Sunday, February 9, 2014

የነሌንጮ ምልሠት ፖለቲካዊ እንድምታዎች




ግርማ ሠይፉ ማሩ
ሰሞኑን የፖለቲካ እውቀትና ይህንኑ የማከናወን ክዕሎታችንን የሚፈትኑ ብዙ ነገሮች ብቅ ብቅ ማለት ጀምረዋል፡፡ ከነዚህ ውስጥ አንዱ የሆነው የኦቶ ሌንጮ ለታ ወደሀገር ቤት የመመለስ ዜና ነው፡፡ ፋክት መፅሔት አቶ ሌንጮ ለታም እንዲመጡ፤ በእሳቸው እና ሌሎች የኦነግ አመራሮች ጦስ በሀገር ውስጥ ለእስር የተዳረጉትም ይፈቱ የሚል መልዕክት አስተላልፋ ነበር፡፡ እዚህ ጋ ልብ ማለት ያለብን የኦነግ ታፔላ ተለጥፎላቸው እስር ቤት የገቡት ሁሉ የኦነግ ደጋፊና ተላላኪ ነበሩ ማለት በፍፁም እንዳልሆነ ሊሰመርበት ይገባል፡፡ ሌላ እርግጠኛ መሆን የሚቻለው ግን ኦነግን በመንፈስ የሚደግፉ መኖራቸውን ጭምር ነው፡፡ ይህ ግን በምንም ዓይነት በእስር ለመማቀቅ በቂ ምክንያት ሊሆን አይችልም፤ ወንጀል የሚባል ውጤት እስካላመጣ ድረስ፡፡ በተጨማሪ ግልፅ መሆን ያለበት ዋና ነጥብ ደግሞ ምንም ዓይነት ምርጥ የፖለቲካ ስርዓት ለመመስረት ይሁን ለውጥ ለማምጣት በሚል ሰበብ፤ ስላማዊ ዜጎችን እይወት ለመቅጠፍ የሚደረግ ሙከራም ሆነ የተፈፀመ ተግባር ወንጀል ብቻ ሳይሆን ተቀባይነት የሌለው አርመኔያዊ ድርጊት እንደሆነ ነው፡፡
የአቶ ሌንጮ ለታ ወደ አዲሰ አበባ መምጣት በብዙ መልኩ በጎ ነው የሚል እምነት አለኝ፡፡ አመጣጣቸው ግን የድሮውን የኦነግን ተረት ሊተርቱልን ከሆነ ግን ተቀባይነት የለውም፡፡ የኦነግ ታሪክ የሚያስፈልገን በመፅሀፍ መልክ ተጠርዞ ለታሪክ ምርምር መሆን አለበት፡፡ ለዚህም አቶ ሌንጮ ብቃቱ እንደሚኖራቸው አልጠራጠርም፡፡ አቶ ሌንጮ ለታ የኦሮሞ ህዝብ ቸግር በመገንጠል ሳይሆን በኢትዮጵያዊነት ጥላ ሰር ሊፈታ ይችላል በሚል እምነት  ወደ ሀገር ቤት ለመምጣት ሲወስኑ በወህኒ ቤት በኦነግ ሰም የታጎሩትን ዘንግተው ከሆነ በቅርቡ ከኦብነግ ተገንጥለው ወደ ሀገር ውስጥ በገቡ አመራሮች እንደተበለጡ መረዳት ይኖርባቸዋል፡፡ አቶ ሌንጮ ለታ በኢህአዴግ ሰዎች አይሞኙም ለማለት ውጤቱን መጠበቅ የግድ ይላል፡፡ የማንረሳው ግን ኢትዮጵያን የምታህል ትልቅ ሀገር እንዲመሩ አቶ ሌንጮ በዕጩነት በአቶ መለስ ዜናዊ ሲጠቆሙ እንቢ ማለታቸው ግን የአደባባይ ሚስጥር ነው፡፡ የዛን ዕለት በአቶ መለስ የፖለቲካ ጫወታ እንደተበለጡ ይረዱታል ብዬ አምናለሁ፡፡
ሰለ ኢትዮጵያና የህወሃት ፖለቲካ ሲነሳ አንድ ልብ ማለት ያለብን ነገር ህወሃት የትግራይ ነፃ አውጪ ድርጅት የሚለውን ስም ባለመቀየሩ አሁንም የትግራይ ሪፐብሊክ የመመስረት እቅድ እንዳለው የሚያስቡ ብዙ ሰዎች አሉ፡፡ ይህ አስተሳሰብ ስህተት ነው ብዬ አምናለሁ፡፡ በተለይ ይህ ስህተት በሀገር ውስጥ ሳይሆን በውጭ በሚኖሩ ኢትዮጵያዊያን ዘንድ ነብስ ዘርቶ ይገኛል፡፡ በምድር ላይ ያለው እውነተኛ ሀቅ ግን ከዚህ የተለየ ነው፡፡ ህወሃት ኢህአዴግ የሚባለውን ግንባርና ሌሎች አጋር ፓርቲዎችን ከሰሜን እሰከ ደቡብ፤ ከምዕራብ እሰከ ምስራቅ በመመስረት ያጠፋውና በማጥፋት ላይ ያለው ሀይል የህወሃት መሪዎችን ለበለጠ ጥቅም የሚያበቃቸው በምኒሊክ ኢትዮጵያ በሚሏት ስር እንጂ በትግራይ ሪፐብሊክ ውስጥ እንዳልሆነ በደንብ የተረዱ መሆናቸው ነው፡፡ ለዚህ ነው ህውሃት ኦነግንም ሆነ ኦብነግን ከተቻለ በፀባይ ካልተቻለ ምትክ በማበጀትና በጉልበት የማዳከም ስልት የሚከተለው፡፡ አቶ ሌንጮ ለታ እና ድርጅታቸው ኦነግ በሽግግር ወቅት የቀረበላቸውን እጅ መንሻ በብልዓት ይዘው አሁን የያዙትን አቋም ቢይዙ አንድ ጠንካራ ተገዳዳሪ ፓርቲ ሊሆን ይችሉ ነበር፡፡ ለኦነግ ወይም አሁን በአቶ ሌንጮ ለታ ለሚመሩት ኦሮሞ ዲሞክረሲያዊ ግንባር/ኦዴግ  እንደ ሽግግር ጊዜው በቀላሉ አማላይ የሆነ እጅ መንሻ የሚገኝ አይመስለኝም፡፡ በሸግግር ጊዜው ኦነግ የህወሃትን “የሚንሊክ ኢትዮጵያን” በጋራ እንግዛ ጥያቄን ቢቀበል፤ ኦህዴድን ለመሰዋትነት ለማቅረብ ብዙ አይቸገርም ነበር፡፡ አሁን ግን ኦህዴድ በፈራረሰ ኦነግ የሚለወጥ ድርጅት ነው ብሎ መገመት የፖለቲካ ቂልነት ይመስለኛል፡፡ አቶ መለስ በሌሉበት ደግሞ በኦህዴድ ቤት እንደፈለገ የሚያዝ ህውሃት ወይም ኢህአዴግ ይኖራል የሚል እምነት የለኝም፡፡ የኦህዴድ መሪዎች አሁን ብዙ ለምደዋል፤ መሬት ይዘዋል፡፡
ለኦህዴድ የእነ ሌንጮ ለታ በፈለጉት መንገድ መምጣት፣ በሀገር ውስጥ መገኘት እና በኦሮሞ ህዝብ ውስጥ እንቅሰቃሴ መጀመር የአብዮታዊ ዲሞክራሲ የመድበለ ፓርቲን አተገባበር ለመተግበር እንደመስታወት ወይም ላንቲካ ከማገልገል አልፎ የፖለቲካ ሚዛን ለውጥ እንደማያመጣ የተረዱት ይመስለኛል፡፡ ከሁሉም በላይ የኦህዴድን ትክክለኛነት ማረጋገጫ ማሕትም አድርገው የሚጠቀሙበትም ይኖራሉ፡፡ ኦህዴዶች ጥንቃቄ ካላደረጉና የኦሮሞን ህዝብ ጨዋነት ካልተጠቀሙ እነ ሌንጮ ለታን ከዚህ ቀደም በኦነግ ሰም ተፈፀሙ ለሚባሉ ጥፋቶች ሁሉ የኢቲቪ የዶክመንተሪ መስሪያ ግብዓት እንደማያደርጉዋቸው እርግጠኛ መሆን አይቻልም፡፡ ለዚህ ተግባር ሲባል በእስር ላይ ያሉትንም በመልቀቅ ጭምር ሊጠቀሙባቸው ይችላሉ የሚል ጥርጣሬ አለኝ፡፡ ይህን ዓይነት ስህተት ከመስራት ኦህአዴድ/ኢህአዴግን ፈጣሪ እንዲጠብቀው እኛም ጭምር መፀለይ ይኖርብናል፡፡ ዋናው ምክንያት የዚህ ዓይነት ተግባር በሀገራችን ሀገራዊ መግባባት ልንፈጥር የምንችልበትን የመተማመን መንገድ ይዘጋዋል የሚል እምነት ስለአለኝ ነው፡፡ አቶ ሌንጮም ቀደም ብለው በዚህ መስመር ፋውል ካልሰሩ ይህን ፅሁፍ ከታናሽ ወንድም እንደተላከ መልዕክት ሊወስዱት ይችላሉ፡፡ ኢህአዴግ እንደ ፖሊሲ ይህን አያደርግም አይባልም፡፡ በቅርቡ አቶ ሬድዋን ሁሴን በምክር ቤት ቀርበው የዶክምንተሪ ስትራቴጂ ልክ ነው የሚቀጥል ይሆናል ማለታቸውን ስናስብ የአቶ ሌንጮ ለታ ምርጥ የዶክመንተሪ መነሻ ኃሳብ ተደርጎ ሊወሰድ ይችላል፡፡ ከዚህ አንፃር በኦህዴድ/ኢህአዴግም ሆነ በኦዴግ/ኦነግ ሰፈር የፖለቲካ ክዕሎታቸው የሚፈተንበት ይሆናል፡፡
ሌሎች  በሀገር ውስጥ የሚገኙ ተቃዋሚ ፓርቲዎችም ቢሆን ከፈተና የፀዱ ሊሆኑ አይችሉም፡፡ አንዳንዶቹ የኦዴግ አመራሮች በእነሱ መስመር እንዲሰለፉ ሲጠብቁ ሌሎቹ ደግሞ ቀደም ሲል ኦነግ ሰራው የሚባለውን ሰህተት በመንቀስ የራስን አቋም ትክክለኛነት ማሳያ መስታወት ማድረግ ሊፈልጉ ይችላሉ፡፡ ይህ የሚጠቅመው ገዢውን ፓርቲ ኢህአዴግ/ኦህዴድ ከመሆን ዘሎ በኦሮሚያ ምድር ላይ ለሚደረግ ፖለቲካ ውሃ የሚቋጥር ነገር አያመጣም፡፡ በሀገር ውስጥ ያሉ ፓርቲዎች በዋነኝነት ማድረግ ያለባቸው ኦዴግ ወደ ሀገር ውስጥ ሲገባ ከኢህአዴግ ጋር የፖለቲካ ምዕዳሩ እንዲሰፋ ያደረገው ተሰፋ ሰጪ ድርድር ካለ፤ ውሻ በቀደደው ጅብ ይገባል እንደሚባለው ሊጠቀሙበት የሚችሉበትን መንገድ ማሰብ ነው፡፡ ኦዴግ ትግሉ ወደ ሀገር ውስጥ ማስገባት ስትራቴጂ ሲቀበል አንዱ ቅድመ ሁኔታ በሀገር ውስጥ በምርጫ ቦርድ ምዝገባ ማድረግ አንዱ ሲሆን ሌላው ግን የፖለቲካ ፓርቲዎች ምክክር መድረክ አባል ለመሆን የምርጫ ስነ ምግባር ደንብ (ትክክለኛው የፖለቲካ ፓርቲዎች የምርጫ ሰነ ምግባር አዋጅ ነው) መፈረም የሚሉት ሊሆኑ ይችላሉ፡፡ የአቶ ሌንጮ ለታ ፓረቲ ኦዴግ የምርጫ ሰነምግባር ደንቡን ከፈረመ ኢህአዴግ በሀገር ውስጥ ያሉትን ፓርቲዎች በማግለል በውጭ ሆነው ከሚያስፈራሩት ጋር ለሚያደርገው ድርድር ሽፋን እንደሰጠ ነው የሚቆጠረው፡፡ ይህ ደግሞ ኦዴግን በተቃዋሚነት እና አማራጫ ያለው የኦሮሞ ህዝብን የሚወክል ፓርቲነት ሳይሆን በኦህዴድ ሀጋርነት ለመሰለፍ እንደመጣ ተደርጎ እንዲወሰድ ስለሚያደርገው ፈተናውን ያከብድበታል፡፡ ከዚህ አንፃር ተቃዋሚዎችም የሚስጡት የመልስ ምት ሌላ የፖለቲካ ክዕሎት የሚጠይቅ ሆኖ ይታየኛል፡፡
ለማነኛውም በዓለም ላይ በልዩ ሁኔታ ከምንታወቅባቸው ነገሮች አንዱ የሆነው ኦነግ ሲያራምደው የነበረውን የቅርንጫፎች ጥያቄ መሆን ያለበትን ግንዶች ጠየቁት ሲባል የነበረውን የመገንጠል (የኦሮሚያ ሪፐብሊክ) ጥያቄ የሚያሻሽል እርምጃ በአዎንታዊነት መታየት ያለበት ነው፡፡ ስለዚህ ኢትዮጵያዊያን ዜጎች ኦሮሞ፣ አማራ፣ ጉራጌ፣ ሲዳማ፣ ትግሬ፣ ወዘተ ሰብዓዊ ክብራችንን የሚመጥን ዲሞክራሲያዊ ስርዓት ሲመሰረት የአንድ ቡድን አባል በመሆናችን የደረሰብን የሚመስለን በደልና ግፍ ሁሉ ይወገዳል ወደሚል እየመጣን እንደሆነ ይሰማኛል፡፡ በአንድ ቡድን ላይ ደረሰ የምንለው ግፍና በደል ያልደረሰበት ካላ የገዢው ቡድን አባል በመሆን ነው እንጂ የአንድ ቡድን አባል በመሆኑ ከግፍ አያመልጥም፡፡ ገዢዎቻችን ደግሞ አሁን የአንድ ብሔር ብቻ ናቸው ለማለት የሚያስደፍር አይደለም፡፡ በኦሮሚያ ክልል የሚደርስ በደል በኦሮሚያ ካድሬዎች ነው፡፡ በትግራይ ክልል በቅርቡ በአረና አባላት ላይ የሚደርስ ያለው በደል በትግራይ ካድሬዎች ነው፡፡ የሁሉም ካድሬዎች መመሪያ ቀራጭና አሰማሪ ደግሞ በጋራ የመሰረቱት ግንባር ኢህአዴግ ነው፡፡ ትግላችን የስርዓቱ መሪ የሆነውን ፓርቲ በመቀየር ላይ ማተኮር ይኖርበታል፡፡ እንዴት? የሚለው የፖለቲካ ክዕሎታችን የሚጠየቅበት ሌላኛው ጥያቄ ነው፡፡

Monday, February 3, 2014

የሁለት ሺ ሰባት ምርጫ ወዴት ይመራናል?




ግርማ ሠይፉ ማሩ
girmaseifu32@yahoo.com
በኢህአዴግ መንደር የምርጫ ዘመቻ በይፋ መጀመሩን የሚያሳዩ ምልክቶች መታየት ጀምረዋል፡፡ የምርጫ ቦርድ በገዢው ሰፈር ሁሉ ነገር መጠናቀቁ ጥቅሻ ሲሰጠው እንቅስቃሴ ይጀምራል ተብሎ ይጠበቃል፡፡ የምርጫ ዘመቻው በተቃዋሚ ጎራ እንደምንፈልገው ነፃ፣ ፍትሓዊ እና ሁሉም ተወዳዳሪ እኩል በተዘጋጀ ሜዳ ይሆናል ማለት ከባድ ሊሆን እንደሚችል ከአሁኑ መገመት ለዝግጅት የሚረዳ ይመስለኛ፡፡ ኢህአዴግ ከጅምሩ የመጫወቻ ሜዳውን ብቻ ሳይሆን አጫዋቾችን ሁሉ ተቆጣጥሮ ጨዋታው እንዲጀመር መፈለጉን የሚያሳዩ ምልክቶች መታየት ጀምረዋል፡፡ በዚህ ወቅት የመንግሰት አካላት የሆኑት ህግ አውጭውም ሆነ አሰፈፃሚውም በዚህ ጉዳይ ላይ ተጠምደው ነው የሚገኙት፡፡ እንደ አሰፈላጊነቱም የፍትህ ስርዓቱ ይቀላቀላል ተብሎ ይጠበቃል፡፡ ካለን ልምድ በመነሳት ይህ ከግምት በላይ ነው፡፡
ህግ አውጭው ማለትም ምክር ቤቱ ውስጥ የሚገኙት ሰዎች በምርጫ የሚሰየሙ ስለሆኑ በዋነኝነት ተግተው ለቀጣይ አምስት ዓመት በምክር ቤት በመቆየት የአዲስ አበባ ኑሮን ማጣጣም ይፈልጋሉ፤ ይህን ሀቅ መካድ አይቻለም፡፡ ለዚህ ማሳያ የሚሆነው በኮንዶሚኒየም ስርዓት ውስጥ ቅድሚያ ለማግኘት ብዙ ሙከራዎች ይደረጋሉ፤ በቀጣዩ ካልተመረጡ ወደ መረጣቸው ህዝብ ተመልሰው በሌላ መስክ ለማገልገል ዝግጁ የሆኑት በጣም ጥቂቶች ናቸው፡፡ አስፈፃሚውም ቢሆን በቀጣይ በገዢነት ለመቆየት ቆርጦ የተነሳ ነው የሚመስለው፡፡  ስለዚህ አስፈፃሚው የሚያወጣውን ምርጫ መተግበሪያ እቅድ ነፃ ፍትዊ ይሁን ብሎ የሚከላከል አይኖርም፡፡ ይልቁንም የሚጠበቀው ተባብሮ በቁርጠኝነት መተግበር ነው፡፡ ከዚህ ዘለግ አድርገን ስናስብ ደግሞ አስፈፃሚው የሚያስበው የኢህአዴግ ዕጮዎችን ብቻ ሳይሆን በተቃዋሚ ጎራ ማን? እንዴት? መወዳደር እንዳለበት ሁሉ የመወስን ፍላጎት አላቸው፡፡ ለዚህ ጉዳይ ፓርቲዎችን አብዮታዊ ዲሞክራሲያዊ የሆኑ በአሁኑ አጠራር ልማታዊና ዲሞክራሲ አመለካከት ያላቸው፤ ከዚህ ውጭ ኒዎ ሊብራል ቢሆንም በኢህአዴግ እይታ ፅንፈኛ አይደሉም የሚባሉት ብቻ ቢወዳደሩ እና ለአበዳሪዎቻቸው እና ዕርዳታ ሰጪዎች ማስመሰያ ቢሆኑ ደስ ይላቸዋል፡፡ የመድበለ ፓርቲ ስርዓት አለ እንዲባል ይህ ቻይናን እና መሰሎቿን አይጨምርም፡፡ በዚህ ጉዳይ ኢህአዴግ ማፈር ትቶዋል፡፡ ኢህአዴግ አውራ ፓርቲ የሆነው ተቃዋሚዎች ሰራቸውን ስለማይስሩ ነው ብሎ ማውራትና ማስወራት ጀምሮዋል፡፡ ተገደን ነው ውስኪ የለመድነው አሉ የደርግ ባለስልጣናት ይባል ነበር፡፡ ኢህዴግም ተገዶ አውራ ፓርቲ ሆኖዋል፡፡ አንግዲህ በዚህ ዓይነት ድባብ ውስጥ ነው የሁለት ሺ ሁለት ምርጫ የሚካሄደው፡፡ ምርጫ መወዳደር ካለብን ይህን ሁሉ ተረድተን ነው፡፡ ምን እናድርግ? ብለን ማስብ የሚኖርብን ይመስለኛል፡፡
በኢህአዴግ በኩል ለምርጫ ዘመቻ በእቅድ የተያዙት ዋና ዋና ተግባራት ይህችን ሀገር ሊመሩ ይችላሉ የሚባሉ ምርጥ ምርጥ ካቢኔ እና የምክር ቤት አባላትን በማቅረብና በይፋ በማስገምገም አይደለም፡፡ እንደ አለመታደል ሆኖ ይህችን ሀገር በቁንጮነት የሚመራትን ሰው ለመምረጥ ዕድል የለንም አንድ ወረዳ የመረጠልንን ሀገር እንዲመራ ከመጋረጃ ጀርባ በሚዶልቱ ሰዎች ዕድል ይሰጠዋል፡፡ በነገራችሁ ላይ ኢህአዴግ ትንንሽ አባላቱን በወረዳ ደረጃ ያስገመግማል፡፡ ኢህአዴግ ምርጫ ማሸነፍ የሚፈልገው በብቃቱ አይደለም፡፡ ይልቁንም ለዚህ ጉዳይ ጉልዕ ሚና ይጫወታሉ ብሎ ያመነባቸውን አካላት በማሸማቀቅ እና አንገት በማስደፋት ነው፡፡ ከዚህ በዘለለም የፓርቲው ያልሆኑ በመንግሰት ኃላፊነት የተከናወኑ ተግባራትን ለምርጫ ዘመቻ በማቅረብ ነው፡፡ እነዚህን በትንሽ በትንሹ መመልከት እንችላለን፡፡
ቀዳሚው ተግባር ተቃዋሚ ፓርቲዎችን በፀረ ሰላም ሀይልነት መፈረጅ ለዚህም “የፀረ ሽብር ህጉን” እንደመሳሪያ በመጠቀም ቅስቀሳዎችን ማድረግ፡፡ ከዚህ በተጨማሪ የተለያዩ የልማት ስራዎችን ከፊት በማስቀደም ተቃዋሚዎችን በፅንፈኝነት መፈረጅ ሲሆን ተቃዋሚዎች ለዚህ ምላሽ መስጠት እንዳይችሉ ሚዲያ መከልከል፡፡ ከተቻለ የተወሰኑ አስተያየቶችን እንዲሰጡ በማድረግ እየቆረጡ ማቅረብ ናቸው፡፡
ለምሳሌ አሽባሪነት በተመለከተ ፓርቲዎች በይፋ የያዙት አቋም እና ፕሮግራማቸው ላይ ያስቀመጡትን ግልፅ አቅጣጫ ወደ ጎን በመተው ኦነግና ኢህአዴግ አብረው ሀገር ሲመሩ የተፈፀሙ ወንጀሎችን በፊልማ በማሳየት የሽብር ስራ ነው በማለት ድራማ እየሰሩ ከዚህ ጋር ምንም ግንኙነት የሌላቸውን ፓርቲዎች የሚወነጅልበት ፕሮፓጋንዳ ይሰራሉ፡፡ እን አንዱዓለምን ከእንዲህ ዓይነት እኩይ ተጋባሮች ጋር በማገናኘት ሌሎች የፓረቲ አመራሮቸን ተጠንቀቁ ማለት አንዱ በመተግበር ላይ ያለ ዕቅድ ነው፡፡ ሲከፋም ህዝቡ መምረጥ የሚገባው የሰላም ሀይል የሆነውን ኢህአዴግን ወይም ፀረ ሰላም የሆኑትን ተቃዋሚዎች ብሎ የተሳሳተ ምርጫ ያቀርባል፡፡ ይህን እውነት ለማስመሰል ሚዲያውን በህገወጥ መንገድ ይጠቀማሉ፣ ሚዲያውም መደበኛ ሰራው አድርጎት እየሰራው ይገኛል፡፡
ለተቃዋሚዎች ኢህአዴግና መንግሰት ተለይተው እንደ ፓርቲ መወዳደር ካልጀመሩ ምርጫ የተወሰኑ ወንበሮች ከማግኘት በዘለለ የስልጣን መያዣ መንገድ መሆኑ እያከተመ ነው፡፡ ይህ ደግሞ የአብዮታዊ ዲሞክራሲ መስመር ነው፡፡ መድበለ ፓርቲ ስርዓት ለገዢው ፓርቲ እንደ መታጠቢያ ቤት መስታውት ፊትን መመልከቻ ሆኖ ማገልግል ነው፡፡ ይህን ዕቅድ ተግባራዊ እንዳያደርጉ ተቃዋሚዎች ከምንግዚውም በላይ ከህዝቡ ጋር በመሆን ማክሸፍ የግድ ይላል፡፡ በቀጣይ ዓመት ምርጫ ኢህአዴግ እንደ ከዚህ ቀደሙ በሙሰሊም ማህበረሰብ ድጋፍ ላይ ስለማይተማመን አሁን በከፍተኛ ደረጃ የክርስትና ሃይማኖት ተከታዮችን ስጋት ውስጥ በመክተት ድምፃቸውን ለኢህአዴግ ድምፅ እንዲሰጡ ማድረግ አንዱ እቅድ ነው፡፡
በሌላ በኩል ኢህአዴግ ለምርጫ የሚጠቀምበት በመንግሰት በጀት የተከናወኑ እና በመከናወን ላይ ያሉ ተግባራትን በመጠቀም ነው፡፡ ለዚህ ጉዳይ የሚነሱት የልማት ስራዎች፤
·        ብዙ ነጥብ ማስቆጠር ባይችልም ኮንዶሚኒየም ቤት ግንባታ፤
·        የስኳር ፋብሪካ ግንባታ (በእድገትና ትራንስፎርሜሽን ከታቀደው 70 በመቶ ይሳካል በሚል)፤
·        የአባይ ግድብና የግብፅ እንቢተኛነት መሰረት በማድረግ፤
·        የጨርቃ ጨርቅ ኢንዱስትሪዎች፤
·        ጥቃቅን እና አነስተኛ ተቋማት (ምንም ያህል ያልተሳካ ቢሆን)፤ ወዘተ
ዋና ዋናዎቹ ናቸው፡፡
ለቀጣይ ምርጫ ሚዲያዎች ሌላው የመስዋዕት በግ ይሆናሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡ ይህ የሚተገበረው ሚዲያዎቹን የፅንፈኞች ልሳን በማለት እና ምንም ዓይነት ዕለታዊ ጋዜጣ እንዳይኖር በማድረግ ነው፤ ካስፈለገም የተወሰኑትን በመዝጋት እና እንዲሰደዱ ምቹ ሁኔታ በመፍጠር ጭጭ ማሰኘት ተግባራዊ ይደረጋል፡፡ በዚህ መስመር ከአድማስና ሪፖርተር ጋር ማዝገም ነው የሚፈቀደው፡፡ እነርሱም ቢሆኑ ወደ መጨረሻው ካልሆነ ቀደም ብለው ጠንከር ያለ ነገር ማድረግ አይጠበቅባቸውም፡፡ እንደ ሪፖርተር “ያሳከከው ፓርላማ ጥርስ ያውጣ” ምክር ግን አይከለከልም፡፡ አሁን በምክር ቤት ውስጥ ያለን የምንረዳው አባላት በቀጣይ ምርጫ ይቀጥሉ አይቀጥሉ በከፍተኛ ውጥረት ላይ ነው የሚገኙት፡፡ አሁን የብዙዎቹ ጭንቅ ዕጩ ሆነው ካልቀረቡ አዲስ አበባ እንዴት እንደሚቀሩ ማሰብ ነው፡፡ በዚህ ጉዳይ ችግር ከሌለባቸው ምርጫ ክልሎች ውስጥ የአቶ መለስ ምርጫ ክልል እና ሌሎች በሞት የተለዩ የምክር ቤት አባላት፣ በወህኒ የሚገኙ፣ እንዲሁም በስደት ከሀገር የወጡት ወንበሮች ናቸው፡፡ እንደው ለነገሩ አቶ አባዱላ አሁን ከያዙት ወንበር ወደ ክልል የሚሄዱ አይመስላችሁም፣ እኔ ግን ዝም ብሎ ይህ ይታየኛል፡፡ እሰኪ ሃሳብ ስጡበት …. ነው ጡረታ ይወጡ ይሆን?
የሲቪል ማህበራትና በጎ አድራጎት ድርጅቶች በአሁኑ ሰዓት ይህ ነው የሚባል ጫና በመንግስት ላይ እያደረጉ አይደለም፡፡ እንደዚያም ሆኖ ግን በፍፁም ዘንግተው ወደ ምርጫ 97 ዓይነት እንቅስቃሴ እንዳይገቡ ማስፈራራያ መሰል መልዕክቶች እየተላለፉ ነው፡፡ እነዚህ ማህበራት ደግሞ በጣት ከሚቆጠሩት በስተቀር ስብሰባ ተጠርተው ሌባ ሲባሉ እንኳን አይደለንም ለማለት ሞራል ያላቸው አይደለሙ፤ ባይሰረቁ እንኳን የእንጀራ ገመዳቸው ወይም የመኖር ዋስተናቸው የተመሰረተበት እንደሆነ መንግሰትን ከሚወክለው ኤጀንሲ ጋር የተዋወቁ ይመስላሉ፡፡ … በዚህ መስመር በአሰሪዎችና ሰራተኞች ፌዴሬሽን፣በወጣትና ሴቶች ሊጎች የመሳሰሉ “ነፃ” ተብዬ ማህበራ ካልሆነ በስተቀር ለመታዘብ እንኳን እንዳያሰቡ መልዕክቱ ቀድሞ እንዲደርሳቸው በመደረግ ላይ ነው፡፡

በሁለት ሺ ሰባት ምርጫ ኢህአዴግ ለመከተል የመረጠው መንገድ በምንም ሁኔታ ስዕተት ባለመስራት የቀድሞ ስትራቴጂስቱም በሌሉበት ምርጫ በዝረራ የሚያሸንፍ ደርጅት እንደሆነ ማሳየት እና የቀጣዩን ዓመት የመውጫ ስትራቴጂ ለማድረግ ይመስላል፡፡ ይህ የመውጫ ስትራቴጂ ግምት በቅንነት እንጂ በፍፁም በመረጃ የተመሰረተ አይደለም፡፡
ስለዚህ አሁንም ገዢው ፓርቲ አውራ ፓርቲ በሚል አውሬ ለመሆን የቆረጠ ይመስላል፡፡ ይህ ቁርጠኝነት ግን በጎ ቁርጠኝነት እንደማይሆን መገመት ይቻላል፡፡ በደም የተፃፈውን ህገ መንግሰት፣ በደም የማስከበር ወይም የመቀየር አብዮት አማራጭን የሚያስመርጥ እንዳይሆን ስጋት አለኝ፡፡ ይህ ምርጫ ወደ ዲሞክራሲ ስርዓት እንጂ ወደ አብዮት ባይመራን ደስታችን እጅግ የላቀ ነው፡፡ ነገር ግን ይህች ሀገር ሃምሳ ዓምት ባልሞላ ጊዜ ውስጥ ሶስተኛ አብዮት አያስፈልጋትም ያልን ብንሆንም  ሃምሳ ዓመት ከሚዘልቅ “በምርጫ ሰበብ ከሚመጣ ባርነት” አብዮት ይሻላል የማንልበት ምንም በቂ ምክንያት የለም፡፡ ምን ዓይነት አብዮት ሌላ ቀን እመለስበታለሁ፡፡