Sunday, June 1, 2014

ሚዛናችን ለምን ተዛባ?



የልክነት ሚዛናቸን የጠፋብን ወይም ደግሞ ሁለትና ከዚያ በላይ መለኪያ አስቀምጠን በምናደርገው ተግባር ሳይሆን በውጤት መመዘን የምንፈልግ ብዙዎች ነን፡፡ አሁን በስልጣን ላይ ያለው ስርዓት ደግሞ የዚህ ዓይነት ሚዛን አልባነትን ጎሽ በርቱ ብሎ ቡራኬ የሰጠ ነው የሚመስለው፡፡ እንደአስፈላጊነቱ ይጠቀምበታል፤ እንድንጠቀምበትም እያበረታታን ይገኛል፡፡
መንግሰት “አሸባሪ” ብሎ ከፈረጀው ግንቦት ሰባት ከሚባል ድርጅት አባሎች ጋር የአባልነት ፎርም ሲለዋወጥ፣ ሌሎችንም ለማደራጀት ጥረት ሲያደርግ የነበረ አንድ ግለሰብ በኋላ ላይ አዳፍኔ ምስክር  ሆኖ ቀርቦ እርሱ ነፃ ዜጋ ሆኖ ከዚህ ጋር አንድም ግንኙነት እንዳላቸው ሊያሳዩን ባልቻሉበት መልኩ እነ አንዱዓለም እና ናትናኤል በእስር ቤት ይገኛሉ፡፡ “ነፃነት” የሚሰማው ከሆነ ይህ ግለሰብ በነፃነት “የዞን ዘጠኝ” ታሳሪ/ነዋሪ ሆኖ ቀጥሎዋል፡፡ በቅርቡ “ዞን ዘጠኝ” የሚለው ስያሜ አሰጣጥ ነፃነታቸውን ለማስከበር ዳተኛ ለሆኑ የአዲስ አበባ ነዋሪዎች ተሰማሚ ሆኖ ስላገኘሁት ነው፡፡ ይህ ለታሪክ የተመዘገበ ሃቅ መስካሪ የሆነውንም ሆነ ተመስክሮባችኋላ ተብለው በግፍ በእስር ቤት ለሚገኙት ዜጎች ወደፊት ታሪክ የሚፋረዳቸው ይሆናሉ፡፡ ይህ ውርስ በባንዳነትም ይሁን በጀግንነት ለልጅ ልጅ የሚተላለፍ ሰለሆነ እንደ ቀላል የሚታይ አይደለም፡፡ ለመግቢያ ያህል በግፍ በእስር የሚገኙትን ጓዶቼን ካስታወስኩዋችሁ ይህ ጉዳይ ውስብስብ የፖለቲካ ቋጠሮ ስላለው እንለፈው እና ወደ ሌሎች ቀጥታ ፖለቲካ ያልሆኑ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ግንኙነታችን የሚያወሱ ጉዳዮች ብንሻገር መረጥኩ፡፡
በእለት ከእለት ግንኙነታቸን ጎቦ ሰጪና ተቀባይ እያለ ጣታችን የሚጠነቁለው ተቀባዩ ላይ ብቻ አድርገናል፡፡ ጠንቋይና አስጠንቋይ ባለበት ሀገር የጠንቋዩን ክፋት እንጂ የአስጠንቋይ እኩይ ተግባር እንደቅንነት ተወስዶዋል፡፡ የአራጣ አበዳሪና ተበዳሪ ድራማ በድፍኑ በአበዳሪ ላይ ተደፍድፎ አራጣ ተበዳሪዎች ቅን ኢንቨሰተሮች ተብለው በይፋ ሲሞካሹ መሰማት መደበኛ ነገር ሆኖዋል፡፡ እነዚህን ሁኔታዎች በአንድ ወቅት ዲያቆን ዳንኤል ክብረት ወንድ አዳሪዎች እያሉ ትኩረታችን በሴቶቹ ላይ መሆኑን ባሳየው መስመር ማየት ፈለጉህ፡፡ ሜሪኩሪ ሸጦ ያለ አግባብ ለመክበር የፈለገን ግለስብ ወይም ብርን ዶላር አድርግልሃለው ተብሎ የተጃጃለን ማነኛውንም ስው በውጤቱ ጉዳት ስለደረሰበት ማዘን የፈለገ መብቱ ቢሆንም ህገወጥ መሆናቸውን በግልፅ ያለመንገር ግን ተገቢ ነው ብዬ ለመውስድ ስለተቸገርኩ ነው፡፡

ጎቦ ስጪና ተቀባይ
ከህግ አንፃር ጉቦ መስጠትም ሆነ መቀበል ወንጀል ነው፡፡ ከሞራል አንፃርም ቢሆን መስጠትም መቀበልም አሰነዋሪ ድርጊት ነው፡፡ አሁን ባለንበት ደረጃ ግን ጠቅላላ መግባባት የተደረሰ በሚመስል መልኩ ስናወግዝ የምንሰማውም ሆነ የምንታየው ጉቦ ተቀባይ ላይ ብቻ ነው ባይባል እንኳን ከልክ በላይ ነው፡፡ ለምሳሌ ትራፊክ ፖሊሶች አብዛኞቹ ጉበኞች ናቸው ብለን የተሰማማነውን ያህል፣ መኪና አሽከርካሪዎች ጎቦ ሰጪዎች ናቸው ሲባል አይሰማም፡፡ አንድ ሺ ትራፊክ ጉቦ ቢቀበል መቶ ሺ ጎቦ ሰጪ መኖሩን ዘንግተን በአንድ ሺ ትራፊክ ላይ እንረባረባለን፡፡ ጎቦ ሰጥቶ መንጃ ፈቃዱን ወይም ታርጋውን ያስመለሰ አሸከርካሪ በኩራት በአደባባይ ሲያወራ ምንም ነውር የለውም፡፡ ገቢዎችና ጉምሩክ ስራተኞች ላይ ጣታችንን ስንቀስር ለእነዚህ ሰዎች ጎቦ የሚሰጡትን ነጋዴዎች ሁል ጊዜ ተገደው የሞት ሽረት ሕይወት ለመምራት አድርገን እንቆጥርላቸዋለን፡፡ የትራፊክ ህግ የጣሰ ግለሰብ በህግ በተቀመጠው አግባብ ቅጣቱን መክፈል ሲገባው ለመንግሰት መግባት ያለበትን ብር ሁለት መቶ ተደራድሮ በማስቀረት አንድ መቶ ጉቦ ሲሰጥ አንድ መቶ መስረቁን ልብ የሚለው አይደለም፡፡ ለመንግሰት መከፈል ያለበትን ግብር ላለመክፈል ከግብር አስከፋይ ጋር ተደራድሮ ግማሹን ጉቦ ሰጥቶ ግማሹን “ሲያድን” እንደ ሌብነት ሳይሆን ጮሌነት መቁጠር እየተለመደ የመጣ የተሳሳተ ሚዛን ውጤት ነው፡፡ እረ ጎበዝ ሚዛናችንን ምን ነካው?

አራጣ አበዳሪና ተበዳሪ
የከተማችን ኢንቨስተሮች በአራጣ ብር እንደሚነግዱ መረጃ መውጣት ከጀመረ ሰነባብቶዋል፡፡ አሁንም ግን ዘመቻው ያለው አራጣ አበዳሪ የተባሉት ላይ ያመዘነ ነው፡፡ ለአራጣ ብድር ባዶ ቦርሳ ይዘው የሄዱት ሰዎች ለምን እንዲህ እንዳደረጉ የሚጠይቃቸው ያለ አይመስልም፡፡ ለአራጣ የሚሆነውን ወለድ የዜጎችን ደም በሚመጥ የዋጋ ጫና ወደ ዜጎች አስተላልፈው ሊከብሩ እንዳሰቡ የሚነግራቸው ደፋር የተገኘ አይመስልም፡፡ ዛሬ በአራጣ መደህየታቸው እንጂ ስንቱን ለማደህየት ታጠቀው ተነስተው የነበሩ መሆናቸው ተዘንግቶዋል፡፡ አራጣ አበዳሪዎች ብቻ ሳይሆን አራጣ ተበዳሪዎች እኩል ጥፋተኞች መሆናቸውን አምነን መቀበል ይኖርብናል፡፡ አንድ አራጣ አበዳሪ እንዲከብር ብዙ አራጣ ተበዳሪዎች የመኖራቸው ሀቅ በፍፁም ሊሰወርብን አይገባም፡፡ በሀገራችን ኢትዮጵያ በመንግሰት ፖሊሲ ምክንያት መስሪያ ካፒታል እጥረት እንደሚኖር ሀቅ ነው፡፡ የመስሪያ ካፒታል ዕጥረት በህገወጥ መንገድ መሸፈን ግን በምንም ሚዛን ልክ ሊሆን አይችልም፡፡ የፖሊሲ ስህተት ግለሰቦች በሚሰሩት ስህተት አይሰረይም፡፡ በተለይ ከእለት ኑሮው አልፎ ለሌሎች ዕድል ልፈጥር ነው የሚል “ኢንቨስተር” የሚጠበቅበት ህገ ወጥ ወይም ኢ-ሞራላዊ መሆን ሳይሆን የስራውን ስፋት መቀነስ ነው፡፡ ስኬት በውጤት ሳይሆን የሚለካው ውጤቱን ለማምጣት በተሄደብት ህጋዊነት ጭምር ነው፡፡ የትም ፍጪው ዱቄቱን አምጪው አይስራም፡፡ የስራ ዕድል ለመፍጠር፣ የውጭ ምንዛሪ ለማስገኘት፣ ባለሀብት ለመባል የተሄደበት መንገድ ከተደረሰበት ውጤት እኩል ወይም በላቀ ሁኔታ ግልፅና በሃቅ ላይ የተመሰረተ ሊሆን ግድ ይላል፡፡ ከላይ የተዘረዘሩትን ውጤት ለማሰመዝገብ ወንጀል ውስጥ መዘፈቅ ተቀባይነት የለውም፡፡
ጠንቋይና አሰጠንቋይ
አንድ ሰሞን ታምራት የሚባል ጠንቋይ የከተማችን ዋነኛ አጀንዳ እንደ ነበር የሚዘነጋ አይመስለኝም፡፡ በዚህ ጉዳይ ከእምነት ነፃነት ጋር አያይዤ የግል ምልከታዬን አቅርቤ እንደ ነበር አስታውሳለሁ፡፡ በአብዛኛው ግን ታምራት ቤታችው ሄዶ ሳይሆን ቤቱ ድረስ እየሄዱ ያለ አግባብ ለመበልፀግ ወይም “የቸገረው እርጉዝ ያገባል” በሚል ብሂል ለጤናችን መሻሻል ብለው ከህክምና ተቋም ይልቅ ጠንቋይ ቤት መርጠው የሄዱትን ሰዎችን በግልፅ ጥፋተኛ መሆናቸው ሳይነገራቸው ይልቁንም ተበድለዋል በሚል ከንፈር ተመጦላቸው ተገቢ ያልሆነ ድርጊት አብረው ማድረጋቸው ተዘንግቶ ምስክርና ከሳሽ ሆነው መቅረባቸው አሳፋሪ ነው፡፡ እኔ በምንም ሚዛን ለጠንቋይ ጥብቅና እንደማልቆም የታወቀ ቢሆንም ለአሰጠንቋዮችም የምቆምበት ልብ የለኝም፡፡ አንድ ጠንቋይ ቤት በካዳሚነት ይሰራ የነበረ ሰው ጠንቋዮች የሚባሉት የደንበኞቻቸው ስግብግብነት የገባቸው የሰነ ልቦና አዋቂዎች ናቸው ይለኛል፡፡ ጠንቋያቸው ካዘዛቸው የሰውን ልጅ ክብር ነብስ ለገንዘብ ሲሉ ከማጥፋት ለማይመለሱ አስጠንቋዮች በግልፅ ቋንቋ በእኩል ደረጃ ጥፋተኞ መሆናቸው ሊነገራቸው ይገባል፡፡ ለዚህ ነው ሚዛናችን በውጤቱ ሳይሆን ሂደቱንም ከግንዛቤ ያሰገባ መሆን ይኖርበታል የምለው፡፡ ምንም ጥርጥር የሌለው ጤናቻውን ለማስመለስ ህይወት የከፈሉ፤ እንከብራለን ብለው የደኸዩ እንሚኖሩ እርግጥ ነው - ይህ ውጤት ነው፡፡

የሎተሪ ቁጭበሉና ባለመታወቂያዎቹ/ሜሪኩሪና ዶላር
ሎተሪ አሰር ሺ ብር ደርሶኝ መታወቂያ ስለሌለኝ ያለህን/ያለሽን ሰጡኝና ቀሪውን ውሰዱት ብሎ ለሚያታልል ቁጭ በሉ ንብረቱን ያስረከበ ሰው ሊታዘንለት ይገባል ብዬ አላምንም፡፡ አንድ ሺ ብር ንብረት ወይም ጥሬ ገንዘብ ሰጥቶ የሰው ዕድል አሰር ሺ ለመውሰድ የተዘጋጀ መታወቂያ ያለው ሰው ይህ ሳይሳካለት ቢቀር ቁማር እንደተበላ ቁማርተኛ እንጂ ሎተሪ የደረሰውን ሰው ለመርዳት የተነሳ ቅን ሰው አድርጌ ለመውሰድ ልብ የለኝም፡፡ ተማሪ እያለሁ “ቀይዋን ያየ በሚባል የካርታ ጨዋታ” ተሣታፊ ሆኜ ለጫማ መግዣ የተሰጠኝን ሃምሣ ብር ኮልፌ ታይዋን የሚባል ገበያ ውስጥ ተብልቻለሁ፡፡ ከዚህ መማርና ከቁማር መራቅ የእኔ ፋንታ እንጂ የካርታ አጫዋቾቹ አይመስለኝም፡፡ ትርፍ ለማግኘት ብዬ ተበላው፡፡ ቁማር ህገ ወጥ ከሆነ ካርታ አጫዋቹ ብቻ ሳይሆን እኔም አለሁበት፡፡ በፖሊስ ፕሮግራም እንባቸውን እያወረዱ የሚቀርቡት ሰዎች እንባቸውን ማበስ የእነሱ ፋንታ ነው የሚል እምነት አለኝ፡፡ እርግጠኛ ባልሆንም ፖሊስ እነዚህን አትርፍ ባይ አጎዳዮች  የሚያቀርባቸው ሌሎች በተመሳሳይ አተርፍ ብለው በቁጭ በሉ እንዳይወናበዱ ከተማሩ በሚል ይመስለኛል፡፡ በሌላ በኩል በብዙ ሚሊዮን ብር የሚሽጥ ሜሪኩሪ አለ ተብሎ በእጅ ያለን መቶ ሺ ተጠቅመን ገዝትን እንሽጥ ሲባል እሺ ብሎ ሚሊየነር ለመሆን የወሰነ ሰው ጤነኛ ነው ማለት ይቻላል? በተመሳሳይ በእጅ የያዝከውን ብር መቶ ሺ በመቶ ሺ ዶላር ይቀየራል ተብሎ መቶ ብር የማያወጣ ወረቀት ተሸክሞ ቤቱ የገባን ሰው ምን ልንለው እንችላለን? ይህ በምድራዊ ህግም ሆነ በሞራል ተቀባይነት የሌለው የሀብት ማጋበስ አባዜ ከየት ነው ያመጣነው? ይህን አባዜ ትክክል አይደለም የደረሰብ ጉዳት ለሰራህ ተመጣጣኝ ቅጣት ነው ለማለት ለምን ድፍረት አጣን? በእኔ እምነት ይህን ድፍረት የምናጣው በአንድ ወይም በሌላ መስመር ይህችን ጫወታ ለመጫወት በየግላችን ሳናስብ የምንቀር አይመስለኝም፡፡ ልክ ነኝ?
ሴት አዳሪነት ወንድ አዳሪነት
ሴት አዳሪነትን የምንፀየፍ ወንድ አዳሪወች በብዛት አለን፡፡ ወንዶች የሴቶችን አገልግሎት ባይፈልጉት ሴቶቹ በብርድ እራቃናቸውን ለመቆም ምንም ገፊ ምክንያት አይኖራቸውም፤ የፍላጎቱ መኖር ነው አቅርቦቱ እንዲኖር እያደረገ ያለው፡፡ በዚህ ጉዳይ በልዩ ችሎታው ዲያቆን ዳንኤል ክብረት መክሮናልና መድገም አልፈልግም ይህን የሴት አዳሪዎችን ጉዳይ ካነሳው አይቅር አንድ ጉዳይ ሳላነሳ ማለፍ ግን አልፈለኩም፡፡ በሴት አዳሪነት የተሰማሩት ሴት እህቶች የመንግሰትን ድጋፍ አግኝተው ከዚህ ኑሮ ለመውጣት ሳውዲ ሀረብያ ሄደው በግፍ  ተባረው መምጣት ይኖርባቸው ይሆን? የሚል ጥያቄ አለኝ፡፡ በዚህ ጉዳይ በቂ መረጃ ባይኖረኝም በከተማችን አንድ ድንክ አልጋ ዘርግተው ደጃቸው ላይ ቆመው ደንበኛ የሚጠብቁ ሴቶች ቁጥር የሳውዲ ሰደተኞችን እንደማያክሉ እርግጠኛ ነኝ፡፡ እነዚህን እህቶች ከዚህ ስራ ማውጣት ቀላል ባይሆንም የማይቻል ነው የሚል እምነት የለኝም፡፡ በባቡር ዝርጋታ ሰበብ መንገድ በመዘጋቱ ምክንያት የቀድሞ አራተኛ ክፍለ ጦር ጀርባ ወይም መሸዋለኪያ አካበቢ በምሽት ሰመላለስ የማየው ነገር በፍፁም ሰላም አይሰጠኝም፡፡ የዚህች ሀገር እድገት ትሩፋት መቼ ነው የሚደርሳቸው የሚል ምፀት ይመጣብኛል፡፡ እነዚህን እህቶች የወረዳው ጥቃቅን እና አነሰተኛ ተቋም አደራጅቷቸው ይሆን ይህን ስራ የሚሰሩት? ካልሆነ ለእነዚህ ሴቶች የሚሆን የስራ ምክረ ሃሳብ አለው?

እነዚህን ሁሉ ደምረን ለምንድነው የዚህ ዓይነት ሰግብግብ ሰዎች እየተበራከቱ ከሚገባቸው በላይ ጥቅም ለማግኘት የሚደራጁት ብለን ማሰብ ተገቢ ነው፡፡ እነዚህ በሙሉ ከላይ ያነሳዋቸው የተበላሸ ስርዓት መገለጫዎች ናቸው፡፡ የአባት ቤት ሲዘረፍ አብረህ ዝረፍ የሚል የተሳሳተ ብሂል ውጤት ናቸው፡፡ ሕግ ያለማክበር፤ ግብር ለመክፈልም ሆነ በተገቢው ሁኔታ ፈቃደኝነት ማጣት፣ በህገ ወጥ ገንዘብ መክበርና ከዚህም የተገኘውን ገንዘብ ወደ ውጭ ማሻሽ፣ ሰካርና ዝሙት የስርዓት መበስበስ በግለሰብ ደረጃ ደግሞ የሞራል ውድቀት ማሳያ ናቸው፡፡ ምንም እንኳን በስርዓቱ ውስጥ የምንገኝ ብንሆንም በቁጥጥራችን ስር ያለውን የግልና የቤተሰብ ሞራላችን በመጠበቅ ይህን ስርዓት ማስወገድ ይኖርብናል፡፡ ስህተት በስህተት አይታረምም፡፡ ሚዛናቸን ትክክል ይሁን!!!!

No comments:

Post a Comment