Monday, February 3, 2014

የሁለት ሺ ሰባት ምርጫ ወዴት ይመራናል?




ግርማ ሠይፉ ማሩ
girmaseifu32@yahoo.com
በኢህአዴግ መንደር የምርጫ ዘመቻ በይፋ መጀመሩን የሚያሳዩ ምልክቶች መታየት ጀምረዋል፡፡ የምርጫ ቦርድ በገዢው ሰፈር ሁሉ ነገር መጠናቀቁ ጥቅሻ ሲሰጠው እንቅስቃሴ ይጀምራል ተብሎ ይጠበቃል፡፡ የምርጫ ዘመቻው በተቃዋሚ ጎራ እንደምንፈልገው ነፃ፣ ፍትሓዊ እና ሁሉም ተወዳዳሪ እኩል በተዘጋጀ ሜዳ ይሆናል ማለት ከባድ ሊሆን እንደሚችል ከአሁኑ መገመት ለዝግጅት የሚረዳ ይመስለኛ፡፡ ኢህአዴግ ከጅምሩ የመጫወቻ ሜዳውን ብቻ ሳይሆን አጫዋቾችን ሁሉ ተቆጣጥሮ ጨዋታው እንዲጀመር መፈለጉን የሚያሳዩ ምልክቶች መታየት ጀምረዋል፡፡ በዚህ ወቅት የመንግሰት አካላት የሆኑት ህግ አውጭውም ሆነ አሰፈፃሚውም በዚህ ጉዳይ ላይ ተጠምደው ነው የሚገኙት፡፡ እንደ አሰፈላጊነቱም የፍትህ ስርዓቱ ይቀላቀላል ተብሎ ይጠበቃል፡፡ ካለን ልምድ በመነሳት ይህ ከግምት በላይ ነው፡፡
ህግ አውጭው ማለትም ምክር ቤቱ ውስጥ የሚገኙት ሰዎች በምርጫ የሚሰየሙ ስለሆኑ በዋነኝነት ተግተው ለቀጣይ አምስት ዓመት በምክር ቤት በመቆየት የአዲስ አበባ ኑሮን ማጣጣም ይፈልጋሉ፤ ይህን ሀቅ መካድ አይቻለም፡፡ ለዚህ ማሳያ የሚሆነው በኮንዶሚኒየም ስርዓት ውስጥ ቅድሚያ ለማግኘት ብዙ ሙከራዎች ይደረጋሉ፤ በቀጣዩ ካልተመረጡ ወደ መረጣቸው ህዝብ ተመልሰው በሌላ መስክ ለማገልገል ዝግጁ የሆኑት በጣም ጥቂቶች ናቸው፡፡ አስፈፃሚውም ቢሆን በቀጣይ በገዢነት ለመቆየት ቆርጦ የተነሳ ነው የሚመስለው፡፡  ስለዚህ አስፈፃሚው የሚያወጣውን ምርጫ መተግበሪያ እቅድ ነፃ ፍትዊ ይሁን ብሎ የሚከላከል አይኖርም፡፡ ይልቁንም የሚጠበቀው ተባብሮ በቁርጠኝነት መተግበር ነው፡፡ ከዚህ ዘለግ አድርገን ስናስብ ደግሞ አስፈፃሚው የሚያስበው የኢህአዴግ ዕጮዎችን ብቻ ሳይሆን በተቃዋሚ ጎራ ማን? እንዴት? መወዳደር እንዳለበት ሁሉ የመወስን ፍላጎት አላቸው፡፡ ለዚህ ጉዳይ ፓርቲዎችን አብዮታዊ ዲሞክራሲያዊ የሆኑ በአሁኑ አጠራር ልማታዊና ዲሞክራሲ አመለካከት ያላቸው፤ ከዚህ ውጭ ኒዎ ሊብራል ቢሆንም በኢህአዴግ እይታ ፅንፈኛ አይደሉም የሚባሉት ብቻ ቢወዳደሩ እና ለአበዳሪዎቻቸው እና ዕርዳታ ሰጪዎች ማስመሰያ ቢሆኑ ደስ ይላቸዋል፡፡ የመድበለ ፓርቲ ስርዓት አለ እንዲባል ይህ ቻይናን እና መሰሎቿን አይጨምርም፡፡ በዚህ ጉዳይ ኢህአዴግ ማፈር ትቶዋል፡፡ ኢህአዴግ አውራ ፓርቲ የሆነው ተቃዋሚዎች ሰራቸውን ስለማይስሩ ነው ብሎ ማውራትና ማስወራት ጀምሮዋል፡፡ ተገደን ነው ውስኪ የለመድነው አሉ የደርግ ባለስልጣናት ይባል ነበር፡፡ ኢህዴግም ተገዶ አውራ ፓርቲ ሆኖዋል፡፡ አንግዲህ በዚህ ዓይነት ድባብ ውስጥ ነው የሁለት ሺ ሁለት ምርጫ የሚካሄደው፡፡ ምርጫ መወዳደር ካለብን ይህን ሁሉ ተረድተን ነው፡፡ ምን እናድርግ? ብለን ማስብ የሚኖርብን ይመስለኛል፡፡
በኢህአዴግ በኩል ለምርጫ ዘመቻ በእቅድ የተያዙት ዋና ዋና ተግባራት ይህችን ሀገር ሊመሩ ይችላሉ የሚባሉ ምርጥ ምርጥ ካቢኔ እና የምክር ቤት አባላትን በማቅረብና በይፋ በማስገምገም አይደለም፡፡ እንደ አለመታደል ሆኖ ይህችን ሀገር በቁንጮነት የሚመራትን ሰው ለመምረጥ ዕድል የለንም አንድ ወረዳ የመረጠልንን ሀገር እንዲመራ ከመጋረጃ ጀርባ በሚዶልቱ ሰዎች ዕድል ይሰጠዋል፡፡ በነገራችሁ ላይ ኢህአዴግ ትንንሽ አባላቱን በወረዳ ደረጃ ያስገመግማል፡፡ ኢህአዴግ ምርጫ ማሸነፍ የሚፈልገው በብቃቱ አይደለም፡፡ ይልቁንም ለዚህ ጉዳይ ጉልዕ ሚና ይጫወታሉ ብሎ ያመነባቸውን አካላት በማሸማቀቅ እና አንገት በማስደፋት ነው፡፡ ከዚህ በዘለለም የፓርቲው ያልሆኑ በመንግሰት ኃላፊነት የተከናወኑ ተግባራትን ለምርጫ ዘመቻ በማቅረብ ነው፡፡ እነዚህን በትንሽ በትንሹ መመልከት እንችላለን፡፡
ቀዳሚው ተግባር ተቃዋሚ ፓርቲዎችን በፀረ ሰላም ሀይልነት መፈረጅ ለዚህም “የፀረ ሽብር ህጉን” እንደመሳሪያ በመጠቀም ቅስቀሳዎችን ማድረግ፡፡ ከዚህ በተጨማሪ የተለያዩ የልማት ስራዎችን ከፊት በማስቀደም ተቃዋሚዎችን በፅንፈኝነት መፈረጅ ሲሆን ተቃዋሚዎች ለዚህ ምላሽ መስጠት እንዳይችሉ ሚዲያ መከልከል፡፡ ከተቻለ የተወሰኑ አስተያየቶችን እንዲሰጡ በማድረግ እየቆረጡ ማቅረብ ናቸው፡፡
ለምሳሌ አሽባሪነት በተመለከተ ፓርቲዎች በይፋ የያዙት አቋም እና ፕሮግራማቸው ላይ ያስቀመጡትን ግልፅ አቅጣጫ ወደ ጎን በመተው ኦነግና ኢህአዴግ አብረው ሀገር ሲመሩ የተፈፀሙ ወንጀሎችን በፊልማ በማሳየት የሽብር ስራ ነው በማለት ድራማ እየሰሩ ከዚህ ጋር ምንም ግንኙነት የሌላቸውን ፓርቲዎች የሚወነጅልበት ፕሮፓጋንዳ ይሰራሉ፡፡ እን አንዱዓለምን ከእንዲህ ዓይነት እኩይ ተጋባሮች ጋር በማገናኘት ሌሎች የፓረቲ አመራሮቸን ተጠንቀቁ ማለት አንዱ በመተግበር ላይ ያለ ዕቅድ ነው፡፡ ሲከፋም ህዝቡ መምረጥ የሚገባው የሰላም ሀይል የሆነውን ኢህአዴግን ወይም ፀረ ሰላም የሆኑትን ተቃዋሚዎች ብሎ የተሳሳተ ምርጫ ያቀርባል፡፡ ይህን እውነት ለማስመሰል ሚዲያውን በህገወጥ መንገድ ይጠቀማሉ፣ ሚዲያውም መደበኛ ሰራው አድርጎት እየሰራው ይገኛል፡፡
ለተቃዋሚዎች ኢህአዴግና መንግሰት ተለይተው እንደ ፓርቲ መወዳደር ካልጀመሩ ምርጫ የተወሰኑ ወንበሮች ከማግኘት በዘለለ የስልጣን መያዣ መንገድ መሆኑ እያከተመ ነው፡፡ ይህ ደግሞ የአብዮታዊ ዲሞክራሲ መስመር ነው፡፡ መድበለ ፓርቲ ስርዓት ለገዢው ፓርቲ እንደ መታጠቢያ ቤት መስታውት ፊትን መመልከቻ ሆኖ ማገልግል ነው፡፡ ይህን ዕቅድ ተግባራዊ እንዳያደርጉ ተቃዋሚዎች ከምንግዚውም በላይ ከህዝቡ ጋር በመሆን ማክሸፍ የግድ ይላል፡፡ በቀጣይ ዓመት ምርጫ ኢህአዴግ እንደ ከዚህ ቀደሙ በሙሰሊም ማህበረሰብ ድጋፍ ላይ ስለማይተማመን አሁን በከፍተኛ ደረጃ የክርስትና ሃይማኖት ተከታዮችን ስጋት ውስጥ በመክተት ድምፃቸውን ለኢህአዴግ ድምፅ እንዲሰጡ ማድረግ አንዱ እቅድ ነው፡፡
በሌላ በኩል ኢህአዴግ ለምርጫ የሚጠቀምበት በመንግሰት በጀት የተከናወኑ እና በመከናወን ላይ ያሉ ተግባራትን በመጠቀም ነው፡፡ ለዚህ ጉዳይ የሚነሱት የልማት ስራዎች፤
·        ብዙ ነጥብ ማስቆጠር ባይችልም ኮንዶሚኒየም ቤት ግንባታ፤
·        የስኳር ፋብሪካ ግንባታ (በእድገትና ትራንስፎርሜሽን ከታቀደው 70 በመቶ ይሳካል በሚል)፤
·        የአባይ ግድብና የግብፅ እንቢተኛነት መሰረት በማድረግ፤
·        የጨርቃ ጨርቅ ኢንዱስትሪዎች፤
·        ጥቃቅን እና አነስተኛ ተቋማት (ምንም ያህል ያልተሳካ ቢሆን)፤ ወዘተ
ዋና ዋናዎቹ ናቸው፡፡
ለቀጣይ ምርጫ ሚዲያዎች ሌላው የመስዋዕት በግ ይሆናሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡ ይህ የሚተገበረው ሚዲያዎቹን የፅንፈኞች ልሳን በማለት እና ምንም ዓይነት ዕለታዊ ጋዜጣ እንዳይኖር በማድረግ ነው፤ ካስፈለገም የተወሰኑትን በመዝጋት እና እንዲሰደዱ ምቹ ሁኔታ በመፍጠር ጭጭ ማሰኘት ተግባራዊ ይደረጋል፡፡ በዚህ መስመር ከአድማስና ሪፖርተር ጋር ማዝገም ነው የሚፈቀደው፡፡ እነርሱም ቢሆኑ ወደ መጨረሻው ካልሆነ ቀደም ብለው ጠንከር ያለ ነገር ማድረግ አይጠበቅባቸውም፡፡ እንደ ሪፖርተር “ያሳከከው ፓርላማ ጥርስ ያውጣ” ምክር ግን አይከለከልም፡፡ አሁን በምክር ቤት ውስጥ ያለን የምንረዳው አባላት በቀጣይ ምርጫ ይቀጥሉ አይቀጥሉ በከፍተኛ ውጥረት ላይ ነው የሚገኙት፡፡ አሁን የብዙዎቹ ጭንቅ ዕጩ ሆነው ካልቀረቡ አዲስ አበባ እንዴት እንደሚቀሩ ማሰብ ነው፡፡ በዚህ ጉዳይ ችግር ከሌለባቸው ምርጫ ክልሎች ውስጥ የአቶ መለስ ምርጫ ክልል እና ሌሎች በሞት የተለዩ የምክር ቤት አባላት፣ በወህኒ የሚገኙ፣ እንዲሁም በስደት ከሀገር የወጡት ወንበሮች ናቸው፡፡ እንደው ለነገሩ አቶ አባዱላ አሁን ከያዙት ወንበር ወደ ክልል የሚሄዱ አይመስላችሁም፣ እኔ ግን ዝም ብሎ ይህ ይታየኛል፡፡ እሰኪ ሃሳብ ስጡበት …. ነው ጡረታ ይወጡ ይሆን?
የሲቪል ማህበራትና በጎ አድራጎት ድርጅቶች በአሁኑ ሰዓት ይህ ነው የሚባል ጫና በመንግስት ላይ እያደረጉ አይደለም፡፡ እንደዚያም ሆኖ ግን በፍፁም ዘንግተው ወደ ምርጫ 97 ዓይነት እንቅስቃሴ እንዳይገቡ ማስፈራራያ መሰል መልዕክቶች እየተላለፉ ነው፡፡ እነዚህ ማህበራት ደግሞ በጣት ከሚቆጠሩት በስተቀር ስብሰባ ተጠርተው ሌባ ሲባሉ እንኳን አይደለንም ለማለት ሞራል ያላቸው አይደለሙ፤ ባይሰረቁ እንኳን የእንጀራ ገመዳቸው ወይም የመኖር ዋስተናቸው የተመሰረተበት እንደሆነ መንግሰትን ከሚወክለው ኤጀንሲ ጋር የተዋወቁ ይመስላሉ፡፡ … በዚህ መስመር በአሰሪዎችና ሰራተኞች ፌዴሬሽን፣በወጣትና ሴቶች ሊጎች የመሳሰሉ “ነፃ” ተብዬ ማህበራ ካልሆነ በስተቀር ለመታዘብ እንኳን እንዳያሰቡ መልዕክቱ ቀድሞ እንዲደርሳቸው በመደረግ ላይ ነው፡፡

በሁለት ሺ ሰባት ምርጫ ኢህአዴግ ለመከተል የመረጠው መንገድ በምንም ሁኔታ ስዕተት ባለመስራት የቀድሞ ስትራቴጂስቱም በሌሉበት ምርጫ በዝረራ የሚያሸንፍ ደርጅት እንደሆነ ማሳየት እና የቀጣዩን ዓመት የመውጫ ስትራቴጂ ለማድረግ ይመስላል፡፡ ይህ የመውጫ ስትራቴጂ ግምት በቅንነት እንጂ በፍፁም በመረጃ የተመሰረተ አይደለም፡፡
ስለዚህ አሁንም ገዢው ፓርቲ አውራ ፓርቲ በሚል አውሬ ለመሆን የቆረጠ ይመስላል፡፡ ይህ ቁርጠኝነት ግን በጎ ቁርጠኝነት እንደማይሆን መገመት ይቻላል፡፡ በደም የተፃፈውን ህገ መንግሰት፣ በደም የማስከበር ወይም የመቀየር አብዮት አማራጭን የሚያስመርጥ እንዳይሆን ስጋት አለኝ፡፡ ይህ ምርጫ ወደ ዲሞክራሲ ስርዓት እንጂ ወደ አብዮት ባይመራን ደስታችን እጅግ የላቀ ነው፡፡ ነገር ግን ይህች ሀገር ሃምሳ ዓምት ባልሞላ ጊዜ ውስጥ ሶስተኛ አብዮት አያስፈልጋትም ያልን ብንሆንም  ሃምሳ ዓመት ከሚዘልቅ “በምርጫ ሰበብ ከሚመጣ ባርነት” አብዮት ይሻላል የማንልበት ምንም በቂ ምክንያት የለም፡፡ ምን ዓይነት አብዮት ሌላ ቀን እመለስበታለሁ፡፡

No comments:

Post a Comment