Tuesday, January 28, 2014

የኢትዮጵያ ሬዲዮና ቴሌቪዥን ድርጅት ለራሱ ሲል ይጣፍጥ ግርማ ሠይፉ ማሩ



የኢትዮጵያ ሬዲዮና ቴሌቪዥን ድርጅት የስራ እንቅሰቃሴን አሰመልክቶ  አዲሱ የቦርዱ ስብሳቢ አቶ ሬዲዋን ሁሴን ሪፖርት ለምክር ቤት አቅርበው ነበር፡፡ እኔም የበኩሌን አሰተያየት እና ጥያቄዎች አቅርቤ ነበር፡፡ ሪፖርቱ ባጠቃላይ ሲታይ የምናውቀውን ደካማ ተቋም በግልፅ ያሳየን ነበር፡፡ በሪፖርቱ እንደመልካም ስራ የቀረበው ደግሞ ያፈርንባቸው  ዶክመንተሪዎች መሆናቸው ሌላ ነጥብ ነው፡፡ እነዚህ ስራዎቸ ደግሞ በህዝብ የተወደዱ ናቸው ተብለናል፡፡ አስገራሚ ደግሞ በድርጅቱ የሚሰራውን ፕሮግራም የሚወደው ህዝብ ለቴሌቪዥን ኪራይ በዓመት አምሳ ብር ለመክፈል ያለመፈለግ ዝንባሌ ያሳያል መባሉ ነው፡፡ በእኔ አረዳድ የህዝቡ ያለመክፈል አዝማሚያ ምንጭ ህዝቡ በደረሰበት የዕድገት ደረጃ የሚመጥን የቴሌቪዥን አገልግሎት ስለማያገኝ ነው፡፡ አንድ የእግር ኳስ ጨዋታ ለማየት ህዝቡ ስንት እንደሚከፍል እናውቃለን፡፡
በዕለቱ ካቀረቡኩት ጥያቄ ምላሽ የተነፈገው ዋነኛው ጥያቄ የኢትዮጵያ ሬዲዮና ቴሌቪዥን ድርጅት በሪፖርቱ የመድበለ ፓርቲ ስርዓት ከማጠናከር አንፃር ስራዎች ተሰርተዋል በማለት ያቀረበው ልክ አይደለም የሚል ሲሆን፤ ለዚህ ማሳያም አንድነት እና ኢህአዴግ እኩል ፓርቲዎች ቢሆኑም የአንድነት ጠቅላላ ጉባዔ በሚዲያ ሳይዘግብ የኢህአዴግን ጉባዔ ግን ከባህርዳር በቀጥታ ስርጭት ጭምር ሲዘገብ እንደነበረ ያቀረቡክት ነው፡፡ ለዚህ ጥያቄ ክቡር ሚኒስትሩ እንደ ካድሬም ማሳሳቻ ነገር ስለ አልታያቸው በዝምታ ማለፉን እንደ ዘዴ መምረጣቸውን ወድጄዋለሁ፡፡
ሌሎችን አሰተያየቶችን በተመለከተ ደግሞ ሃሳቡን በማሳሳት ተርጉመው ለማሳሳት የሞከሩባቸውን ናቸው፡፡ በሪፖርቱ ውስጥ “ብሔራዊ መግባባት ለማጎልበት ጥረት ተደርጎዋል” ይላል፡፡ እኔ ይህን የሚደግፍ ሰራ በሪፖርቱ ውስጥ የሌለው መሆኑን አመልክቼ ይልቁንም ድርጅቱ ያለመግባባት ለማምጣት ነው የሚሰራ የሚመስለው የሚል ሃሳብ ስሰነዝር፡፡ አቶ ሬድዋን ግን የሚሰሙት መበታተን ብለው ነው፡፡ ኢህአዴግም ሆነ ካድሬዎቹ አንድ ጉዳይ ጠንከር ብሎ ከታያቸው መመሽጊያቸው ይህች ሀገር ልትበተን ነው ወደሚለው ፅንፍ መሄድ ነው፡፡ ኢህአዴግ በፈለገው አስማት ከዚህ ወንበር ቢነሳ፤ ይህች ሀገር ምንም ዓይነት የመበተን አደጋ የለባትም፡፡ ለምን ይህን ካርድ እንደሚወዱት አይገባኝም፡፡
ሌላው አዲስ የሰማሁት ፍልስፍና ደግሞ “መነሻችን ከተለያየ፣ መድረሻችንም ይለያያል” የሚለው ነው፡፡ በየትኛውም ህግ አንድ ቦታ ለመድረስ ከተመሳሳይ ቦታ መነሳት የግድ አይልም፡፡ በኢትዮጵያ የመድበለ ፓርቲ ስርዓት ያሰፈልጋል ብለን ከልብ የምናምን ሰዎች መነሻችን እንደሚለያይ ብቻ ሳይሆን፣ ልንሄድበት የምንፈልጋቸው መንገዶች በአብዛኛው የተለያዩ ቢሆኑ እንኳን መድረሻችን  አንድ ወይም ተመሳሳይ ነው የሚል እምነት አለን፡፡ ይህውም የሀገራችን ዕድገትና ብልፅግና ነው፡፡ ይህ ደግሞ የሚሆነው ሰላም ዲሞክራሲ እና የዜጎች ሰብዓዊ መብት የሚከበርበት ሀገር እና የፖለቲካ ስርዓት ሲፈጠር እንደሆነ ጥርጥር የለንም፡፡ ለዚህም ይመስለኛል ትግሉ፡፡ በሀገራችን ኢትዮጵያ “ትግል” የሚለውን ቃል ከፖለቲካችን ለማውጣት እና ድህነትን በጋራ ለምናደርገው ርብርብ ብቻ እንድንጠቀምበት ለማድረግ ኳሱ ያለው በኢህአዴግ እጅ ነው፡፡ ኢህአዴግ ከቆረበበት የአብዮታዊ ዲሞክራሲ/ግራ ዘመም ፖለቲካ መውጣት የግድ ይለዋል፡፡ ምክንያቱም የዚህ መስመር ተከታዮች ትንተና የሚያደርጉበት ማዕቀፍ ሁልጊዜ ተቃራኒ ወገን ይፈልጋል፡፡ ምቀኛ አታሳጣኝ ፍልስፍና ነው፡፡ ለውጥ ለማምጣት ደግሞ ይህ ተቃራኒ ወገን መጥፋት አለበት ብለው ያምናሉ፡፡ ለዚህ ነው ገድለው እንኳን እርግጠኛ ስለማይሆኑ መቃብር ላይ ግንብ የሚገነቡት፡፡ በዚህ ዓይነት የትንተና መስመር የሚመራ ፓርቲና መንግሰት የመድበለ ፓርቲ ሰርዓትን ከምር ሊወስድ አይችልም፡፡ ስለዚህ ድምዳሜው “መነሻችን ከተለያየ፣ መድረሻችንም ይለያያል” የሚል ፅንፍ የሚደርሰው፡፡
ኢህአዴግ እና አባላቱ አብዮታዊ ዲሞክራሲ አመለካከት መያዝ ምርጫቸው ከሆነ መከበር ያለበት መብት ነው፡፡ ልናከብርላቸው ይገባል፡፡ ሆኖም ግን ልማታዊና ዲሞክራሲያዊ አመለካከት መገንባት እያሉ በየሲቪል ሰርቪሱ እና መንግሰት ተቋማት በአብዮታዊ ዲሞክራሲ አስተሳሰብ ማጥመቅ፤ ህገ መንግሰታዊ ስርዓቱ የፈቀደውን የሃሳብ ልዩነትን መድፈር ነው፡፡ ለዚህ ሁነኛ ምሳሌ ደግሞ የኢትዮጵያ ሬዲዮና ቴሌቪዥን ድርጅት አንዱ ነው፡፡ የኢትዮጵያ ህገ መንግሰት አንቀፅ 29/5 “በመንግስት ገንዝብ የሚካሄድ ወይም በመንግስት ቁጥጥር ስር ያለ መገናኛ ብዙኃን የተለያዩ አሰተያየቶችን ለማስተናገድ በሚያስችል ሁኔታ እንዲመሩ ይደረጋል፡፡” ይላል፡፡ ይህን ህገ መንግሰታዊ ድንጋጌ ጥሰው የመንግሰት ሚዲያዎች ከአብዮታዊ ዲሞክራሲ መንገድ ውጭ ሌሎች አመለካከቶችን ለማስተናገድ ለዜጎችም ሆነ ቡድኖች አንድም ክፍት ቦታ ለመስጠት ዝግጁ አይደሉም፡፡ ይልቁንም አቋም ይዘው የስም ማጥፋት ዘመቻ ይሰራሉ፡፡
በቅርቡ በተደጋጋሚ እየሰማነው ያለው “ልማታዊና ዲሞክራሲያዊ መንግሰት” የሚለው ፍልስፍና መሰረቱ አብዮታዊ ዲሞክራሲያዊ የሚባለው የት መጤው የማይታወቅ ፍልስፍና እንደሆነ ቢታመንም አብዮታዊ የሚለውን ትተነዋል ማለት ጀምረዋል የሚል ነው፡፡ ይህ ጥሩ ሽግሽግ ይመስለኛል፡፡ ግልፅ መሆን ያለበት ግን ልማትና ዲሞክራሲ ግቦች ሲሆን እዚያ ለመሄድ የምንከተለው የፖለቲካ ፍልስፍና በግልፅ ነጥሮ መውጣት እና ለህዝብ ይፋ መሆን ይኖርበታል፡፡ እንደ አለመታደል ሆኖ የፖለቲካ ፍልስፍና አባታቸው በህይወት ስለሌሉ ይህ መንገድ ለኢህአዴጋዊያን ግራ ሳይሆን አይቀርም፡፡ አንድ ጓደኛዬ ከኢህአዴግ ሰፈር አዳዲስ ቃላት ጠፍቶዋል ነገሩ ምንድነው ብሎኝ ነበር፡፡ ይህን ነገር ልብ ብላችኋል?
ሌላው በኢህአዴግ ሰፈር ድንገት ከሚመዘዙት ካርዶች አንዱ ህገ መንግሰት መጣስ፣መናድ ወይም አለማክበር የሚለው ነው፡፡ ህገ መንግስቱን እንደ ቅዱስ መፅሃፍ የማይመለከቱ ብዙ ወገኖች አሉ እኔም አንዱ ነኝ፡፡ ምክንያቱም ሊሻሻሉ የሚችሉ ጉዳዮች እንዳሉት ሰለምናምን፡፡ ይህም ህገ መንግስታዊ ስለሆነ ነው፡፡ የህገ መንግሰቱ አንቀፅ 104 እና 105 ህገ መንግሰት እንዴት እንደሚሻሻል የሚገልፁ ድንጋጌዎች ናቸው፡፡ ለዚህም ነው አሁን ባለው ህገ መንግሰት ከምር በማክበርና በማስከበር ረጅም ርቀት ልንሄድ እንችላለን ብለን ገዢውን ፓርቲ እና መንግሰትን ህገመንግስቱን ለማክበር እና ለማስከበር በፅናት እንዲቆሙ የምንሞግተው፡፡ ከዚህ አንፃር የኢትዮጵያ ሬዲዮና ቴሌቪዥን ድርጅት ህገ መንግሰታዊ ድንጋጌዎችን በማክበር ሚዲያዎቹ የሁሉም ዜጎች የጋራ መጠቀሚያ መድረክ እንዲሆኑ መስራት የሚኖርባቸው፡፡ ይህ ግን በቅረቡ የሚሆን አይመስልም ምክንያቱም የድርጅቱ የቦርድ ስብሳቢ አቶ ሬድዋን በጀመሩት መስመር እንደሚቀጥሉ አበክረው ለምክር ቤቱ ገልፀዋል፡፡
በዚህ አጋጣሚ ስለ አቶ ሬድዋን የቦርድ ስብሳቢነት ስናወራ አንድ የማክያቶ ቡድን አባል የመንግሰት ቦርዶች መብዛት አንስቶ ካጫወተኝ በኋላ ውስጥ ለውስጥ በቦርድ አባልነት ሽኩቻ እንዳለ እና ምክንያቱም ከቦርድ አባልነት ጋር ተያይዞ ከግብር ነፃ የሆነ ከፍተኛ ገቢ እና ሌሎች ጥቅሞች እንዳሉ ገለፀልኝ፡፡ ለነገሩ ሚኒስትሮቻችን በቦርድ አባልነት በሚያገኙት ድጎማ ጭምር እንጂ በመንግሰት በሚከፈል ደሞዝ መኖር እንደማይችሉ ማን ያጣዋል በሚል ወሬው ተቋጭቶዋል፡፡ እሰኪ አንባቢያን የምታውቁትን በቦርድ የሚተዳደር መስሪያ ቤት እና የቦርድ አባላት ጥንቅር የሚከፈላቸውን አበል ጭምር ዘርዘር አድርጉና አስረዱን፣ ስለ ፍትሃዊነቱ ግልፅነት እንዲኖረን ብዬ ነው፡፡
በመጨረሻም አቶ ሬድዋን በሳውዲን ስለሚኖሩ ኢትዮጵያዊያን የመንግስታቸውን አቋም የገለፁበት ቁርጥ አቋም ከአንድ ኮሚኒኬሽን ሚኒስትር የሚጠበቅ ሆኖ አላገኘሁትም፡፡ በህገ ወጥ መንገድ ሳውዲ የገቡትን ዜጎች ህገወጥ ብሎ በስማቸው መጥራት ምንም ችግር እንደ ሌለው ይልቁንም በሌላ ስም ቢጠሩ ወይም ዝም ቢባል ልክ እንዳልሆነ አስረድተውናል፡፡ ይህ ደግሞ የፓርቲያቸውና መንግሰታቸው እውነት መሸፋፈን እንደማይወድ ማሳያ እንጂ ሌላ ተደርጎ መወሰድ እንደሌለበት አስመረውበታል፡፡ በእኔ አረዳድ በመኪና አደጋ ጉዳት የደረሰበትን ሰው በአደጋው ቦታ ተገኝቶ ለምንድነው ግራ ቀኝ አይተህ የማትሻገረው ብሎ እንደማላጋጥ ነው፡፡ በሳውዲ ሀረቢያ ጉዳት የደረሰባቸው ወገኖቻችን አብዛኞቹ ልክ በመሰላቸው መንገድ ከሀገር ስራ ፍለጋ መውጣታቸው የሚካድ አይደለም፣ ይህም በሳውዲ መንግሰት ዕይታ ሕገወጥ ለሆን ይችላል፡፡ የእኛ ሚዲያ በሳዊዲ መንግሰት ጎን ቆሞ ዜጎቹን ህገወጥ እያለ ማሸማቀቅ ተገቢ ነው ብሎዋል፡፡ ስለዚህም በሚዲያ በተደጋጋሚ “ህገ ወጥ” መሆናቸውን መንገር ተገቢና ትክክል ከደረሰባቸው ጉዳት የሚያገግሙት በስማቸው “ህገ ወጥ” ተብለው ሲጠሩ ነው ተብለናል፡፡ ስምተናል!! ግን መስማት መስማማተ አይደለም፡፡
ገዢው ፓርቲ ኢህአዴግ የኢትዮጵያ ሬዲዮና ቴሌቪዥን ድርጅትን እንደ ድርጅት ልሳን እየተጠቀመበት እንደሆነ ምንም ጥርጥር የለውም፤ ይህ ደግሞ ኢህአዴግ ከህግ አግባብ ውጭ የያዘውን የፓርቲ ሚዲያ ማለትም ፋና ብሮድካስትን ጨምሮ በሀገሪቱ ውስጥ ያሉትን ትልልቅ ሚዲያዎች ተቆጣጥሮ ሀገሪቱን የአብዮታዊ ዲሞክራቶች መንደር ለማድረግ ነው፡፡ እርግጠኛ መሆን ያለብን ግን የፈለጉትን ያህል ሚዲያውን ቢቆጣጠሩት የኢትዮጵያ ህዝብ ሌሎች አማራጮችን ተጠቅሞ ከዓለም እኩል ይሆናል እንጂ በእነርሱ መንደር ውስጥ ሲርመጠመጥ አይገኝም፡፡ ይህን የአፈና መረብ ሊበጥሱ የሚችሉ ዜጎች እንደ አሽን እየፈሉ ይገኛሉ …….. ጨው ለራስህ ስትል ጣፍጥ ነው፡፡


No comments:

Post a Comment