Saturday, November 22, 2014

የነፃነቴ ዋጋ ነብሴ ነው!!!


 መረጃ በሃያ አንደኛው ክፍለ ዘመን ጠቃሚ ነው ብሎ መንገር ለቀባሪ እንደማርዳት ነው፡፡ የተሟላ መረጃ የሰውን ልጅ ሙሉ ያደርገዋል፡፡ መረጃን አጣሞ ማቅረብ ደግሞ የሰውን ልጅ ውሳኔ ለማጣመም ካልሆነ በስተቀር ግቡ ምን ሊሆን እንደሚችል አይገባኝም፡፡ በሰሞኑ ሰው በላው የኢትዮጵያ ፖለቲካ በጥርሱም በጥፍሩም ዘመቻ የጀመረው እኔ ላይ ነው፡፡ ዓላማው ግልፅ ነው፡፡ በነፃነት የማሰብ መብቴን ለድርድር እንዳቀርብ ነው፡፡ ለነፃነቴ ያለኝን ዋጋ የማያውቁ ሰዎችን ይህንን ለማድረግ ቢሞክር ካላቸው የመረጃ እጥረት ወይም ማወቅ ባለመፈለጋቸው ነው፡፡ አንዳንድ ቅን ሰዎች ሰህተት እንደሰራው አድርገው ይቅርታ እንድጠይቅ፤ ይቅርም እንድባል አስተያየት ሰጥተዋል፡፡ በቅን ልቦና ላደረጋችሁት ምስጋናዬ ይድረሳችሁ፡፡ ነገር ግን በሰጠሁት አስተያየት ያልተስማማ ሰው በሃሰብ ልዮነት መለያየት እያለ ይቅርታ ጠይቄ፤ ይቅርታም ተደርጎልኝ ወደ እነሱ ሃሳብ እንድገበ መፈለጉ ምን ዓይነት ከፍተኛ ችግር ያለበት አስተሳሰብ እንደሆነ የተረዱት አይመሰለኝም፡፡ ይህ ደግሞ በጣም አስገራሚ የሚሆነው የመድበለ ፓርቲ ስርዓት ደጋፊ፣ ለግለሰብ ነፃነት እንቆማለን የሚሉ ወገኖች መሆናቸው ነው፡፡ ለሃሳብ ነፃነት የማይቆም እንዴት አድርጎ ለመድበላ ፓርቲ ስርዓት ግንባታና የግለሰብ ነፃነት እንደሚያከብር አይገባኝም፡፡
ጫጫታ ወደ ፈጠረው አጃንዳ ስገባ፡፡ አንድነት ፓርቲ የምርጫ ግብረ ሀይል ማቋቋሙን ለህዝብ በይፋ ለማሳወቅ እና በቀጣይ ሳምንት ስለሚያደርገው የህሊና እስረኞች ስለሚታሰብበት ፕሮግራም መግለጫ በሰጠንበት ወቅት በፍፁም ጠቃሚ ያልሆነ የተቃዋሚ ጎራውን በተለይ በሀገር ውስጥ ለምንገኝ ሰዎች የማይጠቅም (በኢቲቪ ቢቀርብ የማይገርም) ጥያቄ ቀረበ፡፡ ጥያቄው በእስር ላይ የሚገኙ የቀድሞ አንድነት አባል የነበሩ ታሳሪ ስም ጠርቶ በአንድነት አቋም እኝህ ሰው የህሊና እስረኛ ናቸው ብላችሁ ታምናላችሁ ወይ? የሚል ነበር፡፡ የሰጠሁት መልስ የማንንም ታሳሪ ስም ማንሳት ሳያስፈልግ የአንድነት ፓርቲ አባል ሆኖ የሌላ ፓርቲ አባል መሆን ትክክል እንዳልሆነ፣ ከአንድነት ጋር በትግል ስትራቴጂ ከማይመሳሰሉት ጋር ብቻ ሳይሆን በትግል ከሚመሳሰሉትም ጋር ቢሆን የተሻለ ወደሚለው መጠቃለል እንጂ ሁለት ቦታ መሆን ትክክል እንዳልሆነ አስረድቻለሁ፡፡ በማስከተልም “በፀረ ሽብር” ህግ መንግሰት እየከሰሰ የሚያስራቸው ሰዎች አንዳንዶቹ በወንጀል ህግ ሊያስጠይቅ የሚችል ሰህተት አልሰሩም የሚል ድምዳሜ እንደሌለኝ አሰረግጬ ተናግሬያለሁ፡፡ ለምሳሌ በፈንጂ ስው የገደለ ሰው በወንጀለኛ ህግ መጠየቅ እና መቀጣት አለበት ብዬ አምናለሁ፡፡ ይህ እምቴ አሁን ፅኑ ነው፡፡ የ “ፀረ ሽብር” የሚባለውን ህግ በይፋ አሸባሪ ህግ ነው፡፡ ፖለቲከኞች እና ጋዜጠኞች አሸባሪ እየተባሉ የሚታሰሩ ያሉት የአራት ኪሎን ወንበር ስለሚያሸብሩ ነው የሚል አቋሜን ከብዙዎቹ ተችዎቼ በላይ እና ከማንም በማያንስ መልኩ ሃሳቤን በነፃነት አራምጃለሁ፡፡ ይህን ሳራምድ ማንንም ለማስደስት ሳይሆን አምኜበት ነው፡፡ አንድነት የ “ፀረ ሽብር” የሚባለው ህግ እንዲሰረዝ የተገበረውን “የሚሊዮኖች ድምፅ ለነፃነት” ዘመቻ በቁርጠኝነት ከመሩት አንዱ ስሆን፤ በተለይ በደሴ ከተማ የተደረገውን የሚሊዮኖች ድምፅ ዘመቻ በቦታው ተገኝቼ የመራሁት እኔ ነኝ፡፡ ይህን ሁሉ የምዘበዝበው በዚህ ህግ ላይ ያለኝን ግልፅ አቋም በድጋሚ ለማረጋገጥ ነው፡፡
በእኔ በኩል የአቋም ለውጥ ሳይኖር እሳት ጭረው ቤንዝን እያርከፈከፉ ያሉት ግለሰቦችና ቡድኖች ለምን ተፈጠሩ?  የሚለው ነው፡፡ በእኔ እምነት የአንድነት በምርጫው የመሳተፍ ውሳኔ በትግል ስልታቸው ላይ የሚፈጥረው ጫና ስለሚያስጨንቃቸው ነው ብዬ ነው የማምነው፡፡ ምርጫ መሳተፍ ትክክል አይደለም ብሎ መሟገት ሲያቅታቸው የፈጠሯት ስልት ነች፡፡ አንድነት ምርጫ መሳተፍ ሲወስን በምንም መመዘኛ የመወዳደሪያው ሜዳ ምቹ ነው የሚል ግምገማ ላይ ደርሶ አይደለም፡፡ የፖለተካ ምዕዳሩ ጠበበ ብቻ ሳይሆን ዝግ ነው የሚል ግምገማ ላይ ደርሶዋል፡፡ ልዩነቱ ማስከፈቻ መንገዱ ምን ይሁን የሚለው ነው፡፡ በህዝብ ድምፅ የተዘጋው የፖለተኪ በር ይከፈታል ነው አንድነት ያለው፡፡ በዚህ ውሳኔ የማይስማማ ሊኖር እንደሚችል ይገመታል፡፡ በዚህ ደረጃ ወርዶ ግን በጥርስና በጥፍር ለመናከስና ለመቧጨር መሞከር ግን ያስተዛዝባል፡፡

የግል ሰሜቴን ለመግለፅ እሰከ ዛሬ ድረስ ለሚቀርብልኝ ሙገሳና የማጀገኛ ቃለቶችን ተመርኩዥ ልቤ አላበጠም፡፡ አንድ ቀን ያለአግባብ ከፍ አድርገው ከሰቀሉ ቦታ ላይ አውርዶ የሚከሰክስ ማህበረሰብ አባል መሆኔን አውቃለሁ፡፡ ያለ አግባብ በእራሳቸው ስሜት ሊወስዱኝ የፈለጉት ከፍታ ላይ ስለአልሄድኩኝ አሁን ሊያወርዱኝ አይችሉም፡፡ እደግመዋለሁ ለነፃነቴ የምሰጠውን ዋጋ የማያውቁ ሰዎች ምንም ሊሞክሩ ቢችሉም ነፃነቴን ለኢህአዴግ አሳልፌ አልሰጥም ስል በተቃዋሚ ጎራ ለተሰለፈ አሳልፌ እሰጣለሁ ማለት አይደለም፡፡ ለነፃነቴ የመደብኩት ዋጋ ነብሴን ነው፡፡ ስም፣ ዝና፣ ክብር፣ ገንዘብ፣ ወዘተ እንዳይመስላችሁ!!!!! ነብሴን ነው፡፡

Monday, November 17, 2014

በኢትዮጵያችን በጥርስና በጥፍር የሚደረግ ትግል እንዴት ይቁም?


አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ/አንድነት አሳዛኙን የ2002 ምርጫ ውጤት ተከትሎ ፍራሽ አንጥፎ ኢህአዴግን ምርጫ ዘረፈ ከሚል መደበኛ ለቅሶ መውጣት አለብኝ ብሎ ቁርጠኛ ውሳኔ በመወሰን ውስጣችንን መፈተሸ ተገቢ አቅጣጫ ነው ብሎ በማመን በእኛ በኩልስ የነበረው ችግር ምንድነው? የሚለውን ጥያቄ አንስቶ ለመመለስ ከፍተኛ ጥረት አድርጎዋል፡፡ ይህ ነገሮች ወደ ውጭ ከማላከክ በዘለለ ሙሉ ቁጥጥር ባለን በራሳቸን ላይ የውስጥ ፍተሻ ማድረግ ጠቃሚና ተገቢ ነው ከሚል እምነት የመነጨ ነበር፡፡ ይህ ማለት ግን የውጭ ጫናዎች በተለይም የኢህአዴግ አፈና የነበራቸውን ተፅዕኖ አሳንሶ ማየት እና የኢህዴግን አፋኝነትን ዝቅ አድርጎ መመልከት አድርገው የሚውስዱ ሰዎች አይጠፉም፡፡ ዋናው ጉዳይ እና ቅድሚያ መሰጠት ያለበት የውሰጥ ጥንካሬና ድክመትን ማወቁ ነው የሚለው ነበር፡፡ በዚህም መነሻ አንድነት በተቃዋሚ ፓርቲዎች ታሪክ የመጀመሪያ የሆነውን የአምስት ዓመት ሰትራቴጂና ዕቅድ አዘጋጅቶ ለህዝብ ይፋ አድርጓል፡፡ ይህም ሆኖ ግን ሪፖርተርን የመሰሉ ጋዜጦች ተቃዋሚዎችን በጅምላ የሚመሩበት አቅጣጫ የሌላቸው አድርገው መፈረጃቸወን አላቆሙም፡፡ ሌሎችም ቢሆኑ ይህን ተከትለው ከማሰተጋባትና ተቃዋሚዎችን በጅምላ ከመክሰስ ወደኋላ አላሉም፡፡ ለማነኛውም ፍረጃው እንደተጠበቀ ሆኖ አንድነት ያለፉትን አራት ዓመታት ጎዞዉን ባስቀመጠው ሰትራቴጅና አምስት ዓመት ዕቅድ መሰረት አድርጎ ቀጥሏል፡፡ የእቅዱ ማጠቃለያ ዘመንም ከምርጫ ሁለት ሺ ሰባት ምርጫ ጋር የሚገጣጠም ነው፡፡
ይህ የአምስት ዓመት ዕቅድ አፈፃፀም ግምገማ ወደፊት እንደሚካሄድ ታሳቢ ተደርጎ የመጨረሻው ዓመት ሊኖረን የሚገባው ዋነኛ ሰራ ምርጫን መሰረት ያደረገ እንደሚሆን ይታወቃል፡፡ ከዚህ አንፃር ገዢው ፓርቲ በጥርሱም በጥፍሩም ምርጫን ለማሸነፍ እየተንቀሳቀሰ ሲሆን እግረ መንገዱን ደግሞ የተቃዋሚዎችን በተለይም ደግም የአንድነትን ጥርስ ማውለቅና ጥፍር ማዶልደሙን ተያይዞታል፡፡ የጫወታው ህግ በጥርስም በጥፍርም መጫወት የሚፈቅድ ከሆነ ተወዳደሪዎች በተመጣጣኝ ጥርስም ጥፍርም ሊኖራቸው ይገባል፡፡ በቦክስ ጫወታ ደረጃ የሚወጣው በኪሎ ነው፡፡  አጫዋቹም/ዳኛውም ጫወታው ከመጀመሩ በፊት ቅድሚያ ሰጥቶ ማረጋገጥ ያለበት ይህን ጉዳይ ሁሉም ተወዳዳሪዎች ማሟላታቸውን ነው፡፡

አንድነት በዚህ ዓይነት የጥርስና የጥፍር ጫወታ ውስጥ ገዢው ፓርቲ ለማድረግ እንደሚፈልገው የተወዳደሪን ጥርስ ማርገፍና ጥፍር ማዶልዶም ተመጣጣኝ ምላሹ የገዢውን ፓርቲ ኢህአዴግ ጥርስ ማርገፍና ጥፍር ማዶልዶም መፍትሔ ይሆናል ብሎ አያምንም፡፡ ለውድድሩ ጥርስም ጥፍርም አስፈላጊ ከሆነ የአንድነት ፓርቲ ጥርስና ጥፍር እንዳይጎዳ መጠበቅ ቅድሚያ ይሰጠው ነው፡፡ ይህ ነው በቁጥጥራችን ስር የሚገኘው እና ዋና ትኩረታችን ሊወስድ የሚገባ እንዲሁም ተገቢ ጊዜ መስጠት አለብን የምንለው፡፡ የገዢውን ፓርቲ ጥርስ ለማርገፍና ጥፍርሩን ለማዶልዶም የምናባክነው ጊዜ የራሳችን በመጠበቅ ብሎም በቁርጠኝነት ባለማስደፈር ቢሆን የበለጠ አዋጭ ነው ብለን እናምናለን፡፡
በገዢው ፓርቲ መንገድ የምንሄድ ከሆነ ግን ወደፊት ለሚደረግ ውድድር በሁለቱም ወገን የሚኖሩ ተወዳደሪዎች በድድ እና በዱልዱም ጥፍር የሚወዳደሩ ይሆናሉ ማለት ነው፡፡ ይህ ደግሞ የጫወታውን ህግ መለወጥ የሚጠይቅ ይሆናል፡፡ በዛሬው የጥርስና ጥፍር ተምሳሌት ዋነኛ ወካይ ባህሪዎች በሁለቱም ጎራ የተሰለፉ ኢትዮጵያዊያን መሆናቸውን ነው፡፡ ኢህአዴግ የተቃዋሚዎችን በተለይ የአንድነትን ጥርስና ጥፍር ላይ አደጋ አደረሰ ማለት በየደረጃው ያሉ የአንድነት አባላትና ደጋፊዎች ላይ የሚወስዳቸው ቅጥ ያጡ ህገወጥ እርምጃዎች ማለታቸን ነው፡፡ በአፀፋው አንድነት ይህን ያድርግ ሲባል ደግሞ በኢህአዴግ አባላትና ደጋፊዎች ላይ ቅጥ ያጡ ሕገ ወጥ እርምጃዎች እንውሰድ ማለት ነው፡፡ የእነዚህ ድምር ውጤት ኢትዮጵያዊያንን በፖለቲካ አቋማቸው ከመጉዳት የሚተናነስ አይደለም፡፡ በዚህ ሁኔታ በተጎዳ ህዝብ ውስጥ ወደፊትም ቢሆን የተሸለ እና የሰለጠነ አማራጭ ይዞ በፖለቲካ መወዳደር ይቻላል የሚል እምነት አይኖርም፡፡ ለዚህም ነው ጉልበታችንን የኢህአዴግ አባላትን ለመጉዳት ወይም ለመበቀል ሳይሆን የአንድነት አባላትና ደጋፊዎችን አቅም በማሳደግ የአይደፈሬነት ሰነልቦና ማዳበር መሆን ይኖርበታል የምንለው፡፡
በአንድነት በኩል የአባላቶቻችንን አቅም እናሳድጋለን ብለን ስንነሳ በዋነኝነት በፖለቲካ ፓርቲዎች መካከል የሚደረግ ውድድር የሚመነጨው አንዱ ሀገር ወዳድ ሌላው ጠላት ነው ከሚል መንፈስ፣ ወይም በግል በደረሰብን በደል በቁጭትና ለበቀል መሆን እንደሌለበት በማሰተማር ነው፡፡ የፖለቲካ ፓርቲዎች የሚለያዩት በሚመርጡት የርዕዮተ ዓለም፣ ይህን ለመተግበር በሚያወጡት ፖሊሲና የማስፈፀሚያ ስትራቴጂዎች መሆኑን በማስረዳት በማስከተለም እነዚህ ልዩነቶች ሀገርን ሊጎዱ እንደሚችሉ ለህዝብ በማሰየት ህዝብ ለሚሰጠው ብይን ተገዢ ለመሆን ዝግጁ ሲኮን ነው፡፡ ይህን ልዩነታችንን ከጠባብ ቡድናዊ/የፓርቲ ወይም ሌላ ስብስብ ፍላጎት ከመነሳት “ሀገር ወዳድ እና የሀገር ጠላት” በሚል እንድንፈራረጅ ምክንያት ከሆነ የጋራ ሀገር እንዲኖረን እየሰራን ነው ማለት አይቻልም፡፡ ኢትዮጵያ ሀገራችን ለሁሉም ፓርቲዎች የጋራ መኖሪያ ከመሆን በዘለለ የሁሉም ፓርቲዎች አባላት የሚኖሩባት ብቻ ሳትሆን ለልጅ ልጆች በተሻለ ደረጃ ልናስተላልፋት ትልቅ ራዕይ ሰንቀን የምንቀሳቀስ መሆኑ በሁሉም ዘንድ መታወቅ አለበት፡፡ ኢትዮጵያችን እንድትኖር እኛም በእርሷ እንድንኮራ በሁሉም ጎራ የተሰለፍን ኢትዮጵያዊያን ሁሉ ከፍተኛ ሀገራዊ ኃላፊነት እንዳለብን አውቀን መንቀሳቀስ ይኖርብናል፡፡
በኢህአዴግ በኩል የሚገኙ አባላት ብሎም ከፍተኛ አመራሮች ጭምር የተቃዋሚ ፓርቲዎችን “ኪራይ ሰብሳቢ” ከሚል ቅጥ አንባሩ ከጠፋው ፍረጃ በላይ ግልፅ ሆኖ በወጣ መልኩ በተቃዋሚ ጎራ የተሰለፍን ዜጎች በፍፁም ለሀገር ደንታ የሌለን አድርገው መሳል የተለመደና አስልቺ ፕሮፓጋንዳ ከሆነ ቆይቶዋል፡፡ ይህ በእውነቱ የኢህአዴግ በጥርስም በጥፍርም ለመጫወታ እንዲመቸው የሌላውን ጥርስ ማርገፍና ጥፍር ማዶልዶሚያ ስትራቴጂው ነው፡፡ ይህ መንገድ ግን ብዙ ርቀት የማያስኬድ ብቻ ሳይሆን ለሀገራችን ዘላቂ ሰላም የሚበጅ ነው የሚል እምነት የለንም፡፡
በተቃዋሚ መስመር የተሰለፍን ሰዎች መካከልም ኢህአዴግን መሳደብ እንደ ዋና የትግል ሰልት የተያዘ እስኪመስ ድረስ ጥግ እንደምንሄድ አምኖ መቀበል ስህተታችንን ለማረም ጉልዕ ድርሻ አለው፡፡ አንዳንዴም የሃሳብ ልዩነትን በሰለጠነ መንገድ ከመግለፅ ይልቅ ሰነምግባር በጎደለው ሁኔታ በተለይ የግለሰቦችን ስብዕና የሚነኩ አላስፈላጊ የቃላት ጫወታዎች እንዳሉ እንረዳለን፡፡ “ቅኔው ሲጣፋበት ቀረርቶ ሞላበት” የሚለው አባባል በሁለቱም ጎራ የመከራከሪያ ሃሰብ ድርቀት ምልክት ሊሆን ይቻላል፡፡ ይህንን ከመሰረቱ ለመቅረፍ ከላይ እንደተገለፀው አባላትን በስነምግባር መኮትኮት እና ዋነኛው የፓርቲዎች ልዩነት መሰረት መሆን የሚገባው የፖሊሲና የስትራቴጂ ጉዳዮች ላይ እንዲያተኩሩ ማድረግ ነው፡፡ ይህ ሲሆን በከፍተኛ ሀገራዊ መግባባት ሰሜት መንቀሳቀስ ይቻላል የሚል ፅኑ እምነት ይዳብራል፡፡


Monday, October 27, 2014

የ “ካዛንችሱ መንግሰት በአዲሰ አበባ ማዘጋጃ ቤት”


ዛሬ ጥቅምት 17/ 2007 እግር ጥሎኝ አዲሰ አበባ ማዘጋጃ ቤት ጎራ ብዬ ነበር፡፡ የታዘብኩት ነገር ያስታወኝ ኤርሚያስ ለገስ “የመለስ ትሩፋቶች” በሚል ባወጣው መፅሃፍ ውስጥ “የካዛንችስ መንግሰት” ብሎ ያስነበበንን በገሃድ ከካዛንችስ ቦታ ቀይሮ አዲስ አበባ መስተዳደር ግቢ ውስጥ መኖሩን ነው፡፡ የካዛንችሱ መንግሰት ምን እንደሚሰራ እዚህ መዘርዘር አይጠበቅብኝም፤ በጥቅሉ ግን የአዲስ አበባ ህዝብ “መርጦ” ወይም ቀጥሮ ያስቀመጣቸው ሰዎች ሳይሆን ውሳኔ የሚስጡት ሌሎች በስውር በደህንነት ስም በኢህአዴግ የተቀመጡ ሰውር እጆች መሆናቸውን የሚያሳይ ነው፡፡
እነዚህ ሰውር እጆች ለእኛ ለተቃዋሚዎች አዲስ አይደሉም ለምሳሌ፤
  • ·         በሆቴሎች አዳራሽ ለማከራየት አንችልም ምንም ጠቃሚ ገንዘብ ቢሆን ሆቴሎች ፈቃደኞች አይደለም፤
  • ·         ማተሚያ ቤቶች የተቃዋሚ ፓርቲዎች ወይም እነርሱን ይደግፋሉ የሚባሉ የግል ጋዜጦችና መፅሄቶች አያትሙም፤
  • ·         መብራት ኃይል ለአንድነት የማተሚያ ማሽን ሊያንቀሳቅስ የሚችል የኤሌትሪክ ሀይል (ሰሪ ፌዝ የሚባል ሀይል) ለፓርቲ ለማስገባት ፈቃደኛ አይደለም፤
  • ·         ቤት አከራዮች ቤታቸውን ለማከራየት ይፈራሉ፤
  • ·         በቅስቀሳ ጊዜ መኪና እና የድምፅ መሳሪያዎች ማግኘት ፈተና ነው፤
  • ·         ለቅስቀሳ የወጡ ሰዎች እንደ በግ በየጣቢያው ሲታሰሩ የሚያስሩት ሰዎች በግልፅ ዩኒፎርም የለበሱት ፖሊሶች ሳይሆኑ በሬዲዮ የሚያዙ ማን እንደሆኑ የማይታወቁ ናቸው፤ ወዘተ

ይህ ሁሉ የሚሆነው በህግ አግባብ ሳይሆን በሰውር መንግስት ውስጥ ያሉ ሰውር እጆች የሚሰሩት ነው፡፡
ለዛሬ ፅሁፌ መነሻ የሆነኝ ግን በአዲስ አበባ ከተማ  መስተዳድር የህዝባዊ ስብሰባና ሰላማዊ ሰልፍ ማሳወቂያ ክፍል ኦፌሰር የሆኑት አቶ ማርቆስ ብዙነህ የሰጡን ምላሽ ነው፡፡ አንድነት ፓርቲ በቀጣይ ፓርቲው በሚያደርገው እንቅስቃሴዎች የፓርቲ አባላትን በስነ ምግባር የታነፁ እና ሰላማዊ ትግል በሰለጠነ መንገድ የሚደረግና በግብግብ ሳይሆን በሃሳብ የበላይነት የተመሰረተ እንዲሆን ለማድረግ ለሚያካሂደው ስልጠና ለማካሄድ አዳራሽ ለመከራየት ባቀረብነው ጥያቄ በጎ ምላሽ እንደሌለ ከውስጥ ሰምተን ምክንያቱን በግንባር ለማወቅ ሄጄ የሰማሁት ምላሽ በአንድ መንግሰታዊ ተቋም ውስጥ ተቀጥሮ ደሞዝ ከሚበላ ሲቪል ሰራተኛ የሚጠበቅ ሆኖ አላገኘሁትም፡፡ የሰጡን ምላሽ “አራት ሰዎች መጥተው ፍቃዱ እንዳይስጥ ጠይቀው አለቃይ እንዳትሰጥ ስለአለኝ ነው የሚል ነው፡፡” በቃ ይህ ነው ምክንያቱ፡፡ አንድነት ፓርቲ ይህን ፈቃዳ ላለማግኘት አንድም ያጎደለው መስፈርት የለም፡፡ አቶ ማርቆስ አለቃቸው ይህን መልስ ሲሰጣቸው ለምን? እንዴት ብዬ? ከመመሪያ አንጻር ልክ  አይደለም ብለው አይጠይቁም፡፡ አለቃቸውንም አይሞግቱም፡፡ እርሳቸውም የሚያውቁት አለቃቸውም ቢሆን እራሳቸው እንደማይወስኑ፡፡ የሚወስነው ይህ ስውር እጅ ያለው ካዛንችስ የነበረው አሁን በመስተዳድር ቅፅር ግቢ የሚገኘው መንግሰት እንደሆነ፡፡
አንድ መስሪያ ቤት ሰራውን የሚሰራው በአዋጅ በተሰጠው ስልጣን በደንብ እና መመሪያ እንደሆነ ይታወቃል፡፡ ኦፊሰሮች ተግባራቸውን ሲያከናውኑ ደግሞ እነዚህ የህግ ማዕቀፎች መሰረት አድረገው ነው ብለን እንጠብቃለን፡፡ በዚህች ምስኪን ሀገር ግን ይህ ምፀት ነው፡፡ በህግ ማዕቀፍ የሚሰራ ኦፊስር ማግኘት ዘበት እየሆነ መጥቶዋል፡፡ አለቃው በቃል አድርግ ያለውን የሚያደርግ የማርቆስ ዓይነት ኦፊሰር ሞልቶ ተርፎዋል፡፡ በጣም የሚገርመኝ የዚህ ዓይነት ኦፊሰሮች ለልጆቻቸው ሰራ ሄጃላሁ የሚሉ ከሆነ ብቻ ነው፡፡ ባይሉዋቸው ደግ ነው፡፡ ይህን ሊያደርጉ መሄዳቸውን ሲያውቁ ያፍሩባቸዋል ብዬ ስለማስብ ነው፡፡ ለምን ለልጆቻችን ማፈሪያ እንደምንሆን አይገባኝም፡፡
መልካም አስተዳደር አስፍናለሁ የሚል መንግሰት መልካም አሰተዳደር የሚሰፍነው በአዳራሽ ኮፍያና ቲ ሸርት ለብሶ በሚደረግ ዲስኩር እንዳልሆነ የገባው አይመስለም፡፡ መልካም አስተዳደር የሚሰፍነው በህግ ማዕቀፍ አገልግሎት የሚሰጥ ሲቪል ሰርቪስ ሰራተኛ አገልግሎት ሲሰጥ እንጂ በስውር በቃል በሚሰጥ ትዕዛዝ እንዳለሆነ መረዳት ይኖርብናል፡፡ ማርቆስ በሚሰጠው  መልስ እየተበሳጨ፣ እያዘነ ሲከፋውም እየተሳደበ የሚሄድ ተገልጋይ መዘዝ እንደሚያመጠ ግን የገባቸው አይመስለኝም፡፡ ይህ ሁሉ የሚሆነው ደግሞ በስውር መንግሰት በዚህ መንገድ እንዲሆን ስለሚፈልግ ነው፡፡
ዛሬ በግልፅ የተረዳሁት በአዲስ አበባ ከተማ መስተዳድር ብሎም በሀገር አቀፍ ደረጃ መልካም አስተዳደር የማሰፈን ችግር ምንጭ በደህንነት ስም በስውር ያለው መንግሰት የሚሰጠው ትዕዛዝ ሲሆን፣ ሲቀጥልም አድርግ ያሉትን ለማድረግ በተጠንቀቅ ዝግጁ የሆነው የማርቆስ ዓይነት ደሞዝ እየበሉ ያሉ ሲቪል ሰራተኞች ናቸው፡፡ አለቃዬ እንዲህ አድርግ ብሎኝ ነው በሚል መመሪያን መሰረት ያላደረግ ትዕዛዝ የሚሰፈፅሙ የማርቆስ ዓይነት ኦፊሰሮች የዚህች ሀገር መከራ እንዲረዝም፣ ህዝቡ የመልካም አስተዳደር ትሩፋት እንዳያገኝ ተባባሪ እንደሆኑ አበክረን መንገር ይኖርብናል፡፡ ይህንን አሜን ብሎ የተቀበለ ህዝብ መከራውና ግፉ ተስማምቶኛል እንዳለ ይቆጠራል፡፡ የዚህ ዓይነት ህዝብ ደግሞ ምንም ዓይነት አንባገነን መንግስት ቢመጣ የሚገባው ነው ማለት ተገቢ ነው ብዬ አምናለሁ፡፡ ኢህአዴግ አይመጥነንም ያለ ህዝብ በቃ!!!! ሊለው ይገባል፡፡ ኢህአዴግ በቃ ሊባል ይገባል!!!!

ቸር ይግጠምን

Saturday, October 18, 2014

የማሻሻያ ሞሽን

ጥቅምት 3/2007
ክቡር የኢፌዴሪ ፕሬዝደንት በምክር ቤቱ ደንብ መሰረት መሰከረም 26/2007 ዓ.ም ለሁለቱ ምክር ቤቶች የመክፈቻ ንግግር በማቅረባቸው ምሰጋናዬን አቀርባለሁ፡፡ በተለይ ባልተለመደ ሁኔታ የተሟላ ባይሆንም በመብራት መቆራረጥ ለተፈጠረው ችግር ይቅርታ ለመጠየቅ ድፍረት በማሳየታቸው ምስጋናዬ የላቀ ነው፡፡ ይህን ስናበረታታ ከፍ ወዳለው ተጠያቂነትን ወደ መውሰድ ያድጋል የሚል ተሰፋ ስለአለን ነው፡፡
ክቡር ፕሬዝዳንቱ ባቀረቡት የመክፈቻ ንግግር ላይ የተካተቱ እና ተገቢ ያልሆኑ ወይም ያልተሟሉ እና መሻሻል የሚገባቸው ያልኳቸውን ነጥቦች አቀርባለሁ፣
F በየዘርፉ በቀረበው ሪፖርት ያለፈውን አራት ዓመት አፈፃፀም ያካተተ ነው፡፡ ይሁን እንጂ በአብዛኛው የቀረበው መንግሰት ተሳክቶልኛል ብሎ በሚያምነው አካባቢ ነው/ ያለመሳካታቸው የታመነው ከወጪ ንግድና ከውሃ አቅርቦት የመሳሰሉት በስተቀር/፡፡ በሪፖርቱ መግቢያ ላይ ባለፉት አራት ዓመታት ሁለት አሀዝ እድገት እንደተመዘገበ በያዝነው ዓመትም 11.4 እንደሚሆን ይገልፃል፡፡ ይህም ማለት በእድገትና ትራንሰፎርሜሽን ዕቅድ ላይ የተቀመጠው 11.2 ግብ አሳክተናል እንደማለት ነው፡፡ አሁን በመሬት ላይ ያለው ሀቅ ግን፣
o   የባቡር መስመር ከታቀደው 2395 ኪሎሜትር100 ኪሎ ሜትርም አይጠናቀቅም (ሁላችንም እንድናተኩር የሚፈለገው በአዲስ አበባ 34 ኪሎ ሜትር ላይ ብቻ ነው)፤
o   662 ሚሊዮን ዶላር በዓመት የውጭ ምንዛሪ ያስገባል የተባለለቻው የሰኳር ፋብሪካዎች፣ ወደ ውጭ መላኩ ቀርቶ ለሀገር ውስጥ ፍጆታ ከውጭ ግዥ እየተከናወነ ነው፤
o   የማንፋክቸሪን ሴክተር እየተሰፋፋ አይደለም፣በዚህ ዘርፍ ለመሳተፍ የሚመጣ ባለሀብት ቢኖር እንኳን ሊያስተናግደው የሚችል የሀይል አቅርቦት የለም (8000 ሜጋ ዋት ይኖረናል ተብሎ የነበረው በዕቅድ ዘመኑ መጨረሻ 3500 መድረስ ከተቻለ ትልቅ ስኬት ነው)፤
o   የመንገድ ግንባታ ከታቀደው ግማሽ መሰራት የሚቻል አይመስለንም፤
o   የትላልቅ ዘመናዊ እርሻዎች ታቅደው የነበረው 3ሚሊዮን ሄክታር ለአልሚዎች ለመስጠት አስር በመቶ እንኳን የተሳካ አይደለለም፣ የተሰጣቸውም ቢሆኑ በአግባቡ እየሰሩ እንዳልሆነ ይታወቃል፤
o   በምግብ እህል እራሳችንን ጭለናል የሚል ፕሮፓጋንዳ ቢኖርም ሰንዴ አሁን ከውጭ እየገዛን ለዋጋ ማረጋጋት በሚል እየቀረበ ነው እየቀረበ ነው፤
እነዚህን ዋና ዋና የልማት ግቦች ማሳካት ባልተቻለበት ሁኔታ በዕቅዱ የመጀመሪያ ሶስት ዓመታት የነበረውን እጅግ አሳሳቢ የዋጋ ንረት ጋር ተደምሮ  የእድገቱ ቁጥር ለዕቅዱ ሊቀንስ ያልቻለው ምን የተለየ እነዚህን ጉድለቶች ማካካሻ ተገኝቶ ነው? የሚል አጠቃላይ አሰተያየት አለኝ፡፡ የእነዚህ ጉድለቶች ለእድገት ምጣኔ ትርጉም የላቸውም አንባልም ብዬ ነው፡፡

F በሪፖርቱ ገፅ 4 ቁጠባ በእድገትና ትራንሰፎሜሽን ከታቀደው በላይ መድረሱን ነገር ግን ከዚህ በላይ መስራት የሚያስችል አቅም እንዳለ ይገልፃል፡፡ አሁን የተገኘውም ውጤት በከተማ የቤቶች ግንባታ እና በቦንድ ሸያጭ የተገኘው ከፍተኛ ነው፡፡ ሪፖርቱ የግብርናው ሴክተር የኤኮኖሚው የጀርባ አጥንት ሆኖ ቀጥሎዋል በተለይም አነሰተኛ ማሳ በሚያካሄደው የአርሶ አደር ሚና ከፍተኛ እንደሆነ አሰቀምጦዋል፡፡ ከዚህ ሴክተር ቁጠባን በተገቢ ሁኔታ ማግኘት ያልተቻለው እና ለሀገር ውስጥ ገቢም ይህ ነው የሚባል ድርሻ ያልታየበት ምክንያት በሪፖርቱ ውስጥ አልተገለፀም፡፡ አሰተያየቴን ግልፅ ለማድረግ ሚሊየነር አርሶ ሀደሮች በቁጠባና በግብር ከፋይነት ያላቸው ሚና ምን ያህል እንዲሆነ አይታወቅም ለማለት ነው፡፡ ሁሌም ሲሸለሙ እንጂ ግብር ከፈሉ ሲባል ሰለማንሰማ ነው፡፡

F በሪፖርቱ ገፅ 4 ላይ “… ሀገራቸን ምንም እንኳን በመንግሰት ዋስትናም ሆነ ከዚያ ውጭ የምትወስደው የብድር መጠን ከጊዜ ወደጊዜ እየጨመረ የመጣ ቢሆንም በተለያዩ የዕዳ ጫና መለኪያዎች መሰረት ዝቅተኛ የዕዳ ጫና ካላቸው ሀገሮች ተርታ ትገኛለች፡፡….. ይህም ተጠብቆ ይቀጥል፡፡” ይላል፡፡ በቅርቡ የኢንተርሸናል ሞነተሪ ፈንድ ያቀረበው ሪፖርት እንዲሁም የዓለም ባንክ የሚያወጣቸው ፅሁፎች ከዚህ በተቃራኒ መንግስት ለመሰረተ ልማት ግንባታዎች የሚወሰዳቸውን ብድሮች ተጠቃለው የማይታዩ በመሆናቸው እነዚህ ብድሮች ጫናቸው ከፍተኛ ነው ብሎዋል፡፡ በዚህ ጉዳይ ላይ ሰምምነት መድረስ አለመቻሉም ተዘግቦዋል፡፡ መንግሰት የሚገነባቸው የመሰረተ ልማት አውታሮች ከመንግሰት በጀትም ሆነ የብድር ዕዳ ውስጥ ለማሳየት ያልተፈለገበት ምክንያት ተቀባይነት ያለው አይመስለኝም፡፡ ሪፖርቱም ከዚህ አኳያ ሙሉ ነው ማለት አይቻለም፡፡

F በሪፖርቱ ገፅ 6 “… ሀገራዊ ባለሀብቱ አሁንም በኢንዱስትሪው ዘርፍ ያለው ተሳትፎ አነሰተኛ ነው፡፡ በያዝነው ዓመት ማነቆዎችን ለመፍታት ተዋናዮችን ያሳተፈ ጥረት ይደረጋል፡፡” ይላል፡፡ ከዚህ አንፃር እጅግ ተሰፋ ሰጪ የሆነ የሀገር ውስጥ ቁጠባና ኢንቨሰትመንት በሚያበረታታ መልኩ በአክሲዮን ተቋቁመው ወደ ሰራ ለመግባት በጅምር ላይ የነበሩ ለምሳሌ ሀበሻ ሲሚንቶ፤ ከዚህ በፊት ጠቅላይ ሚኒስትሩ በስም የጠቀሱት ህብር ስኳር ለመሳሰሉት ትላልቅ የግል ባለሀብት ለሚመጡ ተነሳሸነቶች በቂ ትኩረትና ድጋፍ አለመስጠቱን ስናይ ሪፖርቱ በተግባር ካለው ጋር የሚጋጭ ነው የሚል አስተያየት አለን፡፡ አሁንም በዚህ ዓይነት ከመንግሰት ውጭ ለሚመጡ ተነሳሽነቶች ምንም ዝግጅት አይታይም፡፡

F በቤቶች ልማት በሪፖርቱ የቀረበው ቁጥር እና በሚሊዮን ከሚቆጠረው ቤት ፈላጊ ጋር ሲነፃፀር አሁንም ተመጣጣኝ ነው የሚል እምነት የለኝም፡፡ ባለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት እንዳልኩት መንግሰት የተመዝጋቢዎቹን ፍላጎት በማርካት ተሰፋቸውን ያለመልማል ብዬ አላምንም፡፡ ይህ ፕሮግራም መንግሰት ባለው አቅምና ቁርጠኝነት ላይ የሚፈተንበት እንደሚሆን አሁንም እምነቴ ነው፡፡ በሪፖርቱ ውስጥ “ በማህበር ተደራጅተው የሚሰሩ ዜጎች በተያዘው አቅጣጫ መሰረት የሚሰተናገዱ ይሆናል፡፡” ይላል፡፡ ይህ አቅጣጫ ምንድነው? ዜጎች ተበድረው ገንዘብ ባንክ ካሰገቡ በኋላ የመንግሰት የአቅጣጫ ለውጥ እና የአዳዲስ መመሪያና አቅጣጫ ፍለጋ የገባበት ምክንያት መታወቅ ይኖርበታል የሚል እምነት አለኝ፡፡ ከዚህ ጋር ተያይዞ በውጭ ለሚኖሩ ኢትዮጵያዊያን እና ትውልደ ኢትዮጵያዊያን የተያዘው አቅጣጫ ግብር ከፋዩ ዜጋ በግልፅ ሊያውቀው ስለሚገባ ግልፅ መሆን ይኖርበታል ብዬ አምናለሁ፡፡

F በሪፖርቱ ገፅ 11 “…. የሰኳር ልማት እና የማዳበሪያ ፋብሪካ ግንባታዎች በከፍተኛ ትኩረት እና ክትትል በተያዘላቸው ጊዜ እንዲጠናቀቁ ርብርብ ይደረጋል፡፡” ይላል፡፡ ለምንድነው ልክ የህዳሴ ግድቡ የደረሰበት ደረጃ እንደሚነገረው እነዚህ ሜጋ ፕሮጀክቶች የደረሱበት ደረጃ በግልፅ የማይገለፀው? በዚሁ ገፅ ላይ የመጠጥ ውሃ በተመለከተ በዕቅድ የተቀመጠው እንደማይደረስ ታምኖዋል፡፡ ስንት ለማድረስ ነው ክለሳ የተደረገው፣ ከዚህ ጋር በተያያዘ የተሳሳተ መረጃ ሲያቀርቡ የነበሩ ተጠያቂ ሆነዋል ወይ? የሚለውን ሪፖርቱ ማካተት አልቻለም፡፡

F በሪፖርቱ ገፅ 15 “በ2007 በሀገራችን የሚካሄደው ሃገራዊ ምርጫ ነፃና ዲሞክራሲያዊ እንዲሆን አስፈላጊው የቅድመ ዝግጅት ሥራዎች እንዲሰሩ መንግሰት የሚጠበቅበትን ሁሉ ያደርጋል፡፡ ሁሉም ተዋናይ ወገኖች ዋናው ፈራጁና ወሳኙ ህዝብ በሀገራቸን  የተፈጠረውን ሰፊ የሃሳብ ግብይት ዕድል በመጠቀም ደረጃ በደረጃ እየጎለበተ የመጣውን ዲሞክራሲያዊ ስርዓታችንን ኃላፊነት በተሞላበት መንፈስ ወደሌላ ከፍታ ማሸጋገር ይጠበቅብናል፡፡” የሚል ነው፡፡ በእኛ እይታ

o   ኢህአዴግ አስፈላጊውን ቅድመ ዝግጅት እንዲያደርግ መንግሰት የሚጠበቅበትን ሁሉ እያደረገ እንደሆነ እንረዳለን፡፡ ለምሳሌ የኢህአዴግን ፖሊሲ ለማስረፅ በመንግሰት ተቋማት፣ በዩኒቨርሲቲዎች ረጅም ጊዜ የወሰደ ውይይት ሲያደርግ ነበር፡፡ እኛም ያለንን አማራጭ ለመግለፅ ለአንድ ቀን ፈቃደኛ የሆኑ ተማሪዎችና መመህራን የሚገኙበት ሁኔታ ሊያመቻችልን ይችላል፡፡ በዚህ አጋጣሚ በተደረጉት ውይይቶች ለህዝቡ ከሰብሰባው ምን እንደተማራችሁ መግለፅ ቢችሉ የሚል ሀሳብ አለኝ፡፡
o   በምርጫ መቼም ዋናው ተዋናይ ፓርቲዎች ናቸው፡፡ ኢህአዴግ እንደ አንድ ፓርቲ በአዲስ አበባ ከተማ በየወረዳው ከመንግሰት ያገኘው ፅ/ቤት አለው፡፡ አንድነት እንደ ፓርቲ ቢሮ ለመከራየት ችግር ላይ ነው፡፡ የገንዘብ አይደለም በህዝቡ ላይ ካድሬዎች በሚፈጥሩት ስጋት ነው፡፡ ይህን እንደ መንግሰት አንድ ቢሮ ለመስጠት ፈቃደኛ ነው ብለው ያምናሉ፡፡ ወይም ባዶ ቦታ ቢሰጠን ደረጃውን የጠበቀ ቢሮ ልንገነባበት የምንችል እንደሆነ ላረጋግጥሎት እችላለሁ፡፡
o   “ሰፊ የሃሰብ ግብይት ዕድል መጠቀም” ማለትስ ምን ማለት ነው? የግል ሚዲያ እንዳይኖር ተግቶ የሚሰራ መንግሰት፣ ብሎገሮችን የሚያስር መንግሰት፣ የመንግሰትን ሚዲያ ለገዢው ፓርቲ መጠቀሚያነት ብቻ እንዲውል ለወሰነ መንግሰት ሰፊ የሃሳብ ግብይት ተፈጥሮዋል ለማለት ድፍረቱ ከየት እንደመጠ ግልፅ አይደለም፡፡
ሰለሆነም እነዚህ አገላለፆች ከሪፖርቱ ውስጥ እንዲወጡ ወይም እንዲሻሻሉ ቢደረግ መልካም ነው እላለሁ፡፡
ክቡር ፕሬዝዳንቱ ባደረጉት የመክፈቻ ንግግር ላይ ያልተካተቱና እንዲካተት ወይም ተገቢው ትኩረት እንዲሰጣቸው የምንፈልጋቸው ጉዳዮችን በዋና ዋና ርዕስ በማድረግ አቅርባለሁ፡፡
ፖለቲካዊ ጉዳዮች፤
F የ “ፀረ ሽብር ህግ” ሲወጣ እንደ ምክንያት ቀርቦ የነበረው ምርመራን ለማቀላጠፍ እንደሆነ ሲገለፅ ነበር፡፡ ነገር ግን አሁን ባለው ሁኔታ በፓርቲ ውስጥ ንቁ ተሳትፎ የሚያደርጉ ወጣቶችን እነ ሀብታሙን፤ ለሰላማዊ ለውጥ የሚተጉ ብሎገሮችን፤ አሰሮ ምርመራ እያደረኩ ነው ብሎ ማንገላትት ለዚህች ሀገር የሚጠቅም አይደለም፤ከዚህ ቀደም በወህኒ ቤት የሚገኙ ጓዶቻችን እነ አንዱዓለም ናትናኤል በቀለ ገርባ እንዲሁም  ጋዜጠኞች እስክንድር፣ ርዕዮት የመሳሰሉት የህሊና እስረኞች ናቸው ብለን ስለምናምን አሁንም ፖለቲካው መፍትሔ የሚሻ ጉዳይ ነው ብለን እናምናል፤

F በአሁኑ ሰዓት መንግሰት በውጭ ከሚኖሩ ኢትዮጵያዊያን ጋር የገጠመው አላስፈላጊ ግብ ግብ ለልማት ልናውለው የምንችለውን አቅም ከማባከን ያለፈ አንድም ፋይዳ ስለማይኖረው በሁለቱም ወገን ስክነት በተሞላበት ሁኔታ በውይይት እንዲፈታ ማድረግ ይገባል ብለን እናምናለን፡፡ ይህ በግንባር ቀደምነት መውሰድ ያለበትም መንግሰት ነው የሚል እምነት አለን፡፡ ይህ ሲሆን በውጭ የሚኖሩ ኢትዮጵያዊያን እና ትውልደ ኢትዮጵያዊያን ለሀገራቸው የሚያደርጉትን አስተዋፆ አሁን በሪፖርቱ ከተገለፀው በላይ ማድረግ ይቻላል የሚል እምነት ስለአለን ነው፡፡


F ባለፈው ዓመት ሪፖርት “የመድበለ ፓርቲ ሰርዓቱን ለማጠናከር ይቻል ዘንድም መንግሰት በህገ መንግሰታዊ ሰርዓት በተበጁ ህጋዊና ሰላማዊ ስልቶች ዓላማቸውን የሚያራምዱ የፖለቲካ ፓርቲዎች ለሚያደርጓቸው ፖለቲካዊ እንቅስቃሴዎች ምቹ ሁኔታዎችን ለመፍጠር የሚያደርገውን እንቅስቃሴ አጠናክሮ ይቀጥላል፡፡”የሚለው በዝርዝር ተቀምጦ ለክትትል/ለመጠየቅም በሚመች መልኩ ቢቀመጥ መፍትሄ ይሆናል፡፡ የሚል አስተያየት የሰጠሁ ቢሆንም ተቀባይነት አላገኝም እንደዛ ሆኖም አንድም ነገር ሳይከናወን ዓመቱ ተጠናቆዋል፡፡ አሁንም ቢሆን በሰላማዊ መንገድ በሀገር ውስጥ ለሚደረግ እንቅስቃሴ መንግሰት የሚፈጥረው ምቹ ሁኔታ እጅግ አስፈላጊ መሆኑን በመገንዘብ ግልፅ የሆነ እርምጃ እንዲወሰድ እንጠይቃለን፡፡

F ዛሬም እንደ ሁልጊዜው በድጋሚ መግለፅ የምፈልገው ተቃዋሚዎች እና ገዢው ፓርቲ በማንስማማባቸው የርዕዮት ዓለምና ፖሊሲ ዙሪያ በግልፅ ልዩነታችን እንደተጠበቀ ሆኖ፣ በጋራ የሀገር ጉዳይ እስከአሁን የሄድንበት ቅጥ ያጣ ፍረጃ እንዲቆም ማድረግ፤ ልዩነታችንን የምናራምድበት መድረክ በእኩልነት ማግኘት (በአስተዳደራዊና በፀጥታ ሀይሎች በኩል የሚደርስብን በደል እንግልት ያለምንም ቅድመ ሁኔታ ማስቀረት)፤የቅድሚያ ቅድሚያ የሚሰጠው ተግባር መሆን ይኖርበታል፡፡ በተለይ በዚህ የምርጫ ዓመት ለምርጫ በሚደረግ ቅስቀሳ ከፍተኛ ጥንቃቄ ማድረግ ይኖርብናል ብለን እናምናለን፡፡


F የፖለቲካ ምዕዳሩን መሰፋትና መጥበብ ለዲሞክራሲያዊ ስርዓት ግንባታ ያለውን ሁኔታ በመረዳት፤በጋዜጦችና መፅሄቶች ላይ ከህግ ውጭ ማተሚያ ቤቶች እንዳያትሙ የሚያስፈራሩ ካድሬዎችን፤ ከህግ አግባብ ውጭ የሚደረጉ እንቅስቃሴዎች በሙሉ ከውንብድና የሚለዩ ባለመሆናቸው ማሰቆም የማይችል እንዲሁም ይህንን ድርጊት ደግ አደረጉ የሚሉ የመንግሰት ሹሞችን አደብ የማያስገዛ መንግሰት  ጠመንጃ ካነሱበት ይልቅ በሃሳብ ሊታገሉት የተነሱትን እንዲመፈራ ማሳያ ብቻ ሳይሆን በሃሳብ ለመፋለም ዝግጁ ያለመሆኑን የሚያሳይ ነው፡፡

F ምርጫ በሚመለከት ምርጫ መወዳደር ለፓርቲዎች መደበኛ ተግባር እንደሆነ ይታወቃል፤ ለህዝብ ምርጫ እንዲሳተፍ ሲጋበዝም አማራጭ መኖሩን እርግጠኛ መሆን ያስፈልጋል፤ ከዚህ አንፃር መንግሰት አማራጭ የሌላቸው ተቃዋሚዎች የሚለውን በመተው አማራጫችንን ልናቀርብ የምንችልባቸውን በህግ የተፈቀዱትን ስርዓቶች እንዲያሰከብርልን በድጋሚ እንጠይቃለን፤በዲሞክራሲያዊ መንገድ የሚመጣ ማነኛውንም ውጤት ለመቀበል ግን ገዢው ፓርቲ ዝግጁ መሆኑን ማረጋገጥ ይኖርበታል፡፡


F በሀገራችን ኢትዮጵያ በተለያዩ ቦታዎች ዜጎች በብሔራቸውና የሚናገሩትን ቋንቋ መሰረት በማድረግ እንዲፈናቀሉ እየተደረገ ነው፡፡ ይህ ጉዳይ የፌዴራል መንግሰትን ጣልቃ ገብነት እስከ መጠየቅ ደርሶዋል፡፡ ማነኛውም ኢትዮጵያዊ በፈለገው ቦታ የመኖር ህገ መንግሰታዊ መብት ከመቼውም በላይ አደጋ ላይ እየወደቀ ነው፡፡ ይህ ደግሞ በህገ መንግሰት እውቅና ያገኘውን አንድ የፖለቲካ ማህበረስብ ምስረታ አደጋ ላይ የሚጥል ነው፡፡ ከዚህ አንፃር መንግሰት ችግሩን ከሰሩ ለመፍታት አቅም እንዳነሰው ማሳያ ነው፡፡ መንግሰት የችግሩ ምንጭ ከላሆነ ማለት ነው፡፡
ኤኮኖሚያዊ ጉዳዮች በተመለከተ
F አዲስ አበባ ከተማ ላይ እየቀረበ ያለ የሊዝ ዋጋ ከፍተኛ መሆኑ ምንጩ አሁንም በቁጥ ቁጥ እየቀረበ ያለ የመሬት አቅርቦት ሲሆን፣ በእኛ እምነት ይህን ቦታ በዚህ ዓይነት ዋጋ እየገዙ ያሉ ሰዎች ልማታዊ ባለሀብቶች ናቸው ብለን ለመውሰድ እንቸገራለን፡ይህ ሁኔታ በመኖሪያ ቤትም ሆነ በአገልግሎቶች ላይ የዋጋ ንረት እንደሚፈጥር ግልፅ ነው፡፡ ከዚህ ውጭ በህገ ወጥ መንገድ የተገኙ ገንዘቦች መመሸጊያ እንዳይሆን ሰጋት አለን፡፡ 65 ሺ ብር በካሬ ገዝቶ ምን ሊነግድበት እንደሆነ ማወቅ ከባድ ነው፡፡ መንግስት በአዲስ አበባ የሊዝ ሰርዓት ላይ ተገቢውን ማስተካከያ ማድረግ እንደሚችል ካላረጋገጥ ይህች ከተማ ለመካከለኛ እና ዝቅተኛ ገቢ ላላቸው ዜጎች መኖሪያ አይደለችም ብሎ እንደማወጅ ይቆጠራል፡፡

F ሀገራችን ኢትዮጵያ ንግድ ለመጀመር 2013 ከ 185 ሀገሮች 163 ከነበረችበት በ2014 ወደ 166 ዝቅ ብላለች፣ የሚገርመው ታክስ ለመክፈል ከነበረችበት 103 ወደ 109 ዝቅ ብላለች ይህን መንግሰት የኒዎ ሊብራል ሪፖርት ሊለውና ችላ ሊለው ቢችልም ለኢንቨሰትምንት የሚመጡ ባለሀብቶች ግን እምነት የሚጥሉበት ሪፖርት እንደሆነ ግልፅ ነው፡፡ ኢንቨሰትመንት ለመሳብ እየሰራን ነው እየተባለ ውጤታችን ዝቅ የሚልበት ምክንያት ማወቅ መፍተሔውን ለማግኘት ይረዳል ተብሎ ይታመናል፡፡ ታክስ ለመክፍል መቸገር ማለት ምን ማለት እንደሆነ ታክስ የምንከፍል ሰዎች እናውቀዋለን፡፡


ማሕበራዊ ጉዳዮች
F ወደ ተለያዩ ሀገሮች ለስራ በተለይ ወደ ሀረብ ሀገራት የሚሄዱ ሰዎች ህግድ ሳይነሳ በመቆየቱ ህገወጥ ዝውውሮች እየተበራከቱ መሀኑን ብዙዎች ይናገራሉ፡፡ በሀገራችን ያለው እድገት ዜጎችን ከሰደት መታደግ እስኪችል በህጋዊ መስመር እንዲሄዱና ለዜጎች ተገቢው ጥበቃ ማድረግ የሚችል መንግስት መሻታችን ይቀጥላል፡፡ በዚህ ጉዳይ ክፍተት ያለበት ሪፖርት ነው ብዬ ነው የምወሰደው፡፡

F አሁንም ዜጎች ለህክምና ወደ ውጭ እየሄዱ ከፍተኛ ወጪ እንደሚዳረጉ ይታወቃል፡፡ ከዚህ አንፃር በእድገትና ትራንሰፎርሜሽን ዕቅድ በተቀመጠው መሰረት ውጤት ማምጣት አልተቻለም፡፡ ይህ ጉዳይ አሁንም ይህች ሀገር የግል ባለሀብት በዚህ መስክ ለመሳብ ካለብን ችግር ጋር የተያያዘ መሆኑን ሪፖርቱ መግለፅ የቻለ አይደለም፡፡

በመጨረሻም
መንግሰት/በተለይም ገዢው ፓርቲ በቀጣይ ምርጫ ከግል ቡዳናዊ አስተሳሰብ ወጥቶ ለሀገር በሚበጅ መልኩ ለመድበለ ፓርቲ ስርዓት ግንባት የበኩሉን ድርሻ እንዲወጣ እየጠየቅን፤ በእኛ በኩል በኃላፊነት ሰሜት እንደምንንቀሳቀስ እና የኢትዮጵያ ህዝብ ግልፅ አማራጭ እንዳለን የምናሳይበት እንደሚሆን ለኢትዮጵያ ህዝብ ማረጋገጥ እፈልጋለሁ፡፡ 
ፈጣሪ ኢትዮጵያ ሀገራችንን እና ህዝቧን ይባርክ!!!!!!
አመሰግናለሁ
ግርማ ሠይፉ ማሩ


Thursday, October 2, 2014

የወታደራዊና አንባገነን መንግሰታት መኖሪና ባህሪያቸው

ዛሬ እንድ ፍልስፍና ብጤ አስኝቶኝ ነው ለመፃፍ የተነሳሳሁት፡፡ የወታደራዊ እና/ወይም አንባገነናዊ መንግሰታት መገላጫ በመኖሪያ አካባባያቸው ይገለፅ እንደሆን በሚል፡፡ ከዚህ ቀጥዬ የማነሳቸውን የወታደር መኖሪያዎች እና የቤተ መንግሰት ሁኔታን ይመለከታል፡፡ ዘወትር እነዚህን ግቢዎች ባየኋቸው ቁጥር የሚመጣብኝ አሳብም ስለሆነ ነው፡፡ ለነገሩ የዚህ ዓይነት አስተሳሰብ አዲስ አይደለም፡፡ የኢኮኖሚክስ ትምህርት መጀመሪያ የሆነው አንድ በላተኛ፣ አንድ አቅራቢ፣ አንድ ገበያ የሆነው ከአንድ ሰው ጀምሮ፣ ወደ ቤተሰብ እና ሀገር የሚያድገው ሞዴል ተፅህኖሞ ሊሆን ይችላል፡፡ ነገሮችን ከቀላል በመነሳት ወደ ውስብሰብ ደረጃ ለማጥናት ይረዳል የሚል እምነትም አለኝ፡፡
በወታደራዊ አገዛዝ ውስጥ የሆኑ ሀገሮች መጨረሻቸው እንዴት እንደሚሆኑ መረዳት የሚፈልግ ሰው በቦሌ መንገድ ከቦሌ ወሎ ሰፈር አደባባይ ከመድረሳችን በፊት በሚገኘው የመጨረሻ መታጠፊያ ላይ የሚገኘውን የፌዴራል ፖሊስ የ ”ቪ.አይ.ፒ ጥበቃ” ማረፊያ መመልከት ነው፡፡ ይህ ቤት በደርግ ጊዜ የከፍተኛ ባለስልጣን መኖሪያ እንደነበር የሚነገር ሲሆን፣ ዘመናዊ ቪላ እንደነበር ግን ብዙዎቻችን ምስክር ነን፡፡ ይህ ቪላ በአሁኑ ወቅት በአይናቸን እያየነው ፈራርሶ አሁን ያለበት ደረጃ ላይ ደርሶዋል፡፡ በቅርቡ ደግሞ የብሎኬት አጥር እና በፍፁም ለአካባቢው የማይመጥን የቆርቆሮ ግንባታ ተደርጎበታል፡፡ ህገወጥ ግንባታ የሚባለው እነሱን አይመለከትም፡፡ በአጠቃላይ ይህ ጊቢ ከነበረበት ደረጃ አሁን ወዳለበት ደረጃ የወረደው በእኔ እምነት የወታደር መኖሪያ በመደረጉ ነው፡፡ አንዲት ሀገርም በወታደራዊ አስተዳደር ውስጥ ስትወድቅ እንደዚህ እንደምትወርድ ማሳያ ሆኖ ያገለግላል፡፡ አሁን በግቢው ውስጥ የሚኖሩት ሰዎች ይህ ቤት ቀደም ሲል ምን ይመስል እንደነበር ስለማያውቁ ይህ የምሰጠው አስተያየት ሊገርማቸው ይችላል፡፡ እጅግ የሚያሳፍር ነው፡፡ ኪራይ ቤቶች ይህን ቤት በቅጡ መዝግቦ መያዙንም እጠራጠራለሁ፡፡ በእኔ እምነት ይህ ቤት አሁን ባለው የከተማ የሊዝ ዋጋ ቢሸጥ ለአዲስ አበባ ከተማ ሁሉም ክፍለ ከተሞች ለሚገኙ ፖሊስ ጣቢያዎች ደረጃውን የጠበቀ ፅ/ቤት ሊሰራ የሚችል ገንዘብ ሊያስገኝ ይችላል፡፡ በተመሳሳይ በከተማው ውስጥ ከግለሰቦች ተወርሰው ለፖሊስ ማረፊያ የተደረጉ ቤቶችን መመልከት ተመሳሳይ መሆኑን መረዳት ይቻላል፡፡ ለምንድነው ግን ከመሻሻል ይልቅ ወደኋላ መሄድ የሚቀናን? የእነዚህ ቤቶች አያያዝ ወታደራዊ መንግሰት ሀገርን እንዴት አድርጎ እንደሚያቆረቁዝ ማሳያ ይመስለኛል፡፡
ከላይ ወታደራዊ መንግሰት መገለጫ ያልኩትን ሞዴል ለማሳየት የሞከርኩ ሲሆን፡፡ የአንባገነን መንግሰታት ደግሞ መገለጫ ሊሆን ይቸላል ብዬ ያልኩትን ላካፍላችሁ፡፡ በአጋጣሚ ሆኖ በቀን አንድ ጊዜ በጠቅላይ ሚኒስትራችን ፅ/ቤት በጀርባ መግቢያ በር ማለፌ አይቀርም፡፡ በፕሬዝዳንቱ መኖሪያ ደግሞ በመኪና ብቻ ሳይሆን በእግር ጉዞ ምክንያትም በሳምንት አንድ ሁለቴ አልፋለሁ፡፡ እነዚህን ጊቢዎች ስትመለከቱ መታዘብ የምትችሉት በጊቢያቸው ያደገውን ሙጃ ሳር ብቻ ሳይሆን የንፅህና ጉድለቱን ጭምር ነው፡፡ እነዚህ መሪዎቻችን የሚኖሩበት ጊቢ በዚህ ደረጃ የቆሸሸ እንዲሆን ሲፈቅዱ የሚመሩትን ሀገር እንዴት አድርገው ገነት ሊያደርጉት እንደሚችሉ ማሰብ አስቸጋሪ ነው፡፡ ከእነዚህ ጊቢዎች የሚወጣው ፍሳሽ መንገድ አቋርጦ የሚሄድ ሲሆን አስፋልቶቹን እና የእግረኛ መንገዶቹን አበላሽቶ ስንመለከት ማዘናችን የማይቀር ነው፡፡ እርገጠኛ ነኝ መሪዎቹ የሚሄዱባቸው አካባቢዎች ምንጣፍ እንደሚሆኑ እና ሀገሩ ሁሉ እንደዚሁ እንዲመስላቸው እንደሚፈለግ፡፡ በእነዚህ ጊቢዎች አጥር ተጠግቶ መሄድ ግን አይቻልም፡፡ እሳት የሚተፋ ጠብመንጃ ያነገቱ ሰዎች ውክቢያ ይከተሎታል፡፡ ይህች ሀገር እነዚህን ጊቢዎች በንፅህና ለመያዝና ለተመልካች ማራኪ ለማድረግ አቅም የላትም ቅድሚያ የምንሰጠው ሌላ ነገር አለን ሊሉን አይችሉም፡፡ በእኔ እምነት የእነዚህ ትልቅ የሀገር ገፅታ ግንባታ የሚገለፅባቸው ጊቢዎች በሙጃ ተውጠውና ንፅህናቸው ተጓድሎ ከጊቢው አልፎ ሌሎችን ያበላሹበት ምክንያት በውስጡ ያሉት መሪዎች መገለጫ ነው፡፡
ለንፅፅር እንዲሆን ሁልጊዜ በቴሌቪሽን የምንመለከተውን የባራክ ኦባማን ቤተመንግሰት ልብ ይሏል፡፡ ማንም መጠራጠር የሌለበት በተግባርም እንዲሁ ግልፅ እና ንፁህ ማራኪ ነው፡፡ ውጭ ከሚገኘው ክፍት አጥር እስከ ቤቱ ድረስ ያለአንድ ግርዶሽ ፅድት ብሎ ይታያል፡፡ በቅርቡ ሰላም የሚነሱ ጠብመንጃ የታጠቁ ሰዎች አይታዩም፡፡ ይህ ማለት ጥበቃ አይካሄድም አይደለም፡፡ ለዚህም ፅሁፍ መነሻም የሆነኝ የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ጊቢ በአንድ ሰው መደፈሩን (አጥር ዘሎ መግባት) አስመልክቶ የግቢው የፀጥታ ሃላፊ ከስልጣን መልቀቅ ነው፡፡ ለምን እንደ ኢትዮጵያ ቤተመንግሰት ጠባቂዎች አላስፈራራችሁም በሚል አይደለም፡፡ ወደፊትም ጊቢውን ማጠር እንደመፍተሄ አይወሰድም፡፡ እንደወትሮ ለህዝብ ዕይታ ክፍት ይሆናል ጥበቃው ግን በስርዓት ይጠናከራል፡፡ የህዝብ መብት በማይነካ መልኩ፡፡ በእኛ ሀገር አንድ ሰው አምልጦ ቢገባ ምን ሊሆን እንደሚችል መገመት ቀላል ነው፡፡ ግንባሩን በጥይት ይባላል፡፡ በዚህም ምክንያት የቤተ መንግሰት የጥበቃ ኃለፊ የሚወስደው አንድም ኃላፊነት  አይኖርም፡፡ ከኃላፊነት ይለቃልም ተብሎ አይጠበቅም፡፡ ይህ ነገር  በእኛ ሀገር ስልጣን እንጂ ተጠያቂነት የሚባል ነገር እንደሌለ ማሳያ ነው፡፡ ተረኛ ጠበቂው ግን ዘሩ ተጣርቶ ከአንዱ ድርጅት ጋር ግንኙነት አለው ተብሎ መከራውን ይበላል፡፡ ኦሮሞ ከሆነ ኦነግ፣ አማራ ከሆነ ግንቦት 7፣ ወዘተ. ….
ልጅ ሆኜ በቢቢሲ የሰማሁት ነገር ታወሰኝ፡፡ ጋዜጠኛው ዲሞክራሲ የሌለባቸው መንግሰታት ሰር ያሉ ሀገራትን በምን እነለያለን? የሚል ጥያቄ  ያቀረበለት አንድ የፖለቲካ ተንተኛ እነዚህ ሀገራት በአብዛኛው “ዲሞክራቲክ” የሚል ቅጥል አላቸው ሲል ሰምቻለሁ፡፡ ዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ …….፡፡ ለምሳሌ የእኛን ጉድ ብንመለከት “የኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ” እንደሚለው ማለት ነው፡፡ በተግባር ዲሞክራሲም ፌዴራሊዝምም እንዳልሆነው ማለት ነው፡፡ እኔ ደግሞ ዛሬ የምለው ሀገራት ዲሞክራት መሆናችው እና አለመሆናቸው የሚለየው በቤተመንግሰት ጊቢ አያያዝና ጥበቃ ሰርዓታቸው ነው ቢባልም ሊያስኬድ ይችላል ነው፡፡ ይህን ሞዴል ወደሌላ አፍሪካ ሀገር ሰፋ አድርጎ የሚያየው ቢገኝ በንፅህና የሚጠበቅ ቤተ መንግሰት እና ለህዝብ ግልፅ የሆነ ቤተ መንግሰት ያላቸው ሀገሮች የተሸለ ዲሞክራቲክ ሊሆኑ ይችላሉ የሚል ግምት አለኝ፡፡  አስተሳሰብ በአካባቢ ከሚኖር ሁኔታ ሊመነጭ ይችላል፡፡ አካባቢውንም እንዲህ እንዲሆን የሚፈቅዱት ውስጡ የሚገቡት ሰዎች ናቸው፡፡ ለነገሩ ቤተ መንግሰትን ለማስተዳደር ኃለፊነት የሚሰጣቸው ሰዎች የሚመረጡበት መስፈርት እኮ …….
ሁለት ሺ ሰባት የቤተመንግሰት ጊቢውንም ሆነ ከዚያ ውጭ ያለውን አስተዳደር የምንሻሽልበት እንዲሆን እርምጃ መውሰድ ይኖርብናል፡፡
መልካም አዲሰ ዓመት ….መልካም መስቀል ….መልካም …..
ቸር ይግጠመን!!!!!


Tuesday, September 16, 2014

ተጠያቂነት የማያረጋግጥ የመልካም አስተዳደር ንቅናቄ

ባለፈው ሳምንት ማጠናቀቂያ በክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማሪያም ደሳለኝ ሰብሳቢነት የመንግሰት ከፍተኛ ባለስልጣኖች የ2006 የመልካም አስተዳደር ማሻሻያ አፈፃፀም ሪፖርት አቅርበዋል፡፡ ሁሉም ሪፖርት አቅራቢዎች “ፖወር ፖይንት” በሚባል የማይክሮ ሶፍት ፕሮግራም የተጠቀሙ ሲሆን አብዛኞቹ ይህን ፕሮግራም በቅጡ ለመጠቀም በግል ያላቸውን ዝቅተኛ ችሎታ ያሳየ ብቻ ሳይሆን በየመስሪያ ቤታቸው ሞያ ያላቸውን ሰዎች መጠቀም ያለመቻልና ያለመፈለግን ቁልጭ አድርጎ ያሳየ ነበር፡፡ የተፈቀደላቸውን አጭር ጊዜ ያመጣጠነ ዝግጅት ማድረግ ሳይችሉ ቀርተው ያዘጋጁትን የፅሁፍ ሪፖርት ሲያነቡ ጊዜ አለቀ እየተባሉ ማስተላለፍ የሚፈልጉትን ቁም ነገር (ካለቸው ማለቴ ነው) ትተው በመግቢያና በሪፖርት ይዘት ጊዜ ሲያባክኑ መታዘብ አሰገራሚ ነበር፡፡ ከዚህ አንፃር የውሃ መስኖ ኢነርጂ ሚኒስትሩ አቶ አለማየሁ ተገኑ በንፅፅር የተሻሉ ነበሩ ማለት ይቻላል፡፡ ቴክኖሎጂ የመጠቀም አስፈላጊነቱም ሰዓትን በአግባቡ በመጠቅም ተገቢውን መልዕክት ለማስተላለፍ ነው፡፡ ረፖርት አቅራቢዎች ስዓት በአግባቡ መጠቀም ባለመቻላቸው ሊያቀርቡ ያሰቡትን በሙሉ ካለማቅረባቸው በተጨማሪ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ላይ የሰዓት ቁጥጥር ስራ ጨምረውባቸው ነው የዋሉት፡፡ እርግጠኛ ነኝ የቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትር ቢሆኑ ኖሮ እንዴት ሊበሳጩባቸው እንደሚችሉ፡፡
የሲቪል ሰርቪስ ሚኒሰቴር ሚኒስትሯ ወ/ሮ አስቴር ማሞ ድርጅታቸው ኢህአዴግ ንቅናቄውን እንደ ፓርቲ የምርጫ ቅስቀሳ ግብዓት ለመጠቀም መወሰኑን በሚያሳብቅ ሁኔታ መሪ ድርጅታችን ኢህአዴግ አና መንግስታችን በሰጡት ትኩረት በሚል ነበር ንግግራቸውን የጀመሩት፡፡ የመሪ ድርጅታችን ኢህአዴግ በንግግሩ መግባት መልዕክት ለተሰበሰቡት የመንግስት ሹሞች ሳይሆን ጥሪ ለተደረገላቸው እና በአዳራሹ በብዛት ለታደሙት በኢህአዴግ አጣራር “የህዝብ አደረጃጀት” በመባል ለሚታወቁት የኢህአዴግ አፍቃሪዎች ነው፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትሩም ቢሆን የስብሰባ ታዳሚዎችን እንኳን ደህና መጣችሁ ለማለት “ውድ” የሚል ተቀፅላ ያገኙት እነዚሁ የህዝብ አደረጃጀቶች ናቸው፡፡ እርግጥ ነው በቀጣዩ ምርጫ በአሸናፊነት ለመውጣት የእነዚህ የህዝብ አደረጃጀቶች ሚና የላቀ ነው፡፡ በተለይ በአዲስ አበባ ተቃዋሚዎች ተጠናክረው ታዛቢ ካስቀመጡ ምርጫ ቦርድ ያለነዚህ የህዝብ አደረጃጀት ንቁ ተሳትፎ ቢሮ ቁጭ ብሎ ኢህአዴግን ብዙ ሊረዳው አይችልም፡፡ ጠቅላይ ሚኒሰትሩም ሆነ ፓርቲያቸው ይህ በቅጡ የገባቸው ይመስለኛል፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትሩ የመልካም አስተዳደር ጉዳይ እዚህና እዚያ የጎደሉ አግልግሎቶችን በማስተካከል ብቻ የሚያበቃ እንዳልሆነ ይልቁንም የመልካም አስተዳደር ችግር በቀጣይ የሚያመጣው “መዘዝ” ብዙ መሆኑን አበክረው ገልፀዋል፡፡ እርሳቸው “መዘዝ” ያሉትን እኛ አብዮት ስንለው የመንግሰት ሚዲያዎች ደግሞ ተቀብለው “የቀለምና የፍራፍሬ አብዮት” ይሉታል፡፡ ተመስገን ደሳለኝ አብዮት ብቻውን የማይጥም ከሆነ ብሎ ይመስለኛል “የህዳሴው አብዮት” ብሎታል፡፡ ለማነኛውም በዚህች ሀገር የተንሰራፋው የመልካም አስተዳደር ችግር መዘዙ ብዙ መሆኑ በጠቅላይ ሚኒስትር ደረጃ ከታመነ ይህ መዘዝ የተባለው ነገር ስሙ ብዙ አያስጨንቀንም፡፡ የሚያስጨንቀን ይህ መዘዝ እንዳይከተል ምን ማድረግ ይኖርብናል ነው፡፡ በተለይ መንግሰት ይህን መዘዝ ለመከላከል ብሎ ለናይጄሪያ ሽብርተኝነትን ለመከላከል ልምድ ይሆናል ተብሎ የተነገረለትን “የፀረ ሽብር” ህግ እንደመፍትሔ አሰቦት ከሆነ ከመዘዙ እየራቀ ሳይሆን ወደ መዘዙ በፍጥነት እየተጠጋ መሆኑን መረዳት ይኖርበታል፡፡
ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትሩም ሆኖ ሌሎች ሚኒሰትሮች በተደጋጋሚ ያነሱት ሌላ አብይ ነገር የኪራይ ሰብሳቢነት የሚመለከት ሲሆን ይህን የኪራይ ሰብሳቢነት የገለፁት የኪራይ ስብሳቢነት መረብ በሚል ነበር፡፡ በዕለቱ ያነበብኩት ጋዜጣ ደግሞ በኮንትሮባንድ ሊገባ የነበረ ወተት በኬላ መያዙን የሚገልፅ ክፍል ነበረው፡፡ ታዲያስ ስብሰባ ላይ ቁጭ ብዬ “የሰው ለሰው ድራማ” አስናቀ እና ኢህአዴግ ቁልጭ ብለው ይታዩኝ ጀመር፡፡ ይህን መረብ ለመበጠስ እሰከ አሁን እንዳልተቻለ እና ከፍተኛ ትግል እንደሚያስፈልግ ጠቅላይ ሚኒሰትሩን ጨምሮ ሚኒስትሮቹ  እየገለፁ ኢቲቪ ደግሞ አሰናቀ ለፍርድ ሳይቀርብ ለምን ሞተ ብሎ ዶክመንተሪ ይሰራል፡፡ የኪራይ ስብሳቢነት መረብ እስኪበጣጠስ ድረስ አስናቀ መኖር እና ማጋለጥ ነበረበት የሚል አቋም አለኝ፡፡ እናንተስ ምን ትላላችሁ ጎበዝ? አሁን አንድ የቴሌቪዥን ድራማ አጨራረስ እንዴት መሆን እንዳለበት ዶክመንተሪ ያስፈልገዋል? ለማንኛውም የሰው ለሰው ድራማ ደራሲና አዘጋጆች የህዝቡን እንጂ “ባለሞያ” ተብዬዎች በኢቲቪ ያቀረቡትን አስተያየት እንደማትሰሙ እርግጠኛ ነኝ፡፡
ዶክተር ደብረፅዮን በዕለቱ ሪፖርት ከሚያቀርቡት ሚኒስተሮች ቀዳሚውን ቦታ ያገኙ ነበሩ፡፡ ሪፖርት ያቀረቡት በዋነኝነት የቴሌኮሚኒኬሽን ሴክተሩን  በሚመለከትነው፡፡ ከሚመሩት መስሪያ ቤት አንፃር ሲታይም ቴክኖሎጂ በመጠቀም የተሻለ መሆን ሲጠበቅባቸው ማድረግ አልቻሉም፡፡ የቀረበው ሪፖርትም በፍፁም በመሬት ላይ ካላው የቴሌ ችግር ጋር የሚጣጣም አይደለም፡፡ በሪፖርቱ መስረት ሁሉም ችግሮች በእቅድ ከተያዘው ጊዜ ቀደም ብሎ የተተገበረ ሲሆን በአሁኑ ስዓት በተለይ በአዲስ አበባ ይህ ነው የሚባል ችግር እንደሌለ ነው ያበሰሩን፡፡ ይህ ግን በምንም መመዘኛ ተቀባይነት እንደሌለው ለመረዳት ከሪፖርታቸው በኋላ በሻይ እረፍት የተሰበሰቡት ሹመኞች ሳይቀሩ ሲያፌዙ እንደነበር ልነግራቸው እወዳለሁ፡፡ ዶክትር ደብረፅዩን ከአቀረቡት ሪፖርቱ ውስጥ የቴሌን ሰራ ለመስራት የፈጠሩት አደረጃጀት አንድ ጥሩ ነገር ጠቆም አድርጎን አልፏል፡፡ ይህም ፓርላማው ማፅደቅ የማያስፈልገው የቴሌን አገልግሎት በአሰራ ሦስት ክበቦች ወይም ክልሎች መከፋፈላቸው ነው፡፡ ይህም የተደረገው ለአሰራር ቅልጥፍና ሲባል እንደሆነ መረዳት ይቻላል፡፡ ይህ ተቀባይነት ያለው በጎ ጅምር ነው፡፡ በዚህ አደረጃጀት ሀረሪ ወይም ድሬዳዋ በምንም መለኪያ አንድ ክልል ሊሆን አይችሉም፡፡ አዲስ አበባ እንኳን አንድ ክልል ሊሆን አልቻለም፡፡ ሌሎችም በተመሳሳይ እንዲሁ፡፡ ይህ ለቴሌ አገልግሎት ምቹ የሆነ አደረጃጀት ለሌሎች የመልካም አስተዳደር እንዲሁም ማህበራዊ፣ ኤኮኖሚያዊ እና ፖለቲካዊ ጠቀሜታ በሚመች መልኩ የፌዴራል ስርዓቱ ይዋቀር ለምንል ሰዎች እንደ ጥሩ መግቢያ ሊያገለግል ይችላል የሚል እምነት አለኝ፡፡ የፌዴሬሽን ምክር ቤት ይህን ሀሳብ ከዶክተር ደብረፅዮን ወስዶ የህዝቦችን ቋንቋ እና ስነ ልቦና መሰረት ባደረገ ሁኔታ ቢየጠናው ጥሩ ሀሳብ ይመስለኛል፡፡ እሰኪ አንዴ ከያዝነው አስተሳሰብ ወጣ ብለን በተለየ መንገድ ለማሰብ እንሞክር፡፡ ዶክተር ደብረፅዩን ያቀረቡት ሀሳብ በሌሎች ፌዴራል መስሪያ ቤቶችም ሊሞከር ይችላል፡፡ ይህ የምክር ቤት ውሳኔ አይጠይቀም ብለዋልና፡፡
የንግድ ሚኒስትሩ አቶ ከበደ ጫኔ ባለፈው ዓመት ሰኳር እና ስንዴ እጥረት እንደነበረ በይፋ አምነዋል፡፡ ያቀረቡት ምክንያትም ሰኳር ይደርሳል ተብሎ ተገምቶ በፊንጫ እና ተንዳሆ ሰኳር ፋብሪካ በእቅዱ መሰረት ባለመድረሱ ችግር መከሰቱን ነው፡፡ እኛም ሰንል የነበረው ችግር አለ በእቅድ መስራት አልቻላችሁም እንዲሁም አትችሉም ነው፡፡ የሰንዴም የሰኳርም እጥረት የለም ሲሉን እንዳልነበር አሁን ችግር መኖሩን አምነው ከውጭ ግዥ እየተፈፀመ እንደሆነ ነግረውናል፡፡ ይህች ሀገር በሌላት የውጭ ምንዛሪ በሀገር ውስጥ ሊመረት የሚችልን ምርት ከውጭ እንድታሰገባ እያደረገ ያለን ፖሊሲና ፈፃሚዎቹ ተጠያቂ ሊያደርግ አልቻለም፡፡ ሰኳርና ስንዴ ማቅረብ ያልቻለ የሃያ ዓመት አገዛዝ መዘዝ ሊመጣበት እንደሚችል ቢፈራ ተገቢ ነው፡፡ አንድ በግብርና ላይ የተሰማሩ ባለሀብት ፈራ ተባ አያሉ “ስንዴ ከውጭ ታዞ የሚመጣበት ገዜ እና በሀገር ውስጥ ቢመረት የሚወሰደው ጊዜ ተቀራራቢ ነው፡፡” ብለዋል፡፡ አስከትለውም “ኢትዮጵያ ሰንዴና ሰኳር ኤክስፖርት የምታደርግ ሀገር እንጂ ከውጭ የምታስገባ መሆን የላባትም፡፡” በማለት ድጋፍ እንዲደረግላቸው ጠይቀዋል፡፡ ግብርና ግን መሬት ይፈልጋል መሬት ደግሞ በመንግሰት እጅ ሆኖ እንደልብ የሚገኝ አይደለም፡፡ የመሬት ፖሊሲያችን ይፈተሸ ስንል ለምን ጫጫታ ይበዛል?
የፍትሕ ሚኒሰትር ሪፖርት በጥቅምት ወር ባቀረቡት እቅድ በግርፊያ ምርመራ ያደርጋሉ ያሉዋቸውን ፖሊሶች እንዴት እንደተቆጣጠሩ ሳይነግሩን ቢጫ ታክሲ ማህበራት ጋር ስብሰባ አድርገናል እና የመሳሰሉትን ሪፖርት ማድረግ ምን ፋይዳ እንዳለው መረዳት ከባድ ነው፡፡ አስገራሚው ደግሞ ፍትህ ሚኒስትር የሚያዘጋጀው የዜጎች ቻርተር ነው፡፡ በእኔ እምነት ፍትህ ሚኒስትር ከህገ መንግሰቱ የተሻለ ሌላ የዜጎች ቻርተር የሚያስፈልገው አይመስለኝም፡፡ በፍትህ ሰርዓቱ እምነት እንዲኖረን ህገ መንግሰቱን ማስከበር ላይ ትኩረት መስጠት ይኖርበታል ብዬ አምናለሁ፡፡ ከሌሎች የመንግሰት አካላት ጋር ተባብሮ የህገ መንግስቱን መስረታዊ ድንጋጌዎች መናድ ማቆም አለበት፡፡ ለዚህም ማሳያው በቅርቡ በመፅሔቶች እና ጋዜጦች ላይ በመንግሰት ሚዲያ የተጀመረውን ስም ማጥፋት ተከትሎ በፍትህ ሚኒስትር መሪነት ወደ ፍርድ ቤት ማምራቱ ነው፡፡ ዘጠና ሚሊዮን ለሚሆን ህዝብ ቢበዛ 20 ሺ ኮፒ ለሚያትም  አንድ መፅሔት ሀገር ሊያጠፉ ነው የሚል መዓት ማውራት ምን አመጣው? ለነገሩ የፈሪ ዱላ የሚባለው ብዒል አንደሆነ መገመት አያሰቸግረም፡፡ ግለሰቦችን እያሳደዱ በማሰር እና አሰሮ ማሰረጃ እያፈላለኩ ነው ከሚል ፌዝ  መውጣት ይኖርብናል፡፡ መንግሰት “የፀረ ሸብር ህግ” ያሰፈልገናል ሲል የነበረው ሰዎችን ሳይዝ በቂ ማሰረጃ ለመሰብሰብ ይጠቅመኛል በሚል እንደነበር እናስታውሳለን፡፡
የከተማ ልማትና ቤቶች ሚኒስትሩ አቶ መኩሪያ ኃይሌ ይህ ነው የሚባል ነገር ሳያቀርቡ ሰዓት ሰዓት አልቋል ቢባሉም በከተማው የተንሰራፈውን የቤት ችግር ለመቅረፍ በተለይ በማሕበር ለመገንባት ገንዘባቸውን ባንክ ላስገቡ፣ ቅድሚያ ታገኛላችሁ ተግለው ከሚፈለገው 40 ከመቶ በላይ ባንክ ያስገቡ በ40/60 የተመዘገቡ እና በውጭ በሚኖሩ ኢትዮጵያዊየን በጉጉት ሲጠበቅ የነበረውን የቤት አቅርቦት ማሳካት አለመቻል አንድም ነጥብ ሊያነሱ አልቻሉም፡፡ ዜጎች ቤት እናገኛለኝ ብለው ተብደረው ባንክ ያሰቀመጡትን ገንዘብ የመንግሰት ባንክ እየነገደበት ትርፍ በትርፍ ሲሆን ዜጎች ቀጣይ ተሰፋቸው ምን እንደሆነ እንኳን ማሰረዳት አልቻሉም፡፡ አዲሱ የኮንዶሚኒየም ቤቶች ምዝገባ የተጀመረ ሰሞን አንድ ፅሁፍ አቅርቤ እንደ ነበር ይታወሳል፡፡ በሚቀጥለው ዓመት የቤቶች ግንባታን አስመልክቶ ሂሳብ ማውራረድ ስለሚኖር ለዛሬው በዚሁ ማለፍ ይሻላል፡፡ ዜጎች ግን አሁንም ተሰፋ እያደረጉ ነው?
በመጨረሻ ሁሉም ሪፖርት አድራጊ መስሪያ ቤቶች እንደ ችግር ያነሱት “የከፍተኛ አመራር እና ፈፃሚዎች የአመለካከት ችግር መኖር” የሚለው ይገኘበታል፡፡ ይህ ችግር ሁሌም በኢህአዴግ ሰፈር እንዳለ የምንረዳው ስለሆነ መፍትሔው በየአዳራሹ እየመሸጉ ሰልጣና፣ ስልጣና እየተባለ የሀገር ሀብትና ንብረት ከማባከን ተጠያቂነት የሚያሰፍን ሰርዓት በመዘርጋት ኃላፊነቱን ብቃት ላለው ዜጋ ማስረከብ ነው፡፡ አሁን በኢህአዴግ አባልነት በመንግሰት ስልጣን ላይ የሚገኙት በአብዛኛው ከዝቅተኛ ደረጃ እስከ ማስተርስ እና ከዚያም በላይ በርቀትም ሆነ በመደበኛ ይህች ሀገር አስተምራለች፡፡ እነዚህ ኃለፊዎች ባለፉት ሃያ ዓመታት የሰለጠኑ ቢሆንም ለህዝብ መልካም አስተዳደር ለማስፈን የሚያስችል አመለካከትና ክዕሎት ማደበር አልቻሉም፡፡ ስለዚህ ቦታውን መልቀቅ ግድ ይላቸዋል ብንል ድፍረት ሊሆን አይችልም፡፡ ቦታውን የማስለቀቅ ኃለፊነት ደግሞ የህዝብ ነው፡፡ የህዝብ ድምፅ ይከበር ዘንድ ሁሉም የድርሻውን መወጣት አለበት፡፡ ማንም የማንም ነፃ አውጪ አይደለም፡፡

ቸር ይግጠመን!!!

Thursday, September 4, 2014

የኢቲቪ ጥያቄዎች እና የእኔ መልሶች


በሰሞኑ ሰለ ግል ሚዲያው ትንሽ ለማለት ሞክሬ ነበር፡፡ የዚሁ ተከታታይ የሆነውን ይህ ፅሁፍ ደግሞ በዋነኝነት የአሁኑ የኢትዮጵ ብሮድካሰት ኮርፖሬሽን ለዘጋቢ ፊልም መስሪያ ብሎ ያዘጋጀውን ጥያቄ መሰረት አድርጌ አቀርብላችኋለው፡፡ ከጥያቄው መረዳት እንደምትችሉት ጥያቄዎቹ ለውንጀላ በሚያመች መልኩ የተዘጋጁ ሰለሆነ በግልፅነት ጥያቄውን ለመመለስ የሚሞኩሩ ሰዎች እንደ አትሌት ሀይሌ ገብረስላሴ መጠለፋቸው አይቀርም፡፡ ሚዲያ ብላችሁ አዲስ ዘመንን ስትከሱት ኢቲቪ ከሌላ ቦታ ካመጣው ጋር ቆርጦ ቀጥሎ ዘጋቢ ፊልም የግል ሚዲያውን ለመክሰስ ግብዓት ያደርጋችኋል፡፡ ይህን ለመከላከል ኢቲቪን በሩቁ ማለት ሳይሻል አይቀርም፡፡ ለዚህም ነው የቀረቡልኝን ጥያቄዎች ለኢቲቪ ብመልስ ምን ሊሆን እንደሚችል በምትረዱት ሁኔታ ከዚህ በታቸ የማቀርብላችሁ፡፡
ኢቲቪ እንደ መግቢያ በመጀመሪያ ያቀረበው ጥያቄ “ብሄራዊ ጥቅም ማለት ከኢትዮጵያ አንፃር መገለጫዎቹ ምንድናቸው?” የሚል ነው፡፡ የዚህ ጥያቄ ዓላማ በመጨረሻ ላይ ከሚቀርቡት ጥያቄዎች አንፃር ስታዩት የግል ሚዲያዎቹ እነዚህን ብሔራዊ ጥቅሞች እየተጋፉ ነው የሚል መደምደሚያ ለመስጠት እንዲመቸው ያቀረበው ነው፡፡ በእኔ እምነት በቅርቡ እየሰፋ የመጣውን ሀገር ማለት? የሚለው  ተጠየቅ መሬት ሲደመር ሰው (አንድ እና አንድ ሁለት እንደሚባለው) ማለት አይደለም፡፡ ለምሣሌ የዶክተር በድሉ ዋቅጅራ ሀገር ማለት የእኔ ልጅን ልብ ይሏል፡፡ የመለስ ዜናውንም ሀገር ማለት ህዝብ ነውም የሚረሳ አይደለም፡፡ የዶክተር ሀይሉ ኃርሃያን የሀገር ልክፍት ግጥምም ትዝ ይለኛል፡፡ የዚህን ጥያቄ መልስ እንደ እልም ፈቺ፤ ለእልም ፈቺ እንተውው እና በእኔ እምነት ብሔራዊ ጥቅም ወይም የሀገር ጥቅም ማለት በአጭሩ የዜጎች ጥቅም ብዬ ነው የማስበው፡፡ የሀገረ ኢትዮጵያ ጥቅም የሚባል ነገር ሁሉ የኢትዮጵያዊያን ጥቅም ማለት ነው ብዬ ነው የምረዳው፡፡ ኢትዮጵያዊያኖች እንዴት ነው የሚጠቀሙት ብለን ወደ ዝርዝር ሰንገባ ደግሞ በሠላም ወጥቶ መግባት/መኖር፤ የሰውነት መብት መከበር፤ የህግ የበላይነት መኖር፤ ወዘተ ሲሆኑ መንግሰት እነዚህን ኃላፊነቱን ለመወጣት የሚያስችለው መዋቅር እንዲኖረው ማደረግ ደግሞ የህዝቡ ዋነኛ ኃላፊነት ይሆናል፡፡ አንድ አንድ ሰዎች ጥቅም የሚባለውን ነገር ከራሳቸው በላይ ዘለግ አድርገው ማየት ስለማይችሉ ለልጅ ልጆች ሀገርን እንደ ሀገር አስጠብቆ ማለፍ የእነርሱ ድርሻ አይመስላቸውም፡፡ ለዚህም ነው ድንበር ማስከበርም፣ ዛፍ መትከልም፣ ወንዝ ተራራውም እንዲጠበቅ ማድረግ የመሳሰሉት አብይ ጉዳዩች ባለቤት ያጣሉ፡፡ ንቁ ዜጎች ግን ይህን በፍፁም አይዘነጉትም፡፡ ዛፉ ጥላው አድጎ ባይጠቀሙበት እንኳን ችግኝ መትከል ሀገራዊ ሃላፊነታቸው እንደሆነ ይረዳሉ፡፡ ድንበር ማስከበርም እንዲሁ ለልጅ ልጆቻቸው የሚተላለፍ መሆኑን ስለሚገነዘቡ ሀገር ቆርሰው አይሰጡም፡፡ ለኢቲቪ ይህን መልስ ብሰጠው የት ሰፈር እንደሚቆርጠውና ከምን ጋር እንደሚቀጥለው መገመት አያሰቸግርም፡፡
የኢቲቪ ተከታዩ ጥያቄ “የግል ፕሬሶች የሀገሪቱን ብሔራዊ ጥቅሞች በማሰጠበቅ ረገድ ምን ያህል እየሰሩ ነው?” የሚል ሲሆን ከመጀመሪያው ጥያቄ ጋር ያለው ዝምድና ፍንትው ብሎ ይታያችኋል፡፡ በግሌ ለዚህ ጥያቄ ያለኝ መልስ “አንድም የግል ፕሬስ” የኢትዮጵያን ጥቅም አሳልፎ ለአሜሪካ፣ ለአውሮፓ፣ ለሀረብ ወይም ለሌላ አካል አሳልፎ ይሰጣል የሚል እምንት ሊኖረኝ አይችልም፡፡ በሀገራችን እንዳለመታደል ሆኖ መንግሰት የሚባለው አካል ከላይ የዘረዘርኳቸውን የህዝብ ጥቅሞች ማስጠበቅ ሲያቅተው እና ይህን ችግሩን በሌላ ማለከክ ሲፈልግ የግል ሚዲያዎቹ ቅርብ ሆኖ ያገኛቸዋል፡፡ ስለ መንግሰት በጎ በጎውን መዘመር እንጂ የመንግሰትን ኃላፊነት ያለመወጣት እና ደካማነት ሲነሳ “የሀገር/የህዝብ ጥቅም” ተነካ ብሎ ቡራ ከረዩ ማለት ይቀናዋል፡፡ እውነቱን ስንመለከተው ግን ጥቅም የተነካ ከሆነ ወይም ሊነካ ከሆነ የተነካው የሹሞች ጥቅም ነው፡፡ እርሱም እንደ ዜጋ ከሚያገኙት ሳይሆን በወንበር ተገን የሚዘርፉት ነው፡፡ የግል መልሴ ለኢቲቪ ይህ ነበር የሚሆነው፡፡

ሶሰተኛው ጥያቄ “የግል ፕሬሶቹ መሰረታዊ የሆኑ የግለሰብ መብቶቸን በሚጋፋ መልኩ እየሰሩ ይገኛሉ ይባላል፤ በዚህ ላይ እርሶ ይስማማሉ ወይ?” የሚል ነው፡፡ እነዚህ የግል ፕሬሶች ማሰረጃ የሌለው  ነገር አትመው የግል መብት ነክተው ከሆነ በማስረጃ ፍርድ ቤት ማቅርብ ይቻላል፡፡ የግለሰብ መብት የሚሉት ግን ሹመኞቹን እንደሆነ መረዳት አይከብድም፡፡ አንድ አንድ ሹመኞች የህዝብ ማስተዳደሪያ የሆኑትን የሹመት ቦታዎች ሲረከቡ አብሮ የሚመጣውን የግል መብትና ነፃነት ገደብ ይዘነጉታል፡፡ የመንግሰት ንብረት ሲያስተዳድሩ በትክክል ካልተጠቀሙ ሚዲያው ይህን ለልጆቻቸው ብሎ ዝም ብሎ ሊያልፋቸው አይችልም፡፡ ይህ በመንግሰት ሹመኞች ላይ ብቻ ሳይሆን የህዝብ ህውቅናን ያገኘ ማነኛውም አይነት ታወቂነት ደረጃ ላይ የሚገኝ አርቲስት፣ ባለሀብት፣ ሯጭ፣ ወዘተ ሊሆን ይቸላል፡፡ ከዚህ በዘለለ ግን የግል ሚዲያዎች የግለሰቦችን መብቶች ሊጥሱ የሚችሉበት ምክንያት የለም፡፡ ማንነቱ ስለማይታወቅ ሰው ቢፅፉ ማንም ሊያነብላቸው አይችልም፡፡ ትርፉ ኪሳራ ነው የሚሆነው፡፡ በእርግጥ እነዚህን የግል መብቶች ከላይ እሰከታች የሚጣሱት ጡንቻና መዋቅር ባለው መንግሰት ነው፡፡ መንግሰት ደግሞ እነዚህን ድርጊቶች የሚፈፅመው ለህዝብ ጥቅም ስል ነው ይላል፡፡ እኛ ደግሞ በህዝብ ስም መብታችንን አትጣስ እያልን ለትግል የወጣነው በግል ሚዲያ ላይ ሳይሆን በመንግሰት ላይ ነው፡፡
አራተኛው ጥያቄ “አሁን በገበያ ላይ ያሉት የግል ፕሬሶች የጋዜጠኝነትን መሰረታዊ የስነ ምግባር መርሆዎችን ጠብቀው በመሰራት ረገድ ምን ዓይነት አዎንታዊና አሉታዊ አስተያየት አለዎት?” የሚል ነበር፡፡ ይህ በተደጋጋሚ ጋዜጠኛ ነኝ የሚሉት ሁሉ የሚያነሱት ነጥብ ሲሆን ሰምምነት ተደርሶበት ሁሉም ሊገዛለት ይገባል የተባለ የሰነ ምግባር መርሆ ግን በዓለም ላይ የለም፡፡ አብዛኞቹ የሚስማሙበት ግን ጋዜጣኛ መርዕ ማድረግ ያለበት ነገር ካለ “ተጠያቂነቱን ለህዝብ” ማድረግ ነው፡፡ ይህም ማለት የህዝቡን የመረጃ ፍላጎት ማርካት ነው፡፡ ከዚህ ተከትሎ የሚመጡ የመረጃ ትክክለኝነት፣ግብረገባዊነት፣የመሳሰሉት ሊመጡ ይችላሉ፡፡ ይህን ጋዜጠኛው ማሟላት ካቃተው ደግሞ ተጠያቂነቱ ለህዝብ ይሁን ካልን ፍርድ ሰጪውም ህዝብ ይሆናል ማለት ነው፡፡ ስለዚህ ህዝብ ዓይንና ጆሮ ሲከለክላቸው ከገበያ ይወጣሉ፡፡ ብሎም ይጠፋሉ፡፡ በዚህ ጊዜ “አከፋፋዮች” ናቸው እንዲህ የሚያደረጉት የሚል ክስ ውሃ አይቋጥርም፡፡ በውጭ ሀይል ግፊት ነው የሚለውም ክስ የትም የሚያደርስ አይሆንም ማለት ነው፡፡

በመጨረሻ የቀረበው ጥያቄ “የፖለቲካ ፓርቲዎችና ፕሬስ አንዱ በሌላው ላይ ያላቸው አዎንታዊና አሉታዊ ተፅህዕኖ እንዴት ይታያል?” የሚል ነው፡፡ የዚህ ጥያቄ ዓላማ የግል ፕሬሶቹ የተቃዋሚ ፓርቲዎች ልሣን ሆኑ የሚል መደምደሚያ ላይ መድረስ ነው፡፡ በእውነቱ ግን ሁልጊዜ ፕሬስ  “የWatch Dog - የህዝብን ጥቅም የመጠበቅ” ስራውን መዘንጋት የለበትም - ፓርቲዎች በየተራ ስልጣን የሚይዙ ስለሆነ የፕሬስ ይሁንታን ለማግኘት መጣጣራቸው አይቀርም፡፡ ተገቢም ነው፡፡ በእኛ ሀገር ገዢው ፓርቲ “የህዝብ/የመንግስት” የሚባሉትን ሚዲያዎች ጠቅልሎ የያዘና መረጃም የማይስጥ ስለሆነ፤ የግል ሚዲያዎች ደግሞ በመንግሰት በኩል የተነፈጉትን መረጃ ለማግኘት እና የገዢው ፓርቲ ተግባርም ትክክል እንዳልሆነ ለማሳየት በተቃዋሚ ፓርቲዎች ጋር ቢወግኑ ክፋት የለው፡፡ ለነገሩ መንግስት መረጃ እየሰጣቸውም ቢሆን መንግሰት መደገፍ የማይፈልግ የግል ሚዲያ ማቋቋም ነውር የለውም፡፡ ነውር የሚሆነው በመንግሰት ሚዲያ ገዢውን ፓርቲ ብቻ ማገልገል ነው፡፡