Monday, June 9, 2014

“ስለ ….. ሲባል ምርጫ ይቅር” …. ትግሉም ይቁም ወይ?



“ስለ …. ሲባል ምርጫ ይቅር” በሚል እንድ ፅሁፍ ፋክት ላይ ወጥቶ አንብቤ ለምን? ብዬ ልፅፍ አስቤ ተውኩት፡፡ ምክንያቱም በፋክት መፅሔት ላይ አምደኞች የሃሣብ ፍጭት ማድረግ የተለመደ ቢሆንም ሰሞኑን ግን የበዛ ይመስላል ከሚል ነበር፡፡ ይህ አንድ ዘርፈ ብሉ ጥሩ ጎን አለው፡፡ አንዱ አምደኞቹ ከአንድ ፋብሪካ የወጡ ሳሙና ዓይነት ያለመሆናቸውን ያሳያል፡፡ሌላው የፋክት መንፈስ ብለው ለሚቃዡትም ሆነ፤ ከመሬት ተነስተው ለሚፈርጁት የሚያስተላልፈው መልዕክት አለው፡፡ ጉዳቱ ደግሞ በሳምንት አንዴ ብቅ ለምትል መፅሄት የተወሰነ ሃሳብ በተወሰኑ ሰዎች የሚቧቀሱባት ከሆነች ደግሞ አንባቢን አማራጭ እንዳያሳጣ የሚል ፍርሃት ስለአለኝ፡፡ ይህ ሁሉ ዳር ዳርታ እኔም ተውኩት ወዳልኩት የሃሣብ ፍጭት ለመቀላቀል ሰበብ ፈልጌ ብቻ አይደለም፡፡ በቅርቡ “ሰለ … ሲባል ምርጫ ይቅርብን” በሚል በወዳጄ ዶክተር በድሉ ዋቅጅራ ያቀረበውን ሃሳብ ባልቀበለውም በፋክት ላይ ሳይሆን በጠረጴዛ ዙሪያ ውይይት እናደርጋለን ብዬ እያሰብኩ ሳለ በፌስ ቡክ የውስጥ መዘገቢያ እንዲሁም በግል የሚያገኙን ሰዎች ምርጫ እንዳትወዳደሩ የሚል አንዳንዱ ምክር አንድ አንዱ ደግሞ ትዕዛዝ መሰል መልዕክቶች በብዛት ይደርሱኝ ጀምረዋል፡፡ ውሳኔው ልከም ይሁን አይሁን የምርጫ ጉዳይ የሚወሰነው በፓርቲ መሆኑን ከግንዛቤ በማስገባት የግል አስተያየቴን መስጠት እፈልጋለሁ፡፡ ለዚህም ነው “ሰለ … ሲባል ምርጫ ይቅር” ከተባለ እኔም እንደቅድመ ሁኔታ ትግሉም ይቁም ወይ? በሚል ጥያቄ የጀመርኩት፡፡
በእኔ እምነት ምርጫ መወዳድር ያለመወዳደር የሚባል አማራጭ የለም፡፡ የአንድ ፓርቲ ስራ ምርጫ መወዳድር ነው፡፡ የሰው ልጅ ሞት እንዳለ እያወቀ ሞትን ረስቶ በህይወት እንደሚኖረው ማለት ነው፡፡ ለፓርቲዎች ያለመወዳደር የሚባል ነገር እንዳለ ረስተው ለምርጫ ውድድር መዘጋጀት ዋናው ስራቸው መሆን አለበት፡፡ ፓርቲዎች ምርጫ ላለመወዳደር የሚያበቃ ነገር እንዳይኖር ተግተው መስራትን ትተው፤ ላለመወዳድር ሰበብ የሚፈልጉ ከሆነ እንደ አሸዋ የበዛ ሰበብ ማቅረብ አይገድም፡፡ ከዚህ ሰበብ ውስጥ ግን አንድም ተሰፋ አይገኝም፡፡ ምርጫውም የሰነፍ ነው የሚሆነው እንጂ ባስቸገሪ ሁኔታ ጀግና ለመሆን ለሚታትር ታጋይ የሚመጥን አይደለም፡፡
በሀገራቸን ኢትዮጵያ ለምርጫ የእኩል መወዳደሪያ ሰፍራ ሳይኖር ምርጫ መወደዳር አስቸጋሪ እንደሆነ መረዳት ለማንም የሚገድ አይደለም፡፡ ትግል የሚባለው ነገርም የመጣው ይህ አስቸጋሪ ሁኔታ በመኖሩ ነው፡፡ በአሜሪካን ወይም በሌሎች በዲሞክራሲ በዳበሩ አገሮች የሚደረግ የፖለቲካ ተሳትፎ ትግል አይባልም፡፡ ታጋዮች ማድረግ ያለባቸው ታዲያ ይህን አስቸጋሪ ሁኔታ ለማስወገድ የሚከፈለውን መስዋዕትነት ለመክፈል የሚያስፈልገውን ማድረግ ነው፡፡ ክቡር የሆነውን የስው ልጅ ህይወት ከማጥፋትና ንብረት ከማውደም በመለስ ማለቴ ነው፡፡ እነዚህ ነገሮች ምን ምን ሊሆኑ ይችላሉ ቢባል በምርጫ ሂደት ውስጥ ወሳኝ ናቸው ብዬ የማምናቸውን ዋና ዋና ጉዳዮች በማንሳት ለማብራራት እሞክራለሁ፡፡
የዕጩ ተወዳዳሪ ዝግጅት አንዱ መስረታዊ ጉዳይ ነው፡፡ በምርጫ ለመወዳድር የወሰነ አንድ ፓርቲ በምንም ዓይነት መልኩ ምርጫው ሲደርስ ዕጩ ለማዘጋጀት ደፋ ቀና የሚል ከሆነ ለመሸነፍ መዋጮ ማድረጉን ማመን አለበት፡፡ ለምርጫ ውድድር የሚመለመሉ ዕጩዎች በሁሉም መልክ በተለይ ከገዢው ፓርቲና መንግሰት ሊደርስባቸው የሚችለውን ጫና ለመቋቋም ዝግጁ የሆኑ መሆን አለባቸው፡፡ በዋነኝነት እነዚህ ዕጩዎች እንደ ገዢው ፓርቲ ወጪያቸው በፓርቲ የሚሸፈን ባለመሆኑ ተገቢውን ፋይናንስ ከደጋፊዎቻቸው ለማግኘት የሚያስችል ስልት መቀየስ የግድ ይላቸዋል፡፡ ውድድሩ በእኩል ሁኔታ ላይ እንዳልሆነ ከሚያስረዱት ሁኔታዎች አንዱ ይህ ነው፡፡ የገዢው ፓርቲ ዕጩዎች በዚህ ጉዳይ ቅንጣት ሃሣብ የለባቸውም፡፡ ይህ ጉዳይ የምርጫ ትግል ከሚደረግባቸው አንዱ መሆኑን ተረድተን መፍትሔ መሻት የእኛ እንጂ አንድ አንድ ተቃዋሚ ፓርቲ ነን የሚሉ ፓርቲዎች እንደሚሉት ለዚህ መፍትሔ ኢህአዴግ/መንግሰት የገንዘብ ድጋፍ ያድርግልን የሚለው አይደለም፡፡ በሀገራችን ገዢው ፓርቲ ኢህአዴግና መንግሰት የማይለያዩ የአንድ ሳንቲም ሁለት ገፅታ ከሚባለው በላይ መሆናቸው ይታወቃል፡፡ ስለዚህ መንግሰት ድጋፍ ያድርግልን ሲባል ኢህአዴግ ያድርግ እንደማለት እየሆነ ነው፡፡ ኢህአዴግ ደግሞ ይህን አድርጎ ለመሸነፍ ዝግጁ አይደለም ሰለዚህ ታግለን ተወዳዳሪ ፓርቲዎች በፍትሃዊነት የሚታዩበት ስርዓት እንዲመጣ በትግል ውስጥ ያለን መሆኑን መረዳት የግድ ይለናል፡፡ ይህ ከባድ ከሆነ አማራጩ ትግሉ ይቅር ወይ? የሚለው ነው፡፡
ከዕጩ ዝግጅት በኋላ በዋነኝነት የሚያስፈልገው በየደረጃው ያሉ ታዛቢዎችን ማዘጋጀት ነው፡፡ የታዛቢዎች ዝግጅት በሁለት ይከፈላል፡፡ የመጀመሪያው በምርጫ ቦርድ አስተባባሪነት የሚዘጋጁት ታዛቢዎች ማለትም “የህዝብ ታዛቢ” የሚባሉት ናቸው፡፡ እነዚህ ታዛቢዎች በሚመረጡበት ጊዜ ኢህአዴግ ቀደም ብሎ በአንደ-ለአምስት፣ በጥቃቅንና አነስተኛ፣ በወጣትና ሴቶች ፎረም ያደራጃቸውን በተለይም የፋይናንስ አቅማቸው ደከም ያሉ የአካባቢ ነዋሪዎችን በማዘጋጀት በህዝብ እንደተመረጡ በማስመሰል ይመድባቸዋል፡፡ ይህ ሲፈፀም ተወዳዳሪ ፓርቲዎች በዝምታ በማለፍ አንድ ደጋፊያቸው እንኳን እንዲገባ ሳያደርጉ ያልፋሉ፡፡ ትግሉን በትክክል ተረድተን ከሆነ በየምርጫ ጣቢያዎች እነዚህ ታዛቢዎች ሲመደቡ እኛም ደጋፊዎቻችን እንዲኖሩ ለማድረግ መስራት ይኖርብናል፡፡ ልክ ነው ይህን ለማድረግ ኢህአዴግ የዘረጋው ዓይነት የመንግሰት መረብና ድጋፍ አናገኝም፡፡ ይህ ነው የውድድር ሜዳው ልክ አይደለም የሚያስብለው እና ትግል የሚያስፈለገው፡፡ ይህን ለመለወጥ ትግል ማድረግ ካለብን የማይቻል አይደለም፡፡ ሁሉተኛው በዕጩ ተወዳዳሪዎች በራሳቸው የሚመደቡ ታዛቢዎች ናቸው፡፡ እነዚህን ታዛቢዎች የመምረጥ መብት የዕጩ ተወዳዳሪው ነው፡፡ ከዚህ አንፃር ያለው ፈታኝ ነገር ታዛቢዎችን ማስፈራራት፣ በገንዘብ መደለል ሲበዛም አፍኖ መውሰድ የመሳሰሉት ናቸው፡፡ እነዚህ በሙሉ የትግሉን አስፈላጊነት የሚያሳዩ እንጂ እንዲህ ከሆነማ ምርጫ ይቅር የሚያስብሉ አይመስለኝም፡፡ የማይፈራ፣ በገንዘብ የማይደለል ታፍኖ ለሚደርስበት ፈተና የተዘጋጀ ታዛቢ ማዘጋጅት ትግሉ የሚጠይቀው መሰዋዕትነት ነው፡፡ ለዚህ የሚመጥን ታዛቢ ማዘጋጀት የዕጩ ተወዳዳሪዎችና የፓርቲዎች ሲሆን ይህን በታዛቢዎች ላይ የሚፈፀም ህገወጥ ድርጊት ማሰቀየር ነው በሀገራችን ፖለቲካ ከሌሎች ዲሞክራሲ ከሰፈነባቸው ሀገሮች ለየት የሚያደርገው እና ትግል ያሰፈለገው፡፡ ምርጫቻን የቱ ነው? ታግለን እንቀይር ወይስ ኢህአዴግ በቃኝ እስኪል እንጠብቅ ነው፡፡
የመራጮች ምዝገባ ዘወትር ተገቢ ትኩረት የማይሰጠው በተወዳዳሪ ፓርቲዎች በኩል ነው፡፡ በ1997 ምርጫ በተወሰነ ደረጃም ቢሆን ቅስቀሳ ተደርጎ ብዙ መራጭ የተመዘገበ ቢሆንም መምረጥ የሚገባቸው ያልተመዘገቡና ባለመመዝገባቸው የቆጫቻ እንደነበሩ የቅርብ ጊዜ  ትውስታችን ነው፡፡ የ1997 በተለየ ሁኔታ ትተን በሌሎች ምርጫዎች ተቃዋሚዎች እንዲመርጡን የምንፈልገው ኢህአዴግ ጎትጉቶ ባስመዘገባቸው መራጮች ነው፡፡ ሁሉም ማወቅ ያለበት ኢህአዴግ በመራጭነት እንዲመዘገቡ ቤት ለቤት እየሄደ የሚቀሰቅሰው ባለው መረጃ መሰረት ደጋፊዎች ብሎ ያመነባቸውን ወይም በቀላሉ ደጋፊ ላደርጋቸው እችላለሁ ብሎ የሚገምታቸውን ነው፡፡ በተለይ በትምህርት ደረጃ ዝቅተኛ የሆኑ የህብረተሰብ ክፍሎች እናቶች ከአባለት ቀጥለው ለምዝገባ ከፍተኛ ትኩረት የሚሰጣቸው ናቸው፡፡ ፓርቲዎች በምርጫ ትርጉም ያለው ለውጥ ማየት የምንፈልግ ከሆነ የመራጭ ምዝገባ ከተጀመረበት ቀን ጀምሮ ደጋፊዎች እንዲመዘገቡ መቀስቀስ፣ ማበረታት እንዲሁም የመመዝገብን ጥቅም ማስተማር ይኖርብናል፡፡ ፓርቲዎች ላለመወዳደር ቢወስኑ እንኳን ደጋፊዎቻቸው ወደ ምርጫ ጣቢያ እንዳይሄዱ ማድረግ በምርጫው ላይ ትርጉም ያለው መልዕክት ያስተላልፋል፡፡ ያለመወዳደር ምርጫ ከሆነ ማለቴ ነው፡፡ መራጮችን ለማሰመዝገብ በምናደርገው እንቅስቃሴ በአብዛኛው ችግር ባይኖርም መዝጋቢ የለም፣ መታወቂያ አልታደሰም፣ እሰከ ዛሬ የት ነበርክ፣ በቀበሌ ተሳትፎ የለህም፣ የመሳሰሉት የሚጠበቁ የማደናቀፊያ መንገዶች ናቸው፡፡ ይህን ሊቋቋም የሚችል መራጭ እንዲኖር ቅስቀሳ ማድረግ ከትግሉ አንዱ አካል ነው፡፡ መራጮች በወኔ እንዲመዘገቡ ካደረግናቸው ከተመዘገቡ በኋላ መራጭ ብቻ ሳይሆን ቀስቃሽም በመሆን የምርጫ ምዕዳሩ እንዲስተካከል ድጋፍ ያደርጋሉ፡፡ ህዝብ የተሳተፈበት አፈናን እንቢ የማለት ተግባር ደግሞ በጥቂት ካድሬዎች ቁጥጥር ስር እንዲውል የተውነውን ምርጫ በትግላችን የእኛም ይሆናል ማለት፡፡ ለመምረጥ ያልተመዘገበ መራጫ የምርጫ ምዕዳር ለማስፋት አላፊነት ያለበት አይመስለውም፡፡ ትክክልም ነው፡፡ የምርጫ ምዕዳር የማስፋት አላፊነት ያለበት ዜጋ መፍጠር የትግሉ አካል ነው፡፡ ቆጠራ ሳይጠናቀቅ ካደረ አብረን ስንጠብቅ እናድራለን የሚል መራጭ ማዘጋጀት የግድ ይላል፡፡ ምርጫ 97 ትዝ አይላችሁም፡፡
መራጮች የሰጡትን ድምፅ፣ ታዛቢ ተከታትሎ ቆጥሮ፣ ደምሮ  የተቀበለውን፣ ምርጫ ቦርድ ሊለውጠው አይችልም ባይባልም ለመለወጥ የሚገጥመው ፈተና ከባድ ይሆናል፡፡ እዚህ ላይ እንደመፃፍ ቀላል እንዳልሆነ ይገባኛል፣ ኢህአዴግ ሲጨንቀው በታጣቂ ኮሮጆ እንደሚገለብጥ ዘንግቼው አይደለም፡፡ ይህን ድርጊቱን በተደራጀ መከላከል የትግሉ አንድ አካል እንደሆነ አፅዕኖት ለመስጠት ነው፡፡ ፓርቲዎች አሁን ባለው ደረጃ ይህን ለማድረግ ሙሉ ለሙሉ አልተዘጋጀንም የሚሉ ከሆነ ከምርጫ ለመውጣት ሳይሆን በተደራጁበት ልክ ለመወዳደር መዘጋጀት ይጠበቅባቸዋል፡፡ ሀሉም ቦታ ለመሆን ሲከጀል አንድም ቦታ ያለመሆን የሚመጣው በዚህ ምክንያት ነው፡፡
በታዛቢዎች የተፈረመ የምርጫ ውጤትን በምርጫ ቦርድ በኩል በሚፈፀም ሸፍጥ ወይም በጉልበት መሣሪያ ጭምር ተደርጎ በሚደረግ ንጥቂያ ሌላ ፈተና ላይ የሚወድቀው አካል የፍትህ ስርዓቱ ነው፡፡ የተደራጀ መረጃ ይዘን የፍትህ ስርዓቱን መሞገትም አንዱ የትግል አካል እንደሆነ መዘንጋት የለበትም፡፡ ይህን ሁሉ አድርገን ኢህአዴግ እነዚህን የህዝብ ድምፆች ገፍቶ ማነኛውንም ዓይነት ጉልበት ለመጠቀም ቢወስን ህዝብ የተሳተፈበት ስለሚሆን መዘዙ ብዙ ነው፡፡ ምርጫን ተከትሎ ለሚመጣ አብዮትም ጠሪ የሚሆነው የዚህ ዓይነት ድርጊት ነው፡፡ በምርጫ መሳተፍ ሂደት ውስጥ ህዝብ ካልተሳተፈ የተወሰኑ ሰዎች የሚያደርጉት መፍጨርጨር ሰለሚሆኑ ህዝቡ ድምፁ እንዲከበር የሚያደርገው ግፊት እምብዛም ነው፡፡ እነደከዚህ ቀደሙ ኢህአዴግ ወትውቶ ያስመዘገባቸው ሰዎች ለምን አልመረጡንም ብለን መጠየቅ ተገቢ አይደለም፡፡ በሚስጥር ድምፅ ሰጥተውን ቢሆን እንኳ በይፋ ድምፃችን ይከበር ሊሉ ይችላሉ ብሎ መጠበቅ የዋህ መሆን ነው፡፡ በሚስጥር የካዱትን በአደባባይ እንዲያረጋግጡ መጠየቅ ነው የሚሆነው፡፡
በዚህ ደረጃ ሳንዘጋጅ ቀርተን ምዕዳሩ ጠቧል ብለን “ሰለ …ሲባል ምርጫው ቢቀር” የምንል ከሆነ ኢህአዴግ ደስተኛ ነው፡፡ በግልፅ የሚሰብከውን አውራ ፓርቲ ስርዓት ተግባራዊ ያደርጋል፡፡ ኢህአዴግ ምዕዳሩን በህዝብ ተሳትፎ ሳናስገድደው ያሰፋዋል ብለን የምንጠብቅ ከሆነ በቅርቡ የሚሆን ስለአልሆነ የትግል ስልታችንን መፈተሸ ሊኖርብን ይገባል፡፡ አንዱ አማራጭ አንድ ሺ ትንታግ ታዛቢ ከማዘጋጀት፣ አንድ ሺ ተኳሽ ተዋጊ ሀይል ማዘጋጅት ሊሆን ይችላል፡፡ እንግዲህ ዘመኑ የሚዋጀውን፣ ለሰው ልጅ ከፍተኛ ክብር የሚሰጠውን፣ በወጪ አንፃርም አዋጭ ሊሆን የሚችለውን የትግል ስልት መምረጥ በፓርቲ ውስጥ ያሉ ስትራቴጂሰቶች ሃላፊነት ነው፡፡ በሃላፊነት ሰሜት የሚወሰን፡፡
እርግጠኛ ነኝ “ስለ …. ሲባል ምርጫው ቢቀር” የሚለው ሃሳብ የቀረበው በባርነት እንቀጥል በሚል ወይም የኢህአዴግ አውራ ፓርቲ ፍልስፍና ተስማምቶናል የሚል አይደለም፡፡ በእኔ አረዳድ ሌላ አማራጭ የትግል ስልት እንመልከት የሚል መሆን አለበት፡፡ ለጊዜው የምርጫው መንገድ ገና ብዙ ያልተሄደበት መንገድ ስለሆነ ተሰፋ መቁረጥ ያለብን አይመስለኝም፡፡ ምርጫ መሳተፍ የሰላማዊ ትግል ማሳኪያ አንዱ መንገድ ነው ብዬ አምናለሁ፡፡ ይህ ማለት ግን በፍፁም የምርጫ ሰሞን ደርሶ በሚፈጠር ሆይ ሆይታ ውስጥ ውጤት ለማግኘት መከጀል አይደለም፡፡ ከላይ በአጭሩ ለማስቀመጥ እንደሞከርኩት በሁሉም የምርጫ ደረጃዎች በንቃት በመሳተፍ እና ህዝቡን በማሳተፍ ነው፡፡
ቸር ይግጠመን

No comments:

Post a Comment