Sunday, May 8, 2016

ቅንጅት ፓርላማ አልገባም አላለም የእኔ ዕይታ ….. (የነፃነጽ ዋጋ ሰንት ነው? ከሚለው መፅሃፍ የተወሰደ)



ቅንጅት ፓርላማ አልገባም፣ አዲስ አበባንም አልረከብም በማለቱ ለዚህች ሀገር የመድብለ ፓርቲ ስርዓት ግንባታ ላይ አሉታዊ አሰተወፅኦ አድርጎዋል የሚለው ድምዳሜ ትክክል አይደለም እላለሁ፡፡ ይህም የሆነው አንዳንዶች ሳያውቁ በሰህተት አንዳንዶቹ ደግሞ አውቀው በድፍረት የሚነዙት ፕሮፓጋንዳ ውጤት ነው፡፡ ሃቁ ግን ቅንጅት የወሰነው ፓርላማ እንግባ አዲስ አበባንም እንረከብ የሚል ነው፡፡ ይህ በቃለ ጉባዔ የተያዘና የተወሰነ ነው፡፡ በግልባጩ ግን ኢህአዴግ ፓርላማ እንዳይገቡ አጥር ያጠረበትና፤ አዲስ አበባን አላሰረክበም ያለበት መሆኑ ነው፡፡(ይህንን ጉዳይ መረዳት የፈለገ ግማሽ ሙሉ እና ግማሽ ጎዶሎ - HALF FULL AND HALF EMPETY- በሚለው ምልከታ መሆን አለበት)፡፡
ኢህአዴግ ይህንን በህዝቡ ዘንድ ለማሰረፅ በስፋት የተጠቀመው በሞኖፖል በያዘው ሚዲያ አማካኝነት ነው፡፡ የኢትዮጵያ ሬዲዮና ቴሌቪዥን ድርጅት ቅንጅት ፓርላማ አልገባም አለ፣ አዲስ አባባን አልረከብም አለ የሚለውን የተሳሳተ መረጃ እውነት አሰኪመስል ድረስ ህዝቡን ግቶታል፡፡ ከተራው ባተሌ እሰከ ምሁር ተብዬው ድረስ ማለት ነው፡፡
የኢህአዴግ ካድሬዎች የሚያሳዝኑኝ ፓርቲያቸው የሚመራቸው በተሳሳተ መንገድ መሆኑን አለመገንዘባቸው ብቻ ሳይሆን ለተቃዋሚ ፓርቲዎች እንዲኖራቸው የሚፈልገውን ምስል ሰጥቶ ከዚያ ውጭ ማሰብ እንዳያችሉ ሲያደርጋቸው ነው፡፡ ልጅ ሆነን ጭራቅ እንደሚባለው፤ በእውነታው ዓለም የሌለ ነገር ግን ያለ የሚመስለን ነገር ማለት ነው፡፡ አብዛኞቹ የኢህአዴግ አባላትና ካድሬዎች ከሚነገራቸው ውጭ አለቆቻቸው የሚያነቡትን የግል ሚዲያ እንኳን እንዲያነቡና እንዲከታተሉ አይበረታቱም፡፡ የሚነገራቸውና እንዲያውቁ የሚፈለገው ሰለተቃዋሚ ፓርቲዎች እና የግል ሚዲያዎቹ አፍራሽነት ብቻ ነው፡፡ ተቃዋሚዎች ጭራቅ ከሆኑ የግል ሚዲያዎች አፍራሽ ከሆኑ እነዚህን መቅረብ ምን ያደርጋል፡፡ ይህ የሚደረገው ግን በግልፅ ማወዳደርና ማነፃፀር እንዳይኖር ነው፡፡ 
የኢህአዴግ መካሪ የሆነው ሪፖርተር ጋዜጣ ሁሌም ከሚያነሳቸው ጉዳዮች አንዱ እና የኢህአዴግ አባላትም በተደጋጋሚ የሚሉት ነገር አለ፡፡ ተቃዋሚዎች (በተለይ ቅንጅት) ምራኝ ብሎ የመረጠውን ህዝብ ተመልሶ እንዴት ልምራቸሁ ብሎ ሊጠይቅ ወደ ህዝብ ወረደ ይላሉ (ፓርላማ እንግባ ወይም አንግባ በሚል ከህዝብ ጋር ሲደረግ የነበረውን የህዝብ ውይይት አስመልክቶ)፡፡ በመጀመሪያ ህዝብን ለውሳኔ ማሳተፍ ለቅንጅት ሲሆን ወንጅል ይሆናል፡፡ ኢህአዴግ ግን ብርቱካን ሚደቅሳን ማስር ተገቢ ነበር በሚል ለህዝብ ግንዛቤ ለማሰጨበጥ በመላው ሀገሪቱ ውይይት ሲያደርግ ነበር፡፡ ይህ ዲሞክራሲያዊ ነው፡፡
ለማነኛውም ፓርላማ እንግባ ወይስ አንግባ የሚል ውይይት የተካሄደበት መሰረታዊ ምክንያት ትክክል ነበር፡፡ የህዝብ ድምፅ በተሟላ ሁኔታ ይከበር የሚል ይህም የሆነው ድምፃቸውን ለቅንጅት ስጥተው በጠራራ  ፀሐይ የተዘረፉ ዜጎች ሰለነበሩ ነው፡፡ ውይይቱ ለህዝብ በመከፈቱ የኢህአዴግ ሴረኞች መግቢያ ቀዳዳ አግኝተው ፓርላማ መግባት አይገባም የሚል አጀንዳ በስፋት አራምደዋል፡፡ እነርሱ ብቻም አይደለም ከምር የህዝብ ድምፅ መከበር አለበት የሚሉ ደጋፊዎችም ፓርላማ መግባት ትክክል አይደለም ብለው ሞግተዋል፡፡ በማይጠበቅ ሁኔታም ለደሞዝ ከሆነ እኛ እንከፍላችኋለን እሰከ ማለት የደረሱ ሰዎች ነበሩ፡፡ በቅንጅቱ የተወከሉት የመድረክ መሪዎች ግን ሲያስተላለፍ የነበረው መልዕክት ግን ውሳኔውን ፓርቲው እንደሚያደርግ ነገር ግን የፓርቲውን ውሳኔ ምንም ይሁን ምን ግን ህዝቡ ውሳኔውን በፀጋ እንዲቀበል ነበር፡፡
ይህ አካሄድ ያልጣመው ኢህአዴግ/መንግሰት ግን ቀጣይ ህዝብን የማወያየት ዕቅዶችን አገዱ፤ እንደዚያም ሆኖ ግን ቅንጅት ላዕላይ ምክር ቤት ታሪካዊ ውሳኔ ነው ያስተላለፈው የሚል ዕምነት አለኝ፡፡ ወደ ፓርላማ አትግቡ ያለውን የህብረተሰብ ድምፅ ከግምት ውስጥ ያሰገባና ኢህአዴግ ፓርላማ እንዲገቡ ከፈለገ ደግሞ ዕድል የሚሰጠው ነበር፡፡ ኢህአዴግ ግን የዚህ ዓይት ታሪካዊ ዕድሎችን የመጠቀም በዓል ሰለሌለው አንባገነንቱን ይፋ ያደረገ ጨካኝ እርምጃ መሰረት ያደረገውን ስትራቴጂውን ተግባራዊ አደረገ፡፡ የህዝብ ተመራጮችን ማሰርና ደጋፊዎችን በጠራራ ፀሐይ በአልሞ ተኳሾች መግደል፡፡
የቅንጅት ላዕላይ ምክርቤት ፓርላማ እንግባ የሚል ውሳኔ ነው የወሰነው ሲባል ምን ማለት እንደሆነ ግልፅ ለማድረግ፡፡ ይህ ውሳኔ ሲወሰን የተለያዩ አሰቦች ሲንሸራሸሩ ሰለነበር ጉዳዮችን ነጥብ በነጥብ ለይቶ በማየት በመጨረሻ ውሳኔው የተወሰነው በሙሉ ድምፅ ነው፡፡ ልደቱን ጨምሮ ማለት ነው፡፡ ከየት አምጥቶ እኔ እንጋብ ስል እነርሱ /አክራሪ የቅንጅት አመራሮች/ አንግባ አሉ እንደሚል ግልፅ አይደለም፡፡ ፓርላማ ለመግባት ግን ለኢህአዴግ የቀረበለት ቀላል ጥያቄዎች የሚከተሉት ነበሩ፤ (በቅንፍ የተጨመሩት የህገ መንግሰት አንቀፆች የኔናቸው)
  1. ነፃ፣ገለልተኛና ጠንካራ የማሰፈፀም ብቃት ያለው የምርጫ ቦርድ (ህገ መንግሰት አንቀፅ 102/
  2. ነፃና ገለልተኛ ፍርድ ቤት፤/ህገ መንግሰት አንቀፅ 79/
  3. የፖሊስ፣ የደህንነትና የመከላከያ ከፖለቲካ ጣልቃገብነት መራቅ፣(ህገ መንግሰት አንቀፅ 87/5፣)
  4. ሰኔ1/1997 ዓ.ም የተገደሉ ኢትዮጵያዊያንን ጉዳይ የሚያጣራ ገለልተኛ ኮሚሽን እንዲቋቋም፣ ግድያውን በፈፀሙ ላይም ህጋዊ እርምጃ እንዲወሰድ፤
  5. ፍትሐዊ የመንግሰት ሚዲያ አጠቃቀም እንዲኖር የግል ኤሌክትሮኒክስ ሚዲያ እንዲቋቋም፤(ህገ መንግሰት አንቀፅ 29/5)
  6. ከግንቦት ሰባት በኋላ በተወካዮች ምክር ቤት አሰራርና የአዲሰ አበባ መሰተዳድርን በተመለከተ የወጡትን ህጎች ቀድሞ ወደነበሩበት መመለስ፤
  7. በፖለቲካ አመለካከታቸው የታሰሩ አባላትን መፍታት የታሸጉ ቢሮዎቻችንን መክፈት እንዲሁም በተቃዋሚ ፖርቲ አባላት ላይ ያለው ማሳደድ እንዲቆም፤
  8. እነዚህን ጥያቄዎች በተግባር መዋላቸውን የሚከታተልና የሚያስፈፅም ነፃ ኮሚሽን ይቋቋም፤
የሚሉት ናቸው፡፡
የተጠየቁት ጥያቄዎች እነዚህ ናቸው፡፡ እነዚህ ደግሞ በህገ መንግሰት ላይ ከዚህ በተሻለ ዝርዝር የተቀመጡ ነገር ግን ገዢው ፓርቲ ሊያከብራቸው ያልቻላቸው፣ በተራ ቁጥር አራት የተጠቀሰው ደግሞ ተቃዋሚዎች ወንጀል ሰርተዋል ካለ ለራሱ ለመንግሰት መረጃ የሚያገኝበት ነበር፡፡ ይህም ሆኖ በጥቅምት ከተፈፀመው ድጋሚ ጭፍጨፋ በኋላ የተቋቋመው ኮሚቴ የግድያውን ምክንያት እንዳያጣራ (መንግሰት የወሰደውን እርምጃ ተመጣጣኝ ነው አይደለም የሚለው ብቻ እንዲያይ) ተደረገ፡፡
ከላይ የተዘረዘሩትን ነጥቦች መንግስት ተቀብሎ የቅንጅት መሪዎች ፓርላማ እንዲገቡ ማድረግ ቀላል የሚባል ስራ ነበር ለመንግሰት(በተለይ ለህዝብ ክብር ሲባል የቀረቡ ከመሆናቸው አንፃር - ፓርላማ አትግቡ ሲል የነበረውን የህብረተሰብ ክፍል ጥያቄ ለማስታመም ሰለሆነ)፡፡ ፓርላማ እንዲገቡ ሳይሆን እስርቤት ማስገባት በሚል በቂመኝነት ላይ ተመስርቶ የተነደፈን ስትራቴጂ ለመፈፀም የሚተጋን መንግሰትና/ፓርቲ ለካድሬዎቹ ቅንጅት ፓርላማ አልገባም አለ ብሎ ይነግራል፡፡ ካድሬዎችም ይህንኑ ይደግማሉ፡፡ ጉዳዩም ካለፈ በኋላ ለግል ግንዛቤ እንኳን እንዲሆናቸው በማለት ነገሩን በጥልቀት ከማየት ይልቅ ክሱን ወደ ማይመለከተው ቅንጅት ለማድረግ ይጥራሉ፡፡ እነዚህ ታዳ ምድባቸው አውቀው በድፍረት ከሚያጠፉት ናቸው ማለት ይቻላል፡፡
ለዚህ ማሳያ አቶ በረከተ ሰምዖን በመፅሐፋቸው እንዲህ ብለው ገልፀውታል፤
“ከቅንጅት ኢዴፓ፤ ከሌሎች ተቃዋሚ ድርጅቶች ደግሞ ህብረትና ኦፌዴን መሰከረም ላይ የተሰመረው ቀይ መሰመር የምር እንደሆነ ተገንዝበው አቤት ወዴት ሲሉ ሰንብተዋል፡፡ …….. በመቀጠልም የህብረት መሪዎች … በአድርባይነት ከምንጠላው ከአቶ ልደቱ ጋር አብረን በአንድ ጠረጴዛ አንቀመጥም አሉን፡፡ በበኩላችን አንዱ ሌላውን በአድርባይነት ሊከስ እንደማይችል እናውቃለን፡፡ እነርሱም ያውቃሉ፡፡ ሁለቱም ወገኖች (ህብረትና ኢዴፓ መሆናቸው ነው) ፀጋዬ ገብረመድህን እሳት ወይ አበባ በሚለው የግጥም መድብሉ በተስለምላሚነት የገለፃትን ቢራቢሮ ያስንቁናል፡፡” ገፅ 182 እና 183……………..
አብዛኛው የህብረተሰብ ክፍል በኢቲቪ/በሬዲዮ በሚቀርቡ ታቅደው ለማሳሳት በሚቅርቡ መረጃዎች ቢሳሳት ችግር የለውም ሊባል ይችላል፡፡ የተማረ የሚባለው ክፍል ግን እንደፈለገ የተሳሳተ መደምደሚያ መስራት አግባብ አይመስለኝም፡፡ የተማረ የሚለው መጠሪያ የተጨመረለት የተነገረን ለመስማት ብቻ ሳይሆን፣ ያሉትን መረጃዎች መርምሮ ለማየት የሚችል ነው በሚል ይመስለኛል፡፡
የታሪክ ተመራማሪዎች በተለይ ቅንጅት ለአቅመ ፓርቲ ሳይበቃ/ሳይቀናጅ መፍረስ ዋና ዋና ምክንያቶቸ፤ በተለይም ደግሞ በቅንጅት ጊዜ የተወሰዱትን የሠላማዊ ትግል አካሄዶች ጠንካራና ደካማ ጎኖቹን በዝርዝር እንዲፈትሹት እጠይቃለሁ፡፡ ይህ ሲሆን ከኢህአዴግም ሆነ ከቅንጅትም ግንኙነት የሌላቸው ቢሆኑ(ግንኙነት የለንም በሚል ሳይሆን የምር የሌላቸው ቢሆኑ ይመረጣል) ለታሪካችን እጅግ ጠቃሚ ይሆናል የሚል እምነት አለኝ፡፡ በግሌ ቅንጅት በወቅቱ  በነበረው ነባራዊ ሁኔታ ኃላፊነት የሚሰማው ውሣኔ እንደወሰነ ይሰማኛል፡፡ ምንም ሰህተት የለውም ልል ግን አልችልም፡፡ አንድ አንድ ጉዳዮች ከኩነት በኃላ ሲታዩ እንዲህ ቢሆን ማለት ይቻላል፡፡ ለምሣሌ ቅንጅት ያሰቀመጣቸውን ሰምንት ነጥቦች ባያነሳ ሊባል ይችላል፡፡ ይህንን ግን ማነፃፀር የሚኖርብን በዚያን ጊዜ ከነበረው የህብረተሰቡ ድምፃችን ይከበር ከሚለው ሰሜት ጋር በቅጡ መታየት ይኖርበታል፡፡
አዲስ አበባን በተመለከተ ፓርላማ አልገባም አሉ ካሉ በኋላ በመጨረሻም ከንቲባ ሆኖ የተመረጠውን ዶክተር ብርሃኑን ካሰሩ በኋላ እንደ አሸንጉሊት የሚያሽከረክሯቸውን ሠዎች (በተለይ እነ አየለ ጫሚሶን) ይዞ አዲስ አበባን ለማስረከብና የአዲስ አበባን ህዝብ ሊቀጡት ወስነው ነበር፡፡ ይሄን ጊዜ ከእስር ቤት ውጭ የሚገኙ የቅንጅት አባላት ይህ ሴራ እንዳይሳካ አድርገዋል፡፡ እኔንም ጨምሮ ይህ ደግሞ ትክክለኛ ውሳኔ ነበር፡፡ ሰለ አዲስ አበባ መረከብ ዶክትር ብርሃኑ በነፃነት ጎህ ሲቀድ በሚለው ከቃሊቲ በፃፈው መፅሐፉ በደንብ አስቀምጦታል፡፡ ይሀንን አንብቦ የቅንጅት ውሳኔ ምን አንደነበር መረዳት የባለቤቱ ይመስለኛል፡፡
ለማጠቃለል ቅንጅት ፓርላማ አልገባም አዲስ አበባንም አልረከበም የሚል አቋም አልወሰደም ሰለዚህ የቅንጅት አመራሮች እስር ቤት ከመግባት ፓርላማ ይሻላቸው ነበር የሚለው ምርጫ በኢህአዴግ የተወሰነ እንጂ በቅንጅት የተወሰነ ያለመሆኑን መረዳት ያሰፈልጋል ባይ ነኝ፡፡ ይህንን ውሳኔ በአቶ በረከት ሰምዖን የሁለት ምርጫዎች ወግ አንዲህ ተብሎ ተቀምጦዋል
“… የፌዴራል ፓርላማ ውስጥ እሰከገባችሁ ድረስ አዲሰ አበባን ትረከባለችሁ እንጂ    አንዱን ነጥላችሁ (አዲስ አበባን መረከብ ማለቱ ነው) እንድትወስዱ አይፈቀድም አለ፡፡” ገፅ 157
ሰለዚህ አዲሰ አበባን ቅንጅት አንረከብ አለ ነው መልሱ ሁይስ መንግሰት/ኢህአዴግ አላስረክብም አለ ነው የሚቀርበው፡፡ ወይም ሚዛናዊ ለመሆን ኢህአዴግ አዲስ አበባን ለማስረከብ ቅድመ ሁኔታ አሰቀምጦ ነበር እንበል፡፡ አሁንም ዳኝነቱን ለገለልተኛ አካል መተው ይሻላል፡፡


Thursday, April 21, 2016

ይህች ሀገር ወደፊት የማን ነች?



ወዳጆቼ አንዳንዴ ግራ የገባው ሰው ግራ ያጋባል እና ጥያቄየን በቅንነት ተመልከቱት፡፡ ይህን ምልጃ የጠየቁት ወዳጆቼን ነው፡፡ የእኔ ነገር የማይጥማቸው የምፅፈውን ሳያነቡ ከተፃፈው ፅሁፍ ጋር የማይገጥም፣ ብቻ እኔ ከኢህአዴግ ጋር ሰለማልገጥም ወይም ደግሞ ሌላ እነሱ ከሚፈልጉት ቡድን ጋር ስለማልገጥም ተቃራኒ የሆነ አስተያየት የሚያሰፍሩ አሉ፡፡ ድሮስ አንተ ብለው ስድብ ይጀምራሉ፡፡ ለእነርሱ ትክክለኛው ነገር መሳደብ ነው፡፡ ከእነሱ ስድብ ለማደን መፍትሔው ደግሞ የእነርሱን ቡድን መቀላቀል ነው፡፡ እኔ በእውነቱ በድን አይደለሁም እና ይህን አላደርገውም፡፡
ለማነኛውም ጥያቄ ወደፈጠረብኝ ነገር ልመለስ፡፡ ይህች ሀገር ወደፊት የማን ነች? የሚል ርዕስ ያደረኩት ጥያቄ በእውነቱ አስገራሚ ነው፡፡ መቶ ሚሊዮን የሚገመት ህዝብ የሚኖርባት ሀገር እንዴት የማን ነች? ይባላል ልትሉ ትችላላችሁ፡፡ እስኪ በእርግጠኝነት ኢትዮጵያ ሀገራችን የእኛም የልጆቻችንም ነች? የኢትዮጵያ ግዛትም በግዛቱ ውስጥ የምንኖር ኢትዮጵያዊያንም ከልባቸን በዚህች ሀገር አለን ወይ? ይህን እንድል ያደረገኝ ገፊ ምክንያት ደግሞ በዚህ ሳምንት ውስጥ በሜዲትሪያን ባህር ሰጥመው ያለቁት ኢትዮጵያዊያን ሰደት ሁኔታ ነው፡፡ ባለፈው ዓመት በተመሳሳይ ወቅት ኢትዮጵያዊያን በስደት መድረስ የፈለጉበት ሳይደርሱ ቀሩ፡፡ ይህ ዘንድሮም ተደገመ፡፡ ዘንድሮመ ዘፈኑ ያው ነው፡፡ በደላሎች ተጭበርብረው ሀገር የሚለቁ የሚል፡፡
ከዚህ በፊትም እንዳልኩት አሁንም እንደምደግመው የዚህ የሰደት መንስዔ ሀገራዊ ኢኮኖሚያዊ ችግር እና ኢኮኖሚው መፍትሔ እንዳያመጣ ወጥሮ የያዘው ፖለቲካው ነው፡፡ ሲደመር ግን ዋነኛው ምክንያት ፖለቲካዊ እንደሆነ ግልፅ ነው፡፡ ፖለቲካዊ ነው ሲባል ሰዎች የዚህ ፓርቲ አባል ደጋፊና ተቃዋሚ በመሆናቸው ሳይሆን አሁን ያለው የፖለቲካ ስርዓት ተገቢውን ኢኮኖሚያዊ ነፃነት ማረጋገጥ ያለመቻሉ ነው፡፡ ይህን ያደረጉት ደግሞ ገዢው ፓርቲና መንግሰት ናቸው፡፡ ሰለዚህ ኢትዮጵያዊያንን የሚያባርረው ወደ ስደት የሚልከው ደላላ ሳይሆን መንግሰት ነው፡፡ ደላላ የሚባሉት የሚሰሩት መንግሰት ልባቸውን ያሸፈተባቸውን ዜጎች ትክክል ይሁንም አይሁን በምድር ላይ ያሉትን የስደት አማራጭ ማሳየት ነው፡፡ ሰለዚህ መንግሰት አባራሪ መሆኑን እሰከ አልተረዳ ድረስ  መፍትሔውን ፍላጋ ቢደክምም አያገኘውም፡፡ ይህ እንግዲ ሀገራችን ኢትዮጵያ ዜጎቿን የምታጣበት አንዱ መንገድ መሆኑ ሲሆን፤ ይህች ሀገር ወደፊት የማን ነች? የሚል ጥያቄ ካስነሱብኝ ጉዳዮች አንዱ ነው፡፡
አስገራሚው ነገር እነዚህ ዜጎች ሲባረሩ አባራሪ ያልናቸው የመንግሰት ባለስልጣናትም ቢሆኑ ልጆቻቸው በሀገር የሉም፡፡ ከጅምሩ ልጆቻቸው በአውሮፓና አሜሪካ ይወለዳሉ፡፡ ከዚያም የውጭ ዜጋ ይሆናሉ፡፡ ኢትዮጵያዊነት ምን ያደርጋል ብለው እያደጉ ነው፡፡ እነዚህ ባለስልጣኖች ይህን ቢያደርጉ ብዙ አይገርመኝም፡፡ ምክንያቱም የሚሰሩት ስራ ልጆቻቸውን በነፃነት አንገታቸውን ቀና አድርገው እንዲኖሩ የሚያደርግ አይደለም፡፡ በውስጣቸው ባለው ሰላም ማጣትና በቀል የተነሳ፤ ሌላውም እነርሱን ይበቀላል ብለው ስለሚሰጉ ልጆቻቸውን ከውልደት እስከ እድገት የውጭ ያደርጓቸዋል፡፡ ድሮ ድሮ የመሪ ልጆች ተተኪ መሪ የሚሆኑበት እድል ነበራቸው፡፡ ምክንያቱም ወላጆቻቸው ባገኙት አጋጣሚ እነርሱም የመሪነት ክዕሎት ስለሚያዳብሩ ከሌላው የተሻለ እድል እንደሚኖራቸው ይታመናል፡፡ ምን ያደርጋል የመሪዎቻችን ልጆች በሜዲቴሪያን ባህር በኩልም ባይሆን ሀገረ የለሽ ሰደተኞች ናቸው፡፡
ሌላኛው አስገራሚ ነገር ደግሞ በሀገራችን አሉ የሚባሉት ባለገንዘቦችም (በሀገራችን ባለፀጋ መኖሩን አላውቅም) ልክ እንደ ባለስልጣኖቹ ልጆቻቸው ከውልደት እሰከ አድገት የውጭ የሚያደርጉ ናቸው፡፡ የሰሩት ህንፃ፣ የከፈቱትን ፋብሪካ ሊቆጣጠሩ ሊያስተዳድሩ የሚችሉ አይደሉም፡፡ ከብዙኃኑ የኢትዮጵያ ህዝብ ጋር ሊሆኑ የሚችሉ ኢትዮጵያዊ ዜጋ እያሳደጉልን አይደለም፡፡ አንዳንዶች በሀገር ውስጥ እያስተማሩ እንኳን ቢሆን ሲጀመር ትውልዳቸው ውጭ በመሆኑ እና ዜግነታቸው ሌላ በመሆኑ፣ ሲቀጥልም በሀገር ውስጥ ከፍተኛ ደረጃ ትምህርት ጥሩ ባለመሆኑ ለከፍተኛ ትምህርት ሲደርሱ ወደ ውጭ የሚላኩ ናቸው፡፡ ለስደት፡፡ ይህች ሀገር የእነርሱ አይደለችም እና ወደ ሌላ ሀገር ለከፍተኛ ትምህርትና ስራ ይሄዳሉ፡፡ ይህ ነው እንግዲ ይህች ሀገር ወደፊት የማን ነች? ብዬ የጅል ጥያቄ እንድጠይቅ ያስገደደኝ፡፡
በእርግጠኝነት መናገር የሚቻለው አብዛኛው ኢትዮጵያዊ ከሊቅ እሰከ ደቂቅ ወደ ውጭ ሀገር መሄድና መኖር እድል ቢያገኝ ያለምንም ማመንታት የሚሄድ ነው፡፡ የኢራቅ፣ ሊቢያ፣ ሶሪያ ዓይነት ግልፅ የወጣ የእርስ በእርስ ጦርነት ሳይኖር ኢትዮጵያዊያን ሀገር ለቆ ለመሰደድ የወሰኑበት ሚሰጥር በሀገራችን የተንሰራፋው ድህነት እና ድህነቱን የሚዘራብን የፖለቲካ ስርዓት ነው፡፡ የዚህ ስርዓት ተጠቃሚዎችም ቢሆኑ እንኳን ዜጎች ሀገሪቱን ለቀው እየሄዱ እንደሆነ ይታወቃል፡፡ ድሃው ዜጋ በእግሩ ድንበር አቋርጦ ያለ የሌለውን ጥሪት አሟጦ ከአውሬ እና ከባህር ማህበል ጋር ተጋፍጦ ሀገር ለቆ ይሰደዳል፡፡ የባለስልጣኑ እና የሀብታም ልጆች ደግሞ በቦሌ ደልቀቅ ብለው ሀገራቸውን ጥለው ይሰደዳሉ፡፡ የዚህ ድምር ውጤት በዚህች ሀገር ላይ ተሰፋ ያለው እየጠፋ መሆኑን ከማመላከት ውጭ ምን ሊባል ይችላል?
ለማነኛውም ግን በውጭ የሚኖሩ ኢትዮጵያዊያን እና ትውልደ ኢትዮጵያዊያን ወጣቱ ትውልድ ጥሎት እየሄደ ያለውን ሀገር ሁኔታው ቢመቻች ወደ ሀገራቸው መመለስ ይፈልጋሉ፡፡ እነርሱ የሚመጡት ግን የመጨረሻ የህይወት ዘመናቸውን በደስታና በፍሰሃ ለማሳለፍ እንጂ ጠቃሚ የሆነውን የህይወታቸውን ክፍል ጥገኝነት ለሰጣቸው ሀገር አበርክተዋል፡፡
በዩኒቨርሲት የሚያሰተምረው፣ በትምህርቱ የላቀ ውጤት ያመጣው ተማሪ፣ ለስራ የተሻለ ቦታ አለ የሚለው ወጣት፣ ወዘተ ሀገሩን ለቆ በህጋዊም ሆነ ህገወጥ መስመር ሀገር ለቆ ሲሰደድ ቆም ብሎ አለመጠየቅ መሄጃ መንገድ አጥቶ የቀረው ይበቃል ካልተባለ በስተቀር አሁን ያነሳሁት ጥያቄ የጅል ሊባል የሚችል አይለም፡፡
ቸር ይግጠመን!!!
ግርማ ሠይፉ ማሩ

Tuesday, March 29, 2016

የጠቅላይ ሚኒሰትሩ የለበጣ ስብሰባዎች!!!



ጠቅላይ ሚኒሰትር ኃይለማሪያም ሰሞኑን ስራ በዝቶባቸው እንደከረሙ ሁላችን እንረዳለን፡፡ የስራው ውጤታማነት የሚለካው ግን በሚያሰገኘው ፍሬ ነው፡፡ በእኔ  ግመገማ ስራቸው ለውጤት እንዳልሆነ የተረዳሁት ዘግየት ብዬ “ከተቃዋሚ ፓርቲ” ተብዬዎች ጋር ውይይት ካደረጉ በኋላ ነው፡፡ ቀደም ሲል ከንግድ ማህበረሰብ ቀጥሎም ከምሁራን ጋር ውይይት አድረጉ ሲባል የምር እኚህ ሰው የሚመሩት ድርጅት ልብ ገዛ ብዬ ተሰፋ ማድረጌ አልቀረም ነበር፡፡ ምን ያደርጋል በተመሳሳይ ለህዝብ ግንኙነት ሲባል የሚያደርጉት መሆኑን ያጋለጠ ስብሰባ መጋቢት 14 ቀን 2008 በማድረግ ተስፋዬ አጨለሙት፡፡ የብዙ ሰው ሰሜት እንደሚሆንም ተሰፋ አደርጋለሁ፡፡ ለነገሩ ከሁሉም ጋር የሚያደርጉት ስብሰባ የኢህአዴግ ክፉ መንፈስ የተጫነው ነበር፡፡ ከአቋም ፍንክች እንደማይሉ፣ እነርሱም ሌቦች ሌላውም ሌባ (የመንግሰትና የግል ሌቦች) መሆኑን በሚያስረግጥ መንፈስ የተካሄዱ ናቸው፡፡
ነጋዴዎችን ሰብሰበው ያስተላለፉት የመጨረሻ መልዕክት መንግስት ማሰር ቢፈልግ ሁሉም ከእስር ሊተርፍ እንደማይችል አስጠንቅቀው እና በተቻለ መጠንም አሸማቀው ነው፡፡ መልዕክቱ አሁንም ቢሆን ፀባይ ካሳመራችሁ የምናስረው እስር ቤት ሟቋቋም ድረስ የደረሱትን ብቻ ነው የሚሉ ይመስላሉ፡፡ ጠቅላይ ሚኒሰትራችን ነጋዴዎች እስር ቤት እንዳላቸው የነገሩን ነገር ብዙ የሚገርም አይደለም፡፡ በእኛ ሀገር አንድ የውጭ ኤምባሲ እስር ቤት እንደነበራው ይውራ ነበር (የኤርትራ ኤምባሲ)፤እፍኖም ይወስድ ነበር፡፡ ይህ ይሆን የነበረው ግን በመንግሰት የደህንነት ሰዎች ድጋፍና ትብብር ጭምር ነው፡፡ በእኔ እምነት አሁንም እስር ቤት ያቋቋመው ነጋዴ የደህንነት ድጋፍ አልነበረውም ብዬ አላምንም፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትሩ አሁንም የትኛው ነጋዴ የት ቦታ እስር ቤት አደራጅቶ ከማን ጋር ይስራ እንደነበር በግልፅ በስም ሊገልፁልን ግድ ይላቸዋል፤ በዚሁ ሁኔታም ክስ ተመስርቶ ማየት እንፈልጋል፡፡ (Name and Shame)፡፡  በዚህ አጋጣሚ ፕሮፌስር መስፍን ይህን አስመልክቶ በፌሰ ቡክ ገፃቸው ላይ ማለፊያ ነገር አስነብበውናል፡፡ የሚገርመው በጠቅላይ ሚኒስትር ደረጃ ይህ መነገሩ ነው እንጂ፤ አንባገነን ስርዓት ባበት ማንም ይህን ሊያደርግ ይቸላል የሚል ነው፡፡ ሁላችንም እንደምናውቀው በሶማሊያ ብዙ የጎበዝ አለቆች በነጋዴዎች የሚታዘዙ ማሰሪያዎች አሉዋቸው፡፡ ፀጥታም የሚያስከብሩት እነዚሁ የጎበዝ አለቆች ናቸው፡፡ እስከ አሁን ድረስ ይህ የቀረ አይመሰለኝም፡፡
የነጋዴውን ስብሰባ ጉዳይ ከመቋጨቴ በፊት “ነጋዴ በሙሉ ሌባ ነው” የሚል እንደምታ ያለውን ንግግር ጠቅላይ ሚኒሰትሩ ሲያደርጉ ነፃነቱ ያለው እና ነፃነቱን የሚያስከብር የንግድ ምክር ቤት ተወካይ ቢኖር ጠቅላይ ሚኒስትሩ ይቅርታ እንዲጠይቁ ማስገደድ ባይችል ለወጉ ለማረጉም ቢሆን ጥያቄ ያቀርብ ነበር፡፡ ይህ ሁሉ ነጋዴ ግብር እየከፈለ ያቆማትን ሀገር ሁላችሁም ሌቦች ናችሁ፤ ማሰር ብንፈልግ የሚቀር የለም የሚል መልዕክት ማስተላለፍ በፍፁም ተቀባይነት የሌለው ከጠቅላይ ሚኒስትር የማይጠበቅ ንግግር ነው፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትራችን አንድም ቀን በንግድ ተሳትፈው ስለማያውቅ ነጋዴዎች ትርፍ ለማሳደግ የሚወሰዷቸው የተለያዩ እርምጃዎች በሙሉ “የሌብነት ስራ” ነው ብለው ያምናሉ፡፡ ህጋዊ የሆነ የታክስ መቀነስ እንቅስቃሴ በትምህርት/በህውቀት (Legal Tax Evation) የተደገፈ መሆኑን የሚነግራቸው አማካሪ የላቸውም፡፡ አማካሪዎች ተብለው የተሰየሙት ተመሳሳይ በመሆናቸው ለውጥ ሊመጣ አይችለም፡፡
ከነጋዴዎች ቀጥለው ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከምሁራን ጋር ውይይት ማድረጋቸውን ሰምተናል፡፡ ነጋዴዎቹን ሲያነጋግሩ እንደነበረው ሁሉ ከምሁራኑ ጋር የነበረው መንፈስም ያው የኢህአዴግ ክፉ መንፈስ የተጫነው ነበር፡፡ ይህን ስብሰባ ከነጋዴዎቹ ልዩ የሚያደርገው ነገር “ከፈለጋችሁ ፓርቲ አቋቁሙና እንጋጠም” ማለታቸው ነበር፡፡ በእለቱ ስብሰባ የተገኙ ተሳታፊዎች የዋዛ የማይባል ጥያቄ ማንሳታቸውን እኛ አድማጮች ደግሞ በተሰጠው ኢህአዴጋዊ ማብራሪያና ማፈራሪያ ሳይሆን በጥያቄዎቹ መስመር ላይ መሆናችንን ማሳታወስ ግድ ነው፡፡ ምን ማለት ነው? ብሎ ለሚጠይቅ “ይህች ሀገር ነፃነት ያለው ህዝብ መኖሪያ አይደለችም፡፡ ጋዜጣኛም፣ ነጋዴም፣ ፖለቲከኛም፣ ተማሪም፣ ወዘተ በነፃነት የሚኖርበት ሀገር አይደለም፡፡” የሚለውን የምሁራን አስተያየት የምንደግፍ መሆኑን ለመግለፅ ነው፡፡
ከምሁራኑ ስብሰባ ከተሰነዘሩት አስተያየቶች አንዱ ጠቅላይ ሚኒሰትሩ “ደረታችሁን ነፍታችሁ የምትሄዱት” በሚል ከናይሮቢ ጋር ያደረጉት ንፅፅር ሲሆን ይህ ንፅፅር በምንም መመዘኛ ትክክልም ተገቢም ሆኖ አላገኘሁትም፡፡ እውነቱን ለመናገር ለአንድ ኬኒያዊ የኬኒያ መንግሰት ስጋቱ አይደለም፡፡ እኛ ግን መንግሰታችን ስጋታችን ነው፡፡ በእኛ ሀገር ሀፈና የሚፈፀመው ሊጠብቅን በሚገባ መንግሰት ነው፡፡ ኢትዮጵያ ደግሞ እስከ ዛሬ ከሸብርተኛ ቡድን ነፃ የሆነችውን ጠቅላይ ሚኒሰትሩ ስምም ፆታም አልገልፅም ብለው ነገር ግን እስከ አያት ስሟ የነገሩን ጋዜጠኛ ርዕዮት ዓለሙ ጉቤቦን በግፍ በማሰራቸው አይደለም፡፡ እኛ ኢትዮጵያዊያን በዚህ ደረጃ ለሸብር የደረሰ ሰነ ልቦና ስለሌለን ነው፡፡ ርዕዮትን የፈቷት በግፊት መሆንን ማመናቸው አንድ ነገር ሆኖ፤ በህገወጥ ሁኔታ በእስር እንደነበረች ግን የምንረሳው አይደለም፡፡ (የፍርድ ቤቶች ውሳኔ ልክ ነው ቢባል እንኳን የእስር ጊዜ ጨርሳ አንፈታም ብለው ከህግ ውጭ አስረው ነበር ያስቀመጧት) በኋላ ጠቅላይ ሚኒሰትሩ በግፊት እንደተፈታች ያመኑትን ማለት ነው፡፡
ከላይ የነበሩትን ስብሰባዎች የለበጣ እንደነበሩ ግምት እንድወስድ ያደረገኝ ስብሰባ የተካሄደው መጋቢት 14/2008 “ከተቃዋሚ ፓርቲ” ተብዬዎች ጋር ያደረጉት ውይይት ነው፡፡ በእኔ እምነት የውይይቱ ዋልታና ማገር የነበረው እነዚህ ፓርቲዎች በሀገራችን ከሚያመጡት የዲሞክራሲ ትሩፋት ይልቅ ለሆዳቸው መሙያ የሚሆነውን ቀለብ አስፋፈር ላይ የነበረ መሆኑ ነው፡፡ ተሳታፊዎቹ በሙሉ በሚባል መልኩ ደስተኛ የሆኑት ኢህአዴግ ከመንግሰት ካዝና ከሚደርሰው ገንዘብ ግማሹን ሊያካፍላቸው ፈቃደኝነቱን በጥቂቱም ቢሆን በማሳየቱ ነው፡፡ ለእነዚህ ተቃዋሚ ተብዬዎች ከዚህ ውጭ መልካም ዜና የለም፡፡ በስብሰባው ያልተገኙትም ቢሆን ያናደዳቸው ገንዘቡ ለፓርቲዎች የጋራ መድረክ አባላት ብቻ መሰጠቱ ነው፡፡ በክፍያው ላይ ቢካተቱ አብረው ጮቢ እንደማይረግጡ መረጃ የለንም፡፡ ከዚህ ውጭ መልካም ጅምር ብለው የኢዴፓው መሪ የገለፁት ምርጫን አስመልክቶ ይደረጋል ያሉት ለውጥ ነው፡፡ ይህ አባባል በእውነቱ በኢትዮጵያ ፖለቲካ ውስጥ ለቆየ ሰው ፓርቲዎች ስልጣን የማይዙት ወይም ተወካይ የማይኖራቸው ህዝቡ ተቃዋሚዎችን በአብልጫ ስለአልመረጠ እና “አብላጫ ድምፅ ያገኘ ያሸንፋል” በሚለው የምርጫ ህግ ምክንያት ያስመስለዋል፡፡ ጠቅላይ ሚኒሰትሩም “ምን አባታችን እናድርግ ህዝቡ ሲመርጠን” ያሉትን እንደመደገፍ የሚቆጠር ነው፡፡ በኢትዮጵያ ትልቁ ችግር እኩል መወዳደሪያ ሜዳ ያለመኖሩን አለመቀበል ነው፡፡ ይህ ደግሞ ከኢህአዴግ ጋር እንደመቆም የሚቆጠር ነው፡፡ ለነገሩ ኢዴፓ ከኢህአዴግ ጋር ለምን ቆመ አይባልም፣ ከዚያ ውጭ የት ሊቆም ይቸላል፡፡ ግቡም ትንሸም ቢሆን የፓርላማ ወንበር ማግኘት ነው፡፡
ለማነኛውም ጠቅላይ ሚኒሰትሩ “ተቃዋሚ ተብዬዎች” ምን እንደሚፈልጉ ገብቶዋቸዋል፡፡ ሆዳቸውን የሚሞሉበት ገንዘብ እንደሚያገኙ ቃል ተገብቶላቸዋል፡፡ “ተቃዋሚ ተብዬዎችም” ምን እንደማይችሉም አውቀዋል፡፡ መሻሻል የሚገባቸውን አዋጆች አጥኑና አምጡ በህጉ መሰረት ይታያል ብለዋቸዋል፡፡ እነዚህ አንደ ገፅ ሰርዓት ያለው መግለጫ መፃፍ ለማይችሉ ተቃዋሚዎች ጥናት አጥኑና አምጡ ከባድ ፈተና ነው፡፡ ሌላው ጠቅላይ ሚኒሰትሩ ያልገባቸው ደግሞ የሰበሰቧቸው “ተቃዋሚዎ ትብዬዎች” በኢትዮጵያ ህዝብ ዘንድ አንድም ቦታ የሌላቸው መሆኑን ነው፡፡
ሰለዚህ በቀጣይም ከህዝቡ ጋር የሚካሄትዱትም ሆነ የተካሄዱት ስብሰባዎች እንደ ከዚህ ቀደሙ የፎረም እና የኢህአዴግ ልዩ ልዩ አደረጃጀቶች ውሰጥ በንቃት የሚሳተፉ ሰዎች ተገኝተው ድራማ የሚካሄድባቸው እንደሆነ ግምት ወስደና ወይም ገብቶናል፡፡ ይህ ደግሞ የነፃነት ቀን መምጫውን ያዘገየው እንደሆን እንጂ ጨርሶ አያስቀረውም የሚል እምነት አለኝ፡፡ መፍትሄው ከዚህ በፊት ፀረ-ህዝብ፣ ጸረ -ምናም እያላችሁ ያገለላችሁትን ቡድኖችና ግለሰቦች በንቃት ማስተፍና ትክክለኛውን ሁኔታ መገንዘብ ነው፡፡ በተጨማሪ ያለምንም ቅድመ ሁኔተ ያለ አግባብ በእስር ላይ የሚገኙት ታጋዮች መፍታት ነው፡፡ ስብሰባም ካስፈለገ …….
ቸር ይግጠመን
ግርማ ሠይፉ ማሩ

Monday, March 14, 2016

የጠቅላይ ሚኒሰትር ሀይለማሪያም ደሳለኝ ሪፖርት መድረሻው “የመልካም አስተዳደር ችግር እንፈታለን፤ ሰልጣን ግን አንለቅም” መሆኑ ነው?



የጠቅላይ ሚኒሰትር ሀይለማሪያም ደሳለኝ ሪፖርትን በወፍ በረር ስንቃኛው የሚከተለው ይዘት እንዳለው መረዳት እንችላለን፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ዓመቱ ከመጠናቀቁ ቀደም ብለው የዕድገት ቅናሽ እንደሚኖር በሰበብ ደግፈው አምነዋል፡፡ ይህም ደግሞ ገዢው ፓርቲ ከአስራ አንድ በመቶ የእድገት ልክፍት በግድም ቢሆን መላቀቁን የሚያሳይ ነው፡፡ ከዚህ ቀደም የፈለገውን ያህል ተግዳሮት ቢፈጠር ያልተተገበሩ ግዙፍ ዕቅዶች ዝርዝር ቢቀርብም “ቢሆንም 11 ከመቶ አድገናል” እንደ ነበር አንዘነጋውም፡፡ ጠቅላይ ሚኒሰትሩ የእድገት ቅናሽ መኖሩን  ቢያምኑም “ትንሽ ቅናሽ ያሳያል” በሚል ማለፋቸው ዝናብ ከዘነበ መልሶ ለማቅራራት ዝግጅት እንዳለ አመላካች ነው፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትሩ ባለፈው ዓመት ማጠቃለያ ሪፖርት ሲያቀርቡ የሰበታ-ጅቡቲ የባቡር መስመር ጥቅምት/2008 ላይ እንደሚጠናቀቅ ተናግረው የነበረ መሆኑን ሳንዘነጋ ዛሬም 97 ከመቶ ተጠናቆዋል ብለውናል፤ ይህ አፈፃፀም ስራ ለመጀመር የሚያስችል እንደሚሆን ቢታመንም ባቡሩ አሁንም ስራ አልጀመረም፡፡ የአዲስ አበባ ቀላል ባቡር በኤሌትሪክ ችግር ፈተና እየገጠመው ጄኔሬተር ሊገዛ ነው እየተባለ ባለበት ሁኔታ አሁን ባለው የኤሌትሪክ አቅርቦት ችግር ከ700 ኪሜ በላይ መስመር እንዴት ሊያደርጉት እንደሆነ የጠየቃቸውም የለ፤ ጠቅላይ ሚኒሰትሩም መረጃ ሊሰጡን አልቻሉም፡፡ ከባቡር መሰረተ ልማት ጋር ተያይዞ የቀረበው አስቂኝ ነገር “በዓለም ኢኮኖሚ መቀዛቀዝ” በሚል ሰበብ ሌሎች በዕቅድ የተያዙ መስመሮች ስራ ሊጀመር እንደማይችል ፍንጭ ስጥተውናል፡፡
በተመሳሳይ የስኳር ነገር ለኢህአዴጎች ገዳቸው አይደለም፡፡ ከታቀደው ተቀንሶ በተወሰኑት ትኩረት ይሰጥ የሚል ሃሳብ መያዙን ጠቅላይ ሚኒሰትሩ ይፋ አድርገዋል፡፡ ደስ የሚለው የጠቅላይ ሚኒሰትሩ አባባል ደግሞ “ጓጉተን የምናወጣው ዕቅድ የማሰፈጸም አቅማችንን ጋር አልተመጣጠነም” የሚለው ነው፡፡ እኛም እያልን የነበረው አሁንም የምንለው አቅም የላችሁም ነው፡፡ የገንዘብ ብቻ አይደለም - ገንዘብ የማሰባሰብ አቅም ማለት ነው፡፡ የዕውቀት ብቻ አይደለም - እውቀት የማሰተባበር አቅም ነው፡፡ ተገባብቶ አሰተባብሮ የመስራት አቅም የላችሁም ነው ያለነው፡፡ ጉጉት ብቻ ናቸሁ!!!
ጠቅላይ ሚኒስትሩ የሀገር ውስጥ ቁጠባን ከማሳደግ አንፃር ዋነኛ ያልዋቸውን የመኖሪያ ቤት እና የጡረታ መዋጮ በሪፖርታቸው ውስጥ አንስተዋል፡፡ በእርግጥም ቆጥቦ ህዝቡ የሚጠቀምባቸው ሳይሆን መንግሰት ከአቅሙ በላይ እየለጠጠ ለሚይዛቸው ፕሮጀክቶች ፋይናንስ ማድረጊያ እንደሆኑ ከጅምሩም ግልፅ ነበር፡፡ ለምሳሌ 40/60 በሚል ቆጥቡ ቤት ታገኛላችሁ ተበሎ በጉጉት የቆጠቡ ሰዎች ፕሮግራሙን 100/0 በማድረግ የዜጎችን ሀበት ይዞ በኋላ ብር አትሞ ለመመለስ የተዘጋጀ ይመስላል፡፡ ሌላው ጡረታን በሚመለከት አብዛኛው በአነሰተኛ ስራ ላይ የተሰማራ ዜጋ ትክክለኛ የግብረ ከፋይ መለያ በሌለበት ሁኔታ ከድሆች ላይ በጡረታ ስም ገንዘብ መንግሰት እየዘረፈ ይገኛል፡፡ ለምሳሌ አንድ በሰተናጋጅነት የሚሰራ ሰራተና ሰድሰት ወር ጡረታ ከፍሎ የሚሰራበትን ድርጅት ቢለቅ ጡረታ ስለመክፈሉ የሚሰጠው ምንም መረጃ የለም፡፡ ቀጣይ የሚገባበት ድርጅት እንደ አዲስ ጡረታ እየቆረጠ ለመንግሰት ገቢ ያደረግል፡፡ ይህ ዜጋ በምንም ሁኔታ የዚህ የጡረታ መርሃ ግብር ተጠቃሚ ሊሆን አይችልም፡፡ ይህ ደግሞ አሁን በግልፅ የሚታይ ዘረፋ ነው፡፡ የዚህ ዓይነት በመቶ ሺ የሚቆጠሩ ዜጎች በግል ዘርፍ ውስጥ በጡረታ መዋጮ ስም እየተዘረፉ መሆኑን ማስታወስ ያስፈልጋል፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትሩ በሪፖርታቸው በቅጡ መረጃ ሳይስጡ ያለፉት የውጭ ኢንቨስትመንት የሚመለከተውን ክፍል ነው፡፡ ከዚህ ቀደም በኦሮሚያ አካባቢ የተነሳውን ንቅናቄ አሰመልክት በኢንቨስትመንት ላይ ሊፈጥር የሚችለውን ተፅዕኖ ያብራራው ስለሆነ እዚህ መድገሙ አስፈላጊ ሆኖ አላገኘሁትም፡፡ ለማነኛውም አሁንም ጠቅላይ ሚኒስትሩ የውጭ ኢንቨሰትመንት የተሻለ ነው በሚል አልፈውታል፡፡ በምንም መለኪያ ግን አሁን የተፈጠረው ሁኔታ የውጭ ኢንቨስትመንት ሊስብ አይችልም፡፡ በተለይ ጠቅላይ ሚኒሰትሩ እንዳመኑት “ይህ ችግር ከትግራይ እስከ ደቡብ ጫፍ” መሆኑን በኦሮሚያ ቀድሞ መታየቱ ሌሎቹ ችግር የለባቸው ማለት እንዳልሆነ ማረጋገጣቸው በኢንቨስትመንት ላይ ጉልዕ ጫና አለው፡፡ ኢንቨሰተሮች ደግሞ ይህን ለማወቅ አይቸገሩም፡፡ ይህ ደግሞ የሚታየው በቀጣይ ዓመታት ሲሆን እስከ አሁን ድረስም በኢትዮጵያ ኢንቨስት ለማድረግ የጀመሩትም በሆን ቢያንስ ረዘም ያለ የዝግጅት ጊዜ መውሰዳቸው የግድ ነው፡፡ ይህ ደግሞ በተለያየ መልኩ በተግባራ ተመልክተነውል፡፡ ሰለዚህ የውጭ ኢንቨስትመንት በቅርቡ ያድጋል ብሎ መገመት አይቻለም፡፡ ሰለዚህ በሪፖርቱ በደፈናው የውጭ ኢንቨስትመንት ካለፈው የተሻለ በሚል የቀረበው ተዓማኒነት የለውም፡፡
በሀገራችን ዙራ መለስ የሚታየው ያለመረጋጋት በኢንቨስትመንት ብቻ ሳይሆን እንደ ሀገር መቀጠላችንን ስጋት ላይ ሊጥል ይችላል የሚል ግምት ያላቸው ሰዎች ቀላል አይደሉም፡፡ እንደዚያም ሆኖ ግን ገዢው ፓርቲ ነገሩን ከስሩ አጥንቶ ሁሉንም ያገባኛል ባይ የሚያሳትፍ መፍትሔ ከመፈለግ ይልቅ አሁን በተለመደ አሮጌ መንገድ መሄድ የመረጠ ይመስላል፡፡ ከወትሮ በተለይ “በሌላው አካል ላይ ጣት መቀስር ይቁም” የሚል ሃሳብ ጠቅላይ ሚኒሰትሩ ያነሱ ቢሆንም አሁንም ቢሆን ግን ለመፍትሔው እሩቅ እንደሆኑ የሚያሳያው “በተሃድሶ” ጊዜ ችግር የፈቱበትን መንገድ አሁንም ሊደግሙት ያሰቡ ይመስላል፡፡ ኢህአዴግ የዚህችን ሀገር ለመፍታት ከእኔ ሌላ ማንም የለም የሚል ይመስላል፡፡ አሁን ያለውን በመልካም አስተዳደር ተሸፍኖ የሚቀርብልንን መንግሰታዊ ሌብነት እና ውስልትና በቸልታ እንድናልፈው የሚጠይቁን በሚመስል ሁኔታ መቶ በመቶ ተመርጠናል ባሉበት ዓመት መቶ በመቶ ሲከሸፉ ሌላ አማራጭ ማሰብ አልተቻላቸውም፡፡ መልዕክቱ ግልፅ ነው፡፡ “የመልካም አስተዳደር ችግር እንፈታለን፣ ስልጣን መልቀቅ ግን አይታሰብም” የሚል ነው፡፡
የመልካም አስተዳደር ችግሩን ደግሞ የሚፈቱት ለወጣቱ የስራ እድል የሚፈጥሩ ከዚህ ቀደም ሲዘረዝሩልን የነበሩትን “በጉጉት” ላይ የተመሰረቱ ዕቅዶችን በማቅረብ ነው፡፡ ወጣቱ ስራ ካገኘ ሌላ ጥያቄ ያለው አልመስላቸውም፡፡ የወጣቱ ጥያቄ የስራ መፍታት ብቻ አይመስለኝም፡፡ በሀገሩ እኩል እንደ ዜጋ መቆጠር እና በነፃነት የመኖር ጭምር ነው፡፡ በስራ ፈጠራ ቢሆን አሁን የሚታየውን ስራ አጥነት እንፈታለን እየተባለ በጎን ደግሞ በስራ ላይ ያሉትን የትራንስፖርት አገልግሎት ሰጪዎችን በመንግሰት ጣልቃ ገብነት ከስራ ለማስወጣት እቅድ እንዳለም ከሪፖርቱ ለመረዳት ከባድ አይደለም፡፡ በቅርቡ ወደ ስራ እንዲገቡ የሚታሰቡት “የቢሾፍቱ” አውቶብሶች ዋና ዓላማቸው ባለፈው የስራ ማቆም አድማ በማድረግ አንገታቸውን ቀና ያደረጉትን ዜጎች አንገት ለማስደፋት ነው፡፡ ለማነኛውም ቀኑ ደርሱ ውጤቱን አብረን የምናየው ይሆናል፡፡ ይህ አካሄድ የቁርጡ ቀን መቃረቡን የሚያሳይ ይመስለኛል፡፡
ጠቅላይ ሚኒሰትራችን በሰጡት ማብራሪያ አንድ አዲስ ነገርም አስረግጠው ነግረውናል፡፡ በሀገራችን “የማንነት ጥያቄ የተመለሰ ጉዳይ ነው” ብለውናል፡፡ ማንነት “ኢቮልቭ” የሚያደርግ የሚፈጠርና የሚጠፋ መሆኑ አብቅቶለታል፡፡ በኢትዮጵያ ውስጥ ከአሁን በኋላ አዲስ ማንነት አይፈጠርም፡፡ ይህን ደግሞ የፌዴሬሽን ምክር ቤት እና ክልሎች ተነጋግረው ቋጠሮ ማበጀት አለባቸው የሚል መልዕክት አስተላልፈዋል፡፡ ይህን ንግግር የቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትር አድርገውት ቢሆን እንደ ህግ ልንወስደው እንችል ነበር፡፡ አሁን ግን እንደ የግል አስተያየት አድርገን ከመውሰድ ውጭ ህግ ነው ለማለት ውጤቱን መጠበቅ ይኖርብናል፡፡ እነ ዳንኤል ሺበሽ “ቁጫ ቁጫ ነው ጋሞ አይደለም” በሚል በኢህአዴግ መስመር ጥያቄ በማቅረባቸው ዛሬ በእስር ላይ ይገኛሉ፡፡ ኢህአዴግ የማንነት ድንበር ምን ጋ ሲደርስ እንደሚቆም ዝርዝር መመሪያ ሊሰጥ ይገባል፡፡ በእግረ መንገድ የጉራጌ ብሔር/ብሔረሰብ የባህል ልብስ ደንብ ወጣ ሲባል ሰምቻለሁ …. አውነት ይሆን?
ባጠቃላይ የጠቅላይ ሚኒትሩ ሪፖርት በእኔ ግምት ሪፖርት ሳይሆን አሁንም ሌላ እቅድ ነው አበክረን፣ጠንክረነት እንሰራለን የሚል፡፡አሁንም ልምድ የሚቀመርበት … የሚማሩበት ሁኔታ ነው ያለው፡፡የኢትዮጵያ ህዝብ ዋነኛው ችግር ደግሞ ሰማርት ስልክ መሆኑ ተደርሶበት ሰማርት ስልክ በተመጣጣኝ ዋጋ እንድናገኝ ጥረት ይደረጋል የሚል እቅድ ቀርቦልናል፡፡ በስብሰባው ላይ ህውሃት ከሞላ ጎደል የተሟላ ሲሆን የሌሎች ድርጅት ከፍተኛ ሃላፊዎች ያለመገኘት ምን ማለት ይሆን?
ቸር ይግጠመን
ግርማ ሠይፉ ማሩ