጋቸው ነገሮች አሉ፡፡ ዋና ዋናዎቹን በመጠቆም ሃላፊነቴን ለመወጣት እሞክራሉ፡፡
ፖለቲካዊ ጉዳዮች፤ የኢትዮጵያ አገራችን ፖለቲካ በመንግሰት ሚዲያ ሠላም፣ሠላም፣ ሠላም በሚሉ ዘፈኖች፤ እንዲሁም በቴሌቪዥን በሚበሩ ነጫጭ ወፎች የሚገኝ አይደለም፡፡ የኢትዮጵያ ፖለቲካ ፈውስ የሚያገኘው፣ ሁሉም ዜጋ በአገሬ ጉዳይ ያገባኛል ብሎ በመረጠው መስመር መደራጀት እና ሃሣቡን በነፃነት ለህዝብ ማቅረብ ሲችል፡፡ ሃሣቡን የሚያቀርብበት መድረክ ደግሞ ክፍት እንዲሆን ማድረግ፤ የመንግስት ሃላፊነት ነው፡፡ ባለፉት ሃያ ሰባት ዓመታት ይህ ሊሆን ባለመቻሉ በነፍጥ ያሸነፉት ቤተ መንግሥት በገቡ ማግስት ሌሎች ደግሞ ጥራኝ ጫካው፣ ጥራኝ ዱሩ ብለው ነፍጥ አንስተዋል፡፡ ይህ ሁኔታ ለአንዴ እና ለመጨረሻ ጊዜ እንዲቀለበስ በማንኛውም ሁኔታ ነፍጥ አንስተው ሥርዓቱን ለመጣል የተሰለፉትን ቡድንኖች ወደ ሠላማዊ መድረኩ እንዲመጡ ከልብ የመነጨ ከፖለቲካ ብልጣብልጥነት የፀዳ ጥሪ መደረግ ይኖርበታል፡፡ የሂደቱን ታማኝነት ለማረጋገጠ ደግሞ ገለልተኛ የሆኑ አካላት እንዲሳተፉበት ማደረግ ክብር ያሰጣል እንጂ ውርደት ሊሆን የሚችልበት አንድም ምክንያት አይኖርም፡፡ ይህን ጉዳይ መምራት የክቡር ጠቅላይ ሚኒሰትሩ ኃላፊነት ነው፡፡ በሴራ የተካኑ የቀድሞ ፖለቲከኞች በፍፁም ከዚህ ተግባር ለአገር ፖለቲካ ድህነት ሲባል መራቅ ይኖርባቸዋል፡፡ ቢቻል በፈቃዳቸው ገለል በማለት ሥራቸውን እንዲያቀሉላቸው ጥሪዬን አቀርባለሁ፡፡
በአገር ውስጥ በመንቀሳቀስ ላይ የሚገኙ የፖለቲካ ኃይሎችም ሆኖ ሌሎች ለመንቀሳቀስ ፍላጎት ያላቸው ሁሉ በአገር ውስጥ መንቀሳቀስ እንዲችሉ የሚያስችል ምቹ ሁኔታ መፍጠር የግድ መሆኑን ያህል፤ በግል ጥቅም (ሥልጣን፣ ገንዘብ ወይም ሌላ ሊሆን ይችላል) ተነሳሰተው ሕዝብን አደጋ ላይ ሊጥል የሚችል እንቅስቃሴ ለማድረግ ፍላጎት ያላቸውን ሀይሎች ለመቆጣጠር እና ለማጋለጥ የሚያስችል ጠንካራ የሲቪል ማህበራትና የሚዲያ ተቋማት ሚናቸውን ማሳደግ ያስፈልጋል፡፡ ሲቨል ማህበራት ሕዝቡ አማራጮችን ገምግሞ እንዲወስን ውሣኔውን ደግሞ መቼና እንዴት እንደሚያደርግ ማሰተማር እንዲችሉ ድጋፍ ማድረግ የግድ ነው፡፡ ሚዲያዎች አሁን ካለቸው የአየር ሰዓት ሕዝቡ አማራጨን ለማድመጥ እና ለመመልከት እንዲችል ማድረግ እንዲችል መፈቀድ ይኖርበታል፡፡ ማለትም አሁን የተጫነባቸው የፍርሃት ቆፈን በጠቅላይ ሚኒሰትሩ ንግግር ተስፋ እንዲጫርባቸው ያስፈልጋል፡፡
ዜጎች የተሳሳተ አማራጭም ቢሆን የመምረጥ መብት አላቸው፡፡ ይህ መብታቸው ሊከበር ይገባል፡፡ በተጨማሪ፤ የክልል መንግሰታት ነፃነት ሊከበር እና ፌዴራል መንግሰቱ ደግሞ በጥብቅ የሰብዓዊ መብት አያያዛቸውን ሊከታተል እንደሚገባ ጠቅላይ ሚኒሰትሩ ማስገንዘብ ይኖርባቸዋል፡፡ የክልል መንግስታት የፖለቲካ ነፃነት ለአካባቢያቸው እድገት ብቻ ሳይሆን ለሠላማችን ጭምር ወሳኝ ግብዓት ነው፡፡ የፌዴራል መንግሰቱ ከማገዝ የዘለለ ሚና ሊኖረው አይችልም፡፡ የመድበለ ፓርቲ ሥርዓት የሚወለደው በክልሎች እንደሆነ በግሌ ይሰማኛል፡፡
ከላይ ከተገለፁት አጭር ፖለቲካዊ ጉዳዮች በተጨማሪ ክቡር ጠቅላይ ሚኒሰትሩ እንዲያነሷቸው የሚጠበቀው፤ ምን አልባት በተሻለ ያስቀምጡታል ብዬ የማስበው ኢትዮጵያዊያን ያለን ማህበራዊ ግንኙነት በዘርና ብሔር መከፋፈል እንደሌለበት ይህም ከከፍታችን ያወርደን እንደሆነ እንጂ የሚጨምርልን ነገር አለመኖሩን፣ ሁሉም ዜጋ አገሩ የጋራ መሆኑን አፅዕኖት ይሰጡታል ብዬ አምናለሁ፡፡ ኢትዮጵያዊነታችን የሚደምቀው በማህበራዊ ግንኙነታቸን ውስጥ እንጂ ባለን የፖለቲካ ልዮነት ወይም አስተሳሰብ ሊሆን አይገባም፡፡ ይህን ስፅፍ በፆም ወቅት ምርጥ ዶሮ ወጥ በህሊናዬ እየታየኝ ነው፡፡
ከሁሉም በላይ በአገራችን ኢትዮጵያ ከፍተኛ የኢኮኖሚ እድገት ተመዝግቧል እየተባለ፤ አንዱ በፎቅ ለይ ፎቅ ሲደርብ ሌላው ለምፅዋት እጁን የሚዘረጋበት የኤኮኖሚ ስርዓት መፍረሱን ማብሰር አለባቸው፡፡ ፍትሓዊ ተጠቃሚነት ሲባል፣ ዜጎች በኤኮኖሚ ደረጃ መለያየት መኖሩን ማስወገድ የማይቻል ቢሆንም ልዩነቱ ግን በጥረት የሚመጣ እንጂ ከባልሥልጣን ጋር በመሻረክ እና የእገሌ ዘር በመሆን እንደሌለበት መሰመር ያለበት እና ሁሉም ኢትዮጵያዊ ለሥራ ታጥቆ እንዲነሳ ሊያበረታቱት ይገባል፡፡ ፍትሓዊ ያልሆነ ተጠቃሚነት ምንጩ የፖለቲካ ሥርዓት በመሆኑ ይህ ደግሞ ቀድሞ ማህበራዊ ግንኙነታችንን ቀጥሎም ደግሞ ሥርዓቱን እንደሚገረስሰው ፍንትው ብሎ ታይቷል፡፡ መቼም ይህ ያልተገለፀለት የኢህአዴግ አባል ካለ ችግር ላይ መሆኑን ማስታወስ ያስፈልጋል፡፡
ባለፈው ሶሰት ዓመታት በአገራችን በፖለቲካው ውጥንቅጥ መንስዔ ማህበራዊ እሴቶቻችን እንዲሁም የኤኮኖሚ መሰረቶቻችን አደጋ ላይ ወድቀዋል፡፡ ሰለዚህ ፖለቲካውን በማከም አገራችንን ከውድቀት ልንጠብቃት የግድ ይለናል፡፡ ማንኛውም ዜጋ ደህንነቱ የሚረጋገጠው ኢትዮጵያዊ መንግሰት ሲኖር መሆኑን በማመን የእኔ ብሔር መከላከያ፣ የእኔ ብሔር ደህንነት ካልሆነ አደጋ ላይ እወድቃለሁ ከሚል ስጋት ነፃ እንዲሆን ማድረግ የመጪው ጠቅላይ ሚኒሰትር ትልቁ ሥራ ነው፡፡ የመከላከያ እና የደህንነት እንዲሁም የፖሊስ ተቋማት በሙሉ ለዜጎችና ለአገር ደህንነት እንጂ ለአንድ ቡድን ታዛዥ የሚሆኑበት ሥርዓት ማክተም ይኖርበታል፡፡ የዜጎችን ሃሣብ የሚሰልል ተቋም አያስፈልገንም፡፡ ዜጎችን ከውጭ ጠላት የሚጠብቀን ሠራዊት ያስፈልገናል፡፡ በአገልግሎታችሁ እንኮራለን የምንላቸው የሠራዊት አባላት ይናፍቁናል፡፡ በትምህርት ቤት የሠራዊት ቀን ተብሎ ዩኒፎርም ለብሰው ልጆቻችን ፎቶ ሲነሱ ለማየት ይናፍቀናል፡፡ የኢትዮዮጵ መለዮ ለባሾች ልብስ ዜጎችን ማስፈራሪያ መሆኑ ማብቃት ይኖርበታል፡፡
መልካም የሥራ ዘመን ክበር ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ
ከግርማ ሠይፉ ማሩ


Tuesday, March 27, 2018

ኢትዮጵያችን በመንታ መንገድ በገደል አፋፍ ትገኛለች ዜገች ምን እንወሰን?



የአገራችን ፖለቲካ መበላሸቱ ብቻ ሳይሆን፣ የአገር እልውናን አደጋ ላይ የሚጥል ሊሆን እንደሚችል ስጋት ያላቸው ብዙ ናቸው፡፡ እኔም የፈለገ ተሰፈኛ ብሆን ከዚህ ስጋት ነፃ ነኝ ልል አልችልም፡፡ አፍቃሪ ህወሓት/ኢህአዴግ የሆኑ የማህበራዊ ሚዲያም ይሆን ሌሎች መገናኛ ብዙዓን ይህን ስጋት አጉልተው ለማሳየት የማያደርጉት ጥረት የለም፡፡ ከጥረታቸው ሚዛን የሚደፋው በቅርቡ በመታመስ ላይ ያሉተን ሊቢያ፣ ሶሪያና የመንን እንደምሣሌ በማቅረብ ነው፡፡ ይህ በምሥልና ድምፅ እየተደገፈ የሚቀርበው ዘግናኝ ትዕይንት ለመማር ለሚፈልግ ጥሩ ማሣያ ነው፡፡ ነገሩ ግን ሌላ ነው፡፡ እንደ እነዚህ አገሮች እንዳንሆን አርፋችሁ ተቀመጡ የሚል መልዕክት ያዘለ፣ ሠላም፤ ሠላም፤ ሠላም በሚል መዝሙር አጅበው ማቅረባቸው ነው፡፡ ሊቢያ፣ ሶሪያ እና የመን ለዚህ ደረጃ ያበቋቸው አንባገነን መሪዎች ናቸው፡፡ ከዚህ መማር ያለባቸው አንባገንን መሪዎች እንጂ ህዝቡ ሊሆን አይችልም፡፡ መቼም በእነዚህ አገሮች ውድመት ህዝቡ ነው ተጠያቂ የሚል ሰምቼም አንብቤም አላውቅም፡፡ የእኛም አገር መሪዎች እባካችሁ አገራችን እንደነዚህ አገሮች እንዳተትሆን ከግል ሥልጣን መሻት እና ሌላ ማንኛውም ግላዊ ፍላጎት እራሳችሁ አፅድታችሁ ታሪክ ስሩ እያልነናችሁ ነው፡፡ ኢትዮጵያ ከላይ ከተጠቀሱት አገሮች እንደ አንዳቸው እንዳትሆን ኃላፊነቱ ያለው በፖለቲካ መሪዎች ይልቁንም በህወሓት/ኢህአዴግ እጅ ውስጥ ነው፡፡
አገራችን በመሰቀለኛ መንገድ ላይ እንደምትገኝ፡፡ ከመገዶቹ ዳር እና ዳር ደግሞ ጥልቅ ገደል መኖሩን እንገነዘባለን፡፡ ትክክለኛውን መንገድ መምረጥ እና ከገደሉ መራቅ የግድ ይላል፡፡ ይህ የአሰተዋይ ምርጫ ነው፡፡ የሰሞኑ ነገሮችን አያያዝ ለሚያስተውል ግን የብልዕ አያያዝ አይመስልም፡፡ እስረኞችን መፍታት መጀመሩ በጎ ጎኑ ሲሆን ሌሎችን ያለመፍታት ሲከፋም በተመሳሳይ ሁኔታ እስርን መጀመሩ አሳኙ ክስተት ነው፡፡ እስረኞች የተፈቱበት ምከንያት ለጋራ አገር በጋራ መፍትሔ ለመፈለግ የመሰለን ሰዎች ተሳስተናል ማለት ነው፡፡
የኢህአዴግ አባል ድርጅቶች ፖለቲካ ምህዳር ለማስፋት በቁርጠኝነት የተሻሉ እርምጃዎች ይወሰዳሉ የሚለው ቀርቶ ለቀጣይ ስድስት ወር በአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ስር እንድንሆን ያለፍላጎታችን ሲፈረድብን ደግሞ የበለጠ ግምታችን የተሳሳተ፣ ተሰፋችንም የዕልም እንጀራ እየሆነብን ይገኛል፡፡ ሌላው ተሰፋ የጣልንበት ወፌ ቆመች እያልነው የነበረው ፓርላማ መዋረዱ ተስፋችንን ያጨልምብናል፡፡ ፓርላማውን የሚያዋርዱት ደግሞ “የተከበሩ” ተብለው በምክር ቤት ውስጥ ያሉት ጭምር መሆናቸው ነው፡፡
እንዲህ እንድንል የሚያድርገን ደግሞ ግንባሩ ከዚህ በፊት በሚስጥር ሲያደረግ የነበረው ሁሉ አሁን በይፋ እያደረገው መሆኑ ነው፡፡ ግንባሩ ሸፍጥ እና የሸፍጥ ድርጅት እንደሆነ በግልፅ አውቀናል፡፡ በቅርቡ ኢህአዴግ እንደ ግንባር የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ያስፈልገኛል ብሎ ቆርጦ ተነስቷል፡፡ በግልፅ ቋንቋ ወታደራዊ አገዛዝ ያስፈልገኛል እያለ ነው፡፡ ይህን ደግሞ በኢህአዴግ ስራ አስፈፃሚ በተለመደው አካሄድ ከፀደቀ በኋላ ወደ ካቢኔ በመሄድ ለወጉ እንዲፀድቅ ተደርጓል፡፡ ፓርቲው ያፀደቀውን የመንግሰት አካል ተብዬው “ካቢኔ” የሚባለው የሚቃወምበት አቅም የለውም፡፡ ለዚህ ነበር ቴክኖክራት ካቢኔ ዋጋ የለውም ስንል የነበረው፡፡ ይህ ጉዳይ ወደ ፓርላማ መቅረብ ሰለነበረበት ደግሞ በተመሳሳይ በፓርላማ አባላትም ቀድመው ውይይት እንዲያደርጉ በየድርጅቶች የስራ አሰፈፃማዊ ውሳኔው ተነገራቸው፡፡ ውይይቱ ውሣኔ ለመቀየር ሳይሆን እንደተtለመደወ የስራ አሰፈፃሚውን ውሳኔ እንዲቀበሉ ነበር፡፡ ድርጅታዊ ማዕከላዊነት በሚባል አስራር፡፡ ይህ በተመሳሳይ አጋር ለሚባሉት ድርጅቶችም ተደርጓል፡፡ ሁለት ሶሰተኛ ድምፅ የሚያስፈልግ በመሆኑ 46 ድምፅ ያላቸውን አጋሮችንም ችላ ማለት ሳያስፈልግ፣ አፈ ጉባዔው ፈልገውት እንደነበረው በተባበረ ድምፅ ለማጽደቅ ታስቦ ነበር፡፡ በኢትዮጵያ ህዝብ ላይ ቲያትር ለመስራት፡፡
ድርጅቶቹ ውስጥ ለውስጥ ውሳኔ ካሳለፉ በኋላ ምክር ቤት ሰብሰባ ብለው ይቀመጡና ለቀለድ ጥያቄና መልስ ሲያደርጉ ቆይተው በሙሉ ድምፅ ፀደቀ ለማለት አፋቸው ደንቀፍ ሳይል ለማጠናቀቅ ወስነው ነበር፡፡ ይህን የድርጅታዊ አስራር በመተማመን ነበር አፈ ጉባዔ አባዱላ ገመዳ በተባበረ ድምፅ እንዲፀድቅ የሚል ደፋር ጥያቄ ለምክር ቤት ተብዬው ያቀረቡት፡፡ ለማንኛውም ይህ እንዲሆን ለጊዜውም ቢሆን ያልፈቀዱት እጅግ ብዙ አባላት በታሪክ ፊት በኩራት የሚያቀርባቸውን ውሳኔ ወስነዋል፡፡ በየድርጅቱ ሲደረገ ከነበረው ውትወታና ማገባባት ይልቅ ወደ ሕዝብ ድምፅ፤ የህሊና ፍርድ እና ሕገ መንግሰቱን ወደ ማክበር አድገዋል፡፡ ይህ የፈጣሪ ስራ ነው፡፡

ከህዝብ ጀርባ፤ ከህዝብ ፍላጎት ውጭ ይህ ሁሉ ሲደረግ በእኔ አሰተያየት አቶ ሀይለማሪያም ደሣላኝ ከስልጣን ለመልቀቅ ጥያቄ አቀረብኩ ከሚሉን፤ በእውነትም የለውጡ አካልና መሪ ሊሆኑ የሚችሉበትን እድል በሚያሳዝን ሁኔታ አሳልፈው ሰጥተዋል፡፡ ይህንን ምክር ቤት በህገ መንግሰቱ አንቀፅ 60 መሠረት በትነው በስድስት ወር ውስጥ ምርጫ በማድረግ ለአሸናፊ ስልጣን ማስረከብ ነበር፡፡ ይህ ታሪክ በወርቅ ሳህን ያቀረበላቸውን እደል ሳይጠቀሙበት አልፈዋል፡፡ እናዝናል፡፡ አሁን ደግሞ ማንም ይሁን የሚመጣው ጠቅላይ ሚኒስትር ታሪክ እንዳይስራ እንቅፋት የሚሆን አፈና በአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ስም ለምን እንዳሰፈለገ አልገባንም፡፡ ለለውጥ የተነሳን ህዝብ ማንኛውም የአፈና አካሄድ አያቆመው፡፡ በውሰጥ ለውስጥ ስምምነት ተደርጎ በመጣ ውሳኔ በምክር ቤት ስም ለማላገጥ የመጣን ቡድን አምላክ በኪነ ጥበቡ አጋለጠለን፡፡ አሁን የተፈጠረው የቁጥር ስህተት ለአንደኛ ደረጃ ተማሪም ቢሆን ከባድ አልነበረም፡፡ እንኳን ስማርት ፎን/ስልክ ይዞ ሂሣብ ለሚስራ የምክር ቤት አፈ ጉባዔ፡፡ ፈጣሪ ግን ከኢትዮጵያ ሕዝብ ጀርባ የተሰራን ሴራ በአደባባይ አጋልጦልናል፡፡ ይህን ሸፍጥ ለማጋለጥ ብርታት ላገኙት የምክር ቤት አባላት ምስጋና እና ክብር ይገባቸዋል፡፡ ይህን ስህተት ማረሚያ መንገድም ወደ ምክር ቤቱ መድረክ ተመልሶ በግልፅ በሚሰራ ማስተካከያ ብቻ ነው፡፡
በዚህ አጋጣሚ አቶ ሀይለማሪያም ደሣለኝ እድላቸውን ባይጠቀሙበትም ሌሎች ታሪክ እንዲሰሩ እድል ፈጥረዋል ለማለተም ይቻላል፡፡ አዲሱ ጠቅላይ ሚኒሰትር ማን ይሆናል? የሚል ጥያቄ እንዲነሳ በማድረግ፡፡ ነገር ግን ይህ አዲስ ጠቅላይ ሚኒስትር የመሰየም ጣጣ አሁንም በድርጅት ሴራና አሻጥር ውስጥ መውደቁ አሳዛኙ የህወሓት/ኢህአዴግ ቲያትር ሌላኛው ክፍል ነው፡፡ ሰሞኑን አዲሱ ጠቅላይ ሚኒሰትር ማን ይሁን? የሚለው ጥያቄ እያስነሳ ያለው ጭቅጭቅ የኢትዮጵያ ህዝብ በግልፅ መሪውን የመምረጥ ፍላጎት ብቻ ሳይሆን አቅም አንዳለውም የሚያመላክት ነው፡፡ ከዚህ ቀደም ህወሓት በተለይ አቶ መለስ ዜናው በህዝብ ዘንድ ያላቸውን ዝቅተኛ ተቀባይነት ከግምት በማስገባት “ፓርላሜንታዊ ሥርዓት” በሚል ሸፋን ዜጎች መሪያቸውን በቀጥታ እንዳይመርጡ ይልቁንም ድርጅቶች ከህዝብ ጀርባ መሪ ተብዬ የሚመርጡበት ሴራ ሰርተውብን አልፈዋል፡፡ ይህ አካሄድ ግን ማብቂያው ጊዜ ደርሷል፡፡ ራዕይ አለኝ፣ የኢትዮጵያን ህዝብ ለመምራት እችላለሁ የሚል ዜጋ በይፋ ወጥቶ ለህዝብ ቀርቦ ዳኝነቱን ከህዝብ መጠበቅ አለበት፡፡
ኢትዮጵያዊያን በመንታ መንገድ በገደል አፋፋ ላይ ብንገኝም መውጫውን መንገድ እናውቀዋለን፡፡ ደንቃራ የሆነብን አብዮታዊ ዴሞክራሲ የሚባለው መንፈስ እና የመንፈሱ ተሸካሚ የሆኑት የህወሓት/ኢህአዴግ አመራሮች ናቸው፡፡ ለዚህች አገር ትንሣዔ ሲባል አገራችን የጋራ መሆኗን ከግንዛቤ በማስገባት በጋራ መፍትሄ እንፈልግ፡፡ ቀጣዩ ጠቅላይ ሚኒሰትር ከዚህ የሚበልጥ ታሪካዊ አጋጣሚ አያገኝም፡፡ ይህን እድል ይህችን ትልቅና ታሪካዊ አገር ወደ ከፍታው ማማ ለማውጣት በጋራ አብረን እንቁም!!!!!
ግረማ ሠይፉ ማሩ
መጋቢት 2010