Friday, March 7, 2014

የፍርድ ቤት ያለህ ……



በታሕሳስ ወር አጋማሽ አንድ የፌዴራል ፖሊስ መኮንን ችሎት በመድፈር ተከሰው አሁንም ጉዳይ በፍርድ ሂደት ላይ እንደሆነ እናውቃለን፡፡ ፖሊሶቹ አድመው አሁንም ማን እንደሆነ አላወቅንም ብለው አለቃቸው ፍርድ ቤት እንዲቀርቡ አስደርገዋል፡፡ አሁን አላውቅም ድሮ የመኮንን ማዕረግ የሚሰጣቸው ሰዎች ከፖሊስነቱ በተጓዳኝ የህግ ትምህር እውቀት እንዳላቸው ለማንም ግልፅ ነው፡፡ የዚህ ዓይነት ድፍረት መዳፈር አይቻልም፡፡ ይህን ጉዳይ ያነሳሁት በመፅሔት ላይ በተሰጠ አስተያየት ተደፍርኩ ያለ ችሎት አቶ አስራት ጣሴን የአምስት ወር የእስር ቅጣት በሁለት ዓመት ገደብ መወሰኑን ታዝቤ ነው፡፡ ከአምሰት ወሩ ይታሰብ አይታሰብ ባይታወቅም ለአስር ቀን በወህኒ ቤት እንዲቆዩም ተደርጎዋል፡፡ ለህግ ልዕልና ሲባል ፍርድ ቤት እንዲከበር ከዚህ የበለጠ መሰዋዕትነት ለመክፈል የተዘጋጀን ሰው ችሎት ደፍረሃል ማለት ግን ጠብ ያለሽ በዳቦ ነው፡፡
ለማነኛውም መኮንኑ ይግባኝ ሰለጠየቁ በሚል በገንዘብ ዋስትና ከእስር ያሰፈቱት የፌዴራል የመመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤቶች ፕሬዝዳንት አቶ አስራትን ግን ሊያስፈቱ አልቻሉም፡፡ ከሲቪል ሰርቪስ የሚሰበሰቡት ዳኞች የፖለቲካ ታማኝነት እንጂ የህግ እውቀታቸው ዝቅተኛ ነው የሚል እምነት አለን፡፡ ስለዚህ ለገዢው ፓርቲ ያዳላሉ ማለት እንዴት ሆኖ ነው ችሎት መድፈር የሚሆነው፡፡ በቅርቡ የፍትህ ሰርዓቱን የመልካም አስተዳደር መርዓ ግብር በቀረበበት ወቅት አቅመ ቢስ ያለውን ፍርድ ቤት እኛስ ብንለው ምን ይለዋል፡፡ አቅም የሌላቸው ዳኞች ተገቢውን ፍትህ ይሰጣሉ ብለን አለማመን መብታችን ነው፡፡
የፖለቲካ ትግል ውስጥ የገባነው ትክክለኛ የፍትህ ሰርዓት እንዲዘረጋ ጭምር ነው፡፡ መንግሰትን ፍርድ ቤት ገትረን መብታችንን የሚጠብቅልን ፍርድ ቤት ቢኖር በእውነት ወደ ፍርድ ቤት እንጂ የፖለቲካ ትግል ምን አመጣው፡፡ የዚህ ጊዜ ፖለቲካ የሚሆነው መሪ ለመሆን ዕጩ ሆኖ መወዳደር ብቻ ነው፡፡ ትግል የታባቱ፡፡
የፀረ ሙስና እና ሰነምግባር ኮሚሽን ባስጠናው ጥናት ተዓማኒነት ከጎደላቸው ተቋማት አንዱና ዋነኛው ፍርድ ቤቶች እንደሆኑ ገልፆዋል ይህን ተቋም ትክክለኛ ፍትህ ሊሰጠኝ አይችልም ብዬ ማመን በምን መንገድ ነው ችሎት መድፈር የሚሆነው፡፡ በግሌ በፍርድ ቤት ላይ እምነት ቢኖረኝ ኖሮ ያለ ስሜ የአሸባሪነት ዶክመንተሪ መስሪያ ስሆን በማግሰቱ ነበር ፍርድ ቤት የምገትራቸው፡፡ ነገር ግን ፍርድ ቤቱ ከፖለቲካ ጥቅሻ ነፃ ነው ብዬ ስለማላምን አላደረኩትም፡፡ አንድ ቀን እንዳውም በዚሁ ዶክመንተሪ እኔው ልከሰስ እችላለሁ፡፡ ፍርድ ቤትም ጥፋተኛ ነህ ተከላከል ብሎ ዕድሜ ልክ ሊፈርድ ይችላል፡፡
በአቶ አሰራት ጣሴ ክስ መነሻ ዳኛዋ በሌላ ክስ የማይፈለጉ ከሆነ ልቀቋቸው ብለው ለፖሊስ ሲያዙ፤ ፖሊሱ ያለምንም ማንገራገር አለቅም ሲል ደነገጥኩ፡፡ ፖሊሱ ይዞት የመጣውን እሰረኛ የሚለቅበት ሰርዓት ቢኖርም ክብርት ዳኛ ማዘዣው በፅሁፍ ሲደርሰን በህጉ መሰረት እንፈፅማለን የሚል ለፍርድ ቤት የሚገባን ክብር የማይስጥ ፖሊስ ይህን እንዲያደርጉ የሚያስገድድ ፍርድ ቤት ነፃ ነኝ ቢለኝ መብቱ ቢሆንም፤ እኔ ደግሞ አይመስለኝም ነፃ አለመሆናችሁን ብዙ ምልክት አለ ማለት መብቴ ነው፡፡

የፌዴራል የሥነ ምግባርና ጸረ ሙስና ኮሚሽነር አሊ ሱሌይማን እንደተናገሩት “በአሁኑ ወቅት ጠበቃ የሚመረጠው በሙያ ብቃትና በምስጉን ስነ ምግባሩ  ተከራክሮ እውነት ያወጣል በሚል ሳይሆን ምን ያህል ደላላ አለው? ዳኛና ባለስልጣናትን ያውቃልን? በሚሉ መስፈርት ነው” ብለዋል (አዲሰ ዘመን ጋዜጣ የካቲት 2/2006)፡፡ ይህ አሰተያየት ጠበቆችን ለመዝለፍ ቢመስልም ትክክለኛው ግን ደላሎች የሚያገናኙት ዳኞች፣ በባለስልጣን ጥቅሻ የሚሰሩ ዳኞች መኖራቸውን ነው፡፡ የጠበቃ፣ የዳኛ እና የባለስልጣናት ህገወጥ ግንኙነት የሰፈነበት የፍትህ ሰርዓት ትክክለኛ ፍትህ አይሰጠንም ብሎ ማመን እንዴት አድርጎ ነው ችሎት/ፍርድ ቤትን መድፈር የሚሆነው፡፡

“ፍትህ ከኢህአዴግ ፍርድ ቤቶች ይገኛል ተብሎ ሳይሆን ለታሪክ ምስክርነት ነው” ብሎ ጥርጣሬን መግለፅ ነው ወይስ “በደላላና በባለሥልጣን ጥቅሻ ይስራል” ማለት፡፡ ሁለቱም እውነት ከሆነ እውነት ነው፡፡
ሌባ ዳኞች ብለው ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ በምክር ቤት ሲሳደቡ እረ በህግ ማለት ያልቻለ ፍርድ ቤት ዛሬ ደግሞ ችሎት በአንድ መጣጥፍ ውስጥ በተሰጠ አሰተያየት ተደፈረ ማለት እንዴት እነዴት ነው ነገሩ፡፡

No comments:

Post a Comment