Tuesday, March 29, 2016

የጠቅላይ ሚኒሰትሩ የለበጣ ስብሰባዎች!!!



ጠቅላይ ሚኒሰትር ኃይለማሪያም ሰሞኑን ስራ በዝቶባቸው እንደከረሙ ሁላችን እንረዳለን፡፡ የስራው ውጤታማነት የሚለካው ግን በሚያሰገኘው ፍሬ ነው፡፡ በእኔ  ግመገማ ስራቸው ለውጤት እንዳልሆነ የተረዳሁት ዘግየት ብዬ “ከተቃዋሚ ፓርቲ” ተብዬዎች ጋር ውይይት ካደረጉ በኋላ ነው፡፡ ቀደም ሲል ከንግድ ማህበረሰብ ቀጥሎም ከምሁራን ጋር ውይይት አድረጉ ሲባል የምር እኚህ ሰው የሚመሩት ድርጅት ልብ ገዛ ብዬ ተሰፋ ማድረጌ አልቀረም ነበር፡፡ ምን ያደርጋል በተመሳሳይ ለህዝብ ግንኙነት ሲባል የሚያደርጉት መሆኑን ያጋለጠ ስብሰባ መጋቢት 14 ቀን 2008 በማድረግ ተስፋዬ አጨለሙት፡፡ የብዙ ሰው ሰሜት እንደሚሆንም ተሰፋ አደርጋለሁ፡፡ ለነገሩ ከሁሉም ጋር የሚያደርጉት ስብሰባ የኢህአዴግ ክፉ መንፈስ የተጫነው ነበር፡፡ ከአቋም ፍንክች እንደማይሉ፣ እነርሱም ሌቦች ሌላውም ሌባ (የመንግሰትና የግል ሌቦች) መሆኑን በሚያስረግጥ መንፈስ የተካሄዱ ናቸው፡፡
ነጋዴዎችን ሰብሰበው ያስተላለፉት የመጨረሻ መልዕክት መንግስት ማሰር ቢፈልግ ሁሉም ከእስር ሊተርፍ እንደማይችል አስጠንቅቀው እና በተቻለ መጠንም አሸማቀው ነው፡፡ መልዕክቱ አሁንም ቢሆን ፀባይ ካሳመራችሁ የምናስረው እስር ቤት ሟቋቋም ድረስ የደረሱትን ብቻ ነው የሚሉ ይመስላሉ፡፡ ጠቅላይ ሚኒሰትራችን ነጋዴዎች እስር ቤት እንዳላቸው የነገሩን ነገር ብዙ የሚገርም አይደለም፡፡ በእኛ ሀገር አንድ የውጭ ኤምባሲ እስር ቤት እንደነበራው ይውራ ነበር (የኤርትራ ኤምባሲ)፤እፍኖም ይወስድ ነበር፡፡ ይህ ይሆን የነበረው ግን በመንግሰት የደህንነት ሰዎች ድጋፍና ትብብር ጭምር ነው፡፡ በእኔ እምነት አሁንም እስር ቤት ያቋቋመው ነጋዴ የደህንነት ድጋፍ አልነበረውም ብዬ አላምንም፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትሩ አሁንም የትኛው ነጋዴ የት ቦታ እስር ቤት አደራጅቶ ከማን ጋር ይስራ እንደነበር በግልፅ በስም ሊገልፁልን ግድ ይላቸዋል፤ በዚሁ ሁኔታም ክስ ተመስርቶ ማየት እንፈልጋል፡፡ (Name and Shame)፡፡  በዚህ አጋጣሚ ፕሮፌስር መስፍን ይህን አስመልክቶ በፌሰ ቡክ ገፃቸው ላይ ማለፊያ ነገር አስነብበውናል፡፡ የሚገርመው በጠቅላይ ሚኒስትር ደረጃ ይህ መነገሩ ነው እንጂ፤ አንባገነን ስርዓት ባበት ማንም ይህን ሊያደርግ ይቸላል የሚል ነው፡፡ ሁላችንም እንደምናውቀው በሶማሊያ ብዙ የጎበዝ አለቆች በነጋዴዎች የሚታዘዙ ማሰሪያዎች አሉዋቸው፡፡ ፀጥታም የሚያስከብሩት እነዚሁ የጎበዝ አለቆች ናቸው፡፡ እስከ አሁን ድረስ ይህ የቀረ አይመሰለኝም፡፡
የነጋዴውን ስብሰባ ጉዳይ ከመቋጨቴ በፊት “ነጋዴ በሙሉ ሌባ ነው” የሚል እንደምታ ያለውን ንግግር ጠቅላይ ሚኒሰትሩ ሲያደርጉ ነፃነቱ ያለው እና ነፃነቱን የሚያስከብር የንግድ ምክር ቤት ተወካይ ቢኖር ጠቅላይ ሚኒስትሩ ይቅርታ እንዲጠይቁ ማስገደድ ባይችል ለወጉ ለማረጉም ቢሆን ጥያቄ ያቀርብ ነበር፡፡ ይህ ሁሉ ነጋዴ ግብር እየከፈለ ያቆማትን ሀገር ሁላችሁም ሌቦች ናችሁ፤ ማሰር ብንፈልግ የሚቀር የለም የሚል መልዕክት ማስተላለፍ በፍፁም ተቀባይነት የሌለው ከጠቅላይ ሚኒስትር የማይጠበቅ ንግግር ነው፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትራችን አንድም ቀን በንግድ ተሳትፈው ስለማያውቅ ነጋዴዎች ትርፍ ለማሳደግ የሚወሰዷቸው የተለያዩ እርምጃዎች በሙሉ “የሌብነት ስራ” ነው ብለው ያምናሉ፡፡ ህጋዊ የሆነ የታክስ መቀነስ እንቅስቃሴ በትምህርት/በህውቀት (Legal Tax Evation) የተደገፈ መሆኑን የሚነግራቸው አማካሪ የላቸውም፡፡ አማካሪዎች ተብለው የተሰየሙት ተመሳሳይ በመሆናቸው ለውጥ ሊመጣ አይችለም፡፡
ከነጋዴዎች ቀጥለው ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከምሁራን ጋር ውይይት ማድረጋቸውን ሰምተናል፡፡ ነጋዴዎቹን ሲያነጋግሩ እንደነበረው ሁሉ ከምሁራኑ ጋር የነበረው መንፈስም ያው የኢህአዴግ ክፉ መንፈስ የተጫነው ነበር፡፡ ይህን ስብሰባ ከነጋዴዎቹ ልዩ የሚያደርገው ነገር “ከፈለጋችሁ ፓርቲ አቋቁሙና እንጋጠም” ማለታቸው ነበር፡፡ በእለቱ ስብሰባ የተገኙ ተሳታፊዎች የዋዛ የማይባል ጥያቄ ማንሳታቸውን እኛ አድማጮች ደግሞ በተሰጠው ኢህአዴጋዊ ማብራሪያና ማፈራሪያ ሳይሆን በጥያቄዎቹ መስመር ላይ መሆናችንን ማሳታወስ ግድ ነው፡፡ ምን ማለት ነው? ብሎ ለሚጠይቅ “ይህች ሀገር ነፃነት ያለው ህዝብ መኖሪያ አይደለችም፡፡ ጋዜጣኛም፣ ነጋዴም፣ ፖለቲከኛም፣ ተማሪም፣ ወዘተ በነፃነት የሚኖርበት ሀገር አይደለም፡፡” የሚለውን የምሁራን አስተያየት የምንደግፍ መሆኑን ለመግለፅ ነው፡፡
ከምሁራኑ ስብሰባ ከተሰነዘሩት አስተያየቶች አንዱ ጠቅላይ ሚኒሰትሩ “ደረታችሁን ነፍታችሁ የምትሄዱት” በሚል ከናይሮቢ ጋር ያደረጉት ንፅፅር ሲሆን ይህ ንፅፅር በምንም መመዘኛ ትክክልም ተገቢም ሆኖ አላገኘሁትም፡፡ እውነቱን ለመናገር ለአንድ ኬኒያዊ የኬኒያ መንግሰት ስጋቱ አይደለም፡፡ እኛ ግን መንግሰታችን ስጋታችን ነው፡፡ በእኛ ሀገር ሀፈና የሚፈፀመው ሊጠብቅን በሚገባ መንግሰት ነው፡፡ ኢትዮጵያ ደግሞ እስከ ዛሬ ከሸብርተኛ ቡድን ነፃ የሆነችውን ጠቅላይ ሚኒሰትሩ ስምም ፆታም አልገልፅም ብለው ነገር ግን እስከ አያት ስሟ የነገሩን ጋዜጠኛ ርዕዮት ዓለሙ ጉቤቦን በግፍ በማሰራቸው አይደለም፡፡ እኛ ኢትዮጵያዊያን በዚህ ደረጃ ለሸብር የደረሰ ሰነ ልቦና ስለሌለን ነው፡፡ ርዕዮትን የፈቷት በግፊት መሆንን ማመናቸው አንድ ነገር ሆኖ፤ በህገወጥ ሁኔታ በእስር እንደነበረች ግን የምንረሳው አይደለም፡፡ (የፍርድ ቤቶች ውሳኔ ልክ ነው ቢባል እንኳን የእስር ጊዜ ጨርሳ አንፈታም ብለው ከህግ ውጭ አስረው ነበር ያስቀመጧት) በኋላ ጠቅላይ ሚኒሰትሩ በግፊት እንደተፈታች ያመኑትን ማለት ነው፡፡
ከላይ የነበሩትን ስብሰባዎች የለበጣ እንደነበሩ ግምት እንድወስድ ያደረገኝ ስብሰባ የተካሄደው መጋቢት 14/2008 “ከተቃዋሚ ፓርቲ” ተብዬዎች ጋር ያደረጉት ውይይት ነው፡፡ በእኔ እምነት የውይይቱ ዋልታና ማገር የነበረው እነዚህ ፓርቲዎች በሀገራችን ከሚያመጡት የዲሞክራሲ ትሩፋት ይልቅ ለሆዳቸው መሙያ የሚሆነውን ቀለብ አስፋፈር ላይ የነበረ መሆኑ ነው፡፡ ተሳታፊዎቹ በሙሉ በሚባል መልኩ ደስተኛ የሆኑት ኢህአዴግ ከመንግሰት ካዝና ከሚደርሰው ገንዘብ ግማሹን ሊያካፍላቸው ፈቃደኝነቱን በጥቂቱም ቢሆን በማሳየቱ ነው፡፡ ለእነዚህ ተቃዋሚ ተብዬዎች ከዚህ ውጭ መልካም ዜና የለም፡፡ በስብሰባው ያልተገኙትም ቢሆን ያናደዳቸው ገንዘቡ ለፓርቲዎች የጋራ መድረክ አባላት ብቻ መሰጠቱ ነው፡፡ በክፍያው ላይ ቢካተቱ አብረው ጮቢ እንደማይረግጡ መረጃ የለንም፡፡ ከዚህ ውጭ መልካም ጅምር ብለው የኢዴፓው መሪ የገለፁት ምርጫን አስመልክቶ ይደረጋል ያሉት ለውጥ ነው፡፡ ይህ አባባል በእውነቱ በኢትዮጵያ ፖለቲካ ውስጥ ለቆየ ሰው ፓርቲዎች ስልጣን የማይዙት ወይም ተወካይ የማይኖራቸው ህዝቡ ተቃዋሚዎችን በአብልጫ ስለአልመረጠ እና “አብላጫ ድምፅ ያገኘ ያሸንፋል” በሚለው የምርጫ ህግ ምክንያት ያስመስለዋል፡፡ ጠቅላይ ሚኒሰትሩም “ምን አባታችን እናድርግ ህዝቡ ሲመርጠን” ያሉትን እንደመደገፍ የሚቆጠር ነው፡፡ በኢትዮጵያ ትልቁ ችግር እኩል መወዳደሪያ ሜዳ ያለመኖሩን አለመቀበል ነው፡፡ ይህ ደግሞ ከኢህአዴግ ጋር እንደመቆም የሚቆጠር ነው፡፡ ለነገሩ ኢዴፓ ከኢህአዴግ ጋር ለምን ቆመ አይባልም፣ ከዚያ ውጭ የት ሊቆም ይቸላል፡፡ ግቡም ትንሸም ቢሆን የፓርላማ ወንበር ማግኘት ነው፡፡
ለማነኛውም ጠቅላይ ሚኒሰትሩ “ተቃዋሚ ተብዬዎች” ምን እንደሚፈልጉ ገብቶዋቸዋል፡፡ ሆዳቸውን የሚሞሉበት ገንዘብ እንደሚያገኙ ቃል ተገብቶላቸዋል፡፡ “ተቃዋሚ ተብዬዎችም” ምን እንደማይችሉም አውቀዋል፡፡ መሻሻል የሚገባቸውን አዋጆች አጥኑና አምጡ በህጉ መሰረት ይታያል ብለዋቸዋል፡፡ እነዚህ አንደ ገፅ ሰርዓት ያለው መግለጫ መፃፍ ለማይችሉ ተቃዋሚዎች ጥናት አጥኑና አምጡ ከባድ ፈተና ነው፡፡ ሌላው ጠቅላይ ሚኒሰትሩ ያልገባቸው ደግሞ የሰበሰቧቸው “ተቃዋሚዎ ትብዬዎች” በኢትዮጵያ ህዝብ ዘንድ አንድም ቦታ የሌላቸው መሆኑን ነው፡፡
ሰለዚህ በቀጣይም ከህዝቡ ጋር የሚካሄትዱትም ሆነ የተካሄዱት ስብሰባዎች እንደ ከዚህ ቀደሙ የፎረም እና የኢህአዴግ ልዩ ልዩ አደረጃጀቶች ውሰጥ በንቃት የሚሳተፉ ሰዎች ተገኝተው ድራማ የሚካሄድባቸው እንደሆነ ግምት ወስደና ወይም ገብቶናል፡፡ ይህ ደግሞ የነፃነት ቀን መምጫውን ያዘገየው እንደሆን እንጂ ጨርሶ አያስቀረውም የሚል እምነት አለኝ፡፡ መፍትሄው ከዚህ በፊት ፀረ-ህዝብ፣ ጸረ -ምናም እያላችሁ ያገለላችሁትን ቡድኖችና ግለሰቦች በንቃት ማስተፍና ትክክለኛውን ሁኔታ መገንዘብ ነው፡፡ በተጨማሪ ያለምንም ቅድመ ሁኔተ ያለ አግባብ በእስር ላይ የሚገኙት ታጋዮች መፍታት ነው፡፡ ስብሰባም ካስፈለገ …….
ቸር ይግጠመን
ግርማ ሠይፉ ማሩ

No comments:

Post a Comment