Thursday, November 12, 2015

ፕሮፓጋንዳው ስብዓዊነት ይኑረው!!! ሰው እየሞተ ነው!! ቁጥሩን ቤቱ ይቁጠረው!!!



በሀገራችን ያለው ድርቅ ክብደት ከ1977ጋር የሚመሳሰል እንደሆነ የመንግሰት ሹም ከሸገር ሬዲዮ ጋር ባደረጉት ምልልስ አረጋግጠዋል፡፡ ልዩነቱ ግን አሁን መንግሰት ይህን ለመቋቋም የሚያስችል አቅም አለን የሚልው ጉዳይ ነው፡፡ ይህ አቅም ግን መሬት ላይ ወርዶ ስናየ ወኔ ብቻ ይመስላል፡፡ ከፕሮፓጋንዳ ያለፈ የፈረንጆቹን ደጅ እንዳይጠኑ የሚያደርጋቸው አይደለም፡፡
“ደርግ” በ1977 የነበረፈውን ድርቅ ለዓለም ይፋ አድርጎ የነበረ ሲሆን የዚያን ጊዜ በነበረው ቀዝቃዛ ጦርነት መነሻ በሁለቱ ጎራ በሚደረገው ፍልሚያ ግዳይ የሚጣልብት ወቅት ነበር፡፡ ደርግ ለዓለም ህብረተሰብ ጥሪ ባቀረበበት ወቅት የሶሻሊስቱ ተከታይ በመሆኑ ይህ ጎራ ይህን ድጋፍ የሚያደርግበት አቅም የሌለው ሲሆን ይህን ለማድረግ አቅም ያላቸው ምዕራባዊያን ግን ውጤቱን በደንብ ሳናየው ድጋፍ ላለመስጠት መቁረጣቸው ለችግሩ ክብደት አንዱ እንደ ነበር ለመረዳት ሊቅ መሆን አያስፈልግም፡፡ በተጨማሪ ለ1997 ድርቅ ተገቢው ምላሽ በምዕራባዊያን እንዳይሰጥ በወቅቱ በትጥቅ ትግል ላይ የነበሩት በተለይ ህወሃት እና ሻቢያ የተጫወቱት ሚና ቀላል የማይባል ብቻ ሳይሆን አሁን ላይ ሆነን ስናየው ሰብዓዊነትን ለፖለቲካ ጥቅም እንዳዋሉት ፀሐይ የሞቀው ሀቅ ነው፡፡
አሁን ባለው ሁኔታ የኢህአዴግ መንግሰት ከምዕራባዊያኑ ጋር ያለው ቅርበት ከደርግ እንደሚሻል ስለሚታመን በተጨማሪ ህውሃትና ሻቢያ በዛን ጊዜ የሰሩትን ዓይነት ኢ-ሰብዓዊ ድርጊት ለመስራት የሚችል ታጣቂ ሀይል ባለመኖሩ ችግሩን ለመቋቋም በተሻለ ሁኔታ ላይ ይገኛል፡፡ መንግሰት አቅሙ የከብቶቹን ህይወት ለመታደግ ለምን አልተጠቀመበትም? ካልቻለ ደግሞ ምዕራባዊያኑ ድጋፍ ለማድረግ ከፈለጉ አሁንስ ቢሆን ከብቶቹ ሳይሞቱ እንዲደርሱልን ለምን አልተደረገም? የሚለው ጥያቄ ለማንሳት አርብቶ አድር መሆን አይጠበቅብንም፡፡
ሁሉም የሚረዳው አንድ ሀገር በድርቅ መቼም ቢሆን ሊጋለጥ ይችላል፡፡ ይህ በዓለም ላይ ተደጋጋሚ ክስተት እንደሆነ ማንም ያውቃል፡፡ ድርቅ ሲኖር ግን ይህን ድርቅ የሌላ ሶሰተኛ ሀገር ድጋፍ ሳይጠየቅ ለመፍታት አቅም መፍጠር መቻል ነው፡፡ ኢትዮጵያ አሁን ባላት ስነ ምህዳር ከዚህ የተሻለ ማድረግ እና ለሌሎች መትረፍ ይገባት ነበር፡፡ ይህ ደግሞ አሰማት ሳይሆን ሊተገበር የሚችል የሀገር ሉዓላዊነት መገለጫ ነው ብሎ የሚያምን መንግሰት ያስፈልጋል፡፡ ኤክስፖርት የሚደረግ ታንክ ሰራን በፍፁም በዚህ ወቅት ሊያኮራን የሚችል ስ አይደለም፡፡ አሁን የምንረዳው መንግሰት ችግሩን ሪፖርት አድርጊያለሁ ማለትን እንደመውጫ ቀዳዳ እየተጠቀመበት መሆኑን ነው፡፡
አሁን በመሬት ላይ ያለው ሀቅ በምግብ እና ውሃ እጥረት ከብቶች በብዛት እየሞቱ ሲሆን፤ መቼም እንደ እንሰሳቱ በብዛት ሰው እየሞተ እንዳልሆነ እናውቃለን፡፡ ነገር ግን አሁን በተፈጠረው ሁኔታ ከምግብ እጥረት ጋር ተያይዞ ቀደም ሲል የነበረባቸው የጤና ችግር አግርሽቶም ይሁን አዲስ ጤና መቃወስ ተፈጥሮ ህፃናት ብቻ ሳይሆን አረጋዊያንም ሆኑ ባለጡንቻው ጎልማሳ የሚሞቱበት ሁኔታ እንዳለ ግን መካድ አይቻልም፡፡ ከዚህ ስንነሳ በምግብ እጥረት ምክንያት ሞት የለም ብሎ ፈሊጥ፤ የቢቢሲ ጋዜጠኛ ሁለት ህፃናት በቀን ይሞታሉ ያለው ለሌላ ዓላማ እና የሀገር ገፅታ ለማበላሸት ነው የተባለውን የመንግሰት ሹም መግለጫ ስንሰማ ከማፈር ውጭ ምን ልንል እንችላለን፡፡ የመንግሰት ሹሞቸ ፕሮፓጋንዳውን ጋብ አድርገው ሰብዓዊነት በመላበስ እየሞተ ያለውን ሰው መታደግ የግድ ነው፡፡ ስንት ሰው ሞተ ቤቱ ይቁጠረው፡፡
አንድም ሰው በድርቅ አልሞተም የሚል መግለጫ የሰጡትም የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩም ቢሆኑ አሁን የተፈጠረው ሁኔታ ከላይ እንደገለፅኩት ቀደም ሲል በአካባቢዎቹ የኖረው ችግር ላይ ሲታከል ሰዎች እንደሚሞቱ መገንዘብ አቅቷቸው ሳይሆን ለፖለቲካ ፍጆታ ብቻ የተደረገ መሆኑን ማውቅ ግድ ይለናል፡፡ በዚህ ፕሮፓጋንዳ ማፈራችን እንደተጠበቀ ሆኖ፡፡ የምናፍረው ደግሞ ከ30 ዓመት በኋላ ድርቅን ለመቋቋም የሚችል ህብረተሰብ ሊገነባ የሚችል ስርዓት መመስረት ያለመቻላችን ነው፡፡ ይህን መንግሰት ዛሬም ስህተቱን “በኤሊኖ” ክስተት አሳቦ በስልጣን እንዲቆይ የፈቀድነው እኛው ነን፡፡
ኢትዮጵያ ሀገራችን በምንም መመዘኛ አምስት ዓመት ባልሞላ ጊዜ ውስጥ በፈለገ የተራዘመ የተፈጥሮ ችግር ጊዜ ቢሆን እንኳን ምግብ ለመለመን የማትችል ሀገር ለማድረግ የሚያስችል ፖሊሲና ሰትራቴጂ የሌለው መንግሰት እንዳይኖር ማድረግ ካልቻልን ምርጫው የራሳቸን ነው፡፡ ምን ማለት ነው? የሚል ጥያቄ ሊነሳ ይችላል፡፡ እኛ ከላፈቀድን መሬትን በቁጥጥሩ ስር አድርጎ፤ ሴፍቲኔት በሚባል የመንግሰት ድጎማ ስር ህዝቡን በተራዘመ ሰንፍና እንዲኖር በማድረግ በአምስት ዓመት በሚመጣ የይስሙላ ምርጫ ካርድ አግኝቶ አገዛዙን ለማራዘም የሚፈልግ መንግሰት ይህን ዓይነት ሰርዓት ሊዘረጋ አይችልም፡፡ እንዲህ ሲያደርገን እንቢ ብለን መከላከል ምርጫው የእራሳችን ይሆናል ማለት ነው፡፡
በተለጠጠ ዕቅድ ተሰፋ ውስጥ (የመጀመሪያውን የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ልብ ይሏል) የከተማ ነዋሪውን ሸምቶ ለማብላት የውጭ ሀገር የሰንዴ ገበያን አማራጭ ያደረገ መንግሰት፤ በሀገር ውስጥ በእርሻ ለመሰማራት ለሚፈልጉ ዘመናዊ ገበሬዎች እርሻ መሰሪያና ሌሎች ግብዓቶች ድጎማ አድርግ ሲባል ነፃ ኢኮኖሚ ነው ይለናል፡፡ አንድ በዘመናዊ እርሻ ለመሰማራት የሚፈልጉ ዘመናዊ ገበሬ ጠቅላይ ሚኒስትሩ በሰበሰቡት ስብሰባ ላይ ከጎኔ ቁጭ ብለው የነገሩኝ አስደማሚ ነገር “መንግሰት ሰንዴ ለመግዛት በጨረታ የሚያባክነው ጊዜ እና ገንዘብ ለእኛ ድጋፍ ቢያደርግ ለጨረታ ከሚባክነው ጊዜ ባነሰ በሀገር ውስጥ ሰንዴ ለማምረት እንችላለን” የሚል ነው፡፡ ይህን ሀቅ ለጠቅላይ ሚኒስትሩም ሆነ ለግብርና ሚኒሰትሩ የኪራይ ስብሰቢዎች ወሬ ነው የሚሆነው፡፡ ግብርና መር ስትራቴጂና ፖሊሲ ብለው ምግብ በሀገር ውስጥ ማሟላት ሳይችሉ ለዘላለም ሊገዙን ሲፈልጉ እሺ ብለን አለን፡፡
ለማነኛው ኢትዮጵያ ሀገራችንን ምድሯ “በኤሊኖ” ክስተት ይሁን በሌላ “ድርቅ” ጎብኝቷታል፡፡ ይህ ድርቅ አድጎ ደግሞ ዜጎችን ህይወት ቀሰ በቀስ እየወሰደ ነው፡፡ ይህን “ችጋር” ለመቋቋም ዜጎች በጋራ መነሳት ይኖርብናል፡፡ ፈረንጆቹ ይህ ውጤት እንዲቀለበስ ከልብ ከፈለጉ አንድም ሰው ሳይሞት ሊደርሱ የሚያስችል ሰርዓት አላቸው ነገር ግን የሰጡት ድጋፍ ህይወት አድን መሆኑ እንዲታወቅ ችግሩ እስኪሰማን ብዙ ሀይወት መጥፋቱ በሚዲያ ታይቶ ቅሰቀሳ እስኪደረግ ሊዘገዩ ይችላሉ፡፡ በዚህ መሃል ምትክ የሌለው የሰው ልጅ ህይወት ያልፋል፡፡ ይህ እንዳይሆን መንግሰት አሁን ከጀመረው ተራ ፕሮፓጋንዳ ወጥቶ ወደ ቀጥተኛ ህዝቡን ያሳተፈ ምላሽ እንዲሰጥ ማድረግ ይኖርበታል፡፡


No comments:

Post a Comment