Sunday, February 9, 2014

የነሌንጮ ምልሠት ፖለቲካዊ እንድምታዎች




ግርማ ሠይፉ ማሩ
ሰሞኑን የፖለቲካ እውቀትና ይህንኑ የማከናወን ክዕሎታችንን የሚፈትኑ ብዙ ነገሮች ብቅ ብቅ ማለት ጀምረዋል፡፡ ከነዚህ ውስጥ አንዱ የሆነው የኦቶ ሌንጮ ለታ ወደሀገር ቤት የመመለስ ዜና ነው፡፡ ፋክት መፅሔት አቶ ሌንጮ ለታም እንዲመጡ፤ በእሳቸው እና ሌሎች የኦነግ አመራሮች ጦስ በሀገር ውስጥ ለእስር የተዳረጉትም ይፈቱ የሚል መልዕክት አስተላልፋ ነበር፡፡ እዚህ ጋ ልብ ማለት ያለብን የኦነግ ታፔላ ተለጥፎላቸው እስር ቤት የገቡት ሁሉ የኦነግ ደጋፊና ተላላኪ ነበሩ ማለት በፍፁም እንዳልሆነ ሊሰመርበት ይገባል፡፡ ሌላ እርግጠኛ መሆን የሚቻለው ግን ኦነግን በመንፈስ የሚደግፉ መኖራቸውን ጭምር ነው፡፡ ይህ ግን በምንም ዓይነት በእስር ለመማቀቅ በቂ ምክንያት ሊሆን አይችልም፤ ወንጀል የሚባል ውጤት እስካላመጣ ድረስ፡፡ በተጨማሪ ግልፅ መሆን ያለበት ዋና ነጥብ ደግሞ ምንም ዓይነት ምርጥ የፖለቲካ ስርዓት ለመመስረት ይሁን ለውጥ ለማምጣት በሚል ሰበብ፤ ስላማዊ ዜጎችን እይወት ለመቅጠፍ የሚደረግ ሙከራም ሆነ የተፈፀመ ተግባር ወንጀል ብቻ ሳይሆን ተቀባይነት የሌለው አርመኔያዊ ድርጊት እንደሆነ ነው፡፡
የአቶ ሌንጮ ለታ ወደ አዲሰ አበባ መምጣት በብዙ መልኩ በጎ ነው የሚል እምነት አለኝ፡፡ አመጣጣቸው ግን የድሮውን የኦነግን ተረት ሊተርቱልን ከሆነ ግን ተቀባይነት የለውም፡፡ የኦነግ ታሪክ የሚያስፈልገን በመፅሀፍ መልክ ተጠርዞ ለታሪክ ምርምር መሆን አለበት፡፡ ለዚህም አቶ ሌንጮ ብቃቱ እንደሚኖራቸው አልጠራጠርም፡፡ አቶ ሌንጮ ለታ የኦሮሞ ህዝብ ቸግር በመገንጠል ሳይሆን በኢትዮጵያዊነት ጥላ ሰር ሊፈታ ይችላል በሚል እምነት  ወደ ሀገር ቤት ለመምጣት ሲወስኑ በወህኒ ቤት በኦነግ ሰም የታጎሩትን ዘንግተው ከሆነ በቅርቡ ከኦብነግ ተገንጥለው ወደ ሀገር ውስጥ በገቡ አመራሮች እንደተበለጡ መረዳት ይኖርባቸዋል፡፡ አቶ ሌንጮ ለታ በኢህአዴግ ሰዎች አይሞኙም ለማለት ውጤቱን መጠበቅ የግድ ይላል፡፡ የማንረሳው ግን ኢትዮጵያን የምታህል ትልቅ ሀገር እንዲመሩ አቶ ሌንጮ በዕጩነት በአቶ መለስ ዜናዊ ሲጠቆሙ እንቢ ማለታቸው ግን የአደባባይ ሚስጥር ነው፡፡ የዛን ዕለት በአቶ መለስ የፖለቲካ ጫወታ እንደተበለጡ ይረዱታል ብዬ አምናለሁ፡፡
ሰለ ኢትዮጵያና የህወሃት ፖለቲካ ሲነሳ አንድ ልብ ማለት ያለብን ነገር ህወሃት የትግራይ ነፃ አውጪ ድርጅት የሚለውን ስም ባለመቀየሩ አሁንም የትግራይ ሪፐብሊክ የመመስረት እቅድ እንዳለው የሚያስቡ ብዙ ሰዎች አሉ፡፡ ይህ አስተሳሰብ ስህተት ነው ብዬ አምናለሁ፡፡ በተለይ ይህ ስህተት በሀገር ውስጥ ሳይሆን በውጭ በሚኖሩ ኢትዮጵያዊያን ዘንድ ነብስ ዘርቶ ይገኛል፡፡ በምድር ላይ ያለው እውነተኛ ሀቅ ግን ከዚህ የተለየ ነው፡፡ ህወሃት ኢህአዴግ የሚባለውን ግንባርና ሌሎች አጋር ፓርቲዎችን ከሰሜን እሰከ ደቡብ፤ ከምዕራብ እሰከ ምስራቅ በመመስረት ያጠፋውና በማጥፋት ላይ ያለው ሀይል የህወሃት መሪዎችን ለበለጠ ጥቅም የሚያበቃቸው በምኒሊክ ኢትዮጵያ በሚሏት ስር እንጂ በትግራይ ሪፐብሊክ ውስጥ እንዳልሆነ በደንብ የተረዱ መሆናቸው ነው፡፡ ለዚህ ነው ህውሃት ኦነግንም ሆነ ኦብነግን ከተቻለ በፀባይ ካልተቻለ ምትክ በማበጀትና በጉልበት የማዳከም ስልት የሚከተለው፡፡ አቶ ሌንጮ ለታ እና ድርጅታቸው ኦነግ በሽግግር ወቅት የቀረበላቸውን እጅ መንሻ በብልዓት ይዘው አሁን የያዙትን አቋም ቢይዙ አንድ ጠንካራ ተገዳዳሪ ፓርቲ ሊሆን ይችሉ ነበር፡፡ ለኦነግ ወይም አሁን በአቶ ሌንጮ ለታ ለሚመሩት ኦሮሞ ዲሞክረሲያዊ ግንባር/ኦዴግ  እንደ ሽግግር ጊዜው በቀላሉ አማላይ የሆነ እጅ መንሻ የሚገኝ አይመስለኝም፡፡ በሸግግር ጊዜው ኦነግ የህወሃትን “የሚንሊክ ኢትዮጵያን” በጋራ እንግዛ ጥያቄን ቢቀበል፤ ኦህዴድን ለመሰዋትነት ለማቅረብ ብዙ አይቸገርም ነበር፡፡ አሁን ግን ኦህዴድ በፈራረሰ ኦነግ የሚለወጥ ድርጅት ነው ብሎ መገመት የፖለቲካ ቂልነት ይመስለኛል፡፡ አቶ መለስ በሌሉበት ደግሞ በኦህዴድ ቤት እንደፈለገ የሚያዝ ህውሃት ወይም ኢህአዴግ ይኖራል የሚል እምነት የለኝም፡፡ የኦህዴድ መሪዎች አሁን ብዙ ለምደዋል፤ መሬት ይዘዋል፡፡
ለኦህዴድ የእነ ሌንጮ ለታ በፈለጉት መንገድ መምጣት፣ በሀገር ውስጥ መገኘት እና በኦሮሞ ህዝብ ውስጥ እንቅሰቃሴ መጀመር የአብዮታዊ ዲሞክራሲ የመድበለ ፓርቲን አተገባበር ለመተግበር እንደመስታወት ወይም ላንቲካ ከማገልገል አልፎ የፖለቲካ ሚዛን ለውጥ እንደማያመጣ የተረዱት ይመስለኛል፡፡ ከሁሉም በላይ የኦህዴድን ትክክለኛነት ማረጋገጫ ማሕትም አድርገው የሚጠቀሙበትም ይኖራሉ፡፡ ኦህዴዶች ጥንቃቄ ካላደረጉና የኦሮሞን ህዝብ ጨዋነት ካልተጠቀሙ እነ ሌንጮ ለታን ከዚህ ቀደም በኦነግ ሰም ተፈፀሙ ለሚባሉ ጥፋቶች ሁሉ የኢቲቪ የዶክመንተሪ መስሪያ ግብዓት እንደማያደርጉዋቸው እርግጠኛ መሆን አይቻልም፡፡ ለዚህ ተግባር ሲባል በእስር ላይ ያሉትንም በመልቀቅ ጭምር ሊጠቀሙባቸው ይችላሉ የሚል ጥርጣሬ አለኝ፡፡ ይህን ዓይነት ስህተት ከመስራት ኦህአዴድ/ኢህአዴግን ፈጣሪ እንዲጠብቀው እኛም ጭምር መፀለይ ይኖርብናል፡፡ ዋናው ምክንያት የዚህ ዓይነት ተግባር በሀገራችን ሀገራዊ መግባባት ልንፈጥር የምንችልበትን የመተማመን መንገድ ይዘጋዋል የሚል እምነት ስለአለኝ ነው፡፡ አቶ ሌንጮም ቀደም ብለው በዚህ መስመር ፋውል ካልሰሩ ይህን ፅሁፍ ከታናሽ ወንድም እንደተላከ መልዕክት ሊወስዱት ይችላሉ፡፡ ኢህአዴግ እንደ ፖሊሲ ይህን አያደርግም አይባልም፡፡ በቅርቡ አቶ ሬድዋን ሁሴን በምክር ቤት ቀርበው የዶክምንተሪ ስትራቴጂ ልክ ነው የሚቀጥል ይሆናል ማለታቸውን ስናስብ የአቶ ሌንጮ ለታ ምርጥ የዶክመንተሪ መነሻ ኃሳብ ተደርጎ ሊወሰድ ይችላል፡፡ ከዚህ አንፃር በኦህዴድ/ኢህአዴግም ሆነ በኦዴግ/ኦነግ ሰፈር የፖለቲካ ክዕሎታቸው የሚፈተንበት ይሆናል፡፡
ሌሎች  በሀገር ውስጥ የሚገኙ ተቃዋሚ ፓርቲዎችም ቢሆን ከፈተና የፀዱ ሊሆኑ አይችሉም፡፡ አንዳንዶቹ የኦዴግ አመራሮች በእነሱ መስመር እንዲሰለፉ ሲጠብቁ ሌሎቹ ደግሞ ቀደም ሲል ኦነግ ሰራው የሚባለውን ሰህተት በመንቀስ የራስን አቋም ትክክለኛነት ማሳያ መስታወት ማድረግ ሊፈልጉ ይችላሉ፡፡ ይህ የሚጠቅመው ገዢውን ፓርቲ ኢህአዴግ/ኦህዴድ ከመሆን ዘሎ በኦሮሚያ ምድር ላይ ለሚደረግ ፖለቲካ ውሃ የሚቋጥር ነገር አያመጣም፡፡ በሀገር ውስጥ ያሉ ፓርቲዎች በዋነኝነት ማድረግ ያለባቸው ኦዴግ ወደ ሀገር ውስጥ ሲገባ ከኢህአዴግ ጋር የፖለቲካ ምዕዳሩ እንዲሰፋ ያደረገው ተሰፋ ሰጪ ድርድር ካለ፤ ውሻ በቀደደው ጅብ ይገባል እንደሚባለው ሊጠቀሙበት የሚችሉበትን መንገድ ማሰብ ነው፡፡ ኦዴግ ትግሉ ወደ ሀገር ውስጥ ማስገባት ስትራቴጂ ሲቀበል አንዱ ቅድመ ሁኔታ በሀገር ውስጥ በምርጫ ቦርድ ምዝገባ ማድረግ አንዱ ሲሆን ሌላው ግን የፖለቲካ ፓርቲዎች ምክክር መድረክ አባል ለመሆን የምርጫ ስነ ምግባር ደንብ (ትክክለኛው የፖለቲካ ፓርቲዎች የምርጫ ሰነ ምግባር አዋጅ ነው) መፈረም የሚሉት ሊሆኑ ይችላሉ፡፡ የአቶ ሌንጮ ለታ ፓረቲ ኦዴግ የምርጫ ሰነምግባር ደንቡን ከፈረመ ኢህአዴግ በሀገር ውስጥ ያሉትን ፓርቲዎች በማግለል በውጭ ሆነው ከሚያስፈራሩት ጋር ለሚያደርገው ድርድር ሽፋን እንደሰጠ ነው የሚቆጠረው፡፡ ይህ ደግሞ ኦዴግን በተቃዋሚነት እና አማራጫ ያለው የኦሮሞ ህዝብን የሚወክል ፓርቲነት ሳይሆን በኦህዴድ ሀጋርነት ለመሰለፍ እንደመጣ ተደርጎ እንዲወሰድ ስለሚያደርገው ፈተናውን ያከብድበታል፡፡ ከዚህ አንፃር ተቃዋሚዎችም የሚስጡት የመልስ ምት ሌላ የፖለቲካ ክዕሎት የሚጠይቅ ሆኖ ይታየኛል፡፡
ለማነኛውም በዓለም ላይ በልዩ ሁኔታ ከምንታወቅባቸው ነገሮች አንዱ የሆነው ኦነግ ሲያራምደው የነበረውን የቅርንጫፎች ጥያቄ መሆን ያለበትን ግንዶች ጠየቁት ሲባል የነበረውን የመገንጠል (የኦሮሚያ ሪፐብሊክ) ጥያቄ የሚያሻሽል እርምጃ በአዎንታዊነት መታየት ያለበት ነው፡፡ ስለዚህ ኢትዮጵያዊያን ዜጎች ኦሮሞ፣ አማራ፣ ጉራጌ፣ ሲዳማ፣ ትግሬ፣ ወዘተ ሰብዓዊ ክብራችንን የሚመጥን ዲሞክራሲያዊ ስርዓት ሲመሰረት የአንድ ቡድን አባል በመሆናችን የደረሰብን የሚመስለን በደልና ግፍ ሁሉ ይወገዳል ወደሚል እየመጣን እንደሆነ ይሰማኛል፡፡ በአንድ ቡድን ላይ ደረሰ የምንለው ግፍና በደል ያልደረሰበት ካላ የገዢው ቡድን አባል በመሆን ነው እንጂ የአንድ ቡድን አባል በመሆኑ ከግፍ አያመልጥም፡፡ ገዢዎቻችን ደግሞ አሁን የአንድ ብሔር ብቻ ናቸው ለማለት የሚያስደፍር አይደለም፡፡ በኦሮሚያ ክልል የሚደርስ በደል በኦሮሚያ ካድሬዎች ነው፡፡ በትግራይ ክልል በቅርቡ በአረና አባላት ላይ የሚደርስ ያለው በደል በትግራይ ካድሬዎች ነው፡፡ የሁሉም ካድሬዎች መመሪያ ቀራጭና አሰማሪ ደግሞ በጋራ የመሰረቱት ግንባር ኢህአዴግ ነው፡፡ ትግላችን የስርዓቱ መሪ የሆነውን ፓርቲ በመቀየር ላይ ማተኮር ይኖርበታል፡፡ እንዴት? የሚለው የፖለቲካ ክዕሎታችን የሚጠየቅበት ሌላኛው ጥያቄ ነው፡፡

No comments:

Post a Comment