Saturday, September 3, 2016

የማሪያም መንገድ ሲዘጋ የገብሬሉ ይከፈታል ብለን ነበር!!!



አንድትን ፓርቲን ድንክ ለማድረግ ከመወሰናቸው በፊት አንድነት የሚከተለውን ሰላማዊ የትግል ስልታ፤ ሰላማዊ የሰለጠነ የስልጣን ሽግግር እንዲቀበሉ በተደጋጋሚ አሳሰብን ነበር፡፡ ከመሃከላችን እየመረጡ ማስር ትግሉን እንደማያዳክመው ይልቁንም እንደሚያጠነክረው ነግረናቸዋል፡፡ ከከፋም ትግሉ ወደ ሌላ ደረጃ እንደሚያሸጋግረው በቅርብ ላገኘናቸው ሁሉ ነግረናል፡፡ መግለጫዎች አውጠተን አቋማችን ህዝብ እንዲረዳው አድርገናል፡፡ የመንግሰት ተቋማት ህዝብን እንዲያገለግሉ፣ ከተሰጣቸው ህዝብን የማገልገል ሃላፊነት ውጭ እንዳይንቀሳቀሱ የበኩላችን ለማድረግ ሞክረናል፡፡ ማነኛውም ያደረግናቸው እንቅስቃሴዎች ከፍርሃት ተቆጥሮብናል፡፡ ከሁሉም በላይ በምን ያመጣሉ ትዕቢት የፈለጉትን አድርገዋል፡፡ ይህ እንዲሆን በውስጣችን ታቅፈናቸው የነበሩትን ጭንጋፎች ተሳትፎ የሚያሳንሰው አይደለም፡፡ ይህም ቢሆን ግን ገዢው ፓርቲ በማይመለከተው የፓርቲ የውስጥ ጉዳይ ገብቶ ህገወጥ እርምጃ የፖሊስ ሰራዊት በማሰማራት ወስዶዋል፡፡ ዛሬ በሰላማዊ ትግል ጥላ ስር ለውጥ እናመጣለን ሲሉ የነበሩ ወጣቶች በማነኛውም መንግድ ለውጥ ለማምጣት ቆርጠው ተነስተዋል፡፡ ተገፍተው የገቡበት መሆኑን ስለምናውቅ ምርጫቸውን ማክበር ብቻ ሳይሆን በባርነት ከመኖር ሞትን መምረጥ የሰው ልጅ ትክክለኛ ምርጫ ነው ብለን እናከብራቸዋለን፡፡
የታፈነ ህዝብ ለመተንፈስ የሚያደርገው የዚህ ዓመት ህዝባዊ እንቅስቃሴ በምንም መመዘኛ ሰህተት ሊሆን አይችልም፡፡ ጥያቄዎቹን በየቦታው ያስነሱት ጉዳዮች የተለያዩ ቢመስሉም መንግሰት እንደሚለው የመልካም አስተዳደር ጉድለት አይደለም፡፡ የህዝብ ጥያቄ ያልገባው መንግሰት ደግሞ መልሱን ሊያገኘው እንደማይችል ደግመን ደጋግመን ተናግረናል፡፡ በየቦታው የተነሳውን ህዝባዊ ንቅናቄ ተከትሎ መንግሰት ህገወጥ እርምጃዎችን መውሰዱን ቀጥሎበታል፡፡
መንግሰት በቅርቡ እያደረገ ያለው ዜጎችን መቅጠፍ በምንም መመዘኛ ቀለም አልተሰጠውም እንጂ ከቀይ ሽብር- ነጭ ሸብር የሚለይ አይደለም፡፡ በሃያ አንደኛው ክፍለ ዘመን የፖለቲካ ልዮነቶች በውይይት እና ህዝብ በሚመርጠው መስመር መፈታት አለበት ተብሎ በሚታመንበት ጊዜ መንግሰት ገዳይ ጥይቶቸን በሰላማዊ ዜጎች ላይ እየረጨ ይገኛል፡፡ ይህ መቼም ቢሆን ከተጠያቂነት የሚያድን አይደለም፡፡ የህዝብ መተንፈሻ የሚባሉትን መሰመሮች ሁሉ የዘጋ መንግሰት ህዝብ ለምን አደባባይ ወጣችሁ ብሎ ለመግደል የሚያስችል ስልጣን ማንም አልሰጠውም፡፡ ነገር ግን ጊዚያዊ ማዘዣውን ተጠቅሞ በተግባር ዜጎችን እየገደለ ይገኛል፡፡ ይባስ ብሎ ከነብስ ወከፍ መሳሪያ አልፎ የቡድን መሳሪያዎች፣ በእኔ ግምት ለውጭ ወራሪ ሀይል የተዘጋጀን መከላከያ አንቀሳቅሶ የህዝብን ድምፅ ለማፈን እየተንቀሳቀሰ መሆኑን ለሚታዘብ ወቅቱ የመንግሰት የእብደት ደረጃ ልክ ያለፈበት እንደሆነ ለመረዳት አያስቸግርም፡፡
የኢትዮጵያ ህዝብ ከሰሜን እስከ ደቡብ፣ ከምዕራብ እሰከ ምስራቅ የጠየቀው ለሰው ልጅ የሚገባውን ነፃነት እና ክብር ነው፡፡ መንግሰት ደግሞ ሆዳችሁን ከሞላቸሁ ፎቅ፣ ባቡር እና መኪና መንገድ ካያችሁ መች አነሳችሁ የሚል ይመስላል፡፡ በቅርቡ ጠቅላይ ሚኒስትር ሰብሰበው ለወጣቶች የሚነግሩት በሙሉ ሆድ ሰለሚሞላበት መንገድ ነው፡፡ ወጣቱ በአደረጃጀት ካልገባ ማግኘት እንደማይቻል ያስረዱት ደግሞ የስፖርትና ወጣቶች ሚኒሰትር መስሪያ ቤት የወጣት አደረጃጀት ሃላፊ ናቸው የተባሉ ሰው ናቸው፡፡ በሀገራችን ያለው የተፈቀደ አደረጃጀት መንግሰትን ለማወደስ የተቋቋሙት የወጣቶችና የሴቶች ሊጎች ናቸው፡፡ እነዚህ አደረጃጀቶች ገዢው ፓርቲ ሲየስነጥስ እንባቸው የሚመጣ ናቸው፡፡ እነዚህ ደግሞ የወጣቱን ችግር ሊናገሩ አይችሉም፡፡ ከጠቅላይ ሚኒስትሩ ጋር በወጣት ሰም ስብሰባ ተቀመጡ የተባሉ ሰዎች አብዛኞቹ በእውነት ይናገራሉ ተብለው የሚጠበቁ እንዳልሆነ ብዞዎች የተሰማሙበት ነው፡፡ እነዚህ ተሰብሳቢዎች ቢያንስ እድሜያቸው የወጣት አይደለም፡፡ ወጣት ያልሆነ የወጣት ችግር አያውቅም ማለት ሳይሆን በዚህ ስብሰባ ለመካፈል ለሚከፈል አበል ለማግኘት ሲሉ ወጣቶችን ትተው እራሳቸውን መርጠው የመጡ ሰዎች ናቸው፡፡ በዚህ በትንሹ ያልታመኑ በትልቁ ሊታመኑ አይችሉም፡፡
ጠቅላይ ሚኒሰትሩ የምር ውይይት ማድረግ ከፈለጉ የወጣቶችና ሰፖርቲ ሚኒስትሩ ሬዲዋን ሁሴን ስብሰባ ላይ የነገራቸውን የሚናግሩ ወጣቶችን መሰብሰብ ሳይሆን በአዲስ አበባ እና በየክልሉ ከተሞች ሰላማዊ ሰልፍ ሊወጡ ፈልገው የተከለከሉትን ወጣቶች ወይም ደግሞ የደህንነት ሰራተኞች በየጊዜው እያፈሱ በእስር ቤት የሚያጉሩዋቸውን ወጣቶች ማናገር አለባቸው፡፡ ለምሳሌ እነ አንጋው ተገኝ እና ጓደኖቹን ከጎንደር፣ እነ ስንታየሁ ቸኮል፣ ወይንሸት ሰለሺ  ከአዲስ አበባ፣ እነ ምርቱ ጉታ ከአዳማ፣ እነ ዘሪሁን ገሰሰ ከወሎ፣ ወዘተ ጠርተው ምን ጎደለባችሁ? ማለት ነበረባቸው፡፡ ለነገሩ እንጂ ጉዳዩ ከወጣቶቹ ጋር የሚያልቅ አይደለም፡፡ ጠቅላይ ሚኒስተሩ እና ጓዶቻቸው የምር ለዚህች ሀገር መፍትሔ የመፈለግ ፍላጎት ካላቸው ከማን ጋር መነጋገር እንዳለባቸው ይጠፋቸዋል ብዬ አላምንም፡፡
ዛሬ በጫካ የሚገኙት የሰላማዊ ትግል መስመር ሲዘጋ ወደ ትጥቅ ትግል የገቡት ልጆች በምንም መመዛኛ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ለወጣቶቹ እንደገለፁት በውይይት የሚገኘውን ውጤት ዘንግተው እና በድንጋይ ውርወራ መንግሰት ለመገልበጥ ፈልገው አይደለም፡፡ ይልቁንም መንግሰታቸው ውይይት ሰለሚፈራ እና በተወያየበት ሁሉ በጉልበት አንበርክኮ ለመውጣት ሰለሚፈልግ ነው፡፡ አሁንም በከተማ በድንጋይ ውርወራ መንግሰት ፋታ ለመከልከል የተዘጋጁ ወጣቶች መንግሰት ባዘጋጀው አደረጃጀቶች/ፎረሞች ብቻ እንዲሳተፉ በመምከር መፍትሔ አይገኝም፡፡ የተለያየ አስተሳሰብ ያላች ወጣቶች ሊደራጁበት የሚችሉበት መንገድ መከፈት አለበት፡፡ ትላንት ለእስር የተዳረገቸው የአንድነት አባል የነበረችው ወይንሸት ሰለሺ  በኢህአዴግ ወጣት አደረጃጀት የነበረች ቀጥሎም የባለ ራዕይ ወጣቶች አባል የነበረች ነች፡፡ በሲቪል ሶሳይቲነት ይንቀሳቀስ የነበረው ባለራዕይ ወጣቶች መንቀሳቀስ ሲከለከል አንድነት ተቀላቅላ ስርዓቱን ለመለወጥ ቆርጣ ተነሳች፡፡ ለዚህም ብላ አንድነትን ተቀላቀለች፡፡ አንድነት በህገወጥ መንገድ ሲፈርስ ደግሞ በፌስ ቡክ ትግል የምታደርግ ንቁ ወጣት ነች፡፡ በእኔ እምነት ወይነሸት ላይ የሚያቀርቡት አንድም ወንጀል የለም፡፡ ወንጀለኞች ቢወነጅሏት ለልጇ ዲሞክራሲያዊት ሀገር ለመመስረት ባደረገቸው ጥረት ነው፡፡ ለሆዴ አላድርም ነፃነት ይበልጥብኛል ሰለአለች ብቻ ነው፡፡
አሁንም ጥሪያችን መንግሰት የማሪያሙን መንገድ ክፍት ያድርግ በነፃነት መደራጃት የምንችልበትን መንገድ ክፍት ማድረጉን ማረጋገጫ ይስጠን፣ ከዚያ የኢትዮጵያ ህዝብ ምን እንደሚያደርግ ያውቃል፡፡ በአዲስ አበባ የተኮለኮሉ ኮብል እስቶኖችን መናፈቅ ትቶ በውይይት ወደ መፍትሔ ይገባል፡፡ ለመጀመር በአዲስ አበባ የወጣትና ሴቶች ፎረም አባል ያልሆኑ የአዲስ አበባ ልጆችን ለማነጋገር ከወሰኑ ትልቅ እርምጃ ነው፡፡ ክቡር ጠቅላይ ሚኒሰትር ስራ ላለማብዛት እኛ የዞን ዘጠኝ ወጣቶችን ወክለናል ያነጋግሩዋቸው፡፡
መልካም አዲስ ዓመት በተለመደው ሁኔታ ሳይሆን ለለውጥ የእውነትም አዲስ ዓመት ማድረግ የሁላችንም ሃላፊነት መሆኑን መዘንጋት የለብንም፡፡ ክብር ህይወታቸውን ለሰጡ ጀግኖቻችን ….
ቸር ይግጠመን!!!!!

No comments:

Post a Comment