Thursday, April 24, 2014

ለክቡር ጠቅላይ ሚኒሰትር ሀይለማሪያም ያቀረብኩት ጥያቄዎች የሚከተሉት ሲሆኑ መልሶቹን ከኢቲቪ ጠብቁ



ሚያዚያ 15/ 2006
ክቡር ጠቅላይ ሚኒንስትር ከዚህ የሚከተሉትን ጥያቄዎች ሳቀርብ በዚህ ሀገር ምንም ለውጥ አልተደረገም ከሚል ጨልመተኝነት ከመነሳት አለመሆኑን እንዲረዱልኝ እፈልጋለሁ፤
ሌላው በዚህ ሪፖርት ውስጥ እንደ ከዚህ ቀደሙ መሰረተ ቢስ የሆኑ ውንጀላዎች አማራጭ አለን ለምንል የፖለቲካ ፓርቲዎች ላይ ባለማካተቱ እንደ በጎ ጅምር ወስጄ ማመስገን እፈልጋለሁ፤
ወደ ዝርዝር ጥያቄዎች እገባለሁ፤
1.   ሪፖርቱ የመጀመሪያ ፓራግራፍ “የትራንስፎርሜሽን አቅዳችን የተለጠጡ ግቦች የያዘ እና አፈፃፀሙም ከሞላ ጎደል በጥሩ መልኩ እየሄደ ያለ ሲሆን በዋናነት ለቀጣና ለሁለተኛው የእድገትና ትራንስፎርማሽን ዕቅድ ዘመን የተሻለ ልምድ የቀሰምንበት የህዝባችን እና የመንግስት የመፈፀም አቅም እየጎለበተ እንዲመጣ ያደረገ ሂደት ነው፡፡ ….. በቀሪው የትግበራ ጊዜም ርብርብ በማድረግ ያስቀመጥናቸውን ግቦች በማሳካት የህዝባችን ተጠቃሚነት የበለጠ እንደምናረጋግጥ እሙን ነው” ይላል፡፡ ከዚህ ውስጥ ሁለት ተቃራኒ ነገሮች ይታዩኛል አንደኛው ልምድ የተቀሰመበት ስለሆነ የተቀመጡት ግቦች በተሟላ ባይሳኩም ችግር የለም የሚል ሲሆን ሌላኛው ደግሞ ያስቀመጥናቸውን ግቦች እናሳካለን የሚል እንደምታ አለው፡፡ ጥያቄዬ የእድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅድ በዋና ዋና በሚባሉት መስኮች አሁንም ይሳካሉ ብለው ያምናሉ ወይስ ልምድ ተቀስሞበታል ብለን እንውሰድ?
ከዚህ ጋር በተያያዘ “ጥቂቶችን በተቀመጠው ግብ መሰረት አንደርስባቸውም ቢሆንም የተሻለ አፈፃፀም ደረጃ እንደምናደርሳቸው ለማየት ተችሎዋል” ሲባል ጥቂቶቹ ምን ምንድናቸው? ለምሳሌ
·         የባቡር መስመር ከታቀደው 2395 ስንት ኪሎ ሜትር ሰራ ይጀምራል?
·         ኢነርጂ ከታቀደው 10000 ሜጋ ዋት በእቅድ ዘመኑ መጨረሻ ሰንት ሜጋ ዋት ይኖረናል?
·         ከታቀዱት አሰር ሰኳር ፋብሪካዎች ስንቱ ማምረት ይጀምራሉ? (ከተቀመጠው ዕቅድ 2.2 ሚሊዮን ቶን ምን ያህል ያመርታሉ? ምን ያህሉ ወደ ውጭ ይላካል?)
·         የገጠር መንገድ ከተቀመጠው 71523 ኪሎ ሜትር ምን ያህሉ ይፈፀማል?
·         በጤና ዘርፍ ከታቀደው ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል ምን ተሰፋ አለ?
ዝርዝሩን ለማሳጠር እነዚህ ጥቂቶች ናቸው ወይ? እነዚህ ሁሉ በጅምር ላይ ባሉበት ሁኔታ ልምድ ተቀስሞበታል ከሚል አልፎ እናሳካለን ብሎ ተሰፋ መሰጠት ተገቢ ነው ብለው ያምናሉ?
2.   ክቡር ጠቅላይ ሚኒሰትር “ሪፖርቱ የአፈፃፀም ጉድለቶች መኖሩን ይጠቁማል”  ጥሩ ዕቅድ አቅዶ በአፈፃፀም ጉድለት ማሳየት መንግሰቶን ተጠያቂ ማድረግ የለበትም ብለው ያምናሉ? የመንግሰት ስልጣን መልቀቅና ተጠያቂነት ምን ግንኙነት አላቸው?
3.   በሀገራችን የዋጋ ንረትን ለመቆጣጠር እርምጃ እየተወሰደ መሆኑን ገልፀዋል በአሁኑ ወቅት ከፍተኛ የስንዴ እና የሰኳር እጥረት እየተሰተዋለ ነው በዚህ ሁኔታ የዋጋ ንረቱ ሊያገረሽ የሚችልበት ሁኔታ እንዳለ ሰጋት አለ፡፡ የዕጥረቶቹ ምንጭ ምንድነው? ዋጋ ለማረጋጋት ከሚወሰደው እርምጃዎች አንዱ የስራ እድሎችን በማሰፋ የዜጎችን የገቢ አቅም ማሳደግ የሚል የተገለፀ አለ ይህ በተቃራኒው የዋጋ ንረት ይፈጥራል እንጂ ዋጋ አያረጋጋም፤ የሚፈጠረውን የዋጋ ንረት ለመቋቋም ተብሎ ቢስተካከል ጥሩ ነው፡፡
4.   በእድገትና ትራንስፎርሜሽን ከተሳኩት ግቦች አንዱ የሀገር ውስጥ ቁጠበን ማሳደግ ነው፡፡ ድሃው ህዝብ በአሁኑ ወቅት በተለያየ መንገድ እየቆጠበ ቢሆንም በቁጠባ ልክ ተጠቃሚ ነው ብለው ያምናሉ? ወይስ ታሪክ ለመስራት የተዘጋጀ ትውልድ ነው የሚል ነው የቁጠባው ዋና መርዕ? ከቁጠባ አንዱ የሆነው በሚሊዮን የሚቆጠሩ ዜጎች ቤት ለማግኘት የሚቆጥቡት ገንዘብ አንዱ ነው፡፡ ከዚህ አንፃር የመጨረሳ እድለ ቢስ መቼ ቤት ያገኛል ብለው ያስባሉ?
5.   የመንግሰት ገቢ በከፍተኛ ደረጃ እያደገ መሆኑ የሚታወቅ ነው፡፡ ከዚህ የሚገኘውን ገቢ በሪፖርቱ እንደተጠቀሰው “ ከብክነት በፀዳ እና በግልፅ ቅደም ተከተል ጥቅም ላይ ለማዋል የጀመርነውን ጥረት አጠናክረን መቀጠል ያለብን ይሆናል” ይላል፡፡ ነገር ግን የዋናው ኦዲተሩ ለምክር ቤቱ ባቀረቡት ሪፖርት ከፍተኛ የህዝብ ሀብት ከህግና መመሪያ ውጭ ለብክነት እንደተጋለጠ የሚያሳይ ነው፡፡ ይህን ጉዳይ እንዴት ይመለከቱታል? ከዚህ አንፃር የዋና ኦዲተር መስሪያ ቤት ተግባሩን ለመወጣት የሚፈልገውን የመንግሰት ድጋፍ ለማድረግ በእርሶ በኩል ቁርጠኝነት አለ ወይ?
6.   በሪፖርቱ ገፅ 10 “ጥቃቅን እና አነስተኛ ተቋማት ወደ ማኑፋክቸሪንግ ሽግግር ተሰፋ ናቸው” ይላል፡፡ ተሰፋ ያላቸው የትኞቹ ናቸው? መንግሰት አሰፈላጊው ድጋፍ እያደረገ ነው የተባለው ድጋፍ ምንድነው? ኢንዱስትሪ መንደር ውስጥ ሊገቡ ያሰቡ ወይም የሚችሉ ድጋፍ የተደረገላቸው ጥቃቅን እና አነሰተኛ ተቋሞች ካሉ ቢገልፁልን?
7.   የግልገል ጊቤ 3 በሚቀጥለው ዓመት ውሃ ስለማይሞላ ሰራ አይጀምርም የሚል ዜና በሚዲያ እየወጣ ሲሆን ሪፖርቱ ግን በሚቀጥለው ዓመት ይጀምራል ተብሎ ይጠበቃል ይላል፡፡ በእርግጥ በሚቀጥለው ዓመት ሰራ ይጀምራል? የኢነርጂ አቅርቦታችን በዚህ ዓይነት አዝጋሚ ሁኔታ ሆኖ ማኑፋክቸሪንግ ሴክተሩ ምን ተሰፋ አድርጎ ሊመጣ ይችላል?
8.   ከሱዳን ጋር የጋራ ኮሚሽን የመሪዎች ጉባዔ በካርቱም ተዳሄዱ 13 የትብብር ስምምነቶች ተፈርመዋል፡፡ ሚዲያዎች ኢትዮጵያ ለሱዳን መሬት ሰጥታለች የሚል ዘገባ ቢያወጡም ክቡር ጠቅላይ ሚኒሰትሩም ይህ የማይታሰብ እንደሆነ ገልጸዋል፡፡ እኛም ባይታሰብ እንመርጣለን፡፡ ለግልፅነት ሲባል ሰምምነቶቹ ዝርዝር ለምን ይፋ አይደረግም?
9.   ከኤርትራ በስተቀር ከጎረቤት ሀገሮች ጋር መልካም ግንኙነት እየተፈጠረ እንደሆነ በሪፖርቱ ተገልፆዋል፡፡ ኤርትራን በተለመለከት በግለሰቦችም ሆነ በቡድን ደረጃ የህዝብ ለህዝብ ግንኙነት ለመፍጠር ለሚያሰቡ ሰዎች የኢትዮጵያና የኤርትራን ህዝቦች ለጋራ ጥቅም በሚያሰልፍ መልኩ መንግሰቶ ምን ድጋፍ ሊያደርግ ይችላል?
10. ሰፋፊ እርሻን በሚመለከት ከሶሰት ሚሊዮን ሄክታር በላይ ዝግጅት ተደርጎ ብዙ መሄድ እንዳልተቻለ ይታወቃል፡፡ የተሰጡትም መሬቶች ቢሆን ከውዝግብ የፀዱ አይደለም፡፡ በመርዕ ደረጃ በድንበር አካባቢ ያሉ መሬቶችን ለምሳሌ በጋምቤላ አካባቢ ያሉ መሬቶች ለውጭ ዜጎች መስጥት ወደፊት ከሀገር ሉዓላዊነት አንፃር ያለው ሰጋት ተገምግሞ ያውቃል? ይህን ስጋት ለማስወገድ በድንበር አካባቢ መንግሰት የኢትዮጵያዊያን ተሳተፎ እንዲጎለብት ምን ድጋፍ ያደርጋል?
በመጨረሻም ሪፖርቱ ማካተት ሲገባው ያላካተተው ምን አልባትም ስለ አልተሰራ የሚሆነው የፖለቲካ ምዕዳሩን በማስፋት ቀጣይ ምርጫን በእኩል ውድድር የሚደረግበትን ሁኔታ ለመፍጠር መንግሰቶ አድሎዋዊ ሆኖ ቀጥሎዋል ብለን መውሰድ እንችላለን፡፡ ገዢው ፓርቲ አሁንም በቀጣይ ያለ ምንም ተቀናቃኝ ለመቀጠል የመንግሰትን ጡንቻ መጠቀሙን ይቀጥላል ብለን እንድንወስድ የሚያስገድድ ስለሆነ ይህ ላለመሆኑ የሚሰጡን ማብራሪያ ካለ ቢገልፁልን?
አመሰግናለሁ፡፡
ግርማ ሠይፉ ማሩ
 

Saturday, April 19, 2014

ነፃነት የጎደለው የእድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ




ግርማ ሠይፉ ማሩ
girmaseifu32@yahoo.com
የእድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅዱን በዝርዝር ተመልክቶ የገመገመ ተቃዋሚ ፓርቲ ከአንድነት በስተቀር ያለ አይመስለኝም፡፡ በተለያዩ ምክንያቶች የዕቅዱን ግምገማ ውጤት ለህዝብ ለማድረስ ባለመቻሉ ግን ይህ የሚታወቅ ነገር አይደለም፡፡ ግምገማው የተከናወነው የተለያዩ ዘርፎችን ለሙያው ቅርበት ባላቸው ሰዎች በሚመሩት ሁኔታ ነው የተገመገመው፡፡ የእድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅዱን አንድ ክፍል ለመገምገም ሃላፊነት ከወሰዱት ሰዎች ውስጥ/አሁን ስም መጥቀስ አያስፈልግም/ ኢህአዴግ ይህን ዕቅድ ካሳካ ኢህአዴግ እሆናለሁ ማለታቸውን አሰታውሳለሁ፡፡ እኔ በግሌ ዕቅዱን እንደማያሳካ ሰጋቴን ባስቀምጥም እቅዱን ቢያሳኩትም ኢህአዴግ እንደማልሆን አውቃለሁ፡፡ እነዚህ ቁሳዊ ነገሮች የበዙበት ዕቅድ ነፃነቴን ለመውሰድ የተዘጋጀ እንደሆነ ይገባኛል፡፡ የኢህአዴግ ደጋፊም አባልም መሆን የምቸገረው ኢህአዴግ የሚያራምደው አብዮታዊ ዲሞክራሲ ለግለሰብ ነፃነት የሚሰጠው ቦታ ስለሌለ ወይም የይስሙላ ስለሆነ ነው፡፡ አሁንም አቋማችን መሆን ያለበት የእድገትና ትራንሰፎርሜሽን ዕቅድ የዜጎችን ነፃነት ቀምቶ የሚመጣ ከሆነ ባአፍንጫችን ይውጣ የሚል መሆን አለበት፡፡ ከዚህ በተቃራኒው የሚቆም መብቱ ነው፡፡ በህዳሴው ግድብ ከሚገኝ መብራት ኢትቪን እየተመለከተ ነፃነቱን በእልሙ ማየት ይችላል፡፡ ወይም በህዳሴው ግድብ መነሻ በሚፈጠር ማነኛም የስራ ዕድል ተጠቃሚ ሆኖ ነፃነት ድሮ ቀረ ብሎ የሌሎች ሀገር ዲሞክራሲን ማወደስ ሲሻው መሳደብ መብቱ ነው፡፡ ነፃነት በነፃ አይገኝም ብቻ ሳይሆን ነፃነትን ለፈለጉት ቁሳዊ ጥቅም አሳልፎ መሸጥ የግለሰቦች ምርጫ ነው፡፡ ነፃነት የሚገኘው በ “ምርጫ” ነው፡፡ ነፃ ለመሆን በመፈለግና ለዚህ ፍላጎት የሚከፈለውን ዋጋ በመክፈል የሚገኝ ነው፡፡
እኛና ኢህአዴጎች የእድገትና ትራንሰፎርሜሽን ዕቅዱን በዕቅዱ ዘመን መጨረሻ ሰንገመግም እንዲሁም አቋም ስንይዝ በብርጭቆ ውስጥ እንደሚገኝ ውሃ “ግምሻ ሙሉ እና ግማሽ ጎዶሎ” በሚል ፍልስፍና መነፅር ኢህዴጎች ግማሽ ሙሉ እኛ ግማሽ ጎዶሎ እንደመረጥን ተደርጎ ቢወሰድ ልክም ተገቢም አይደለም፡፡ ኢህዴጎች ከአሁኑ እንደማይሆንላቸው ስላወቁ በዕቅድ ዘመኑ ከተቀመጡት “ወሳኝ ቁሳዊ ግቦች” ቢሆን ፈቀቅ ብለው፤ አሁን የደረሱበትን እና ወደፊት ያለውን “ተስፋ” በመመገብ ለቀጣይ ምርጫ እንደ ዋናኛ የምርጫ ግብዓት እየተዘጋጁ ነው፡፡ በቀጣይ ዓመት በዕቅድ የተቀመጡትን ግቦች ከማሳካት ይልቅ በዋነኝነት በፕሮፓጋንዳው ስለሚጠመዱ አሁን ከደረሱበት ብዙ ፈቀቅ እንደማይሉ ለመገመት አያስቸግርም፡፡
የኢህአዴግ ሰዎች በዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅዱ በእያንዳንዱ ዘርፍ የተጣለው ግብ በዋና ዋናዎቹ ግማሽ ለመደረስ እንደማይቻል አመላካች ነገሮች እንዳሉ ይረዳሉ፡፡ እንደዚያም ሆኖ ግን አጠቃላይ ግቡ ሊሳካ ይቻላል ብለው ማመን መርጠዋል፡፡ ግማሽ ሙሉ ፍልስፍናን እንደመስፈርት እንደንጠቀም የሚገፉንም ለዚህ ነው፡፡ ለዚህም መከራከሪያ ብለው ያስቀመጡት በመሰረታዊ ዕድገት አማራጭ ከአስራ አንድ በመቶ በላይ እናድጋለን ብለን ነበር አሰር በመቶ ከዚያም ትንሽ ዝቅ ያለ ቢሆንም ዋናው ዕቅዱ የተለጠጠ ስለነበር ጥሩ ነበር ብቻ ሳይሆን እጅግ በጣም ጥሩ የሚባል እንደሆነ ተደርጎ ስለሚነገረን መዘጋጀት ያለብን ይመስለኛል፡፡ ለምን? ቢባል መልሱ ባለ ብዙ ዘርፍ ነው፡፡ አንዱ በምክር ቤት ደረጃ ባሉ የኢህአዴግ አባላት የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ አልተሳካም ተብሎ በሚመጣ ጣጣ ከሞቀ /አንፃራዊ ነው/ ወይም ከአዲስ አበባ ኑሮ ወደ ወረዳ መውረድ ሊያስከትል ይቻላል፡፡ ይህ ጠቅላይ ሚኒስትር ሀይለማሪያም እንዳሉት ወረዳ ወርዶ መስራት ቀላል አይደለም፡፡ ሌላው ደግሞ ይህ የተጠቀሰው ስጋት የብዙዎቹ ካድሬዎች ሊሆን ቢችልም ይህ ሰጋት የሌላቸው ጎምቶዎቹ ኢህዴጎች ግን የተንደላቀቀ የገዢነት ቦታ ላለማጣት የእድገትና ትራንስፎርሜሸን ዕቅድ በአብዛኛው ተሳክቶዋል በሚለው የመንግሰት ሚዲያ ፕሮፓጋንዳ እኛንም እራሳቸውንም ለማሳመን መጣራቸው የማይቀር ነው፡፡ በኢህዴግ የሚዲያ አጠቃቀም ስትራቴጂ የተወሰኑ ሰዎች ሰለጉዳዩ የፈለገ ጥልቅ እውቀት ቢኖራቸው አጠቃላይ ህዝቡን በተለይም ለስልጣኝ መሰረቴ ነው የሚለው ድሃውን እስካታለለ ድረስ ስለ መረጃ ትክክለኝነት አይጨነቅም እና ለዚህ በሚደረግ ሽርጉድ እኛንም እውነት እስኪመስለን ድረስ ይህን እውሸት ልንሰማው መቻላችን በቅርብ ርቀት ያለ ሀቅ ነው፡፡
የዚህ ፅሁፍ መነሻ በቅርቡ በዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ሶስተኛ ዓመት አፈፃፀም ግምገማ አሰመልክቶ ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ሪፖርት ቀርቦ ነበር፡፡ ሪፖርቱን ተከትሎ የኢህአዴግ አባላት የሚሰጡት አስተያየት ሪፖርቱን ያነበቡት አይመስሉም፡፡ ከሪፖርቱ ይዘት ይልቅ ቀልባቸውን የሳበው የኢቲቪ ፕሮፓጋንዳ ነው፡፡ ሪፖርቱ በግልፅ ዋና ዋና የተባሉትና ዕቅዱ በቀረበበት ወቅት እነዚህ ዕቅዶች አሁን ባለ የፋይናንስ እና የመፈፀም አቅም የሚታሰቡ አይደሉም በሚል ትችት ሲቀርብባቸው የነበሩትን በሙሉ ለማሳካት የማይቻሉ እንደሆኑ አሳይቶዋል፡፡ ይህ ደግሞ ሲቀርብ የነበረው ትችት ትክክለኛነት የሚያረጋግጥ ነው፡፡ የቀረበው ሪፖርት “በአጠቃላይ በመሰረተ ልማት ፕሮግራሞች አፈፃፀም ዙሪያ የፕሮጀክት ማኔጅመንት ሁለንተናዊ አቅም ማነስ፤ የመሰረተ-ልማት ግንባታና ማማከር አግልግሎት ለመስጠት የሚያስችል ተቋማዊ አቅም ማነስ እና የፋይናንስ እጥረት ቁልፍ ማነቆዎች ሆነው ታይተዋል” ይላል፡፡ ሲጀመር እኛም ያልነው ኢህአዴግ በሚመራት ሀገረ ኢትዮጵያ ከላይ የተጠቀሱት ዋና ግብዓቶች ማነቆ ስለሆኑ እንደዚህ ያለ የተለጠጠ ዕቅድ መሳካቱ ያጠራጥራል ነው እንጂ በዓለም ላይ በእድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ላይ የሰፈሩት ፕሮጀክቶ አይተገበሩም መተግበር የማይችሉ አስማት ናቸው አላልንም፡፡
አንባቢ ልብ እንዲልልኝ የምፈልገው በእድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ዘመን መጨረሻ የሀገራችን እድገት 11.2 በመቶ አማካይ ይሆናል የተባልነው፤ የኢንዱስትሪ/ማኑፋክቸሪንግ ዘርፍ ከ20 በመቶ በላይ፤ የአስፋልት መንገድ ሳይጨምር የገጠር ቀበሌዎችን ከዋና መንገድ ጋር የሚያገናኙ ከ71 ሺ ኪሎ ሜትር ክረምት ከበጋ የሚያገለግሉ መንገዶች ግንባታ፤ የአዲስ አበባን ቀላል ባቡር ግንባታን ሳይጨምር 2395 ኪሌ ሜትር የባቡር መስመር ግንባት፤157 ሺ ቤቶችን መገንባት፤ 10 ሺ ሜጋ ዋት የሚደርስ የኢነርጂ ልማት፤ በስኳር ልማት የሀገር ውስጥ ፍጆታን ሸፍኖ ከስድሰት መቶ ሚሊዮን ዶላር በላይ የውጭ ምንዛሪ ማሰገባት፤ በማዳበሪያ ምርት ከፊል የሀገር ውስጥ ፍጆታን መሸፈን፤ወዘተ የሚጠቀሱ ናቸው፡፡ አሰማተኛውን የብረታ ብረትና ኢንጂነሪንግ ድርጅት የተሰጠውን ተግባር የተቀመጠለትን ግብ ትተን ማለት ነው፡፡ በግብርና ዘርፍ በሰፋፊ እርሻ የታቀዱትን ዝርዝር ግቦችንም ሳንረሳ ማለት ነው፡፡

እነዚህ ሁሉ በማነኛውም መመዘኛ በዕቅዱ ዓመት ማጠናቀቂያ የዕቅዱን ግማሻ ሊያሳኩ እንደማይችሉ ለመገመት ነብይ መሆን አይጠይቅም፡፡ ከላይ ከተዘረዘሩት ዋና ዋና በተለይም ኢቲቪ ለፕሮፓጋንዳ የሚጠቀምባቸውን እንደማሳያ ወስደን እንመልከት፡፡ የባቡር መስመር ዝርጋት ከተጣለለት ግብ 2395 ኪሎ ሜትር በዕቅድ ዘመን 239 ኪሎ ሜትር ወይም 10 ከመቶ ማሳካት አይቻልም፡፡ በኢነርጂ ዘርፍ የህዳሴው ግድብ ያማነጫል ተብሎ የሚጠበቀውን 750 ሜጋ ዋት እና ግልገል ጊቤ 3ን ጨምሮ አጠቃላይ የሀይል አቅርቦት የእቅዱን ግማሽ ማድረሽ ከባድ ነው፡፡ የማኑፋክቸሪንግ ሴክተሩ የተጣለወን ሃያ በመቶ እድገት ለማሳካት የሚያስችል የግል ሴክተር ተነሳሽነት አይታይም፤ ቢመጣም ማነቆ ብዙ ነው፡፡ የማዳበሪያ ፋብሪካ የብረታ ብረትና ኢንጅነሪንግ ኮርፖሬሽን ኮንትራቱን ለወዳጅ ዘመዶቹ ቆርሶ በመስጠት /sub-contracting ለሙስና የተጋለጠ አሰራር አለ እየተባለ አሜት ውስጥ ነው፡፡ በዚህ መስመር ምንም የሚታይ እንደሌለ ልማታዊው ኢቲቪ ምስክር ነው፡፡ በቤቶች ግንባታ በአዲስ አበባ ከ850 ሺ በላይ ቤት ፈላጊዎች ቢመዘገቡም በዕቅድ የያዙትን ያህል መስራት ሳይሆን ከተማውን ማፍረስ ነው የተያያዙት፡፡ እነዚህን ሁሉ ደምረን ስናያቸው የ11.2 በመቶ እድገት እንደማይመጣ እነርሱም እኛም ብናውቅ የፖለቲካ ቁጥር ሁለት አሃዝ እድገት ከ 10 በመቶ በላይ እድገት አሰመዝገበናል ይህም ከሰሃራ በታች ካሉ አገሮች ጋር ሲነፃፀር በእጥፍ ይበልጣል እንባላለን፡፡ እንዴት ነው ጎበዝ ይህ ነገር ልክ አይደለም ስንል ፀረ ልማት የሚል ቅፅል የያዘ የፕሮፓጋንዳ ዘመቻ ይከፈታል፡፡ እንግዲህ ሁሉም ከዚህ አንፃር መዘጋጀት ያለበት ይመስለኛል፡፡
የእድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ዘመን ሲጠናቀቅ ኢህአዴግ ቀጣይ የአስር ዓመት መሪ ዕቅድ እንደሚያቀርብ ፍንጭ የሚሰጡ ነገሮች እየታዩ ነው፡፡ አዲስ የተቋቋመው በአቶ መኮንን ማንያዘዋል ኮሚሽነርነት የሚመራው የዕቅድ ኮሚሽን ይህን ሃላፊነት ወስዶ እየሰራ ነው፡፡ ቀጣዩ እቅድ የአምስትም ይሁን የአስር አንድ ሀገር ከዚያም ያለፈ መሪ እቅድ እንዲኖራት ማድረግ ራዕይ ካለው መሪና ፓርቲ ይጠበቃል፡፡ በቀጣይ አስር ዓመትም ያለነፃነት ቁሳዊ ግቦችን አስቀምጦ ለመመራት ፍላጎት ያለውን ማነኛውንም ቡድን ግን እያንዳንዱ ዜጋ እንቢ ማለት ያለበት ጊዜ አሁን ነው፡፡ ጊዜው አሁን የሚሆንበት ገፊ ምክንያትም ኢህአዴግ አሳካለው ብሎ ያቀደውን ቁሳዊ እቅድ እንኳን ለማሳከት አቅም እንደሌለው አስመስክሮዋል፡፡ ቀጣዩን ዘመን ከቁሳዊ ግቦች በተጨማሪ ነፃነታችንን የማይገዳደር ዲሞክራሲያዊ ሰርዓት ለሚገነባ ቡድን እድል ለመስጠት መዘጋጀት ይኖርብናል፡፡ ኢህአዴግም ድርቅናውን ትቶ በቁሳዊ ዕቅድ ግማሽ ያደረሰውን ብርጭቆ ሳይሰብር ሌሎች የድርሻቸውን መወጣት የሚችሉበት እድል መኖሩን መቀበል ይኖርበታል፡፡ ነፃነት የራቀው የቁሳዊ እቅድ ጋጋታ መቀበል ያለመቀበል የነፃ ዜጎች ምርጫ እንጂ ፀረ ልማት መሆን ወይም የሀገር ልማት መጥላት አይደለም፡፡

ቸር ይግጠመን

Saturday, April 12, 2014

ሙስና እና ክብር …..




ግርማ ሠይፉ ማሩ
እንዴት በክብር መኖር እንዳለብን የሚያስረዳ መፅሐፍ እያነበብኩ በክብር መኖር እንዳንችል ከሚያደርጉን ነገሮች አንዱ ሙስና መሆኑ የሚገልፀው ክፍል ስደርስ ከወቅቱ የሀገራችን ሁኔታ ጋር እየተመሳሰለ ቢያሰቸግረኝ ላካፍላችሁ ወደድኩ፡፡ ስለ ሙስና ሲነሣ ብዙ ሠዎች በፀረ ሙስና እና ሰነ ሙግባር ኮሚሽን የሚገኙ ሃላፊዎችን ጨምሮ የሚያነሱት በእኛ ሀገር ያለው ከአፍሪካ ለምሣሌ ናይጄሪያና ኬኒያ በአውሮፓም ሆነ በኤዥያ ካሉት ብዙ ሀገሮች ጋር ሲነፃፀር  እዚህ ግባ የሚባል እይደለም፤ የሚሉ አሉ፡፡ የኮሚሽኑ ሰራተኞችም በተለያየ መድረክ ይህን ሲያነሱ መሰማት የተለመደ ሆኖዋል፡፡ በእኔ እምነት ይህ መስመር በፍፁም ተገቢ እንዳልሆነ ተገንዝቦ በእንጭጩ መቀጨት ያለበት እንደሆነ መረዳት ከሁሉም የሚጠበቀው መሆኑን ነው፡፡ ለዚህ ፅሁፍ መነሻ ያደረኩት መፅሃፍ ስለሙስና የሚገልጸው ክፍል እንዲህ ብሎ ይጀምራል፤
“አንድ ሰው ወደ ቤቱ መግቢያ መንገድ ላይ እሾሃማ ቁጥቋጦ እየበቀለ አይቶ ዝም ይላል፣ ጎረቤቶቹም እባክህ ይህ ነገር ልክ አይደለምና ንቀለው ቢሉትም በእጄ ብሎ ከመንቀል ዛሬ ነገ ሲል ቀን ቀንን እየወለደ ቁጥቋጦውም እያደገ ሄዶ በአንደኛው ቀን ባለቤቱን ክፉኛ አቆስሎ ክፉኛ ጎዳው፤ ጉዳት የደረሰበት የቁጥቋጦ ባለቤት ጉዳት ከደረሰበት በኋላ ቁጥቋጦውን ለመንቀል ቢሞክር ከአቅሙ በላይ ሆነ፤ ብቻውን የማይችለው አሰቸጋሪ ሆነበት ይላል ”
ከዚህ ምሳሌ የምንረዳው ተገቢ ያልሆኑ ነገሮች በወቅቱ ካልተወገዱ፤ እየጠነከሩ መጥተው ከአቅም በላይ እንደሚሆኑ …. አንድ አንዶቹ እንደ ሙስና ያሉት ደግሞ እነርሱ ሲጠናከሩ እኛን እያዳከሙ መሆኑን ችግሩን የከፋ እንደሚያደርገው ነው፡፡ ሙስና እንደ እሾሃማው ቁጥቋጦ በአንድ አንድ ምን አገባኝ በሚሉና ግዴለሽ ሰዎች ይተከልና ከአቅም በላይ ሆኖ በመጠናከር የዜጎችን እልውና የሚፈታተን ይሆናል፡፡ በመጨረሻም ትክክል እስኪመስል ድረስ በቤታችን ቤት ሰርቶ በሚስቶቻችን እና በልጆቻችን ፊት ቢዝንሰ እያልን እስክናወራው ድረስ ማዕረግ ያገኛል፡፡
ለፅሁፌ መነሻ የሆነኝ መፅሐፍ ሙስና “እድል ፊት ያዞረችባቸውን፣ ተከላካይ የሌላቸውን እንዲሁም ለችግር የተጋለጡትን ለመዝረፍ የተነሣ ሠይጣናዊ ፍላጎት” በሚል ይገልፀዋል፡፡ ብዙ ሰዎች እንዴት እንዲህ ያሉ ሰዎችን ሙስና አግኝቶ ይዘርፋቸዋል ሊሉ ይችላሉ፡፡ በሙስና የሚሳተፉትን ተዋንያን ስንመለከት ጎቦ በመስጠት ሀብታሞች፤ ጎቦ በመቀበል ደግሞ ሹሞች እንደሆኑ የምንታዘብ ሰዎች ይህ ትርጉም ምን ፍች አለው? የሚል ጥያቄ ብናነሳ ልክ ባይሆንም ተገቢ ነው፡፡ የሙስና ክፋቱም የሚጀምረው ከዚህ ዓይነት አሳሳች ባህሪው ነው፡፡
በሙስና የተሰማሩት ሰዎች በቀጥታ ተጎጂዎች አይደሉም፡፡ እነርሱማ በሙስና ከተመሰረተ ሰርዓት ተጠቃሚዎች ናቸው፡፡ ለጊዜውም ቢሆን፡፡ ጉቦ በመስጠት ጥቅም ያገኙ ሰዎች የሰጡትን ጉቦ ለሌላ ጊዜ ጉቦ እንዲተርፍ አድርገው በብዙ እጥፍ ለማስመለስ ዕዳውን የሚያስተላልፉት ዕድል ፊት ወዳዞረችባቸው፣ ተከላካይ ለሌላቸው እንዲሁም ለችግር ለተጋለጡት ምስኪን ዜጎች ላይ መሆኑ ነው፡፡ በሀገራችን የሚታየው የኑሮ ውድነት ተሸካሚው ማን እንደሆነ መረዳት ያስፈልጋል፡፡ ጎቦ ተቀባይም ሆነ ሰጪው ይህ የኑሮ ውድነት የምንለው መከራ አይመለከታቸውም፡፡ እነርሱ የመከራው ምንጭ ናቸው፡፡ በገበያ ላይ የአቅርቦት እጥረት እንዲፈጠር አጭበርባሪ ጉቦ ይሰጣል፤ ሹመኛው ለዚህ የሚመች መመሪያ ያወጣል፣ ሸማች በዓለም ላይ በሌለ ዋጋ እንዲገዛ ይገደዳል፡፡ የሙሰኞቹ መከራ ሰክረው መትፋትና በስካር እየነዱ መሞት ነው፡፡
በዲሞክራሲያዊ ሰርዓት በበለፀጉ ሀገሮች እነዚህን ምስኪኖች የሚጠብቅ የህግ ስርዓት አለ፡፡ እንዲህ ዓይነት ድርጊት ሲፈፀም በህግ ሰርዓት መፍትሔ ይሰጣል፡፡ እንደ ኢትዮጵያ ባለ ሀገር ህጎች ደካማን እና ድሃውን ለማጥቃት የሚውሉ መሣሪያዎች ናቸው፡፡ ጎልበተኞች የህግን አቅም የመደምሰስ አቅም አላቸው፡፡ ስልክ ተደውሎ ፋይላቸው የሚዘጋና ከእስር ይፈቱ የሚባሉ ሠዎች እንዳሉ ስናስብ ይህ ጉዳይ ሊገርመን አይችልም፡፡
በመግቢያዬ ላይ እንዳነሳሁት ሙስና ዓለማቀፋዊ የሆነ፣ ያለና የሚኖር በሚል መንፈስ ከተውነው ልክ እንደ ካንስር ያለንን ማህበራዊ መሰተጋብር በልቶ ሀገርን የሚያጠፋ መሆኑን ተረድተን፣ ህግ እሰኪደርስልን ድረስ የራሳችንን የመከላከያ መላ ማበጀት ያለብን ይመስለኛል፡፡ የእምነት ተቋማት አንዱ መንገድ ቢመስሉም በሀገራችን ሙስና ከመንግሰት ሰርዓት አልፎ ወደ ቤተ ዕምነት ከገባ ቆይቶዋል፡፡ የማሪያም ቤተ ክርስቲያን እንዲሰራ የተመደበ ምዕመን እገረ መንገዱን የራሱን ቤትም አዘንጦ ሰርቶ፤ ከየት አመጣህ ሲባል “ማሪያም ሰራቸው” እንዳለው  …. እየቆየን ስንሄድ ሁሉንም ገንዘብ ጠቅልሎ ወስዶ የማሪያምን ታቦት ጎዳና የሚያሳድር የቤተ ክርስቲያን አሰሪ ኮሚቴ እንደማይኖረን እርግጠኛ መሆን አይቻልም፡፡
እንደሚታወቀው እንደ ኢትዮጵያ ባሉ “ዲሞክራሲያዊ መንግሰት” አለን የሚል መንግሰታት “ሙሰኛ ዲሞክራሲ” ያላቸው ናቸው፡፡ የዚህ ዓየነቶቹ የተደራጁ ዘራፊዎች ሲሆኑ ህዝቡን በማሸበር ሀገር የሚገዙና የሚዘርፉ ናቸው፡፡ መገለጫቸውም “መንግሰታችን ዜጎችን ለመርዳት ዝግጁ ነው” ይላሉ፡፡ የሚገርም ነው፡፡ መንግሰት ዜጎችን ሊያገለግል የሚቀመጥ መሆኑ ቀርቶ ህዝብን ሊረዳ የተቀመጠ አድርገው ይመፃደቃሉ፡፡ ድሃ ህዝብ ሀብታም መንግስት በሚል የፃፍኩትን ልብ ይሏል፡፡ በቅርቡ ደግሞ ኢህአዴግ ካድሬዎችን ሲያስመርቅ አንድ “ተመራቂ” ያለው ለዚህ ሁነኛ ማስረጃ ይሆናል፡፡ ይህ ወጠጤ ካድሬ  ያስተማሩትን ነው የተናገረው “እኛ ከፊት ሆነን ህዝቡን ከኋላ አሰከትለን ልማታችንን እናፋጥናለን” ነው ያለው፡፡ እሱ ብሎ ከፊት መሪ - እንዴት አድርጎ እንደናቁን ነው የሚያሳየው፡፡ ይህን አባባል ለጦር ሜዳ ውሎ ቢሆን አይለውም፡፡ ህዝቡን ከፊት አስቀድሞ ነበር ከኋላ ሊመራ የሚፈልገው፡፡ ዜጎች የዚህ ዓይነት ወጠጤ እንቢ ካላልን … በመግቢያ ላይ ያነሳናት እሾሃማ ቁጥቋጦ በጊዜ ባለመነቀሏ ያሰከተለችውን ጉዳት እንደሚያስከትሉ መጠርጠር የለብንም፡፡ እኛ እየተዳከምን እነርሱ እየፈረጠሙ ሲሄዱ፤ አቅም ሲዳከም የማይነቀሉ አረሞች ይሆናል፡፡ ወንጀል ከመስራትም አይመለሱም፡፡
በሙስና በተዘፈቀ ሰርዓት ውስጥ ህጎች በህዘብ ስም የግል/የቡድን ጥቅም ለማረጋገጥ ይዘጋጃሉ፡፡ ይህንንም ለማስፈፀም ሙሰኞችና ብቃት የሌላቸው ሰዎች በቦታው ይመደባሉ፡፡ በዚህ መነሻም የህዝብ ሀብትና ንብረት ይመዘበራል እንዲሁም የዜጎች መብት ይረገጣል፡፡ ከዚህ ሁሉ ሊታደገን ይገባ የነበረው የፍትሕ ሰርዓት በተቃራኒው እነዚህን ህጎች ለመተግበር ይተጋል፡፡
የዚህ ሁሉ ውጤት እሴት የሌለው ማህበረሰብ መፍጠር ሲሆን በእንደዚህ ያለ ማህበረስብ በሙስና የሚገኝ ሀብት የሚያስከብርና በህብረተስብ ዘንድ ከፍተኛ ቦታ የሚያሰጥ ይሆናል፡፡ ለጊዜውም ቢሆን ሙስና የሀብት መንገድ ሲሆን ሀቀኝነት ትርጉም ያጣ ሊመስል ይችላል፡፡ በክብር መኖርም አደጋ ላይ ይወድቃል፡፡ ይህ እንዲሆን ሙስና ዓለማአቀፋዊ ነው እያሉ የሚያስተኙን በዝተዋል እና ነቅተን ውጊያ መግጠሚያው ጊዜ አሁን ነው፡፡
የማህበራዊ እሴቶች መውረድ የሚጀምሩት ሙስና ተቀባይነት ሲያገኝ እና ሙሰኞች በዚህ ምክንያት ምንም ዓይነት ማህበራዊ መድሎሆ እና መገለል የማይደረግባቸው ከሆነ ነው፡፡ ሙሰኞችን ከማህበራዊ ኑሮ ማግለልና መፀየፍ ሰዎች እራሳቸውን ከሙስና ለማራቅ ከሚያግዙ መንገዶች እንዱ ነው ብዬ አምናለሁ፡፡ አሁን ባለው ሁኔታ ሲሾም ያልበላ ሲሻር ይቆጨዋል፤ ገንጥሎ ወጣ፤ ከሀብቶች ጀርባ ወንጀል አለ፣ ወዘተ ተቀባይነት ያገኙ ይመስላሉ፡፡ ሁሉም እንደሚረዳው ሙስና በራሱ ግብ አይደለም፣ ዋናው ግብ ሀብትና ስልጣን ብሎም ከዚህ የሚመነጨውን ጉልበትም ለመጨበጥ ነው፡፡ ይህም የፈለጉትን ወንጀል እንዲሰሩ ይገፋፋቸዋል፡፡ ሙስና እና ወንጀል የአንድ ሳንቲም ሁለት ገፅታ ናቸው፡፡ በሀገራችን ሙስና የተጠረጠሩ ሰዎች ቤት የተገኙትን መሳሪያዎች ልብ ማለተ የግድ ነው፡፡ ወፍ ሊያድኑበት አይደለም በቤታቸው መሳሪያ የሚያስቀምጡት፡፡ በሙስና ምክንያት የተፈፀሙ ወንጀሎችን ይዞ ለፍርድ ማቅረብ በፍፁም አስቸጋሪ ነው፡፡ ሙሰኞችን የማስያዣውም ሆነ ለፍርድ ማቅረቢያውን መንገድ  በገንዘብ ይገዙታል፣ በሃይል ይቆጣጠሩታል፡፡ ሙስና ከአሽባሪነት እኩል ወይም የበለጠ አደጋ ያደርሳል ነገር ግን ሙስና የሚያደርስው ጉዳት በአሸባሪዎች እንደሚደርስ ጉዳት በግልፅ አይታይም፡፡ ለሚመለከተው ሁሉ ተብሎ እንደተላከ ደብዳቤ ለሁሉም በተለይ ለምሰኪኑ ዜጋ በየቤቱ ይደርሳል፡፡
በአብዛኛው የሙስና ምንጭ የሚሆኑት ተግባራዊ ሊደረጉ የማይችሉ ህጎችና በህጎች ውስጥ የሚቀመጡ ክፍተቶች ሲሆን ይህን የሚያደርጉትም ከዚህ ለመጠቀም የተዘጋጁ ሞራል የሌላቸው ሹመኞች ናቸው፡፡ በእርግጥ በአንድ ማህበረሰብ ውስጥ ከፍተኛ የሰነ ምግባር ደራጃ ላይ የደረሱ ሰዎች እንዳሉ ሁሉ ብልሹ ስነ ምግባር ያላቸውም መኖራቸውም ሀቅ ነው፡፡ ልምዶች የሚያሳዩት ለሙስና የተጋለጡ ህጎች በበዙበት ሀገርም ቢሆን ከፍተኛ የሰነ ምግባር ደረጃን የሚተገብሩ ዜጎች ይገኛሉ፡፡ በተመሳሳይ ጠንካራ የህግ ስርዓት ባለባቸው ሀገሮችም ጥቂት ወረዳዎች መኖራቸው አይቀርም፡፡ ለማንኛውም አብዛኛው ሰው በህግ ሰርዓት ማዕቀፍ ውስጥ እንደሚሆን መገንዘብ ያስፈልጋል፡፡ በጠንካራ ሰርዓት ውስጥ ሙሰኞች አስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ ሲኖሩ፣ በሙስና በተዘፈቀ ስርዓት ውስጥ ለክብራቸው የሚኖሩ ሰዎች መከራ ይገጥማቸዋል፡፡
ይህን ፅሁፍ በምሳሌ ብናሳርገው ጥሩ ነው፡፡ አንድ ንጉስ የሾመው ሚኒስትር በሙስና መዘፈቁን ሰምቶ የማያዳግም መፍትሔ ብሎ ወደ ባህር ሄዶ የባህር ማዕበል የሚፈጥረውን እንቅስቃሴ እንዲቆጥር ይልከዋል፡፡ ይህ ልማደኛ ሙሰኛ እዛም ሄዶ ጎቦ ከጀልባ ቀዛፊዎች መቀበል ይጀምራል፡፡ ምክንያቱም መንግሰት የሰጠኝን የማዕበል እንቅስቃሴ የመቁጠር ሃላፊነት በጀልባችሁ እንቅስቃሴ አወካችሁ በሚል ነው፡፡ ቃሊት የወረዱ ብዙ ሙሰኞች አሁንም ብዙ ነገሮችን በህገ ወጥ መንገድ እያደረጉ እንዳለ በቅርቡ ቃሊቲ ጎራ ካለ ጓደኛችን ተረድቻለሁ፡፡
ቸር ይግጠመን!!!

ኢህአዴግ፣ ምርጫ እና አማራጭ ፓርቲዎች




ግርማ ሠይፉ ማሩ
ባለፈው ፅሁፌ በሀገራችን ያሉ ተቃዋሚ ፓርቲዎች በአንድ እጅ ጣት ቁጥር ከማይሞሉት ውጭ ያሉት እንዲሁም ምርጫ ቦርድ ተገፍተው እንኳን ለመነሳት ባትሪያቸውን የጨረሱ እንደሆነ ለማሳየት ሞክሬ ነበር፡፡ ይህን ሀሳብ የሚያጠናክር ዜና በጋዜጣ ላይ አነበብኩኝ እና ድጋሚ ስለ ኢህአዴግ፣ ምርጫ እና አማራጭ ፓርቲዎች ግንኙነት ለመፃፍ ወሰንኩ፡፡ ለዚህ ፅሁፍ መነሻ የሆነው የምርጫ ስነ ምግባር ደንብ የፈረሙ አና በፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት አባል የሆኑ ፓርቲዎች ኢህአዴግ (ልብ በሉ መንግሰት አላሉም) ከዚህ በፊት ሲሰጣቸው የነበረውን ብር አንድ ሚሊዮን ድጋፍ ወደ ብር ሁለት ሚሊዮን ሊያሳድገው እንደሆነ ነገር ግን እነርሱ ምርጫ ለመሳተፍ ዝግጅት እንዲረዳቸው ወደ ብር አራት ሚሊዮን እንዲያሳድግላቸው ፍላጎታቸው መሆኑን፤ ይህን ጥያቄም በቀጣይ የጋራ ምክር ቤት ስብሰባ ላይ እንደሚያነሱት ገለፁ የሚል ዘገባ ማንበቤ ነው፡፡
ተቃዋሚ ፓርቲች ገዢውን ፓርቲ ገንዘብ ጠየቁ የሚለው ፌዝ መሳይ እውነት ለብዙ ሰው እንዲገባ በእግር ኳስ ምሳሌ ማስረዳት ጥሩ ነው፡፡ አቶ ሀይማሪያም ደሳለኝ የክልል ርዕስ መስተዳደር በነበሩ ጊዜ ለክልል ምክር ቤት አባላት ምርጫን በእግር ኳስ ምሳሌ ሲያስረዱ፤ ከከንባታ ዞን፣ ከአንጋጫ ወረዳ የተወከለ ተቃዋሚ አይደለም በሩጫ ይሁን ብሎ ተሰብሳቢውን አሰቆ እንደነበር ትዝ ይለኛል፡፡ እኔ በእግር ኳስ ላስረዳ የእንግሊዝ ጫወታ ለሚወድ ማንችስተር ሲቲ ወይም ማንችስተር ዩናይትድ ተቀናቃኛቸው አርሴናል ዋናጫ መብላት ስለተቸገረ ቡድኑን ለማጠናከርና ለዋንጫ እንዲበቃ ማሊያ እና ጠንከር ያሉ አዳዲስ ተጫዋቾች መግዣ ብለው ገንዘብ እንደመስጠት የሚቆጠር ነው፡፡ ወይም በሀገራችን ጊዮርጊስ ቡናን ለማጠናከር የገንዘብ ድጋፍ እንደማድረግ ነው፡፡ የልምድ ልውውጥ እንዳይመስላችሁ ጊዮርጊስ ብዙ ዋንጫ ስለበላ በአዘኔታ ቡና ዋንጫ እንዲያገኝ ለማገዝ ነው፡፡ እንዲህ ዓይነት ስላቅ በኢትዮጵያ ፖለቲካ ውስጥ ነብስ ዘርቶ ነው ያለው፡፡
ለነገሩ እነዚህ ፓርቲዎች በኢህአዴግ ተቆራጭ እየተደረገላቸው የሚቆሙ በመሆናቸው ለወጉ ነው እንጂ አማራጭ ናቸው ብለን የምናስባቸው አይደሉም፡፡ እነዚህ ፓርቲዎቸ ከኢህደዴግ ሀጋር ድርጅቶች የሚለያቸው የአብዮታዊና ልማታዊ መንግሰት ፍልስፍና ተቀብለናል ብለው በኢህአዴግ ፕሮግራም ነው የምንመራው ያለማለታቸው ነው፡፡ ከዚህ በሰተቀር በሚባል ደረጃ የፓርቲያቸው ፕሮግራም ስለመኖሩ አይታወቅም እና አማራጭ አላቸው ብለን እኛም አናምንም ህዝቡም በዚህ ጉዳይ አይጠረጥራቸውም፡፡ ሁሌም እንደምለው የእነዚህ ፓርቲዎች መኖር በኢትዮጵያ የመድበለ ፓርቲ ስርዓት ግንባታ ለማገዝ ሳይሆን ምዕራባዊያን በኢትዮጵያ ብዙ ፓርቲዎች አሉ ለማስባል ነው፡፡ ይህ ደግሞ ገዢው ፓርቲ ለረዥም ጊዜ ያለተቀናቃኝ በስልጣን ለመቆየት ያስቀመጠውን ዕቅድ ለማሳካት ጭምር የሚጠቀምበት ነው፡፡ አማራጭ እንዲሆኑ የሚጠበቅባቸው ፓርቲዎች በተቃራኒው ቆመው ሀገር አማራጭ ያሳጣሉ፡፡
ይህ ተግባር የሞራልና የመርዕ ጥሰት ብቻ ሳይሆን ህገወጥ ድርጊት ነው፡፡ ኢህአዴግ ለእነዚህ ፓርቲዎች የሚያድለውን ገንዘብ የሚያገኘው ከመንግሰት ካዝና ነው፡፡ ምርጫ ቦርድ ባለፈው ዓመት ለምክር ቤት ባቀረበው ሪፖርት መሰረት ለፓርቲዎች የሚሰጠው ድጋፍ በክልልና በፌዴራል ምክር ቤቶች ባገኙት መቀመጫ መሰረት በመሆኑ እነዚህ በፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት አባል የሆኑ ፓርቲዎች ደግሞ መቀመጫ ስለሌላቸው ገንዘቡን በሙሉ ጠቅልለው የወሰዱት ኢህአዴግና አጋሮቹ መሆናቸው አስታውቆዋል፡፡ ኢህአዴግ ግን በዚህ መሰረት ያገኘውን ገንዘብ በቸርነቱ ለነዚህ ፓርቲዎች እንዲታደል አድርጎዋል፡፡ ለዚህም ምርጫ ቦርድ ትብብር ማድረጉን በአደባባይ አምኖዋል፡፡
የመጀመሪያው ህገወጥ ተግባር ኢህአዴግ እንዲጠቀምበተ ከመንግሰት ካዝና በምርጫ ቦርድ በኩል የተሰጠውን ገንዘብ ለሌሎች ፓርቲዎች አሳልፉ የሚስጥበት አንድም የህግ አግባብ የለም፡፡ ለምሳሌ ጤና ጥበቃ ሚኒስትር ከመንግሰት የተመደበለትን በጀት ለክልል ጤና ቢሮ ወይም ለትምህርት ሚኒስትር አሳልፎ መስጠት አይችልም፡፡ ካልተጠቀመበት ወደ መንግሰት ካዝና መመለስ ብቻ ነው ያለው አማራጭ፡፡ ይህን ድርጊት ለምርጫ ቦርድ ሃላፊው ፕሮፌሰር መርጊያ በቃና የተነገራቸው ቢሆንም አሁንም ለማረም ዝግጁ የሆኑ አይመስልም፡፡ በሹመት ላይ ሆኖ ህግ የሚተላለፍ ባለስልጣን የሚቀጣበት ሀገር ስለአልሆነ በማንአለብኝነት በህገወጥ ድርጊቱ ቀጥለዋል፡፡ ቀን የጨለመ ዕለት ግን ማጣፊያው እንደሚያጥር ጥርጥር የለኝም፡፡ ይህን ፅሁፍ እያዘጋጀው እያለ ፕሮፌሰር መርጊያ መግለጫ ሲሰጡ ሰማው እንዲህ ብለው “ገለልተኛ አይደላችሁም ይሉናል፤ ለገዢው ፓርቲ ያደላሉ ይሉናል፤ በእውነት ገዢው ፓርቲ የእኛ ድጋፍ ያስፈልገዋል?” እስኪ አንድ ዳኛ ጫወታ ከመጀመሩ በፊት እንዲ ማለት ምን ማለት ነው? ገዢው ፓርቲ ተቃዋሚዎችን እንደሚበልጥ እርግጠኛ ቢሆኑ እንኳን እንዲህ ዓይነት አስተያየት አይሰጥም፡፡ ቢያንስ በአደባባይ፡፡ ለነገሩ ከኢህአዴግ ጋር ተባብሮ የመንግስት ገንዘብ በማከፋፈል ተግባር መሰማራት ድጋፍ ካልሆነ ምን ይሆናል?
ስለዚህ ሌላኛው ህገወጥ ተግባር ምርጫ ቦርድ ከመንግሰት ካዝና ወስዶ ለኢህአዴግ የሰጠውን ገንዘብ በህጉ መሰረት ለታለመለት ዓላማ ብቻ ማዋሉን ማረጋገጥ ሲገባው ይልቁንም በዚህ ጉዳይ ኢህአዴግ ለሚፈልጋቸው ፓርቲዎች የማሰራጨት ተግባርን መስራቱ ቦርዱ ከተሰጠው ኃላፊነት እና ተግባር ውጭ ህገወጥ ድርጊት መፈፀሙን የሚያሳይ ነው፡፡ ኢህአዴግ ለፈፀመው ህገወጥ ተግባራም ቦርዱ ተባባሪ ነው፡፡ ይህ ቦርዱ አድሎዋዊ መሆኑን ያሳያል፡፡ ቦርዱ በግፊም አይነሳም ወይም በግፊ የሚነሳው ኢህአዴግ ሲገፋው ነው ያልኩት ለዚህ ነው፡፡
ሌላ አስቂኙ ነገር ደግሞ ኢህአዴግ ለሰጣቸው ገንዘብ የኦዲት ሪፖርት እንዲያቀርቡ ከተጠየቁት ውስጥ የኦዲት ሪፖርት ማቅረብ የቻሉት ሶሰቱ ብቻ ናቸው የሚለው መረጃ ነው፡፡ የሚያስቀው የኦዲት ሪፖርት ያለማቅረባቸው ወይም የኦዲት ሪፖርት ያቀረቡት ትንሽ መሆናቸው አይደለም፡፡ የኢህአዴግ ሪፖርት ጠያቂነት እና እነርሱም ሪፖርት ለማድረግ ፈቃደኛ መሆናቸው ነው፡፡ ለነገሩ እነዚህ ፓርቲዎች መሞታቸው የተረጋገጠው ገንዘብ ከኢህአዴግ ለመቀበል የወሰኑ ዕለት ነው፡፡ የዛን ዕለት አለቃቸው ማን እንደሆነ ተጠሪነታቸውም ለማን እንደሆነ ተረጋግጧል፡፡ እነዚህ ፓርቲዎች እንዴት ብለው አማራጭ ያቀርባሉ? ሌላው አስገራሚ ነገር የተጠበቀባቸውን አማራጭ ያለማቅረባቸው ብቻ ሳይሆን የኢህአዴግንም ፖሊሲ በቅጡ ሊደግፉ የሚችሉ ያለመሆናቸው ነው፡፡ ከሁለቱም የሌሉ ጉዶች ናቸው፡፡ የእነዚህ ፓርቲዎች ስብስብ አባል ነው እንግዲህ ሰሜን አጣፋችሁ እያለ ክስ መስርቶ ዜጎችን በየጣቢያው እያስጠራ የሚያንገላታው፡፡ ሰም ሲኖር መስሎኝ የሚጠፋው!!
ፓርቲዎች በዋነኝነት የገቢ ምንጫቸው መሆን ያለበት ከአባላት የሚያገኙት መዋጮ ነው፡፡ አባላት ከሌሏቸው ደግሞ ፓርቲ ናቸው ብሎ ከምር መውሰድ አይቻልም፡፡ በዚህ ፅሁፍ ያነሳሁትን ሃሳብ የሰጠሁት ኢህአዴግ ለነዚህ ፓርቲዎች የሚያድለው ገንዘብ ከምርጫ ቦርድ የወሰደውን ታሳቢ በማድረግ ነው፡፡ ነገር ግን የኢህአዴግ የገንዘብ ምንጭ ይህ ብቻ አይደለም፡፡ በህገወጥ መንገድ ከያዛቸው የንግድ ድርጅቶች በሚስጥር ከሚያገኘው በተጨማሪ የፓርቲውን አቅም ለማሳደግ በቀጥታና በተዘዋዋሪ የመንግሰትን ሀብትና ንብረት ያለአግባብ ይጠቀማል፡፡ የተወሰኑ ማሳያዎችን ለመግለፅ፤
·         በቅርቡ ኢህአዴግ ያሰለጠናቸውን ካድሬዎች ለምሳሌ የመንግሰት ተቋም በሆነው የሲቪል ሰርቪስ ዮኒቨርሲቲ ሲያስመርቅ፣ በተከታታይ በዩኒቨርሲቲው ጊቢ ውስጥ ውለው አድርው አብዮታዊ ዲሞክራሲ ሲሰለጥኑ ማየትና መስማት የተለመደ ነው፡፡ ይህ ገንዘብ ፓርቲው በተዘዋዋሪ ከመንግሰት የሚወስደው መሆኑን ልብ ይሏል፡፡ ኢህአዴግ ከመንግሰት በተዘዋዋሪ የሚወስዳቸው እነዚህ ብቻ አይደሉም፡፡ የፓርቲ አባላት በተደራጁበት መዋቅር አይደለም ወርሃዊ መወጮ የሚከፍሉት፤ በመንግሰት መዋቅር በኩል ነው መዋጮ የሚሰበሰበው፡፡
·         በቅርብ በማውቀው የተወካዮች ምክር ቤት ከላይ እስከ እታች ያለው መዋቅር በመንግሰት የስራ ሰዓት ሁሉ የፓርቲ ስብሰባ ይደረጋል እንዲሁም ሌሎች ልዩ ልዩ ተግባራትንም ያከናውናሉ ለነዚህ ተግራራት ሁሉንም አስተዳደራዊ መዋቅር ይጠቀማል፡፡
·         የኢህአዴግ ቢሮዎች በሙሉ የመንግሰት ናቸው፡፡ ይህ አልበቃ ብሎ ከመንግሰት ቢሮዎች ጋር ብዙ ሀብት በሚጋሩበት ሁኔታ ነው ቢሮዎቹን የሚከፈቱት፡፡
·         በኢህአዴግ አባል ድርጅቶች ፅ/ቤቶች በዋና ዋናዎቹ የክልል ፖሊሶች ጥበቃ ሲያደርጉ ብታዩ በፍፁም መገረም አይኖርባችሁም፤ አሁን እርግጠኛ አይደለሁም እንጂ ሬዲዮ ፋና በፌዴራል ፖሊስ ነበር የሚጠበቀው፡፡ ሸገር ኤፍ ኤምን ፌዴራል ፖሊስ የሚጠብቀው አይመስለኝም፡፡
·         የመንግሰት መኪና ያለምንም እፍረት ለፓርቲ ስራ ሲያውሉ ማየት በፍፁም የሚያሸማቅቅ ሳይሆን፣ በኩራት ልብ የሚያስነፋ ነው፡፡ ለፓርቲ ስብሰባ ከመንግሰት ነዳጅ ሞልተው ነው የሚንቀሳቀሱት፡፡
ይህን ሁሉ ስታሰቡት ኢህአዴግ ለአነዚህ ፓርቲዎች ያሰበውን ብር ሁለት ሚሊዮን ወይም እነርሱ የፈለጉትን ብር አራት ሚሊዮን ቢሰጣቸው በእጅ አዙር ከመንግሰት የሚቀበለው ነው፡፡ አሉኝ ከሚላቸው ስባት ሚሊዮን አባሎችም ሃምሳ ሳንቲም ቢሰበስብ ሊሰጣቸው ይችላል፡፡ የገንዘቡ ምንጭ ሳይሆን መርዕ ያለመከበሩን ስናስብ ነው ጉዳዮን ጉዳይ ብለን እንድናነሳው የሚያስገድደን፡፡
በነገራችን ላይ እነዚህ ከኢህአዴግ ድርጎ/ደሞዝ የሚቆረጥላቸው ድርጅቶች ከመንግሰት ለፅ/ቤት የሚሆን ቢሮ አላቸው፡፡ አንዳንዶቹ አከራይተው እንደሚጠቀሙበት እና ለግል ጥቅም እንደሚያውሉት እርስ በራስ ሲካሰሱም ሰምተናል፡፡ ለማነኛውም ገንዘብ ሰጪው ኢህአዴግ፣ ገንዘብ ተቀባይ ፓርቲ ተብዬዎችም ሆኑ ምርጫ ቦርድ ይህን በማድረጋቸው ምንም ቅር የሚላቸው አይመስልም፤ ዶክትር በድሉ ዋቅጅራ ባለፈው ሳምንት ባቀረበው መጣጥፍ ላይ በተጠቀመው አባበል ብዘጋው ወደድኩ፡፡ እነዚህ ተዋንያን ተግባራቸው ለአስደሳች ህልም ካልሆነ በቀር ለአሰፈሪ ቅዠት አይዳርጋቸውም፡፡ ይህ ሲሆን ስታዩ አንድ የጎደላቸው ነገር ያለ አይመስላችሁም፡፡
ቸር ይግጠመን!!!