Monday, March 14, 2016

የጠቅላይ ሚኒሰትር ሀይለማሪያም ደሳለኝ ሪፖርት መድረሻው “የመልካም አስተዳደር ችግር እንፈታለን፤ ሰልጣን ግን አንለቅም” መሆኑ ነው?



የጠቅላይ ሚኒሰትር ሀይለማሪያም ደሳለኝ ሪፖርትን በወፍ በረር ስንቃኛው የሚከተለው ይዘት እንዳለው መረዳት እንችላለን፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ዓመቱ ከመጠናቀቁ ቀደም ብለው የዕድገት ቅናሽ እንደሚኖር በሰበብ ደግፈው አምነዋል፡፡ ይህም ደግሞ ገዢው ፓርቲ ከአስራ አንድ በመቶ የእድገት ልክፍት በግድም ቢሆን መላቀቁን የሚያሳይ ነው፡፡ ከዚህ ቀደም የፈለገውን ያህል ተግዳሮት ቢፈጠር ያልተተገበሩ ግዙፍ ዕቅዶች ዝርዝር ቢቀርብም “ቢሆንም 11 ከመቶ አድገናል” እንደ ነበር አንዘነጋውም፡፡ ጠቅላይ ሚኒሰትሩ የእድገት ቅናሽ መኖሩን  ቢያምኑም “ትንሽ ቅናሽ ያሳያል” በሚል ማለፋቸው ዝናብ ከዘነበ መልሶ ለማቅራራት ዝግጅት እንዳለ አመላካች ነው፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትሩ ባለፈው ዓመት ማጠቃለያ ሪፖርት ሲያቀርቡ የሰበታ-ጅቡቲ የባቡር መስመር ጥቅምት/2008 ላይ እንደሚጠናቀቅ ተናግረው የነበረ መሆኑን ሳንዘነጋ ዛሬም 97 ከመቶ ተጠናቆዋል ብለውናል፤ ይህ አፈፃፀም ስራ ለመጀመር የሚያስችል እንደሚሆን ቢታመንም ባቡሩ አሁንም ስራ አልጀመረም፡፡ የአዲስ አበባ ቀላል ባቡር በኤሌትሪክ ችግር ፈተና እየገጠመው ጄኔሬተር ሊገዛ ነው እየተባለ ባለበት ሁኔታ አሁን ባለው የኤሌትሪክ አቅርቦት ችግር ከ700 ኪሜ በላይ መስመር እንዴት ሊያደርጉት እንደሆነ የጠየቃቸውም የለ፤ ጠቅላይ ሚኒሰትሩም መረጃ ሊሰጡን አልቻሉም፡፡ ከባቡር መሰረተ ልማት ጋር ተያይዞ የቀረበው አስቂኝ ነገር “በዓለም ኢኮኖሚ መቀዛቀዝ” በሚል ሰበብ ሌሎች በዕቅድ የተያዙ መስመሮች ስራ ሊጀመር እንደማይችል ፍንጭ ስጥተውናል፡፡
በተመሳሳይ የስኳር ነገር ለኢህአዴጎች ገዳቸው አይደለም፡፡ ከታቀደው ተቀንሶ በተወሰኑት ትኩረት ይሰጥ የሚል ሃሳብ መያዙን ጠቅላይ ሚኒሰትሩ ይፋ አድርገዋል፡፡ ደስ የሚለው የጠቅላይ ሚኒሰትሩ አባባል ደግሞ “ጓጉተን የምናወጣው ዕቅድ የማሰፈጸም አቅማችንን ጋር አልተመጣጠነም” የሚለው ነው፡፡ እኛም እያልን የነበረው አሁንም የምንለው አቅም የላችሁም ነው፡፡ የገንዘብ ብቻ አይደለም - ገንዘብ የማሰባሰብ አቅም ማለት ነው፡፡ የዕውቀት ብቻ አይደለም - እውቀት የማሰተባበር አቅም ነው፡፡ ተገባብቶ አሰተባብሮ የመስራት አቅም የላችሁም ነው ያለነው፡፡ ጉጉት ብቻ ናቸሁ!!!
ጠቅላይ ሚኒስትሩ የሀገር ውስጥ ቁጠባን ከማሳደግ አንፃር ዋነኛ ያልዋቸውን የመኖሪያ ቤት እና የጡረታ መዋጮ በሪፖርታቸው ውስጥ አንስተዋል፡፡ በእርግጥም ቆጥቦ ህዝቡ የሚጠቀምባቸው ሳይሆን መንግሰት ከአቅሙ በላይ እየለጠጠ ለሚይዛቸው ፕሮጀክቶች ፋይናንስ ማድረጊያ እንደሆኑ ከጅምሩም ግልፅ ነበር፡፡ ለምሳሌ 40/60 በሚል ቆጥቡ ቤት ታገኛላችሁ ተበሎ በጉጉት የቆጠቡ ሰዎች ፕሮግራሙን 100/0 በማድረግ የዜጎችን ሀበት ይዞ በኋላ ብር አትሞ ለመመለስ የተዘጋጀ ይመስላል፡፡ ሌላው ጡረታን በሚመለከት አብዛኛው በአነሰተኛ ስራ ላይ የተሰማራ ዜጋ ትክክለኛ የግብረ ከፋይ መለያ በሌለበት ሁኔታ ከድሆች ላይ በጡረታ ስም ገንዘብ መንግሰት እየዘረፈ ይገኛል፡፡ ለምሳሌ አንድ በሰተናጋጅነት የሚሰራ ሰራተና ሰድሰት ወር ጡረታ ከፍሎ የሚሰራበትን ድርጅት ቢለቅ ጡረታ ስለመክፈሉ የሚሰጠው ምንም መረጃ የለም፡፡ ቀጣይ የሚገባበት ድርጅት እንደ አዲስ ጡረታ እየቆረጠ ለመንግሰት ገቢ ያደረግል፡፡ ይህ ዜጋ በምንም ሁኔታ የዚህ የጡረታ መርሃ ግብር ተጠቃሚ ሊሆን አይችልም፡፡ ይህ ደግሞ አሁን በግልፅ የሚታይ ዘረፋ ነው፡፡ የዚህ ዓይነት በመቶ ሺ የሚቆጠሩ ዜጎች በግል ዘርፍ ውስጥ በጡረታ መዋጮ ስም እየተዘረፉ መሆኑን ማስታወስ ያስፈልጋል፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትሩ በሪፖርታቸው በቅጡ መረጃ ሳይስጡ ያለፉት የውጭ ኢንቨስትመንት የሚመለከተውን ክፍል ነው፡፡ ከዚህ ቀደም በኦሮሚያ አካባቢ የተነሳውን ንቅናቄ አሰመልክት በኢንቨስትመንት ላይ ሊፈጥር የሚችለውን ተፅዕኖ ያብራራው ስለሆነ እዚህ መድገሙ አስፈላጊ ሆኖ አላገኘሁትም፡፡ ለማነኛውም አሁንም ጠቅላይ ሚኒስትሩ የውጭ ኢንቨሰትመንት የተሻለ ነው በሚል አልፈውታል፡፡ በምንም መለኪያ ግን አሁን የተፈጠረው ሁኔታ የውጭ ኢንቨስትመንት ሊስብ አይችልም፡፡ በተለይ ጠቅላይ ሚኒሰትሩ እንዳመኑት “ይህ ችግር ከትግራይ እስከ ደቡብ ጫፍ” መሆኑን በኦሮሚያ ቀድሞ መታየቱ ሌሎቹ ችግር የለባቸው ማለት እንዳልሆነ ማረጋገጣቸው በኢንቨስትመንት ላይ ጉልዕ ጫና አለው፡፡ ኢንቨሰተሮች ደግሞ ይህን ለማወቅ አይቸገሩም፡፡ ይህ ደግሞ የሚታየው በቀጣይ ዓመታት ሲሆን እስከ አሁን ድረስም በኢትዮጵያ ኢንቨስት ለማድረግ የጀመሩትም በሆን ቢያንስ ረዘም ያለ የዝግጅት ጊዜ መውሰዳቸው የግድ ነው፡፡ ይህ ደግሞ በተለያየ መልኩ በተግባራ ተመልክተነውል፡፡ ሰለዚህ የውጭ ኢንቨስትመንት በቅርቡ ያድጋል ብሎ መገመት አይቻለም፡፡ ሰለዚህ በሪፖርቱ በደፈናው የውጭ ኢንቨስትመንት ካለፈው የተሻለ በሚል የቀረበው ተዓማኒነት የለውም፡፡
በሀገራችን ዙራ መለስ የሚታየው ያለመረጋጋት በኢንቨስትመንት ብቻ ሳይሆን እንደ ሀገር መቀጠላችንን ስጋት ላይ ሊጥል ይችላል የሚል ግምት ያላቸው ሰዎች ቀላል አይደሉም፡፡ እንደዚያም ሆኖ ግን ገዢው ፓርቲ ነገሩን ከስሩ አጥንቶ ሁሉንም ያገባኛል ባይ የሚያሳትፍ መፍትሔ ከመፈለግ ይልቅ አሁን በተለመደ አሮጌ መንገድ መሄድ የመረጠ ይመስላል፡፡ ከወትሮ በተለይ “በሌላው አካል ላይ ጣት መቀስር ይቁም” የሚል ሃሳብ ጠቅላይ ሚኒሰትሩ ያነሱ ቢሆንም አሁንም ቢሆን ግን ለመፍትሔው እሩቅ እንደሆኑ የሚያሳያው “በተሃድሶ” ጊዜ ችግር የፈቱበትን መንገድ አሁንም ሊደግሙት ያሰቡ ይመስላል፡፡ ኢህአዴግ የዚህችን ሀገር ለመፍታት ከእኔ ሌላ ማንም የለም የሚል ይመስላል፡፡ አሁን ያለውን በመልካም አስተዳደር ተሸፍኖ የሚቀርብልንን መንግሰታዊ ሌብነት እና ውስልትና በቸልታ እንድናልፈው የሚጠይቁን በሚመስል ሁኔታ መቶ በመቶ ተመርጠናል ባሉበት ዓመት መቶ በመቶ ሲከሸፉ ሌላ አማራጭ ማሰብ አልተቻላቸውም፡፡ መልዕክቱ ግልፅ ነው፡፡ “የመልካም አስተዳደር ችግር እንፈታለን፣ ስልጣን መልቀቅ ግን አይታሰብም” የሚል ነው፡፡
የመልካም አስተዳደር ችግሩን ደግሞ የሚፈቱት ለወጣቱ የስራ እድል የሚፈጥሩ ከዚህ ቀደም ሲዘረዝሩልን የነበሩትን “በጉጉት” ላይ የተመሰረቱ ዕቅዶችን በማቅረብ ነው፡፡ ወጣቱ ስራ ካገኘ ሌላ ጥያቄ ያለው አልመስላቸውም፡፡ የወጣቱ ጥያቄ የስራ መፍታት ብቻ አይመስለኝም፡፡ በሀገሩ እኩል እንደ ዜጋ መቆጠር እና በነፃነት የመኖር ጭምር ነው፡፡ በስራ ፈጠራ ቢሆን አሁን የሚታየውን ስራ አጥነት እንፈታለን እየተባለ በጎን ደግሞ በስራ ላይ ያሉትን የትራንስፖርት አገልግሎት ሰጪዎችን በመንግሰት ጣልቃ ገብነት ከስራ ለማስወጣት እቅድ እንዳለም ከሪፖርቱ ለመረዳት ከባድ አይደለም፡፡ በቅርቡ ወደ ስራ እንዲገቡ የሚታሰቡት “የቢሾፍቱ” አውቶብሶች ዋና ዓላማቸው ባለፈው የስራ ማቆም አድማ በማድረግ አንገታቸውን ቀና ያደረጉትን ዜጎች አንገት ለማስደፋት ነው፡፡ ለማነኛውም ቀኑ ደርሱ ውጤቱን አብረን የምናየው ይሆናል፡፡ ይህ አካሄድ የቁርጡ ቀን መቃረቡን የሚያሳይ ይመስለኛል፡፡
ጠቅላይ ሚኒሰትራችን በሰጡት ማብራሪያ አንድ አዲስ ነገርም አስረግጠው ነግረውናል፡፡ በሀገራችን “የማንነት ጥያቄ የተመለሰ ጉዳይ ነው” ብለውናል፡፡ ማንነት “ኢቮልቭ” የሚያደርግ የሚፈጠርና የሚጠፋ መሆኑ አብቅቶለታል፡፡ በኢትዮጵያ ውስጥ ከአሁን በኋላ አዲስ ማንነት አይፈጠርም፡፡ ይህን ደግሞ የፌዴሬሽን ምክር ቤት እና ክልሎች ተነጋግረው ቋጠሮ ማበጀት አለባቸው የሚል መልዕክት አስተላልፈዋል፡፡ ይህን ንግግር የቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትር አድርገውት ቢሆን እንደ ህግ ልንወስደው እንችል ነበር፡፡ አሁን ግን እንደ የግል አስተያየት አድርገን ከመውሰድ ውጭ ህግ ነው ለማለት ውጤቱን መጠበቅ ይኖርብናል፡፡ እነ ዳንኤል ሺበሽ “ቁጫ ቁጫ ነው ጋሞ አይደለም” በሚል በኢህአዴግ መስመር ጥያቄ በማቅረባቸው ዛሬ በእስር ላይ ይገኛሉ፡፡ ኢህአዴግ የማንነት ድንበር ምን ጋ ሲደርስ እንደሚቆም ዝርዝር መመሪያ ሊሰጥ ይገባል፡፡ በእግረ መንገድ የጉራጌ ብሔር/ብሔረሰብ የባህል ልብስ ደንብ ወጣ ሲባል ሰምቻለሁ …. አውነት ይሆን?
ባጠቃላይ የጠቅላይ ሚኒትሩ ሪፖርት በእኔ ግምት ሪፖርት ሳይሆን አሁንም ሌላ እቅድ ነው አበክረን፣ጠንክረነት እንሰራለን የሚል፡፡አሁንም ልምድ የሚቀመርበት … የሚማሩበት ሁኔታ ነው ያለው፡፡የኢትዮጵያ ህዝብ ዋነኛው ችግር ደግሞ ሰማርት ስልክ መሆኑ ተደርሶበት ሰማርት ስልክ በተመጣጣኝ ዋጋ እንድናገኝ ጥረት ይደረጋል የሚል እቅድ ቀርቦልናል፡፡ በስብሰባው ላይ ህውሃት ከሞላ ጎደል የተሟላ ሲሆን የሌሎች ድርጅት ከፍተኛ ሃላፊዎች ያለመገኘት ምን ማለት ይሆን?
ቸር ይግጠመን
ግርማ ሠይፉ ማሩ

No comments:

Post a Comment