Monday, June 8, 2015

ቀጣዩ ጠቅላይ ሚኒስትር ማን ነው?


ግርማ ሠይፉ ማሩ
girmaseifu32@yahoo.com
ሰሞኑን ልብ አውልቁ በዝቶዋል፡፡ አማራጭ በሌለው ምርጫ ተብዬ ውስጥ ምን ይጠበቅ እንደነበር ግን አልገባኝም፡፡???? በኢትዮጵያ ፖለቲካ ላይ የሚፈላሰፉ በትምህርታቸው የገፉ የሚባሉ የሀገራቸውን ፖለቲካ ቢያንስ በዚህ ዓመት ምን ምን ክንውኖች እንዳሰተናገደ ያለማወቅ  የአባት ሆኖ የሰው ልብ ያወልቃሉ፡፡ ዋነኛው በምርጫ ያለመወዳደሪ የአደባባይ ሚስጥር ሆኖ እያለ እንዴት ነው ውጤት ብለው የሚጠይቁኝ አሉ፡፡ አልተወዳደርኩም ሰል - ለምን? ከሌላ ፓርቲ ጋር አትሞክርም ነበር? በግል ለምን አልተወዳደርክም? ወዘተ የሚመስሉ አስቀያሚ ጥያቄዎች ይገጥመኛል፡፡ ለማነኛውም ይህ የግል ጉዳይ ነው እንደ አመጣጡ ይመለሳል፡፡
አሁን ጠቅላይ ሚኒስትር ማን ነው የሚሆነው? የሚለው ጥያቄ ደግሞ ሌላው አሰቂኝ ጥያቄ ሆኖ አግኝቼዋለሁ፡፡ ከተሳሳትኩ እታረማለሁ፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ከመሞታቸው በፊት የተከበሩ አቶ ቡልቻ ደመቅሳን በአንድ ግብዣ ላይ ተገናኝተን አውርተን ነበር፡፡ አሁን በሚቀጥለው ምርጫ ስልጣን ከህውሃት ውጭ ለሌላ ይሰጣሉ ወይ?  ብለው ጠይቀውኝ ነበር፡፡ በእኔ ግምት የአሁን ጠቅላይ ሚኒስትር በዚያን ጊዜ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር በአቶ መለስ ስልጣን ሊሰጣቸው እንደሚችሉ ያለኝን ግምት ነገርኳቸው፡፡ ይህን ያልኩበትን ምክንያትም አብራርቼ አስረዳሁ፡፡ እንዲህ ብዬ፤ አቶ ሀይለማሪያም ደሳለኝ ስልጣን ቢሰጣቸው እና ያለ አግባብ (ማለትም መለስ ከጀርባ ሆነው ከሚሰጡት መመሪያ ውጭ) ቢንቀሳቀሱ በደቡብ ውስጥ ባለው የስልጣን ስሪት ምክንያት ወላይታን በሲዳማ ማውረድ ከባድ አይደለም፡፡ የፓርቲያቸውን ስልጣን በማሳጣት ጠቅላይ ሚኒስትርነቱን ይቀማሉ፡፡ በሌላ በኩል ለኦሮሞ የጠቅላይ ሚኒሰትርነት ቦታ ለመስጠት የኦህዴድ/ኦሮሞ የፕሬዝዳንት ቦታ መልቀቅ የግድ ይላል፡፡ እሱን ቢያደርጉ እንኳን ይህን ከፍተኛ ስልጣን ለኦሮሞ በመስጠት የህውሃትን ዋነኝነት ማስጠበቅ አስቸጋሪ ነው፡፡ እንደ ቀልድም መቀበል አይቻለም፡፡ ይህን ስልጣን ከዋነኞቹ አባል ፓርቲዎች ለአማራ ተወካይ ነኝ ለሚለው ብአዴን መስጠት አንዱ አማራጭ ቢሆንም ይህ ደግሞ አሁንም ይህች ሀገር ለአማራ ተመልሳ ተሰጠች የሚል የብሔረተኞች ዘማቻና ጫጫታ ይከፈታል (በግሌ ይህች ሀገር  የአማራ ነበረች የሚል እምነት የለኝም-የአማራ ገዢ መደብ በሚል ትንታኔም አላምንም)፤ በዋነኝነት ከትግራይ እና ኦሮሞ ፖለቲከኞች፡፡ ሰለዚህ ኢህአዴግ ያለው አማራጭ በቀላሉ ሊቀበለው ለሚችለው ወጥነት ለሌው ደቡብ በሚል አቅጣጫ ለተደራጃው ቡድን ወኪል መስጠት ግድ ነው፡፡ የሚል መልስ ስጥቻቸው ነበር፡፡
አሁንም ይህን አመክንዮ የሚያስቀይር ምንም ነባራዊ ሁኔታ የለም፡፡ ይህንኑ መስረት አድርጌ የቀጣዩ አምስት ዓመት ጠቅላይ ሚኒስትር በምንም መልኩ በአቶ ሀይለማሪያም ደሳለኝ ስም መቆየቱ የግድ ነው፡፡ እራሳቸው እንዳመኑት በግላቸው የሚወስኑት ነገር የለም፡፡ የቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትር እንደዚሁ ነበር ውሳኔ የሚሰጡት የሚለውን ፌዝ ትተን ማለት ነው፡፡ አንድ ምሳሌ ላቅርብ፡፡ የእድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅድ በምክር ቤቱ ሲቀርብ አቶ ሶፊያን አህመድም ሆነ የብሔራዊ ባንክ ገዢው በማያውቁት ሁኔታ የወለድ ምጣኔ፣ የሀገር ውስጥ ቁጠባን ለማሳደግ ይረዳሉ ያሉትን ሀገራዊ የማክሮ ኢኮኖሚ ውሳኔዎችን ይፋ አድርገዋል፣ ሟቹ ጠቅላይይ ሚኒስትር የግል ሰራተኞች ጡረታ የመሳሰሉትን በከፍተኛ ደረጃ ምክክር የሚጠይቁትን ነጥቦች በእጅ በተፃፈ ማስታወሻ መጥተው ነው ይፋ ያደረጉት፡፡ ይህ ከመሆኑ አንድ ቀን ቀደም ብሎ አቶ ሶፊያ በምክር ቤት ስለቁጠባም ሆነ ሌሎች ውሳኔዎች የሰጡት መልስ በተለየ ሁኔታ ነበር፡፡ ለማነኛውም አቶ መለስ ዜናው በራሳቸው የቆሙ ያመኑበትን አማክረው ይሁን ሳያማክሩ የሚወስኑ እንደነበር ፀሃይ የሞቀው ሀቅ ነው፡፡
ለማነኛውም አቶ ሀይለማሪያም በራሳቸው የሚወሰኑት ነገር ከሌለ፤ ውሳኔ የሚወሰኑት በቡድኖች ፍላጎት መሰረት ነው ማለት ነው፡፡ ይህ ደግሞ የቡድኖች ጥቅም እስከተጠበቀ እርሳቸውን ማንሳት ከጥቅሙ ጉዳቱ ያመዝናል ብዬ ነው የምወስደው፡፡ አቶ ሀይለማሪይም ደሳለኝ ከስልጣን ቢነሱ ማን ይተካል? መቼም ኢህአዴግ ኦሮሞ ጠቅላይ ሚኒስትር በኦሮሞ ፕሬዝዳንት ላይ ደርቦ ይስጣል ተብሎ አይጠበቅም፡፡ ኦህዴድ የዚህን አምስት ዓመት ሳይሆን የሚቀጥለውን ጊዜ ጠቅላይ ሚኒስትርነት ቦታ እፈልጋለሁ የሚለውን ምልክት የሚያሳየን ዶክተር ሙላቱ ተሾመ የዛሬ አራት ዓመት ለድጋሚ ፕሬዝዳንትነት እንዳይወዳድሩ በማድረግ ይህችን ቦታ ለአማራ ወይም ለሌላ ብሄር እንዲሰጥ ያደረገ እንደሆነ ነው፡፡ ከአማራ ውጭ ፕሬዝዳንትነቱን ከያዘ ጠቅላይ ሚኒስትርነት ቦታ በኢህአዴግ ውስጥ አማራና በኦሮሞ ወኪል ነን በሚሉት መሃከል ሸሚያ የሚደረግበት ይሆናል፡፡ ይህ ደግሞ የሁለት ዝሆኖች ጥል ስለሚሆን የሚጎዳው ብዙ ነው፡፡
ህውሃት ከአሁን በኋላ የኢህአዴግ አባል ድርጅቶች በዙር ይህን ወሳኝ ቦታ ሳይዙ ደግሜ እይዛለሁ ካለ በግንባሩ ውስጥ ያለውን የእኩልነት (የእውሸትም ቢሆን) መንፈስ በመፃረር በግልፅ ጌታ ነኝ እንዳለ ስለሚቆጠር ተረኞች ዝም ሊሉ አይችሉም፡፡ በተለይ በኦሮሚያ ውስጥ ያቆጠቆጠው መካከለኛ አመራር የሚባለው ቡድን ይህን በዝምታ የሚመለከት አይመስለኝ፡፡ እግረ መንገዳችን ኢትዮጵያ የምትባል ሀገር በኢህአዴግ አገዛዝ ውስጥ እስካለች ጊዜ ድረስ በሀገር ፍቅርና ችሎታ ጠቅላይ ሚኒስትር የሚኮንበት እድል የለም፡፡ በተለይ የኢህአዴግ አባል ድርጅት ያልሆኑ ሀጋር በመባል የሚታወቁት በሚኒስትር ዴኤታ ወይም ከፍ ሲል ብዙ ትርጉም የሌላቸው የሚኒስትር ቦታ ከመያዝ በዘለለ ይህችን ወሳኝ የጠቅላይ ሚኒስትርነት ቦታ የሚያገኙበት አንድም መስመር የለም፡፡ ጋምቤላ፣ ሶማሌ፣ አፋር፣ ወዘተ ሆኖ ጠቅላይ ሚኒስትር መሆን የሚታሰብ አይደለም፡፡ በነገራችን ላይ በደቡብ ውስጥም ቢሆን በወላይታ ጠቅላይ ሚኒስተር መሆን የተነሳ ስልጤም፣ ጉራጌም፣ ከፍቾም፣ ሲዳማ ወዘተ ድርሻውን አግኝቶዋል ተብሎ ቢታሰብ ልክ አይመጣም፡፡ ለማነኛውም ደቡብ ደርሶታል፡፡
በቀጣዩ አምስት ዓመት ኢህአዴግ ከዚህ ዓይነት ቅርቃር ለመውጣት የሚያስችለው የሰነ ልቦናም ሆነ የሞራል ዝግጅት ያደረገ ግንባር አይመስለኝም፡፡ በእኔ እምነት ይህን መቶ በመቶ የምርጫ ውጤት የመጨረሻው እንዲሆንለት ለማድረግ ሀጋር ፓርቲዎችን ያሳተፈ የሀገር ሀቀፍ ፓርቲ ምስርታ እቅድ በፓርቲው ውስጥ አዘጋጅቶ መተግበር ይኖርበታል፡፡ የሀገር መሪ በኮታ በአባል ፓርቲ በዙር ሳይሆን በችሎት መሆኑን የሚያሳይበት መስመር ማሰየት ካልቻለ ችግሩ ውሎ አድሮ ዘወትር የሚያሟርቱት ሀገር መፍረስ ሊሆን ይችላል፡፡
ቸር ይግጠመን