Monday, October 31, 2016

ለኢትዮጵያ ፖለቲካ መሪነት ተቃዋሚ መሆን ብቻ አይበቃም!!!




በሀገሩ ጉዳይ  እገሌ ያገባዋል እገሌ አያገባውም ማለት ተገቢ ነው ብዬ አላምንም፡፡ ነገር ግን መሃንዲሰ ሀኪም መሆን እንደሌለበት ሁሉ የሚያገባን በምን በምን ጉዳይ መሆኑ ተለይቶ መታወቅ እና የበለጠ ውጤታማ የምንሆንበትን መምረጥ ተገቢ ይመስለኛል፡፡ በኢትዮጵያ ሀገራችን ፖለቲካ ውስጥ ሁሉም ያገባዋል ነገር ግን በምን ደረጃ ሃላፊነት ሊወስድ ይችላል በሚባለው ጉዳይ ግን ዝርዝር መታወቅ ይኖርበታል፡፡ እገሌ ማን ነው? ተብሎ መጠየቅ ይኖርበታል፡፡ ይህ መጠይቅ ደግሞ በተለይ መቅረብ ያለበት በአንድ ቡድን ውስጥ ሆኖ በአንድ ማዕቀፍ ለመስራት ለሚፈልግ ሰው የግድ ነው፡፡ ሀገራችን ኢትዮጵያ ከፍተኛ የፖለቲካ አመራር ችግር አለባት፡፡ ተቃዋሚ መሆን ብቻ ለፖለቲካ መሪነት አያበቃም፡፡ ብቃት ያለው የፖለቲካ መሪ እንዳይኖረን ካደረጉት ነገሮች ዋነኛው እስከ ዛሬ በፖለቲካ ፓርቲ ውስጥ ለመሳተፍ እራሳቸውን ያዘጋጁ ሁሉ ከስሜት አልፈው የፖለቲካ አመራር ማፍራት ትክክለኛ የፖለቲካ ፓርቲ ተግባር ነው ብለው አምነው ያለማወቃቸው ነው፡፡ አሁንም ቢሆን ይህ ትልቅ ኃላፊነት ለፖለቲካ ፓርቲዎች የተተወ እንደሆነ የሚረዱ አይመስለኝም፡፡ ይልቁንም የፖለቲካ ፓርቲዎች ሰልፍ መጥራት፣ መግለጫ ማውጣት እና ከፍ ሲል ጋዜጣ ማሳተም ትልቁ የፓርቲ ስራ ይመስላቸዋል፡፡ የሚገርመው አንዳንዶቹ መደበኛ ትምህርታቸውን እንኳን ፓርቲ እንደያስተምራቸው የሚፈልጉ ናቸው፡፡ ለዛሬው መደበኛ ትምህርታቸውን ፓርቲ እንዲያስተምራቸው የሚፈልጉትን ምስኪኖች ሳይሆኑ እራሳቸውን የፖለቲካ መሪ አድርገው ያስቀመጡ ልሂቃን ላይ ብቻ ማተኮር ነው የምፈልገው፡፡
ሁሉም እንደሚረዳው የኢትዮጵያ ፖለቲካ ፓርቲ ምስረታ በእነ ኢህአፓ እና መኢሶን የተጀመረ ሲሆን ከዚያ በኋላ ብዙ ፓርቲዎች በወቅቱ የነበረውን የስልጣን ክፍተት ለመሙላት መደራጀት በሚል ሲደራጁ እንደ ነበር ይታወሳል፡፡ የዚህ ታሪክ ባለቤቶች አሁንም በኢትዮጵያ ፖለቲካ ውስጥ ዋናዎቹ ተዋናዮች ናቸው፡፡ ሲደክማቸው እያረፉ፣ መልካም አጋጣሚ የተገኘ ሲመስላቸው ብቅ እያሉ ዛሬ ደርሰናል፡፡ በቅርቡ ትዝታችን ሁሉንም ኢትዮጵያዊ ከሀገር ውስጥም ሆነ ከውጭ ከፍተኛ ንቅናቄ የፈጠረው የቅንጅት መንፈስ ነው፡፡ ይህ መንፈስ ምን ዓይነት እንደነበር ለታሪክ እንዲተው የምንፈልግ ብንኖርም አሁንም የዚህ መንፈስ ተከታዮች አሉ፡፡ በኢትዮጵያ የፖለቲካ እንቅስቀሴ ውስጥ ከኢህአፓ መንፈስ ቀጥሎ ከፍተኛ ህዝባዊ ንቅናቄ የፈጠረ መንፈስ የቅንጅት መንፈስ ነው ቢባል የሚቀየም አይኖርም፡፡
ቅንጅትን ከሁሉም በላይ በህዝቡ ዘንድ ተደማጭነት እንዲኖረው ካደረጉት ነገሮች አንዱ ህዝቡ በግንባር የሚያያቸው መሪዎች ከጥቂቶቹ በስተቀር ፕሮፌሰር፣ ዶክተር፣ ኢንጅነር፣ ወዘተ በሚባሉ ማዕረጎች የሚጠሩ ነበሩ፡፡ የተማረ ይግደለኝ የሚባለው ዓይነት መሆኑ ነው፡፡ ይህ መንፈስ ታዲያ ዛሬም የሞተ አልመሰለኝም፡፡ ኢንጀነር የሚል ማዕረግ ከዩኒቨርሲቲ ውጭ በእለት ከእለት ኑሮ መጠሪያ ሲሆን ይህ ዘመን የመጀመሪያ ይመስለኛል፡፡ ይህን ፉርሽ ነገር “መንግሰት” ተብዬውም ተከትሎ “ኢንጅነር” እገሌ እያለ መጥራት ሙያ አድርጎታል፡፡ የተማራ ይግደለኝ መንፈስ አልሞተም ያልኩበት ምክንያት ዛሬም ከዚህ በፊት በተቃዋሚ ፓርቲ ፖለቲካ አፍራሽ ሚና የነበራቸው ሁሉ ድንገት ክፍተት ከተገኘ ብለው ጥፋታቸውን ለማረም ሳይሆን ጥፋታቸውን አድሰው ለመድገም እየተንቀሳቀሱ እንደሆነ በመስማቴ ነው፡፡
በሀገራችን በሚፈጠር ችግር ከእድሜያቸውም አንፃር ሸምግልና የሚገባቸው ሁሉ ዛሬም በፓርቲ ፖለቲካ ውስጥ ሆነው እራሳቸውን ለስልጣን ሲያጩ ማየት የእውነት ያማል፡፡ ያለፈውን ፓርቲያችሁን ምን አደረጋችሁት? የሰባሰባችሁትን ወጣት ምን በላው? ወዘተ ብሎ የሚጠይቃቸው ያለ አይመስለኝም፡፡ ይልቁንም እነርሱ ከሰሻ እና ፈራጅ ሆነው መድረኩን የክፋታቸውን ጥላ አጥልተውበታል፡፡
በኢትዮጵያ ፖለቲካ ከአሁን በኋላ የከዚህ ቀደም የፖለቲካ ሂሳቡን ሳያወራርድ ኢንጂነር፣ ዶክተር የሚል ማዕረግ ይዘው ለጡረታ ጊዜ የሚንቀሳቀሱትን አቤት የሚላቸው ካገኙ ይገርመኛል፡፡ የኢህአዴግ መተካካት ምኞት ሆኖ ቢቀርም፣ በተቃዋሚ ጎራ መሪዎች መተካት ባይችሉም በራሳቸው ተነሳሸነት ሃላፊነት ለመውሰድ ለሚመጣ አዲስ ኃይል ቦታ መልቀቅ የግድ ነው፡፡ ቦታ ልቀቁ ሲባል ስልጣኑን ብቻ አይደለም፣ ትግሉንም ጭምር ነው፡፡ እሰከ ዛሬ ላደረጉት ሙከራ ክብር በመስጠት የነበራቸውን ረጅም የትግል ታሪክ በመፅኃፍ መልክ ለትውልድ በታሪክ መልክ በታማኝነት ማሰቀመጥ ይጠበቅባቸዋል፡፡ ይህ ለራሳቸውም ቢሆን ምን ያህል ታማኝ እንደሆኑ ሌላው እንዲረዳቸው እድል ይስጣል፡፡
ከኢትዮጵያ ፖለቲካ ጡረታ መውጣት ካለባቸው ሰዎች አንዱ እና ዋነኛው ግዛቸው ሸፈራው (ኢ/ር) ነው፡፡ በፌስ ቡክ ላይ “በቅንጅት መንፈስ በሚል ፓርቲ ለመመሰረት መንገድ ላይ ያለው ግዛቸው ለአንድነት መፍረስ ያሰቀመጠውን የመሰረት ድንጋይ እረስቶት ፓርቲ በማፍረስ ኢህድግን ብቻ ይከሳል፡፡ እሱ ቢረሳው እኛ ግን አንረሳውም እና ……. ከአሁን በኋላ የፓርቲ ፖለቲካ ቢቀርበት ምከሩት” ብዬ ለጥፌ ነበር፡፡ ፌስ ቡክ ላይ ባያየውም በደንብ እንደሰማው መረጃው አለኝ፡፡ ግዛቸው በቅንጅት ጊዜ የተጫወታቸው ሚናዎች በወቅቱ በነበረበት ጊዜ የሚገመገም ቢሆንም አንድነትን በመስራችነት እና በመሪነት ሲያገለግል ምን ሰርቶ ምን አድርጎ ፓርቲውን እንዳፈረሰ ማስረዳት ይኖርበታል፡፡ ይህን በቅጡ ሳይወጣ ዛሬም የፖለቲካ ፓርቲ መስርቶ መሪ ሊሆን ያሰባል፡፡ የሚገርመው “እኔ ከሞትኩ ሰርዶ አይብቀል” እንዳለቸው አህያ አንድነትን በመሪነት ከሚያፈርስ ሚዲያ ጋር ቀርቦ እራሱን ሲከስ የነበረ ጀግና፣ በአንድነት ንቅናቄ ላይ ቀዝቃዛ ውሃ መቸለሱን ረስቶ ዛሬም ፖለቲካ መጫወት ያምረዋል፡፡ ግዛቸው ፓርቲ ካማረው ከትዕግሰቱ አወሉ ጋር ተሰማምቶ መሰራት ነው ያለበት፡፡ ይህን ለማድረግ የሬዲዮ ፋናው ብሩክ ሊረዳው እንደሚችል እገምታለሁ፡፡ ምክንያቱም የትዕግሰቱ አወሉ ቡድን ከምርጫ ቦርድ ድጋፍ ያገኘው “ግዛቸው ከስልጣን የተነሳው በህጋዊ መንገድ አይደለም” የሚለው መከራከሪያ አቅርቦ ነው፡፡ ግዛቸው “በፈቃዴ ነው የለቀቅሁት” ብሎ ቃሉን ለመስጠት ዳተኛ መሆኑ ብቻ ሳይሆን “በሀሰት ከኃላፊነቴ እንደለቅ የተገደድኩት ፋይናንስ በባንክ ይሁን ስላልኩ ነው” ብሎ ራሱን ጭምር በሬዲዮ ፋና ቀርቦ ከሶዋል፡፡ አንድነት ፓርቲ ከማንም ፓርቲ በተሻለ የፋይናንስ ስርዓት እንዳለው እያወቀ ቢሆንም ክፋቱን እወነት ሊያሸንፈው አልቻለም፡፡ ከዚህ ዓይነት ክፉ ሰው ጋር የፖለቲካ ማህበር አይደለም እንዴት ሌላ ማህበራዊ ኑሮ ይታሰባል፡፡ ያለፈውንም ይቅር ይበለን!!
ከግዛቸው ጋር የፓርቲ ምስረታ ጥንስስ ላይ ያለ ሁሉ /ለጊዜው ስም አልጠራም/ በዝርዝር እራሳችሁን ማየት ይኖርባችኋል፡፡ ከደርግ የማይሻል የለም ተብሎ የመጣው ህወሃት/ኢህአዴግ ደርግን በአፈና አስንቆታል፡፡ እናንተም ከዚህ መሻላችሁን በእውነት ቀድማችሁ አስመስክሩ፡፡ ሀገራችን የወላድ መሃን የሆነችበት ወቅት ላይ እንገኛለን እና በጥንካሬ መሪ ለመፍጠር አስበን መስራት እንዳለብን ማወቅ ይኖርብናል፡፡
ቸር ይግጠመን!!


No comments:

Post a Comment