Thursday, January 23, 2014

የአቶ አዲሱ ለገሠ ሚዛናዊነት የጎደለው ሚዛናዊ ሁኑ ጥያቄ



የቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ አዲሱ ለገሠ በአደባባይ ድንገት ጡረታ ውጡ ተብለው በጡረታ ላይ ናቸው ብለን ስናስብ፣ አንድ አንዱ ደግሞ መተካካት አለ ብሎ እያሰበ ባለበት ወቅት እርሳቸው ግን በጓሮ በር የተለያየ መንግሰታዊ ተቋም ቦርድ ኃለፊ በመሆን ብቅ ብቅ ማለት ከጀመሩ የቆየ ነበር፡፡ የኢትዮጵያ አየር መንገድ መጥቀስ ይቻላል፡፡ አሁን ግን ከእነ ሙሉ ክብሩ እና ጥቅሙ ጋር ብቅ ብለዋል፡፡ የመንግሰት ሹሞች ጥቅማ ጥቅምን አስመልክቶ አዋጅ ከመውጣቱ በፊት ምክትል ጠቅለይ ሚኒስትር መሆን ከመደበኛ ጡረታ ውጭ ብዙም ትርጉም አልነበረውም፡፡ የአሁን ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ግን ትርጉም ያለው ጥቅም አለው፡፡ እንደ “ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር” የተባሉትን አይጨምረም፡፡ በነገራችን ላይ በስልጣን ላይ ካለ ሚኒስትር በጡረታ ያለ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር እንደሚበልጥም ትምህርት አግኝተናል፡፡
አቶ አዲሱ በፌዴራል ልዩ ድጋፍ ቦርድ ስብሳቢነት ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ሪፖርት ያቀርባሉ ብለን ስንጠብቅ፤ የፌዴራል ጉዳዮች ሚኒስትሩን ሪፖርት እንዲያነቡ አድርገው በሪፖርቱ ላይ ከምክር ቤት አባላት ለተነሱ ጥያቄዎች የቦርዱ ስብሳቢ አቶ አዲሱ ምላሽ ይሆና ያሉትን ስጥተዋል፡፡ አቶ አዲሱ ለገሠ ያለ አግባብ ጡረታ ውጡ የተባሉ እንደሆነ የተሰማኝ በመልስ አሰጣጣቸውም ሆነ በሚጠቀሙባቸው ቃላት ጥንካሬ እንዲሁም ምክር ቤቱን በማሳቅ ሟቹን ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ መለስ ዜናዊን ለመተካት የበለጠ ቅርብ እንደነበሩ ስመለከት ነው፡፡ አማራ ባይሆኑ የአማራ ገዢ መደብ ተመልሶ መጣ ያስብላል የሚባለውን ፈረተው ሟቹ ለእንዲህ ዓይነት ሀሜትና ፈተና የማያጋልጥ ዕጩ ባያዘጋጁባቸው ኖሮ አቶ አዲሱ አቶ መለስን ለመተካት የተሻሉ ነበሩ የሚል ግምት ወስጃለሁ፡፡ ጥሩ ጠቅላይ ሚኒስትር አላልኩም - አቶ መለስን ለመተካት ነው ያልኩት፡፡
አቶ አዲሱ መልስ መመለስ የጀመሩት እነዚህ ልዩ ድጋፍ የሚሹ ክልሎች እራሳቸውን የቻሉ መንግሰት መሆናቸውን አስረግጠው ነግረውን ነገር ግን አመራር የሌላቸው መሆኑን ማወቅ እንዳለብን ጭምር ነው፡፡ ስለዚህ በእኔ አረዳድ አጋር ክልሎች አመራር የሌላቸው ሰለሆነ አሁን በሞግዚት የሚተዳደሩ ናቸው፡፡ ፌዴራሊዝም የሚባለው ፌዝ ነው ለሚሉ ተቺዎች አቶ አዲሱ በአደባባይ ማስረጃ የሰጡ ነው የሚመስለኝ፡፡ በራሱ አመራር የማይሰጥ ፌዴራሊዝም ከፌዝ ውጭ ምን መልስ ይኖረዋል፡፡ እነዚህን ጉዳዮች እና ሌሎች ጠጠር ያሉ ጥያቄዎች ከአጋር ድርጅቶች ይቀርባል ብዬ ስጠብቅ የነበረ ቢሆን ምንም መስማት አልቻልኩም፡፡ ጥፋቱ የአፈ ጉባዔው አይመስለኝም፡፡ በምክር ቤቱ አሰራር ጥያቄ ማቅረብ የሚፈልግ ሰሙን ማስመዝገብ ስለሚኖርበት እነዚህ የሀጋር ክልል ወዳጆቼ ሳይመዘገቡ ቀርተው ዕድሉ አመለጣቸው ፤ እንደዛም ሆኖ በቀረበው ሪፖርት መናደዳቸውን ታዝቢያለሁ፡፡
አቶ አዲሱ ጥያቄ ሲመልሱ በሙሉ ልብ ነው፡፡ መንግሰት አቅጣጫ ብሎ አስቀምጦ ለአመታት ሲዳክርበት የከረመውን የቢፒራ እና የቢ.ሴሲ እንዲሁም የልማት ሠራዊት ግንባታን በደንብ አላግጠውበታል፡፡ እውነቱን ለመናገር እዚህ ጋ አንጀቴን ነው ያራሱት፡፡ “እነዚህ ድጋፍ የሚደረግላቻው ክልሎች ከጎሳ አሰተሳሰብ ሳይወጡ፣ ስለ ሠራዊት ግንባታ እና ሌሎች ወሬዎች ማውራት ቦታው አይደለም ነው” ያሉት፡፡ በማስከተልም “በክልሉ ያሉት መሪዎችም አንዳንዴ ሠራዊት ገንብተናል ይሉናል፡፡ የታለ የሠራዊቱ መሪ? ስንላቸው የለም ይላሉ፤ ያለ መሪ ሰራዊት ምን ማለት ነው?” ብለው ሊጠየቁበት የቀረበውን ምክር ቤት በጥያቄ አፋጠዋል፡፡ እንዲህ ነው ልበ ሙሉነት፡፡ ጥያቄው “ሰራዊት እንዲገነቡ እገዛ አድርገሃል ወይ? ከሆነ አላደረኩም” ብለዋል፡፡ አንዳንዶች ሠራዊት ግንባታ ሲሉም አቁም ነው ያለኩት ነው ያሉን፡፡ ጎበዝ እንዲህ ያለ አቁም የሚል ልባም ባለስልጣን አላማራችሁም፡፡
የቤቶችና ህዝብ ቆጠራ የሚባለውን መስሪያ ቤት አፈር ድሜ ነው ያስገቡት፡፡ የሚገርመው ይህን መስሪያ ቤት በበላይነት የሚመራውን ኮምሽን እርሳቸው የሚጠቅሱትን ሪፖርት ሲያወጣ ስብሳቢ የነበሩት እራሳቸው መሆናቸው ነው፡፡ ሴንሰሱን (የህዝብና ቤት ቆጠራ ማለታቸው ነው) መሰረት አድርገን ዕቅድ አወጣን መሬት ላይ ሲከድ የተባለውን የሚያክል ህዝብ የለም፡፡ በሌለ ሰው ምን እናድርግ? ብለውናል፡፡ ምንም ነው መልሱ፡፡ የሚገርመው በእንስሳት ቆጠራውም ይኽው ነው በመሬት ላይ ያለው ሀቅ ብለውናል፡፡ ሀቅ ይውጣሉት ማለት ነው የእኛ ድርሻ ለእንዲህ ያለ ደፋር ታጋይ፡፡ ምን ዋጋ አለው ታዲያ ከዚህ በማስከተል፤ ሌላ ደፋር እንዴት ብሎ ህዝብ ሲቆጥር አምስት መቶ ሺ ህዝብ በብልጫ ተቆጠረ ብሎ ጥያቄ የሚያነሳ እና ተጠያቂ የሚያገኝ ያስፈልግ ነበር፡፡ እንደው ለነገሩ ባለፈው ቆጠራ ከአማራ የጎደሉት ሰዎች አፋርና ሶማሌ ሄደው ይሆን እንዴ? የአማራ ነገር እኮ አይታወቅም፡፡
አቶ አዲሱ የክልሎች ስም ሲጠሩ እንደ ፖለቲከኛ ብዙም አይጠነቀቁም፡፡ የደቡብ ብሔራዊ ክልል መንግስት ይላሉ፡፡ በእውነቱ እራሳቸውም ቢሆኑ ይህን ልዩነቱ ለትርጉም እንኳን የማይገባን ወይም ለብዙ ቃል አንድ ትርጉም ያለውን ብሔር፣ ብሔረሰቦች እና ሕዝቦች የምትለዋን በአቅጣጫ መጠቆሚያው ደቡብ አጠቃለውታል፡፡ ይህ ለሲዳማዎች ከፍተኛ ቅሬታ የሚፈጥር አጠራር እንደሆነ አንድ ወዳጄ አጫውቶኛል፡፡ በቅርቡ ከምክር ቤት ሹመት ያገኘ አንድ ስው ደቡብ አቅጣጫ ነው፤ ትግራይ መባል እንደምትፈልጉ እኛንም በሰማችን ጥሩን በሚለው ሙግቱ ይታወቃል፡፡ ይህ የአጠራር ስህተት ለሌሎች ሹሞች ቢሆን ትልቅ የፖለቲካ ስህተት እንደሆነ መገንዘብ ያስፈለጋል፡፡ ደቡቦች አልተጠራንም ብለው ዝም ማለት ይችላሉ፡፡
አንድ የምክር ቤት አባል እነዚህ ክልሎች በጠረፍ ከመገኘታቸው አንፃር ለህገ ወጥ የሰዎች ዝውውር ካላቸው ተጋላጭነት አንፃር ምን እየተሰራ ነው? በሚል ላቀረቡት ጥያቄ አቶ አዲሱ ሰፋ አድርገው ለመመለስ ሲሉ ወደ ውጪ ለማስወጣት ብቻ ሳይሆን እነዚህ ክልሎች ሌሎች የፀረ ሰላም ሀይሎችና አክራሪዎች የሚንቀሳቀሱበት በመሆኑ ክልሎች ይህን እንቅሰቃሴ ተቋቁመው ነው ይህን የልማት ድል ያሰመዘገቡት፣ ሰለዚህ ይህን በልማት የተገኘውን ድል ካለባቸው የፀጥታ ፈተና አንፃር ሚዛናዊ ሆኖ ለሚመለከት ኃይል ከፍተኛ ሰራ እንደተሰራ ይረዳል ብለዋል፡፡ ከዚህ አንፃር ሚዛናዊነትን የጠየቁት አቶ አዲሱ የቀድሞ መንግሰታት አሁን እሳቸው አለ ከሚሉት በላይ ፀረ ህዝብ እንዲሁም ገንጣይ አስገንጣይ የሚሉዋቸውን ኃይሎች ተቋቁመው ነው ይህችን ሀገር አሁን እርሳቸው እና ጓዶቻቸው አዲሲቱ የሚሏትን ኢትዮጵያ ያቆዩት፡፡ ስለዚህ ሚዛን በትክክል ከስራ በእረሳችው ሰፈር ያለውን ሚዛን ማስተካከል ያስፈልጋል፡፡
ለነገሩ ኢህአዴግ ሚዛኑ በትክክል እንዲሰራ ስለማያፍለግ በተመቸው ጊዜ ሁሉ እራሱን ከራሱ ጋር እያነፃፀረ መቶ ለማግኘት የሚጥረው፡፡ የኢህአዴግ መንግሰት በእነዚህ ታዳጊ ክልሎች እሰከ 2000 ዓ.ም ድረስ ምንም ስለ አልሰራ (የክልሉም የፌዴራሉም) ማወዳደር የሚፈልጉት ከ1983 ጋር ነው፡፡ ደርግ በስልጣን ላይ የቆየው ለአሰራ ሰባት ዓመት ነው፡፡ ኢህአዴግም በስልጣን እስከ 2000 ድረስ ያለው ሲቆጠር አሰራ ሰባት ነው፡፡ ስለዚህ ከደርግ ጋር እራሱን ማወዳደር ነውር ነው፡፡ ደርግም ሆነ ንጉሱ በሱማሌ ክልል ያላቸው ወታደር በምንም መለኪያ አሁን ኢህአድግ ካለው ጋር ተመጣጣኝ አይደለም፡፡ ተጨፈኑ ላሞኛችሁ ልንባል አይገባም፡፡ ለዚህ ነው ሚዛኑ ይስተካከል፤ ውድድሩ ከዜሮ ጋር አይሁን የምንለው፡፡
ለኢህአዴግ መንደር ምስረታ ዳገት የሆነበት እንደሚለው ተቃዋሚዎች እና አክራሪ ኒዎሊብራሎች ስለ አስቸገሩት ሳይሆን በትግል ጊዜ መንደር ምሰረታን አሰመልክቶ ይሰራው የነበረው አሉታዊ ቅስቀሳ ነው፡፡ አሁንም ቢሆን ውሃ፣ መብራት እና ሌሎች መሰረተ ልማቶች ከተሟሉ ለማሰባሰብ ችግር ፈጣሪ አይኖርም፣ ቢኖርም እዚህ ግባ የሚባል አይደለም፡፡ ነገር ግን እነዚህ መሰረታዊ ነገሮች ባልተሟሉበት ዜጎቸን ስትሰባሰቡ ይሟላል ማለት አስቸጋሪ ፈተና ነው፡፡ ከተሰባሰቡ በኋላም ተመልሰው የሚሄዱት ለዚህ መሆኑ መረዳት ጥሩ ነው፡፡
አቶ አዲሱ ከጡረታ በኋላ ቆለኛ የሆኑ ይመስላሉ መቼም እንደ እርሳቸው ብረት ይዘን ዱር ገደል ባንልም ይህችን ሀገር ግን ብዕርና ወረቀት ይዘን ከሳቸው በላይ እንደምናውቀው እድሉ በተገኘ እና በነገርናቸው ጥሩ ነበር፡፡ በነገራችን ላይ በሱማሌ ክልልም ቢሆን እሳቸው በኮንቮይ ስለሚሄዱ እንጂ ጅጅጋ መግባት እንኳን ክልክል ነበር ባለፈው ሰሞን፡፡ ደርግ እኮ ጎዴ ሆኖ ነበር ክልሉን የሚያስተዳድር፤ እረ ጎበዝ ጅጅጋ ሆኖ ይህ ሁሉ ፉከራ አያስፈልግም፡፡ በዚህ ጉዳይ ማለት የምፈልገው የአቶ አዲሱ “ለነገሩ ማን ሄዶ አይቶዋቸው?” ምፀት አውነት ወይም ውሸት መሆኑ ለማጣራት ይህን ፅሁፍ ድንገት ካነበቡት በኋላ በቦርድ በሚመሩት ክልል የስራ ጉብኝት ለማድረግ ዝግጁ ስለሆንኩ እባክሆትን ሁኔታዎችን ያመቻቹልን፡፡ እንደ አርቲስቶቹ … በእርግጥ እኛ እንደ አርቲስቶቹ እናንተ የምትፈልጉትን ብቻ ሳይሆን ያየነውን የሰማነውን በሙሉ ነው የምንናገረው፡፡ ምክንያቱም እኛ ነፃ … ነፃ ዜጎች ነን፡፡
ባለፈው በጅጅጋ የብሔር ብሐረሰቦች ዕለት ማስታወሻዬ አቶ አዲሱ ለምን …. እንደሚሉ በግርምት አካፍያችሁ ነበር፡፡ አሁንም በምክር ቤት ቀርበው “አብዛኛው ሰው ሱማሌ ክልል ነዳጅ ብቻ የሚገኝበት ነው ሲል ነው የምሰማው፡፡ የክልሉ የግብርና መሬት ግን እጅግ ከፍተኛ መሆኑን አይረዳም” ብለዋል፡፡ አቶ አዲሱ ለገሠ ሱማሌ ክልልን አስመልክቶ የሚያናግሯቸው ሰዎችና አስተያየት የሚስጡዋቸው ግለሰቦች ችግር እንዳለባቸው መረዳት አያስቸግርም፡፡ እርሳቸውም ቢሆን ከዚህ ዓይነት አሰተያየት ሰጪዎች መራቅ አለባቸው፡፡ የመረጡት እራሳቸው ከሆኑም የምርጫ ስሕተት ፈፅመዋል ማለት ነው፡፡ እኔ የማውቃቸው ሰዎች ከዋቢ ሸበሌ ጋር  ተያይዞ ያለውን መሬት የማልማት አቅም በከርሰ ምድር ያለውን ዕምቅ ሀብት ነው፡፡ በተሳሳተ አስተያየት ሰጪ ወይም የግል የተሳሳተ ምልከታን የብዙዎች ማድረግ ተገቢ አይደለም፡፡ የሱማሌ ገበሬ እንዳለም እርሶ ከበረሃ ሳይመጡ እናውቃለን፡፡ ነገር ግን ብዙ አይደሉም አብዛኛው አርብቶ አደር ነው፡፡ ይህችም እውቀት ነች ብሎ ፌዝ ተገቢ አይመስለኝም፡፡ ነዳጅም ሆነ የእርሻ መሬት ክልሉን የምንፈልገው ለሀብት ሲባል አይደለም፡፡ ደረቅ ምድረ በዳም ቢሆን የኢትዮጵያ አካል ነው እያልን ነው፡፡ እዚህ ጋ የዶክተር በድሉ ዋቅጅራን “ሀገር ማለት ልጄ” የሚለውን ግጥም መጋበዝ ተገቢ ይመስለኛል፡፡
በመጨረሻ እሰኪ አሁን ታዳጊ ተብሎ ድጋፍ ከሚደረግላቸው ክልሎች ሰማቸው የማይታወቅ የነበረው ሱማሌ፣ ጋምቤላ፣ ጉሙዝ፣ አፋር የትኛው ነው? እረ እየተሰተዋለ ይሁን፡፡ የአፋርኛ እና የሱማልኛ ሬዲዮ ፕሮግራም እንደነበረ ማስታወስ ይኖርብን ይሆን?
መልካ በዓል አመሰግናለሁ!!!!!




No comments:

Post a Comment