Thursday, January 23, 2014

ዲታ መንግሰትና ምስኪን ህዝብ



የ “አባት ቤት ሲዘረፍ አብረህ ዝረፍ” የሚባል አባባል አለ፡፡ ይህን አባባል ሰረዳው ዘራፊዎችን ማስቆም ካልቻልክ በዘረፋወ በመሳተፍ የድርሻህን ማንሳት ችግር የለውም የሚል እንደምታ እንዳለው ነው፡፡ ከዚህ በመነሳት ይመስለኛል በአብዛኛው የመንግሰት በሚባለው ንብረት ላይ በዘረፋ ላይ የተሰማሩ ሰዎች ድርሻቸውን እንደወሰዱ እየተሰማቻው ይህን በማድረጋቸው አንድም ቅሬታ አይታይባቸውም፡፡ ይልቁንም የጀግንነት ሰሜታቸው ሀይሎ ይህን ዘረፋ የሚጠየፉትን እንደ ጅል መቁጠር እየተለመደ መጥቶዋል፡፡ በዘረፋው ላይ ያልተሳተፉም ቢሆኑ ይህ የመንግሰት የሚባለው ንብረት ሲዘረፍ ከመመልከት ዘለው ለምን አይሉም፡፡ አንድ አንዶች ደግሞ በመዝረፍ ባይሳተፉም በማዘረፍ እየተሳተፉ ይገኛሉ፡፡ የአዲስ አበባ መንገዶች ባለስልጣን ለመዝረፍም ለማዘረፍም ጥሩ ማሳያ ነው ብዬ ነው የማምነው፡፡
የአዲሰ አበባ መንገዶች ባለስልጣን አሰርቶት ከአገልግሎት ውጭ ሆኖ የነበረው ከመሰቀል አደባባይ ቃሊት ያለው መስመር አሰፋልቱ እየፈረሰ ሰፊ ጉድጓድ እየተማሰ አደሲ ቁፋሮ እየተካሄደ ሰመለከት ከባከነው ገንዘብ ይልቅ ያብከነከነኝ ተጠያቂነትን እንዲያረጋግጡ፣ ካልቻሉም እራሳቸው የሚጠየቁት ጠቅላይ ሚኒስትራችን የሰጡት ማብራሪያ ትውስ ብሎኝ ለምን መዋሸት ያስፈልጋል ብዬ ጉዳዩን ማንሳት ወደድኩ፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትሩ በመዝረፍ ተሳትፈዋል ለማለት መረጃም ማስረጃም የሌለኝ ቢሆንም ሲዘረፍ ዝም ብሎ በመመልከት እና ሲከፋም ለማዘረፍ ከለላ እየሰጡ መሆናቸው ግን የአደባባይ ሚስጥር ነው፡፡
ከመስቀል አደባባይ ቃሊቲ ድረስ ያለው መንገድ አንድ ዓመት እንኳን ሳያገለግል በመንገዱ አሰፋልት መሆን ምክንያት የተማሪዎችን ህይወት መቅጠፍ ሳይበቃው ይህን ሊከላከል ይችላል የተባለ የብረት አጥር ግንባትን ጨምሮ ከፍተኛ ገንዘብ ከንቱ ቀርቶዋል፡፡ በዚህ ጉዳይ ዋነኛ ተጠያቂ መሆን ያለበት የአዲስ አበባ መንገዶች ባለስልጣን ሲሆን፤ የባለስልጣኑ መስሪያ ቤት ሃላፊ ጉዳዩን፤ የባቡር መስመሩ ድንገት በመምጣቱ ነው የሚል አስተያየት መስጠት ዕቅድ አልባ መንግስት መሆኑን ማሳያ ነው፡፡ ይህ በሚመለከት ሃሳቡን ያጋራኝ በመንገድ ዘርፉ ኃላፊ የሆነ ሰው የነገረኝ ደግሞ፤ በባቡር ኮርፖሬሽን ቦርድ ውስጥ የአዲስ አበባ መንገዶች መስሪያ ቤት ኃላፊ ያሉበት መሆኑን አስተያየታቸውን አሰገራሚ ያደርገዋል ነው ያለኝ፡፡ ይህ ብቻ አይደለም ኃላፊው ባቡር መስመሩ መንገዱን ሊጠቀምበት ይችላል የሚል ግምት ነበር ብለዋል፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትራችንም የዚህ ሰበብ አውቀው ይሁን ሳያውቁ ሰለባ የሆኑ ይመስለኛል፡፡ በዚህ ጉዳይ ላይ ማስተባበያ በሰጡበት ወቅት ባለ ሞያ መሐንዲስ መሆናቸውን ጠቅሰው ከላይ ያለው አሰፋልት ብቻ ስለሚነሳ ከሰር ያለው ሙሊት ስራ ላይ ይውላል በዚህ የተነሳ ብክነቱ ዝቅተኛ ነው ብለው ለኢትዮጵያ ህዝብ ገልፀው ነበር፡፡ የነበራቸው መረጃ ይህ ከሆነ አሁን እያየን ያለው ጠቅላይ ሚኒስትሩ እንዳሉት ሳይሆን እንደ አዲስ ተቆፍሮ ሌላ እየተሞላ ነው፡፡ አሁንም ጉዳዩ ቀላል ነው ሊሉን አይችልም፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትራችን ዋሽተውናል፤ አልዋሸውም የሚሉ ከሆነ ደግሞ በሹሞቻቸው ተታለዋል፡፡ ሰለዚህ የተሳሳተ መረጃ የሰጧቸውን ይጠይቁልን ወይም እራሳቸው ኃላፊነቱን ይውሰዱ፡፡ ይህ የጠቅላይ ሚኒሰትሩ አሰተያየት የህዝብ ሀብት ብክነት ሲነገራቸው እርምጃ ከመውሰድ ይልቅ ከለላ መስጠታቸው ተባባሪነታቸውን ነው የሚያሳየው፡፡ አሁንም አሰቸኳይ እርምጃ እንዲወስዱልን እንጠይቃለን፡፡
በቅርቡ ደግሞ ከፍተኛ ወጪ የተደረገበት ግንባታ ከተከናወነ በኋላ መፍረሱን አስመልክቶ መስሪያ ቤቱ ኃፊዎች የሰጡት አሰተያየት አሁንም ያስገርማል፡፡ ዲዛይን ለውጥ በመደረጉ የተነሳ ግንባታው መፍረሱን አረጋግጠው፤ እንደዚያም ቢሆን ወጪው የሚመለከተው ግንባታውን የሚያከናውነው የቻይና ድርጅት ነው፡፡ ለዚህም ምክንያቱ ኮንትራቱ ሰሰጥ ዲዛይንም ግንባታንም የሚጨምር የኮንትራት ዓይነት ስለሆነ ነው ብለውናል፡፡ እንዲህ ከሆነ ደግሞ ይህ ኮንትራት የተሰጠበት ዋጋ እንደፈለጉ አባክነውም ቢሆን አትራፊ ያደርጋቸዋል የሚል እንደምታ በጆሮዋችን ያቃጭላል፡፡ ድሮም ቢሆን ገንዘብ ይዞ መጥቶ ዲዛይንም ግንባታም ለመስራት የሚገባበት ውል ሰላማዊ እንደማይሆን ልባችን ያውቀዋል፡፡ ለማነኛውም ይህ የባቡር ፕሮጀክት ተጠናቆ ሰራ ሲጀምር ወጪውን በግራም በቀኝ አሰበን በወቅቱ ካለው ዋጋ አንፃር ማየታችን የግድ የሚል ነው፡፡ ከዚህ አንፃር ዋነኛ ዘራፊው የቻይና መንግሰት ሲሆን አዘራፊው ደግሞ የብድር ስምምነት የገባው የፌዴራል መንግሰትና የባቡር ኮርፖሬሽን ነው፡፡ የእነዚህ አካላት ሀለቃ ደግሞ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ናቸው፡፡
ከመንገድ ጋር በተያያዘ የማንረሳቸው በባቡር ግንባታ ስም የህዝብን ሃብት ያባከኑት ከሾላ ገበያ፣ በለም ሆቴል ወደ ቀለበት መንገድ ማቋረጫ መንገድ፤ በደሳለኝ ሆቴል ሳርቤት የሚወስዱት መንገዶች አገልግሎት ሳይሰጡ መፍረሳቸው የአዲስ አበባ መንገዶች ባለስልጣን ሃላፊዎችን እንቅልፍ ይሰጣቸው እንደሆነ ማወቅ ያስፈልጋል፡፡ ምን ችግር አለው ለዘመናዊ ባቡር ሲባል ነው ብለው በሚዲያ የሚሰጡት መልስ ውሃ የሚቋጥር አይሆንም፡፡ አሁንም በድፍረት ሚዲያ እየወጡ ይህን መልስ የሚሰጡ ሰዎች ትዝብት ላይ ከመውደቅ ባለፈ ይህ ሰበብ ግብር ከፋዩን ዜጋ እንደማያሳምነው መረዳት ይኖርባቸዋል፡፡ ይህን የሚዲያ ዘማቻ አሁንም አላቆሙም፤ ልብ ማለት ግን የተሳናቸው ይመስለኛል፡፡
በከተማችን በከፍተኛ ወጪ እየተገነቡ ያሉት የትራፊክ መብራቶች ለመፍረስ አንድ ወር ሲቀረው የሚሰሩ መሆናቸው የዚህ መብራት ባለቤት ማን ነው? የሚል ጥያቄ ያስነሳል:: የመንገድ ማካፈያዎች፣ አደባባዮች የሚሰሩት በጥቃቅን በተደራጁ ይሁን በኮንትራክተር መፍረሳቸው እየታወቀ የሚገነቡበት ምክንያት ግራ የሚያጋባ ነው፡፡ የጥላሁን ገሠሠ አደባባይ የሚባለው የተጠናቀቀው እንደሚፈርስ ታውቆ ሌሎች መንገዶች መፍረስ ከጀመሩ በኋላ ነው፡፡ ይህን ተግባር ለማከናወን ውል ተገብቶ እንኳን ቢሆን ገንብቶ ከማፍረስ ተደራድሮ ሀብት እንዳይባክን ማድረጊያ “አስገዳጅ ሆኔታዎች” የሚል የውል አንቀፅ  እንዳለ ይታወቃል፡፡ ይህ የኮንትራት አስተዳደር ሀሁ ነው፡፡ በግርግር የሚባክነው ግን ከፍተኛ የሆነ የህዝብ ሀብት መሆኑ ተዘንግቷል፡፡ ህዝብና መንግሰት የተለያዩበት ሀገር የመንግሰት ሀብት የሚባለውን መዝረፍ ለፅድቅ እንደሚደረግ ተግባር ይወሰዳል፡፡
 በነገራችን ላይ በመርዕ ደረጃ የመንግሰት የሚባል ነገር የለም፡፡ መንግሰት ህዝብ በመወከል ለህዝብ የጋራ ጥቅም የሚውል የጋራ የሚባሉ ንብረቶች ሊኖሩት ይችላሉ፡፡ ከዚህ ጋር ተሰማሚ የሆነው የህገ መንግሰት አንቀፅ 89፡3 “መንግሰት መሬትንና የተፈጥሮ ሀብትን በህዝብ ስም በይዞታው ስር በማድረግ ለሕዝብ የጋራ ጥቅምና እድገት እንዲውሉ የማድረግ ኃላፊነት አለበት፡፡” ይላል፡፡ በተቃራኒ ደግሞ የሚቆመው አንቀፅ 40፡3 “የገጠርም ሆነ የከተማ መሬትና የተፈጥሮ ሀብት ባለቤትነት መብት የመንግስትና የህዝብ ብቻ ነው”  በማለት መንግሰት እራሱን ከህዝብ የተለየ ሌላ አካል አድርጎ ያስቀምጣል፡፡ አሁን በተግባር ያለውም የመንግሰት ባለቤትነት እንጂ የህዝብ ባለቤትነት አይደለም፡፡ ለመንግሰት ንብረት ዜጎች የማይቆረቆሩት የመንግሰት የሆነ የእነርሱ ባለመሆኑ ነው፡፡ የእኛ መንግሰት ከህዝብ ይበልጣል፤ ለዜጎች የሚያስፈልገውን እየነፈገ ለራሱ ጡንቻ ማደበሪያ የሚሆነውን ሀብት፣ ንብረት ያፈራል፡፡ በዚህም ህዝብን ይጨቁናል፡፡ ይህም ሆኖ የመንግሰት የሆነ የማንም ስለአልሆነ ቀዳዳ ያገኘ ሁሉ ይዘርፋል ያዘርፋል፡፡
አሁን እዚህም እዚያም የሚባክነው ገንዘብ በእኔ እምነት የህዝብ ንብረት ነው፡፡ መንግሰትም በህዝብ ስም የማስተዳደር ስራ እንዲሰራ የተቀመጠ እንጂ ንብረት እንዲያፈራ የተቀመጠ አካል አይደልም፡፡ የህዝብን ንብረት ሲያስተዳድር የሚያባክን ደግሞ ሃላፊነቱን በአግባቡ ባለመወጣቱ ምንም ዓይነት ሰብብ ሳያቀርብ ቦታውን መልቀቅ ይኖርበታል፡፡ እንቢ ካለም ባለቤት የሆነው ህዝብ ማስለቀቅ ይኖርበታል፡፡ ምን ያደርጋል ህዝቡ ይህ የሚሰራው ስራ በገንዘቡ ወይም በስሙ ልጆቹና የልጅ ልጆች በሚከፍሉት ዕዳ መሆኑን እንዲዘነጋ እና መንግሰት በቸርነት የሚሰራው እስኪመስል ድረስ የተሳሳተ ፕሮፓጋንዳ ሰለባ እየሆነ ነው፡፡ የዚህ ፕሮፓጋንዳ ዓላማ አንድና አንድ ነው፡፡ መንግስትን ከተጠያቂነት ማሽሽ፤ ንብረት ሲያባክንም የራሱን ንብረት እንዳባከነ እንዲቆጠር ማድረግ፡፡ ከተቻለም የመንግሰት ንብረት መዝረፍ ነውር እንዳልሆነ ማስጨበጥ ናቸው፡፡
ልብ በሉ የባቡር መስመር፣ የመንገድ. የቴሌ፣ የመብራት መሰረተ ልማቶች የሚገነባልን ዲታ መንግሰት ነው ያለን፡፡ መንግሰት ቸርነቱ የበዛ፣  እንዲሁም ደግ ሲሆን መንግሰት ለህዝቦቹ የሚያስብ አንድ አካል ነው፡፡ ህዝብ ደግሞ  እነዚህ ሁሉ የመሰረተ ልማቶች የሚያስፈልጉት ምሰኪን ከመንግሰት እጅ የሚጠብቅ፡፡ የሚገርም ነው!!  የገዛ ንዘቡን እና ንብረቱን እንዲያስተዳድር የተቀመጠ አካል አዛዥ ናዛዥ ሲሆን፤ ባለ ገንዘቡ ደግሞ ምስኪን ተመፅዋች የሚኮንበት ጥቂት ሀገሮች ካሉ አንዷ ምስኪኗ ኢትዮጵያና ህዝቦቿ ናቸው፡፡
ቸር ይግጠመን!!!!

No comments:

Post a Comment