Monday, June 27, 2016

ለዲሞክራሲ ስርዓት ምን ዓይነት ፓርቲ ያስፈልገናል?



በሀገራችን የዲሞክራሲያዊ ስርዓት ግንባታ የፖለቲካ ፓርቲዎች፣ የሲቪል ማህበራት እንዲሁም የሚዲያ ተሳትፎ አጅግ ወሳኝ እንደሆነ ሁሉም ይረዳዋል ማለት ባይቻልም በተለይ የፖለቲካ ፓርቲ አባል አመራር የሆኑ ሰዎች ይጠፋቸዋል ብሎ የሚገምት ላይኖር ይችላል፡፡ እውነቱ ግን ከዚህ የተለየ ነው፡፡ በአሁኑ ጊዜ የፖለቲካ ፓርቲ ውስጥ ሰዎች የሚሳተፉት በዋነኝነት በሀገራቸን የዲሞክራሲ ስርዓት ግንባታ ያላቸውን መዋጮ በማስላት ሳይሆን ገዢውን ፓርቲ በማስወገድ ላይ ብቻ ያጣነጠነ ይመስላል፡፡ ይህንንም ማድረግ የሚፈልጉት ደግሞ በትርፍ ጊዚያቸው ከስራ መልስ ወይም በጡረታ ጊዚያቸው ነው፡፡ ይህን ሲያደርጉ ደግሞ የብዙ ወጣቶች ጊዜና ጉልበት መስመር ባልያዘ አቅጣጫ እንደሚመሩ አይረዱም፡፡ ለነገሩ የወጣቶችን ጊዜ በማባከን እና የወጣቶችን ፍሬያማ ጊዜ በከንቱ በማባከን ገዢውን ፓርቲ የሚወዳደር የለም፡፡ በሰራ እናገኛለን ተሰፋ እና እራሳቸውን ከደህንነት ስጋት ለመጠበቅ ገዢውን ፓርቲ በምሽግነት ስለሚጠቀሙበት፡፡ ይህም ቢሆን ገዢው ፓርቲ ይህን ስለሚያደርግ ተቃዋሚዎች የወጣቶችን ጊዜ ያለአግባብ ማባከን አለብን የሚል ክርክር ሊገጥሙ አይገባም፡፡
በእኔ እምነት የፖለቲካ ፓርቲ አባል ሲኮን በተለይም አመራር ሲኮን በቀጣይ የመንግሰትን ስልጣን ለመያዝ መዘጋጀትን ይጠይቃል፡፡ በአሁኑ ወቅት በዚህ ልክ እራሳቸውን ያዘጋጁ የገዢው ፓርቲም ሆነ የተቃዋሚ ፓርቲ አባላት ማግኘት አስቸጋሪ ነው፡፡ ገዢው ፓርቲ ከሰበሰባቸው ሰባት ሚሊዮን አባላት ምርጥ ብሎ አውጥቶ አመራሩን መቀየር ባለመቻሉ ያሉትን የጡረታ ጊዜ እያራዘሙ 25 ዓመት ሞልቶታል፡፡ አሁንም ቢሆን በገዢው ፓርቲም ሰፈር ከፊት መጥተው ተሰፋ የሚደረግባቸው አይታዩም፡፡
በተቃዋሚ ጎራ ይህን ወሳኝ የፖለቲካ አመራር እና የመንግሰት ስልጣን ቁርኝትን ባለመረዳት ፓርቲ የመሰረቱ እና ለመመስረት የሚራወጡ ሰዎች ግባቸው እንደ ከዚህ ቀደሙ የጡረታ ወይም ደግሞ ከሰራ መልስ ጊዜ ማሳለፊያ ከማድረግ የዘለለ ፋይዳ ያላቸው አይመስለኝም፡፡ ከዚህ በፊት ይህን ለማሳካት አንድነት ፓርቲ ያዘጋጀውን ስትራቴክ ሰነድ መሰረት አድርጎ የመድረክ አመራሮችን “ሻዶ ካቢኔ” እናቋቁም ብሎ ጥያቄ ሲያቀርብ በግልፅ ለፖለቲካ ስልጣን የምናደርገውን ትግል በድብቅ ማድረግ የለብንም የሚለውን የአንድነትን ግልፅ አቋም በድብቅ በውስጣቸው ባለ ሰውር የስልጣን ጥም (ማን የካቢነዊ መሪ ይሆናል?) ሳይቀበሉት እና ሳይሳካ ቀርቷል፡፡ በዚህም መነሻ አንድነት ያቀረበውን የስትራቲጂክ ፕላን ሰነድ ሳይቀበሉት ቀሩ፣ቀጥሎም አንድነትን ገፍትረው አስወጡት፡፡ ለነጉሩ አንድነትም በዚህ ትብትብ ውስጥ ድንክ ሆኖ አይቆይም ነበር፡፡
አሁን ደግሞ በድጋሚ ማሳካት የሚፈልገው ዓላማ ምን እንደሆነ የማይታውቅ ከአንድነት ፓርቲ ፍርስራሽ “ነፃነት” የሚባል ፓርቲ መመስረቱን ሰምተናል፡፡ ለምስረታው ከፍተኛውን ሚና ሲጫወት የነበረው አቶ ብሩ ቢርመጂ በድንገት ከዚህ ዓለም በሞት ቢለይም የፓርቲው መሪ ሆኖ የተመረጠው ዶክተር ንጋት በእርግጥም የጃንሜዳ ልጅ ቢሆንም በሰሜን ሸዋነቱ በቀጣይ መድረክ ውስጥ ለሚታየው የአማራ ፓርቲ ክፍተት ማሟየ እንደሚሆን ግልፅ ነው፡፡
አንድነትን ገፍትሮ ያስወጣው የፕሮፌሰር በየነ አና የዶክተር መረራ መድረክ አሁን ለነፃነት ፓርቲ ምስረታ ሁሉን አቀፍ ድጋፍ በማድረግ ላይ ይገኛል፡፡ ይህ የሚያሳየን ኢትዮጵያ የፓርቲዎች እጥረት ስለአለባት የዜጎችን የመደራጀት ዲሞክራሲያዊ መብት ለመደገፍ ካላቸው ቀና አመለካካት ሳይሆን መድረክ የኢህአዴግ “ፎርጅድ ኮፒነቱን” ለማሳካት የጎደለውን የአማራ ፓርቲ ለመሙላት ብቻ ነው፡፡ መድረክ በትግራይ ዓረና ለህውሃት፣ በኦሮሚያ ኦፌኮ ለኦህዴ፣ በደቡብ የፕሮፌሰር በየነ ፓርቲዎች እና የሲዳማው ድርጅት ለደህዲን የተዘጋጁ ሲሆን ለብአዴን ግን የአቻ ፓርቲ ችግር ነበረበት፡፡ ከዚህ በፊት አንድነትን በውስጠ ታዋቂነትም ሲከፋም በይፋ የአማራ ፓርቲ አድርገው ይፈርጁ ሰለነበር ከአንድነት መውጣት በኋላ ይህ ክፍተት “ፎርጅድ ኮፒ” ለመሆን እንኳን አላሰቻላቸውም፡፡ አሁን ግን የነፃነት ፓርቲ መምጣት ከመኢህአድም ሆነ ከሰማያዊ ጋር ያላቸውን ስር የሰደደ ጥላቻ አስወግደው ከመሻረክ ይህን የአንድነት ፍራሽ በማሰገባት ድሮ አንድነት ሊውጠን ነው ከሚለው ስጋታቸው ወጥተው እኩያቸው የሆነ ፓርቲ እንዲያገኙ ይረዳቸዋል፡፡ ነፃነት ቢሮ የሌለው ማህተምና ፋይል በሰዎች መኖሪያ ቤት የሚገኝ፣ ይህ ነው የሚባል ድርጅታዊ ጥንካሬ የሌለው ፓርቲ ሰለሆነ ለመድረክ አባል ድርጅቶች የእኩዮች ጥምረት ይሆናል፡፡ “የፎርጅድ ኮፒ” ፕሮጀክት ክፍተትም ይሞላል፡፡ እንደሚታወቀው የፓርቲዎች ውህደት እኩል ሳይሆኑ በእኩልነት መንፈስ ይባላል፡፡
ለማነኛውም የኢትዮጵያ ህዝብ እውነተኛ የዲሞክራሲ ስርዓት እንዲኖር ይፈልጋል፡፡ ይህ ደግሞ የሚሆነው አውነትኛ የድርጅት አቅም ያላቸው አማራጭ የሚሆኑ፤ ህዝቡ ቢመርጣቸው የመንግሰት ሃላፊነት ተረክበው ሊያስተዳድሩት የሚችሉ፤ የፖለቲካ ፓርቲዎች ይፈልጋል፡፡ በግሌ አንድ ፓርቲ መንግሰት ብሆን የካቢኔ አባሎቼ እነ እገሌ ናቸው ብሎ ብቃት ያላቸው 30 ሰዎች የሚያሳየኝ ካለ አባል ለመሆን ዝግጁ ነኝ፡፡ አንድነት ውስጥ ይህን ማደረግ ስለሚቻል ነበር ለፖለቲካ ስልጣን የምንሰራው፣ ይህ በገዢው ፓርቲ አልተወደደም፡፡ በገዢው ፓርቲ ብቻ ሳይሆን ተቃዋሚ ነን በሚሉት ጭምር (ሰማያዊና መድረክን ጨምሮ) በተለይ ሰማያዊ በአንድነት ፍራሽ የሚጠነክር መስሎት ስለነበር፡፡ ነገሩ ግን የተገላቢጦሸ ነው የሆነው፡፡
አሁንም በኢትዮጵያ የዲሞክራሲ ስርዓት እንዲኖር ካስፈለገ፤ የሚፈጠረው ፓርቲ እንደ ኢህአዴግ አመራር የማይወጣው 7 ሚሊዮን አባል በመስብሰብ የመልካም አስተዳደር ችግር የሚፈጥሩ አባላትን በማብዛት ሳይሆን ምርጦች የሚሰበሰቡበት፣ ለጥቅም ሳይሆን “ለአቅመ መስጠት” የደረሱ፤በአውቀታቸው እና ከራሳቸውና ከቤተሰባቸው አልፈው ለዜጎች ኢኮኖሚያዊ፣ ማህበራዊ ፍትህ የሚጨነቁ ብቻ ሳይሆን አማራጭ መፍትፈሔ የሚያቀርቡ፣ በየደረጃው ለፖለቲካ አመራር የሚሰባሰቡበት መሆን ይኖርበታል፡፡ ሰለዚህ መስጠት የማይችሉ ለአቅመ መስጠት እስኪበቁ በደጋፊነት መቆየት ይኖርባቸዋል፡፡ መረዳት ያለባቸው የተቃዋሚ ፓርቲ አባልም ሳይሆኑ በዲሞክራሲ ስርዓት ተጠቃሚ ይሆናሉ፡፡ በዚህ የሚጠቀሙት የኢህአዴግ አባለት ጭምር ስለሚሆኑ፡፡
በተመሳሳይ ጠንካራ ሚዲያ እና ሲቪል ተቋማት መኖር አለባቸው፡፡ አርዳታ ለማሰጠት እና ለራሳቸው የስራ እድል ለመፍጠር የተደራጁ ሲቪል ማኅበራት፣ በዕትመት ለመቆየት ለዘብተኛ የሆኑ ሚዲያዎች ለዲሞክራሲ ስርዓት ግንባታ ፋይዳ የላቸውም፡፡ ይፍረሱ!!!!!

Monday, June 6, 2016

መድረክ ንጉሣዊ ነው እንዴ?



ለመድረክ ቅርብ የሆነ አንድ ወዳጄ የመድረክን የእሁድ ግንቦት 28/2008 ጉባዔን አስመልክቶ የነገረኝ ነገር መድረክ ንጉሣዊ ነው እንዴ? የሚል ጥያቄ እንዳነሳ አድርጎኛል፡፡ መቼም በመድረክ ስም ፓርላማ ስለነበርኩ ለመድረክ ቅርብ የምመሰላቸው ካሉ ተሳስተዋል፡፡ የመድረክ ስብሰባ እንደሚታወቀው ውሣኔ የሚሰጠው የጉባዔ አባላት ተሰብሰበው በውይየት አቋም ይዘው በነፃነት በሚሰጥ ድምፅ አይደለም፡፡ አባል ድርጅቶች አድማ መተው የሚመጡበት ነው፡፡ ሌላው በመድረክ ውስጥ ኃላፊነት የሚያዘው በአባል ድርጅቶች በዙር ነው፡፡ ከአባል ድርጅቶቹ ደግሞ የሚልኩትን መሪ ቀይረው የማያውቁት ደግሞ ፕሮፌስር በየነ እና ዶክተር መረራ ናቸው፡፡ አሁን ባለኝ መረጃ መሰረት መድረክን የመምራት ተራው የሀረና ነበር፡፡ ይህ ማለት ግን የስብሳቢነት ቦታው ለሀረና እንዲሲጠው ሀረና ለቦታ የሚያቀርበው ዕጩ ወሳኝነት አለው፡፡ ሰለዚህም ሀረና ያቀረበው ዕጩ ለመድረክ ሊቀመንበርነት አይደለም፣ ለምክትልም አይሆንም በሚል ቦታው በቃኝ ለማያውቁት ለፕሮፌሰር በየነ አንዲሰጥ ተደርጎ ዶክተር መረራም ምክትል ሆነው ቀጥለዋል፡፡
አቶ አስፋ ጫቦ በቅርቡ ባሳተመው መፅኃፍ ውስጥ የሸዋ ንግስና ከተመለሰ የእኛም መመለስ አለበት የሚል ስላቅ አቅርቦ ነበር፡፡ ፕሮፌሰር በየነም ቤተሰቦቻቸው በአካባቢው እንዲህ ዓይነት የንግሰና ጥያቄ ከመጠ ከሚጠይቁት ወገን ናቸው ስለሚባል፤ ይህ እስኪመጣ ድረስ መድረክን የንግስና መለማመጃ ያደረጉት መስለኝ፡፡ ይህ ካልሆነ ግን ብዙ ሙከራ አድርገው ያልተሳካላቸውን የአመራር ቦታ ቢቻል ፖለቲካውን ጭምር መተው ለምን ተቸገሩ?
ከወዳጄ ጋር ሰለምርጫው ስናወራ የፕሮፌሰሩ በተደጋጋሚ ከሚቀርብባቸው ከተቃዋሚ መሪነት እራሳቸውን ያግልሉ ጥያቄ ችላ ማለት ብቻ ሳይሆን ሃያም ሆነ ሰላሣ ሰዎች ድምፅ ሰጥተዋቸው በሃላፊነት የሚቆይቱ ባለፈው የሃላፊነት ዘመናቸው ምን ሰርተው ነው? የሚል ጥያቄ ለምን አያነሱም ነው፡፡ በፕሮፌሰር በየነ አመራር ወቅት መድረክ ምን ውጤት አስገኝቶ ያን ውጤት ለማስቀጠል ሲባል ነው የተሰጠው ሊባል የሚችል ውጤት አልታየም፡፡ በኦሮሚያ ለነበረው ህዝባው ንቅናቄ እንኳን በቂ ድጋፍ መስጠት ያልቻለ ስብሰብ እንደሆነ በስብሰባው ወቅት ጥያቄ ተነስቶበታል፡፡
የተነሳው ጥያቄም “በኦሮሚያ ለነበረው እንቅስቃሴ ኦፌኩ ብቻውን ለምን ተንቀሳቀሰ?” በሚል ነበር፡፡ መልሱ ግን የበለጠ አስደማሚ ነበር፡፡  “ኦሮሞዎች የተለየ ጉዳይ ስለነበረን ነው” የሚል እንደምታ ያለው መልስ ተሰጥቷል፡፡ አስገራሚው ነገር በአንድ ወቅት ሀብታሙ አያሌው  “ሰለ ኦሮሞ ችግር ለመናገር ኦሮሞ መሆን አያስፈልግም ሰው መሆን ይበቃል” ብሎ በሰጠው አስተያየት መድረክ አጀንዳ አድርጎት ኦሮሞ ያልሆነ የኦሮሞ ችግር አይገባውም የሚል መልስ ተሰጥቶ አንድነት እና ሀረና ታዲያ እዚህ ምን እንሰራለን? በሚል ስብሰባው ተቀውጦ እንደነበር የቅርብ ጊዜ ትዝታ ነው፡፡ አሁንም መድረኮች አብረን ነን ይበሉ እንጁ የትግሬው ችግር የሀረና፣ የኦሮሞ ችግር የኦፌኮ አድርገው በመያዝ ዳር ይዘው ተቀምጠዋል፡፡ በነገራችን ላይ መድረኮች አንድነትን ካስወጡ በኋላ የአማራ ተወካይ የሚያደርጉት ወይም የሚመስልላቸው ሳያገኙ እስከ አሁን አሉ፡፡ በቅርቡ የተመሰረተው የአንድነት ሽራፊ “ነፃነት” የሚባለው ፓርቲ ይህን ቀዳዳ ለመሙላት ተሰፋ ሳያደርጉ አይቀሩም፡፡ ወይም “ሰመያዊ” ፓርቲ ዓይኑ በጨው ታጥቦ ሊቀላቀላቸው ይችላል፡፡ የመድረክ አመራሮች ይህ ያለባቸውን የአማራ ወኪል ክፍተት በመሙላት “ፎርጂድ” የኢህአዴግ ኮፒ አደረጃጀት እንዲሳካ መጣራቸው የማይቀር ነው፡፡ ለህወሃት-ሀረና፣ ለኦህዴድ-ኦፌኮ፣ ለደህዴን-የበየነ ፓርቲዎች፣ ለብአዴን- ? ? ? ? - ፡፡ ክፍቱን ቦታ ለመሙላት እንግዲ ነፃነትና ሰማያዊ እድሉ አላቸው፡፡
የሀረና ልጆች በመድረኮች ፊት ዓይን የማይሞሉ ሆነው የተገኙት በመተካካት ፖሊሲ የቀድሞውን መሪ አቶ ገብሩ አስራትን ለዕጩነት ባለማቅረባቸው ነው፡፡ አስገራሚው ነገር በመድረክ አንፃር የተሻለ የውጭ ደጋፊ ያለው ሀረና ለክፉም ለደጉ በሚል የፋይናንስ ኮሚቴ ሃላፊነት እንደተሰጠው ተሰምቷል፡፡ በእርግጥ ዶክተር መረራም ከውጭ ድጋፍ ያለው ቢሆንም ድጋፉን በግል ከፈለገ ለኦፌኮ ካልሆነ ለመድረክ የማድረግ ፍላጎት የለውም፡፡ ለማነኛውም ፕሮፌሰሩ ሲመሩት ከነበሯቸው ድርጅቶች የተወሰኑትን “ምርጫ ቦርድ” ተብዬው ቢሰርዘውም በንግሰና በሚመስል መልኩ የመድረክን ሃላፊነት አለቅ ብለው ቀጥለው፡፡ ወይም ደግሞ አባላቱ በግድ ጭነውባቸዋል፡፡ በዚህ የሃላፊነት ዘመናቸው መቼም በቀጣይ ሊያድርጉት ያሰቡትን መርዓ ግብር በሆነ መልኩ ይፋ ያድርጋሉ ብለን እንጠብቃለን፡፡ በእኔ ግምት የመድረክ ሰዎች ይህን ኃለፊነት ይዘው መቆየት የፈለጉት በአንድ አጋጣሚ ኢህአዴግ ሸብረክ ቢል አለን!!! ለማለት ካልሆነ በስተቀር በተጠና ሰትራቴጂ ትግሉን መርተው መንግሰት ለመሆን አይደለም፡፡ እራሱን ለመንግሰትነት ያላዘጋጀ ፓርቲ/ሰብሰብ፣ ህዝቡን ለማድራጀት የማይተጋ ስብስብ ፋይዳው አይታየኝም፡፡
ሀገራዊ ሰብስብ ነኝ የሚል መድረክ ጠቅላላ ጉባዔ ሲያካሂድ በማህበራዊ ድረ ገጽ እንኳን የውይይት አጀንዳ አለመሆኑ አሳዝኖች ይህችን አካፈልኳቹ፤ እናንተስ ምን ታዘባችሁ፡፡ ከመድረክ ስብሰባ ተካፋዮች ዝርዝር እንጠብቃለን ….. ዘላለማዊ ስልጣን ….


Monday, May 30, 2016

የግንቦት 20 ፍሬዎች ሲመዘኑ ….



ዛሬ ግንቦት 22 /2008 ዓ.ም ነው፡፡ ይህን ፅሁፍ ግንቦት 20 በሀዋሳ ከተማ ሆኜ ፃፍኩትና ለመለጠፍ ስል ፅሁፌ ሁሉ የደርግ ደጋፊ የሆንኩ አሰመሰለኝ፡፡ እውነት ከሆነ ደርግ የሰራውን በጎ ነገር መደገፍ አጢያት ባይሆንም እራሴን ከስህተት ለመጠበቅ የፅሁፉን አጭር መደምደሚያ እና የግምገማ ማዕቀፌን ለህዝብ ግምገማ እና ተጨማሪ ግብዓት በአጭሩ በፌስ ቡክ ገፄ ላብለጥፈው በቂ ስድቦች እንጂ ሃሳቦች ማግኘት አልተቻለም፡፡ ሰለዚህ በእራሴ ሚዛን ይህን የግምገማ ውጤት እንደወረደ ማሰቀመጥ እንዳለብኝ ወሰንኩኝ፡፡ ለዚህ ግምገማ የተጠቀምኩበት ማዕቀፍ በብዙ ቦታዎች የተለመደ ነው፡፡ በእርግጥ ይህ ማዕቀፍ ስድስት መለኪያዎች ቢኖሩቱም አንዱ ከአንደኛው ጋር የሚገናኝ እንደሆነ ለመረዳት አያስቸግርም፡፡ በእንግሊሰኛ (PESTEL – Political, Economy, Social, Technology, Environment and legal framework ) የሚባለው ነው፡፡ በእነዚህ መመዘኛዎች የግንቦት 20 ፍሬዎችን እንመዝናለን፡፡ ለማጠቃለል እንዲመቸን ከመጨረሻው እጀምራለሁ፡፡
የህግ የበላይነትና ግንቦት 20
ደርግ በህግ የሚገዛ መንግሰት ነበር የሚል ሰው ሊኖር አይችልም፡፡ የደርግ ስርዓት ሲወድቅ ያየ ወይም እንዲወድቅ ጠብታም ያዋጣ በህግ የሚገዛ ስርዓት መጠበቁ ከእባብ እንቁላል እርግብ መጠበቅ ሊሆንበት አይችልም፡፡ ስህተትም አይደለም፡፡ የደርግ ስርዓት በተለይ የፖለቲካ ተቀናቃኞች ናቸው ያላቸውን ከህግ ስርዓት ውጭ በኮሚቴ እና በአውጫጭኝ እንደገደለ ምስክር መጥራት ወይም ማስረጃ ማቅረብ አይጠበቅብኝም፡፡ ግንቦት 20 1983 ዓ.ም የደርግ ስርዓት ሲቀየር ያለ ህግ ግድያ ይቀራል የሚል ተሰፋ በአብዛኞች ዘንድ ነበር፡፡ ነገር ግን እንደ አንባገነኑ ደርግ ገድሎ ፉከራው ቢቀርም ያለ ህግ ግድያ፣ እስራት እና ግፍ  ለኢትዮጵያዊያን የእለት ከእለት ጉዳይ መሆኑ አልቀረም፡፡ አንድ እውነትም አለ ደርግ ፍርድ ቤቶችን ለፖለቲካ ቲያትር መስሪያ አልተጠቀመባቸው፡፡ ኢህአዴግ መራሹ መንግስት የፍትህ ስርዓቱን ባጠቃላይ ለፖለቲካ ግብ ማስፈፀሚያ በማዋል ደርግን አስከንድቶታል፡፡ ሁሉም እንደሚረዳው በጥናትም እንደተረጋገጠው ዜጎች ፖለቲካው ሊበላቸው ሲመጣ “በህግ አምላክ” ብለው የሚጠለሉበት የፍትህ ስርዓት በግንቦት ሃያ ፍሬነት ያለማገኘታችን ነው፡፡ በሃያ አንደኛው ክፍለ ዘመን ዜጎች በፍርድ ቤት ውሳኔ እምነት ያጡባት ሀገር ኢትዮጵያ ብቻ ትሆናለች ብዬ እገምታለሁ፡፡ ግንቦት ሃያ ይህን ሊያረጋግጥልን አልቻለም፡፡ ዕውቀት ያላቸው የህግ ባለሞያዎች ከዳኝነት ይልቅ ጥብቅና ብለው፣ ለፖለቲካ ላለማጎብደድ ወሰነው በችሎታ ከማይመጥኗቸው ዳኞች ፊት ይቆማሉ፡፡ በእውቀት የላቁ ዳኞችን ከዳኝነት ወንበር መግፋት ፍሬ ከሆነ የግንቦት ሃያ ፍሬ አድርገን ልንወሰደው እንችላለን፡፡
ፍርድ ቤቶቻችን የሰጡት ውሳኔ እንኳን ለማሰፈፀም አቅም እንደሌላቸው በተደጋጋሚ አይተናል፡፡ በሃያ አንደኛው ክፍለ ዘመን የህሊና እስረኞች ካሉባቸው ሀገሮች አንዷ ኢትዮጵያ ነች፡፡ ደርግ ያሰራቸውን ሰዎች መጠየቅ አይከለክልም ነበር፡፡ ይህን ፅሁፍ ከማጠናቀቄ በፊት በዝዋይ የሚገኘውን ጓደኛችንን ተመስገን ደሳለኝን መጠየቅ አይቻልም ተብለን ተመልሰናል፡፡ በህገመንግሰት የተቀመጠን መብት ማንም በመመሪያና ደንብ ሲሸረሸር አቤት የሚባልበት ቦታም ሰርዓተም የሌለበት ሀገር ኢትዮጵያ ነች፡፡ ይህን ማሻሻል የማይችል መሰዋዕትነትን ለማክበር ግንቦት 20 አደባባይ ልንወጣ የምንችልበት ምክንያት አልታይህ ብሎኛል፡፡ የሚገርመው ይህንን የግንቦት 20 ፍሬ ተብሎ እነዚሁ ታሳሪዎች እንዲያከብሩት ይገደዳሉ፡፡
ግዴታን በተመለከተ እንግዲህ ከየመስሪያ ቤቱ እየሾለከ የወጣው ግንቦታ ሃያ ካላከበርክ/ሽ ወዮልህ ማስፈራሪያ መስከረም 2 ለአብዮት በዓል ውጡ ግዴታ በምን እንደሚሻል እና ኢህአዴግ ከደርግ በምን እንደሚሻል የሚያስረዳን ቢገኝ ለመረዳት መዘጋጀት አለብን፡፡ በጭፍኑ ከደርግ እንሻላለን የሚያዋጣ አይመሰለኝም፡፡ ግንቦት 20 አላከብርም ያለ ዜጋ ምን እንደሚደርስበት እና ጉዳት እንዳይደርስበት አፋጣኝ የፍትህ ስርዓት ስለመኖሩ እርግጠኛ መሆን አይቻልም፡፡
ሲጠቃለል ግንቦት 20 “በህግ አምላክ” የሚባለውን ኢትዮጵያዊ የህግ አክባሪነት ባህል ያጣንበት ነው፡፡ ፍትህን ለደህንነታችን መሸሸጊያ ሳይሆን ለፖለቲካ መሳሪያነት የበለጠ እንድናውቃት የተደረገበት መሆኑ ጎልቶ የታየተበት ነው፡፡ ከህገ መንግሰት ድንጋጌ ይልቅ የግለሰቦች ቁጣና ግልምጫ የሚፈራበትና የሚከበርበት ሀገር ላይ መኖራቸን ነው፡፡ በተለይ ሟቹ ጠቅላይ ሚኒስትር ቃላቸው ህግ ሊሆን የተቃረበበት ወቅት ነበር፡፡
ቴክኖሎጂ እና ግንቦት 20
ይህን ሚዛን ኢህአዴግ እና የፕሮፓጋንዳ አውታሮቹ የሚጠቀሙበት ቁጥር በማነፃፀር ነው፡፡ ለምሳሌ እኔ የዛሬ 25 ዓመት 24 ዓመቴ ነበር ዛሬ 49 ስሆን ይህን በምንም መለኪያ የግንቦት 20 ፍሬ አድርጌ ለመቁጠር አልችልም፡፡ በተመሳሳይ በሚኒሊክ ጊዜ ይሁን በደርግ ጊዜ የነበረ የስልክ መስመር ቁጥር ብዛት፣ አሁን ካለው ጋር በማነፃፀር የግንቦት 20 ፍሬን ማግኘት አይቻልም፡፡ በኢትዮጵያ አሁን አሉ የምንላቸው ቴክኖሎጂዎች በተለይ የማህበራዊ ድረ ገፅ መጠቀሚያ የሆኑት መሰረተ ልማቶቸ፣ የሞባይል ስልክ፣ ኮምፒውተር፣ወዘተ ደርግ በስልጣን ቢቀጥል የኢትዮጵያ ምድር ሊረግጡ የሚችሉበት መንገድ አይኖርም ብሎ ማሰብ ይቻላል ወይ? ብሎ መጠየቅ የተሻለ ትክክለኛ ሚዛን ይሆናል ብዬ አምናለሁ፡፡ ደርግ በስልጣን ቢቀጥል ኢትዮጵያ ውስጥ ቴክኖሎጂ እንዳይገባ ያደርግ ነበር? ብዬ ለማሰብ ግን አቃተኝ፡፡
አንድ ነገር ማሰብ ቻልኩ ህወሃት እና ሻቢያ እንዲሁም ኦነግ እና ሌሎች ለመገንጠል የሚሰሩ ድርጅቶች ውጊያ ካላቆሙ፣ አሁን ይገኝ የነበረው እርዳት በገፍ የማይግኝ ቢሆን መሰረተ ልማቶቹ ሊኖሩ አይችሉም ነበር፡፡ ሰለዚህ ደርግ ይህን ሊሰራው የማይችል የነበረው አሁን በመንግሰት ላይ ያሉት ኃይሎች እንዳይስራ የማደናቀፍ ስራ ከሰሩ ብቻ ነው ሊሆን የሚችለው፡፡ ከቀዝቃዛው የዓለም ጦርነት ማክተም በኋላ የውክልና ጦርነቶች ስለማይኖሩ በሌሎቸ ሀገራትም ያሉት በመክሸፋቸው ጦርነቶቹ የሚቀጥሉበት እድል ጠባብ ነበር፡፡ እርዳታና ብድር ደግሞ እንደ ኤርትራ እንቢ ያላለ ይልቁንም በዓለም ከሚገኙ ከምስራቅም ከምዕራብም ለመውሰድ ዝግጁ የሆነ ብድር ማግኙት አይቀርም ነበር፡፡ ሰለዚህ በቴክኖሎጂ በኩል ኢትዮጵያ ከዓለም ተለይታ እንደ ኩባ እና ሰሜን ኮሪያ ትሆን ነበር ብሎ ማሰብ አይቻለም፡፡ ይልቁንም በቅይጥ ኢኮኖሚ ጅማሮ የታየው የግል ባለሀብት መስፋፋት በመቀጠል ወደ ተሻለ መሰመር ሊኬድ ይችል ነበር፡፡ ማለትም ተጨማሪ ቴክኖሎጂ የሚያቀርቡ የግል ሴክተሮች ሊኖሩ የሚችሉበት እድል ይኖር ነበር፡፡ ይህን ለማድረግ የደርግ ቅይጥ ኢኮኖሚ ከኢህአዴግ ቅጥ አንባሩን ካጣው “አብዮታዊ ዲሞክራሲ መር ኢኮኖሚ” እንደሚሻል በግሌ አምናለሁ፡፡ ሰለዚህ ግንቦት 20 በቴክኖሮለጂ መስክ ያመጣው ለውጥ ኢህአዴግ ስልጣን ባይዝ እናጣው ነበረ ብሎ ማሰብ አይቻልም፡፡
ሲጠቃለል በዓለም ላይ ሆኖ ከቴክኖሎጅ እራሱን ማራቅ አይቻልም፡፡ ሰለዚህ እኛም አሁን ካለንበት በተሻለ ልንሆን የምንችልባቸውን ወርቃማ 10 ዓመታት (1983-1993) ከተሜ ጠል በሆነ የኢህአዴግ አስተሳሰብ አምልጦናል፡፡ ከዚያም ቀጥሎ ያሉት ዓመታት ከውድድር ይልቅ የግል ዘረፋን በህዝብ ስም ለማድረግ በሚያስችል አሰራር የህዝብ ሀብት ማባከኛ ሆኗል፡፡ በቴሌ መሰረተ ልማት ብንወሰድ ዘላቂ ለመቶ ዓመትና ከዚያ በላይ ማሰብ ባለመቻል፣ በተደጋጋሚ የመሰረተ ልማት ለውጦችና ውድመቶች የደረሱባት ሀገር ነች፡፡ ስለዚህ ግንቦት 20 የሰርዓት ለውጥ ባይመጣ የምናጣው ነገር ሳይሆን ያጣነው ብዙ ነገር እንዳለ ይሰማኛል፡፡ ኢትዮጵያ የዜጎቿን ሙሉ ሀይል መጠቀም ብትችል ከዚህ የተሻለ መሆን እንደሚቻል ይስማኛል፡፡
የአካባቢ ጥበቃና ግንቦት 20
ሀገራችን ኢትዮጵያ ለረዥም ጊዜ የደን ሸፋን እየተራቆተ ሄዶ ሁለትና ሶሰት በመቶ ቀርቶዋል ስንባል ልጆች ነበርን፡፡ አሁን ደግሞ ድንገት ተነስተን ከአስራ ሁለት እስከ አስራ አምሰት በመቶ መድረሱ እየተነገረን ነው፡፡ እኔ በእድሜዬ አዲስ አበባ ከተማ ጫካ እንደነበር አውቃለሁ፡፡ ሰፈራችን መሳለሚያ አካባቢ ድረስ ጅብ ይመጣ እንደነበርም አውቃለሁ፡፡ ኮልፌ ከሚኖሩ ዘመዶቼ ከሄድኩ ከመሸ ማደር ግዴታ ነበር፡፡ አሁን ባለው ሁኔታ አዲስ አበባ ውስጥ በደብሮች እና በዮኒቨርሲቲ እንዲሁም በቤተ መንግሰት እንመለከት የነበረው ደን ወደ ሲሚንቶ ክምርነት እየተቀየረ ነው፡፡ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲን ዋና ጊብ ልብ በሉልኝ፡፡ በክልልም ያለው ተመሳሳይ ሁኔታ ነው፡፡ በደርግ በተፈጥሮ ሀብት ልማት በሚኒሰትር ደረጃ አደራጅቶ በእርዳታ የሚገኝ ገንዘብን በነፃ ከመስጠት የአካባቢ ልማት በተለይ የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ እንዲሰሩ በማድረግ እሰከ አሁን የሚታዩ ውጤቶች ተመዝግበው ነበር፡፡ አሁን ኦሮሚያ ክልል ፕሬዝዳንት ፅ/ቤት የሚባለው ቦሌ ፍላሚንጎ አካባቢ ያለው ህንፃ የዚህ ተቋም ውጤት ነበር፡፡ ከግንቦት 20 በኋላ ይህ መስሪያ ቤት ፈርሶ አሁን ከ20 ዓመት በኋላ እንደ አዲስ እንዲቋቋም ተደርጎዋል፡፡ ይህ የሚያሳየን ደርግ የተፈጥሮ ሀብትን በመጠበቅ የተሻለ ሊሆን እንደሚችል መገመት ይቻላል፡፡ ከስራውና ከተገኘው ፍሬ በመነሳት ማለት ነው፡፡ በተወሰኑ አካባቢዎች የተሻለ ሰራ በኢህአዴግ እንደተሰራ አውቃለሁ፣ እነዚህ ስራዎች ግን ደርግ ሃያ አምስት ዓመት ቢቆይ አይስራውም ብዬ ለማመን ግን እቸገራለሁ፡፡ አሁንም ቢሆን በተለይ ከአባይ ግድባ ጋር ተያይዞ መሰራት ያለበት የአባይ ተፋሰስ የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ልዩ ትኩረት ተሰጥቶት መሰራት እንዳለበት ባለሞያዎች ቢናገሩም አሁንም ያለው ስራ ከወረቀት እና የውሸት ሪፖርት ከማምረት የሚዘል እንዳልሆነ በአባይ ተፋሰስ ጎግል በማድረግ ማየት ይቻላል፡፡ የሌለ ጫካ አለ ማለት በሃያ አንደኛው ክፍለ ዘመን አይቻለም፡፡
ሲጠቃለል ግንቦት 20 መሬትን ዜጎች የኢኮኖሚ መሳሪያ አድርገው እንዲጠቀሙበት ማድረግ ባለመቻሉ ዜጎች ለረጅም ጊዜ የሚቆዩ የደን ልማቶችን ሊያስራ አልቻለም፡፡ በመንግሰት የደን ጥበቃ ስራ በአግባቡ እየተሰራ አይደለም፡፡ ይልቁንም ያሉትን ባለቤት እንዳይኖራቸው በማድረግ ከህዝብ ቁጥረ መጨመር ጋር ተያይዞ ደን መመንጠር የበለጠ እየሆነ መጥቷል፡፡ ለማነኛውም ማነኛውም ኢትዮጵያዊ የሆነ መንግሰት ቢመጣ በደን ልማት ከዚህ የተሻለ ፖሊሲና ስትራቴጂ በመንደፍ የህዝብ ተጠቃሚነት ሊያረጋግጥ ይችላል ብዬ አምናለሁ፡፡ ሰለዚህ በግንቦት ሃያ ካገኘነው ይልቅ ያጣናው ያማዝናል፡፡
ማህበራዊ ልማትና ግንቦት 20
ማህበራዊ ልማትና በጤና በትምህርት መስክ ተወስኖ ይታይ ቢባል አሁን ያሉት ሸፋኖች ከደርግ ጋር ሲነፃፀር ከመቶ እጥፍ እንደሚበልጡ ይታወቃል፡፡  ይህ ግን የግንቦት 20 ፍሬ ሊሆን የሚችለው የጤና ተቋማትን እና ትምህርት ቤቶች የሚያፈርስ ኃይል በሌለበት ነው፡፡ ደርግ ትምህርት ቤት መገንባት አቅም ቢያንሰው ሁሉም ትምህርት እንዲያገኝ በሶሰት ፈረቃ እንዲማር አድርጎዋል፡፡ ይህ ደርግ ዜጎች እንዳይማሩ የሚፈልግ መንግስት ነው ብዬ ለመውሰድ ይቸግረኛል፡፡ ያለምንም የእድሜ ገደብ ወንድ ሴት ሳይባል ወደ ትምህርት ቤት እንዲሄድ በአካባቢውም የመሰረተ ትምህርት ጣቢያዎች እንዲኖሩ የተደረገበት ነው፡፡ የእኔ እናት ከመሰረተ ትምህርት ተነስታ መደበኛ ትምህርት መግባት የቻለችው ሰርዓቱ በፈጠረው በጎ ተፅዕኖ ነው፡፡ ትምህርቶች ደግሞ ይሰጡ የነበሩት ሁሉም በቋንቋው እንደነበረ ማንም ያውቃል፡፡ ከዚህ አንፃር ተገኘ የሚባል ለውጥ ካለ በኢትዮጵያ “ቁቤ” በግዕዝ ፊደል ፋንታ በኦሮሚያ እና አንዳንድ አካባቢዎች ተግባራዊ ማድረግ መቻሉ ነው፡፡ “በሬሳ” በግዕዝ ፊደልም ቢሆንም በአዲስ አበባ ከተማ ይሸጥ እንደነበር መካድ አይቻልም፡፡ በግሌ ኢትዮጵያ የብሔረሰቦች እስር ቤት ነበረች ብሎ ተረክ ሊገባኝ አይችልም፡፡ የአሁኑ ጠቅላይ ሚኒስትር ሀይለማሪያም ደሳለኝም እኔም በደርግ የተማርን እንደነበረ መመሰከር ግድ ይላል፡፡ ዶክተር አሸበርወ/ጊዮርጊሰ ይህን ኢትዮጵያ የብሔሮች እስር ቤት ነበረች ተረክ ይወደዋል፡፡ ሩሲያ ለትምህርት የላከው ግን የደርግ ሰርዓት ነበር፡፡ ሌሎችም እንደዚሁ፡፡
የጤና ሸፋን በሀገራችን በአሁኑ ወቅት በከፍተኛ ደረጃ እንደጨመረ ይታወቃል፡፡ ልብ ማለት ያለብን ግን ከግንቦት 20 1983 በፊት በቅጡ ተደራጅተው የነበሩ “የወባ መቆጣጣጠር”፣ የኤች፣አይ ቪ፣ የመሳሰሉ ገዳይ በሸታዎችን በትጋት ይሰሩ የነበሩ ተቋማትን በማፍረስ በወረርሽኝ መልክ የተስፋፉበት ወቅት እንደ ነበርም የምንዘነጋው አይደለም፡፡ ያለፉት ሰርዓቶች ኢትዮጵያዊ ዜጎችን አደንቁረውና በበሸታ አማቀው ሊገዙ ፖሊሲ ነበራቸው ብዬ ለማመን አልችልም፡፡
ሲጠቃለል በማህበራዊ ልማት ግንቦት ሃያ የስርዓት ለውጥ ባይደረግ የሚቀርብን ነገር ምን አልባት “ቁቤ” ብቻ ነው፡፡ እርሱም ቢሆን በህዝበ ውሳኔ ሊደረግበት የማይችል ነገር አልነበረም፡፡
ኢኮኖሚ ልማትና ግንቦት 20
ኢህአዴግ ብዙ እንዲዘመርለት የሚፈልገው እና ሌሎች ነገሮቻችን በተለይ ነፃነታችንን አሳልፈን እንድንሰጠው የሚፈልገው ተመዘገቡ የሚላቸውን የኢኮኖሚ እድገቶች ብቻ እዪ በማለት ነው፡፡ አሁንም ደርግ ኢትዮጵያ በኢኮኖሚ እንዳታድግ፣ ዜጎች በድህነት እንዲማቅቁ የሚፈልግ ሰርዓት ነበር ወይ? ብዬ እራሴን ሰጠይቅ በፍፁም እንዳልሆነ እረዳለሁ፡፡ በተለይ ደግሞ የቅይጥ ኢኮኖሚ በደርግ የመጀመሪያ ዘመን የሚያስቀስፍ እንደነበረ ሁሉ በመውደቂያው ጊዜ ደግሞ “ገንዘብ ገንዘብ ያለው ያውጣ፣ ይስራ ያሰራበት” መመሪያው ሆኖ ነበር፡፡ ደርግ የጥቂት ሰዎች መጠቀሚያ ሀገር ለመመስረት ፍላጎት ያለው መንግሰት አልነበረም፡፡ በቅርቡ ከጓደኞቼ ጋር ሆነን በቀድሞ ስርዓት ብር 500 ይከፈለው የነበረ አንድ ጀማሪ ባለዲግሪ (በዶላር 240) ማለት እንደሆነ እና አሁን ግን 240 ዶላር የሚከፈለው 10 እና 20 ዓመት የስራ ልምድ ያለው ተቀጣሪ እንደሆነ ስናስብ ነበር፡፡ ይህ በምንም ህግ እድገት ሊሆን አይችልም፡፡ የመግዛት አቅሙ የተዳከመ ብር የሚመሰረት ኢኮኖሚ ጠንካራ ኢኮኖሚ ሊሆን አይችልም፡፡ ወደፊትም በውጭ ንግድ የተሻል መሆን ካልቻልን በስተቀር የብር ምንዛሬ እየወረደ የዜጎች ሸክም እየከበደ የሚመጣበት ጊዜ እሩቅ አይደለም፡፡ ይህ ማለት ግን በዶላር ሲለካም ቢሆን የተንደላቀቀ ኑሮ የሚኖሩ ባለ ሚሊዮን ዶላር ጥቂቶች ማፍራት የቻለች ሀገር ሆናለች፡፡ ችግሩ እነዚህ ጥቂት ባለሚሊዮን ዶላር ዜጎች በግልፅ ለህዝብ የሚታወቁ እና የገቢ ምንጫቸውም የሚታወቅ ባለ ሚሊዮን ዶላር በሆኑበት ልክ ግብር የከፈሉ መሆኑን የሚረጋገጥበት ስርዓት አልተዘረጋም፡፡
ኢህዴግ በሚወደው የቁጥር ጫወታ ብንጫወት ከአምሳ ሚሊዮን ህዝብ የዛረ 30 ዓመት 2 ሚሊዮን ቢራብ 4 ከመቶ መሆኑ ነው፡፡ ከዘጠና ሚሊዮን ህዝብ አሁን 10 ሚሊዮን ሲራብ ከ10 በመቶ በላይ ነው፡፡ የተሻለ የኢኮኖሚ ሰርዓት አለኝ የሚለው ኢህአዴግ ከፖሮፓጋንዳ አልፎ ዜጎችን ባስተማማኝ ሊቀልብ የሚችል ስርዓት አልዘረጋልንም፡፡ ያለ እርዳታ ዜጎች ከሞት ሊድኑ የሚያስችል ስርዓት መገንባት አልተቻለም፡፡
ሲጠቃለል ኢትዮጵያ ውስጥ በኢኮኖሚ በተለይ ሁኔታ ሊጠቀሙ የሚችሉ ቡድኖችን መፍጠር ተችሏል፡፡ አብዛኛው ህዝብ የሀገር ሀብት በፍትሃዊነት ሊጠቀም የሚችልበት አልሆነም፡፡ የኢኮኖሚ ተጠቃሚነት በዜጎች መካከል በብሔር በዘር መጠቃቀም ብቻ ሳይሆን፣ ከኢትዮጵያዊ ይልቅ ለውጭ ሰዎች የበለጠ ምቹ እንዲሆን የተደረገ ሰርዓት ነው፡፡ ኤኮኖሚው “በዘረኝነት” የተለከፈ ከመሆኑ የተነሳ የብዙ ሌሎች ፖለቲካ ችግሮች ነፀብራቅ ነው፡፡ ዜጎች ሰርተው ለማደግ እንዲችሉ ምቹ ሁኔታ ከመፍጠር ይልቅ ተከታትሎ ለማጥቃት የተደራጀ መሰረቱ “ምቀኝነት” የሚመሰል የኢኮኖሚ ሰርዓት ነው፡፡ የመንግሰት የገቢ መሰረት ታክስ መሰብሰብ መሆኑ ቀርቶ ከዜጎች ጋር ፉክክር የያዘ ያስመስልበታል፡፡

ፖለቲካና ግንቦት 20
ከላይ የዘረዘርኳቸውን መለኪያዎች ለኢህአዴግ በሚያደላ መልኩ ሊሆን ያልቻሉበት ዋናው ምክንያት ፖለቲካው፣ በመበላሸቱ ነው፡፡ በዓለም ላይ ለውጥ ሊያመጣ የሚችል ተሞክሮ ያለፈ የመድበለ ፓርቲ ስርዓት በመገንባት በህገ መንግሰት ላይ የተቀመጡትን እጅግ አስደማሚ መብቶች ለማክበር ያለመቻል ውጤቶች ናቸው፡፡ ህገመንግሰትን በሚመለከት ከዚህ በፊት የነበሩ መንግሰታትም ቢሆኑ በወቅቱ የነበረውን ስርዓት የፊውዳል ይሁን፣ የኮሚኒሰት የሚመጥን ህገመንግሰት ነበራቸው፡፡ ችግራቸው መተርጎሙ ላይ ነው፡፡ አሁን ያለውም ቢሆን የፖለቲካ ሰነድ መሆኑ እንደተጠበቀ ሆኖ በፍፁም ከመድበለ ፓርቲ ስርዓት ጋር የሚቃረን የአንድን ፓርቲ ብቻ ፍላጎት የሚያሟላ ተደርጎ መቀረፁ ትክክል አይደለም፡፡ ለማነኛውም ህገ መንግሰቱ ይህ ነው፣ ይህ አይደለም ከማለት ይልቅ የተፃፈውን ቢያከብሩልን ብዙ ደስታ ሊፈጥሩ የሚችሉ እና ከላይ የዘረዘርናቸውን የሌሎች መለኪያዎች የታየውን ውድቀት ማከም የሚችል ይሆን ነበር፡፡ በፖለቲካ ሰነድ ውስጥ መሬትን አስመልክቶ የተቀመጠው ድንጋጌ በአካባቢ ጥበቃም ሆነ በኤኮኖሚ መስክ ማሰመዝገብ የሚገባንን ውጤት እንዳናስመዘግብ ያደረገ ማነቆ ነው፡፡
በሀገራችን የሚደረጉ የይስሙላ ምርጫዎች ፖለቲካ በዜጎች ፍላጎት ሳይሆን በጥቂት አውቅላችኋለሁ ባዩች ብቻ እንዲመራ የሚያደርግ ብቻ ሳይሆን የገንዘብ ማባከኛም ጭምር ነው፡፡ በኢትዮጵያ ምርጫ አለ ከማለት ምርጫ የለም የተሻለ የሚገልፃት ሀገር ሆናለች፡፡ ሀገር የሚመሩ ሰዎች ተምረው በአገኙትና በያዙት እውቀት ሳይሆን ሀገር እየመራን ነው እያሉ እየተሳሳቱ የሚማሩባት ቤተ ሙከራ አድርገዋታል፡፡ ከስህተታችን ተመክሮ ወሰደናል እያሉ የሚመፃደቁበት ቦታ የፖለቲካ ስልጣን ሆኖኋል፡፡ ለማነኛውም …… የኢህአዴግ ፖለቲካ ክስረት የክስረታቸው፣ ብሎም የጋራ ክስረታችን መንስዔው እንደሆነ መረዳት ሊቅ መሆን አያስፈልገውም፡፡
ሲጠቃለል ሀገራችን ኢትዮጵያ በፖለቲካው መስረመር ዜጎች የአመለካከት ልዮነታችን ለስጋት ሳይሆን ለዜጎች ምርጫ ለማቅረብ እንደሚያስችል ምርጥ እድል አድርጎ ከመጠቀም ይልቅ፣ ዜጎች በሚይዙት የፖለቲካ አቋም በእስር፣ በግርፋት፣ ቶርቸርን ጨምሮ የሚደረግባት ሀገር ሆናለች፡፡ ግንቦት ሃያ የደርግን ቶርች ሊያስቀርልን ሳይሆን በተሻሻለ ሁኔታ ሊተገብርልን የመጣ እስኪመስለን ድረስ ዜጎች በመሃል አዲስ አባባ ውስጥ ይገረፋሉ ይስቃያሉ፡፡ ሰቃያቸውን ለፍርድ ቤት ሲናገሩ የሚያደምጥ ያለመኖሩ ሳይሆን በዚህ ዓይነት ምርመራ የተገኘን ማስረጃ ተቀብለው ዘግናኝ ውሳኔ በመስጠት የፍትህ ስርዓቱን የፖለቲካ አጋርነት ያረጋግጣለሁ፡፡ ይህ አልበቃ ብሏቸው በቁጥጥር ሰር ያዋሏቸውን እስረኞች በወዳጅ ዘመድ እንዳይጠየቁ፣ በማድረግ ማህበረሰቡን እንዳለ ለማሸማቀቅ ይጠቀሙበታል፡፡ ግንቦት 20 ያስገኘልን አዲስ ነገር ይልቅ ያጣናው ማመዘኑ የሚያስቆጭ ብቻ ሳይሆን በተለያየ ጎራ ተሰልፈው በሀገራችን ማህበራዊ ፍትህ እንዲሰፍን፣ የፖለቲካ እኩልነት እንዲኖር ዜጎች በሀገራችው ያለምንም ገደብ ተንቀሳቅሰው እንዲሰሩ፣ ወዘተ ለማደረግ መስዋዕትነት የከፈሉትን ኢትዮጵያዊያን ደምና ህይውት ከንቱ እንደቀረ የሚያስቆጥር ነው፡፡ በእኔ እምነት በሀገራችን ለብዙ ዘመናት የተከፈሉት መስዋዕትነቶች ጥቂቶችን ሚሊዮኒየር፣ ጥቂቶችን ደግሞ በስልጣን ማማ ላይ ለመስቀል አልነበረም፡፡ ግንቦት 20 1983 ተከትሎ የመጣውም ለውጥ ሀዲዱን ስቶ ያረጋገጠው ነገር ቢኖር ጥቂት ሚሊኒየሮች እና ጥቂት እምብርት አልባ የስልጣን ጥመኞችን ነው፡፡
ቸር ይግጠመን!!!

Friday, May 20, 2016

የአሰፋ ጫቦ “የትዝታ ፈለግ” መፅኃፍ እኔ እንደገባኝ…



የአቶ አሰፋ ጫቦን “የትዝታ ፈለግ” መፅኃፍ እያነበብኩ ተመችቶኛል ብዬ ፌስ ቡክ ላይ ሃሳቤን ባሰፍር፡፡ ለራሴም ለአቶ አሰፋም የሰድብ ምርት ማምረት ቻልኩኝ፡፡ እስኪ እግዜሩ ያሳያችሁ እኔ አንብቤ ተመቸኝ ማለት ሌላው ተመችቶታል ማለቴ ተደርጎ እንዴት ይወሰዳል፡፡ እጅግ ብዙ ሰው የአቶ አሰፋ ጫቦ መፅኃፍ ብሎም ሃሳቡ ላይመቸው የሚችል እንደሚኖር እገምታለሁ፡፡ በምሳሌ ላስረዳ ጋምቤላ ሄጄ ወባ ያዘኝ ብል፤ ጋምቤላ የሄደ ሁሉ ወባ ይይዘዋል ማለት፡፡ እንዴት ነው ታዲያ የእኔ በወባ መያዝ ውሸት የሚሆነው፡፡ እባካችሁ እየተሰተዋለ ለማለት እና የአቶ አሰፋ ጫቦ መፅኃፍ ሊያስደሰተኛ የቻለበትን ሲከፋም ከአቶ አሰፋ ጫቦ ጋር ያለኝን የሃሳብ አንድነት ለመግለፅ ልሞክር፡፡ መብቴን ልጠቀም፡፡
አቶ አሰፋ ጫቦ እስር ቤት ሆነው በግላቸው ግፍ የሚባለው (ቶርቸር) እንዳልደረሰባቸው በይፋ መስክረዋል፡፡ መቼም አሰር ዓመት ከስድሰት ወር በላይ መታሰር ግፍ አይደለም ብለው አይደለም፡፡ ከሌሎቹ ጋር ሲነፃፃር ለማለት ብቻ ነው፡፡ የሌሎችን ስቃይ ግን በደምብ አድርገው እንድንረዳ አድርገው በመፅሃፍ ውስጥ አሳይተውናል፡፡ በዚያ በግፍ ማጎሪያም ውስጥ ቢሆን በጎ ሰዎች ለማየት መቻሉን የአቶ አሰፋ መፅሃፍ ያሳየናል፡፡ እነዚህ በጎ ሰዎች ለበጎነት አጥር እንደሌለው የሚየሰተምሩን ናቸው፡፡
አቶ አሰፋ ጫቦ ከብዙዎች የሚለዩት ደርግን ለመመዘን የተጠቀሙበት ሚዛን አብዛኛው ደርግን ለመመዘን ከሚፈልግበት የተጭበረበረ የወያኔ ሚዛን በተለየ ነው፡፡ ይህ በደርግ ላይ የተጭበረበረ ሚዛን ይዞ የሚመዝነው ወያኔ ብቻ አይደለም- ኢህአፓም፣ መኢሶንም፣ ወዘተ ናቸው፡፡ በሚያስገርም ሁኔታ እነዚን የተጭበረበሩ ሚዛኖች ካልተጠቀመ ሁሉም ሰው ደርግ/ኢሰፓ ወይም የድሮ ስርዓት ናፋቂ የሚል ወይም አንድ ክቡድ የሆነ ተቀፅላ ይሰጠዋል፡፡ እግዜር ያሳያችሁ በዚህ ምክንያት ሁሌም በራሳችን ሚዛን ከመጠቀም ይልቅ ለጊዜውም ቢሆን አሸናፊ በሰጠን ወይም አሸናፊው በፈቀደልን ሚዛን እንድንጠቀም እንገደዳለን፡፡ አቶ አሰፋ ግን እንዲህ ይላል “እስር ቤት ሆኜም ሆነ፣ ከዚያም በፊት፣ ከዚያም በኋላም - ምን አቅብጦኝ ከደርግ ጋር ገጠምኩ- ብዬ አላውቅም፡፡ አምኜ እንጂ ወይ ምናምን ፍለጋ ወይ ሰው  ገፋፍቶኝ አሳስቶኝ አልገባሁም፡፡ በመሸ በጠባ ቁጥር በጥሼ የምቀጥለው ማተብ የለኝም፡፡” በማተቤ ልዳኝ ብለዋል፡፡ ይህ በእውነት ሊደነቅ የሚገባው የመርዕ ሰው መሆንን የሚጠይቅ ነው፡፡
አቶ አሰፋ ጫቦ ለሰዎች ምስጋና የሚሰጠው አብዛኛው ህዝብ ይወዳቸዋል በሃሳብ ከእኔም ጋር ይሰማማል በሚል አይደለም፡፡ “ህዝቡ” የሚባለው አይናችሁን ላፈር ያላቸውን በአደባባይ ያመሰግናለሁ፡፡ ከመንግሰቱ ኃይለማሪያም ጀምሮ፣ የደህንነት ሚኒሰትሩ ተሰፋዬ ወልደስላሴን ጨምሮ የማዕከላዊውን አርጋው እሸቱን በመፅኃፉ ያደንቃል፡፡ እነዚህ ሰዎች በኩራት የሰሩትን በጎ ነገር ይተርካል፡፡ በቦታው ደግሞ መዝገባቸውን ገልጦ ያሳየናል፡፡ ይህን በራስ መመራት ልንማርበት ይገባል፡፡ ከዚህ አንፃር ዶር በፍቃዱ ደግፌ በቀድሞ የኢሠፓ አባሎች የኢሠመጉ አባል ይሁነ አይሁኑ በሚለው ክርክር ወቅት የወሰደውን አቋም መሰረት አድርጎ (ሰበብ/ምክንያት) በግሌ ዛሬም/ወደፊት ለህውሃት እና ሀጋሮቹ የምመኘውን ደፋር ሃሳብ በመፅኃፉ ውስጥ አስቀምጦልኛል፡፡
የህወሃት/ኢህአዴግ ወይም ሌሎች ሀጋር ድርጅቶች በማነኛውም መንገድ ተሸንፈው ስልጣን ቢለቁ እነርሱ በሰፈሩት ቁና እንስፈራቸው የሚል እምነት ጨርሶ የለኝም፡፡ የቀደሞ የኢትዮጵያን ሠራዊት    “የደርግ ሠራዊት” እንዳሉት ሁሉ የአሁኑንም ሠራዊት “የህወሃት ሰራዊት” ብሎ ለመበተን በዝግጅት ላይ ያለ ካላ የአሰፋ ጫቦን ምክር ማዳመጥ ያለበት ይመስለኛል፡፡ የአሰፋ ምክር እንዲህ ይላል “የኢሠፓን ጉዳይ፣ እንዲያውም ማንኛውንም ሀገረ አቀፍ ጉዳይ ስንመለከት በተቻለ ከትልቁ ምስል አኳያ ማየት የሚሻል ይመስለኛል፡፡ ትልቁ ምስል ኢትዮጵያ ነች፡፡ ትልቁ ምስል ይህች ሀገር የጋራ ቤታችን ኢትዮጵያ ነች፡፡” …..  “ፖለቲካ ባዶ ህዋው ላይ የሚሰራ ትርዒት አይደለም፡፡ ዛሬ ያለንበት ሁኔታ የዛሬ መለኪያ፣ የነገውን መፍቻ ቁልፍ ይጠይቃል፡፡ የትላንትናውን ሙሉ ለሙሉ አውልቀን አንጥልም፡፡ ትምህርት እናገኝበታለን፡፡” የሚል ነው፡፡ በአሁኑ ሁኔታ ስንመዝነው አንዳንድ ሰው ከወያኔ/ኢህአዴግ ምንም ትምህርት አይገኝም የሚል ሊኖር ይችላል፡፡ እንደዚህ የሚል ሰው በእኔ እምነት ኢህአዴግ ምንም ጥፋት አልሰራም ከማለት የሚተናነስ አይመስለኝም፡፡ ኢህአዴግ የሰራቸውን ሰህተቶች በሙሉ ነቅሰን አውጥተን መማር ይኖርብናል፡፡ ለመማር ደግሞ ጠርጎ አውጥቶ ጥሎ ሳይሆን አካቶ መሆን ይኖርበታል፡፡
አቶ አሰፋ ጫቦ የታናሽ ወንድሜን ባለቤት ሀገር ጨንቻን በፅሁፉ በደንብ አስጎብኝቶኛል፡፡ አሁን በራሴ ቁስቆሳም ቢሆን ለመጎብኘት ሰበብ ይሆነኛል፡፡ አርባ ምንጭን እና ሌሎች የገጠር ቀበሌዎችን በስራ አጋጣሚ አይቻለሁ፡፡ አጋጣሚ ሆኖ ጨንቻን አላየሁም እና ጥሩ ቅስቀሳ ይመስለኛል፡፡ ከዚህ ሌላ በትዝታ ፈለግ መፅኃፍ ውስት በተለይ ለእኔ ምርጥ ሆነው ያገኘሁት “ነፍጠኛ ማን ነው?” በሚል የኢትዮጵያችን የነፍጠኛፖለቲካ ትርጉም የገለፀበት አንዱ ሲሆን ሌላኛው ደግሞ “ጎበዝ ….! ማውረድ እንዳያቅተን” በሚል ሰለ ኢህአፓው መሪ ዘርዑ ክህሽን የተፃፈው ነው፡፡ በሌሎቹ ላይ ሌሎች አሳብ እንዲሰጡበት ትቼ በነዚህ ላይ ብቻ አተኩራለሁ፡፡
ነፍጠኛ ለህወሃት፣ ነፍጠኛ ለመዐህድ፣ ነፍጠኛ ለኦነግ ወዘተ የራሳቸው የሆነ ትርጉም የሰጡት ሲሆን፡፡ በተለይ ነፍጠኛ ማለትና አማራ ማለት እኩል አቻ ትርጉም ያለው አስመስለው የሚያቀርቡትን የፖለቲካ ሸፍጥ አሰፋ ጫቦ በደንብ አፍታቶ አስቀምጦታል፡፡ ኢትዮጵያ የምትባል ሀገራችን ሳያውቁ በስህተት አውቀው በድፍረት ለፖለቲካ ሸፍጣቸው ሲሉ የሚያደናግሩን እንደሆነ አስረድቶናል፡፡ አሰፋ በማጠቃለያው “ነፍጠኛ ማለት አማራ ብቻ ነው ማለት እምነት እንጂ እውነት አይደለም” ብሎ በመረጃ አስደግፉ አሳይቶናል፡፡ ዋነኛዎቹ የነፍጠኛ ፖለቲካ አቀንቃኞች የሆኑት የትግራይ ልሂቃን ትግራይ ነፍጠኛ የሌለባት ክልል ስትሆን የኦሮሞ ልሂቃን ደግሞ የኦሮሞ ልጆች ደግሞ በብዙ ቦታ ራሳቸው ነፍጠኛ እንደሆኑ እንድናውቅ አይፈልጉም፡፡ የአሰፋ ጫቦ መፅኃፍ በተለይ ሚንሊክ ወደ ደቡብ ኢትዮጵያ ያደረጉት መሰፋፋት ነፍጠኛው የሸዋ ኦሮሞ መሆኑን የሚያሰረዳ ነው፡፡ ቀደም ሲልም ከ400 ዓመት በፊት ኦሮሞ ወደ ሰሜን ነፍጥ ይዞ መሄዱ ሳይዘነጋ ማለት ነው፡፡
መማር ከፈለገን አሰፋ ጫቦ ብዙ ያስተምረናል፡፡ ካወቅነውም ያስታውሰናል፡፡ ትግሬ፣ ኦሮሞ፣ አደሬ፣ ጉራጌ፣ ሶማሊ፣ አፋር፣ ወዘተ መሆን በምንም መልኩ ከኢትዮጵያዊነት ጋር ጠብ እንደሌለበት፡፡ አሰፋ ጫቦ “እኔ ጋሞ ነኝ፡፡ እኔ ኢትዮጵያዊ ነኝ፡፡ ሁለቱ ተጣልተው ለማስታረቅ ተቀምጨ አላውቅም፡፡ እረዳቸዋለሁ፡፡ የእኔ ቢጤ በሺህ የሚቆጠሩ አውቃለሁ፡፡ የማላውቃቸው በሚሊዮን የሚቆጠሩ አሉ፡፡” ይላል፡፡ እኔ አስፋ ጫቦ ከማያውቃቸው ከሚሊዮኖቹ አንዱ ነኝ፡፡ አቶ አሰፋ ይህን “ነፍጠኛ ማን ነው?” ለመፃፍ ሰባት ዓመት ከሰባት ጊዜ በላይ ወረቀት አውጥቶ እንደ ተወው ፅፎልናል፡፡ እኛም ሰባት ጊዜ ሰባ ሰባት ለመናገር ስንሞክር በአድማ ታፍነን ነበር፡፡ የአሰፋን መፅኃፍ ከወደድኩበት ምክንያት አንዱ የገባችሁ ይመስለኛል፡፡ እኔ ላደርገው ያልቻልኩትን የውስጤን ከተበው፡፡ በቃ ወደድኩት!!!
ሌላው ኢህአፓን በሚመለከት ብዙ ኢህአፓ የነበሩ ወደጆቼ ድርጅቱ አመሰራረቱና አመራሩ በደንብ መፈተሸ አለበት፣ ይህ ማለት በቆራጥነት ለነብሳቸው ሳይሳሱ ለትግሉ ቆመው የነበሩትን መክዳት ሳይሆን፣ ትክክለኛው መድረሻው ግብ ሳይታወቅ ምን አልባትም “የኤርትራን ነፃ ሀገርነት” ለማረጋገጥ በሚደረገው ጥረት የውስጥ እሳት እንዲሆኑ ወንድሞቻችን እህቶታችን ተማግደው አለመሆኑን ይጣራ ስንል የሚሰማን አናገኝም፡፡ ሁሌም ሰለ ኢህአፓ ጅግንነት፣ ተራራ አንቀጥቃጭ ትውልድነት ብቻ ይነገር የሚል ሰሜት አለው፡፡ ንፅፅሩም ከደርግ ጋር ብቻ ሆኖ ሰው በላው ደርግ በላቸው በሚለው አንድ መስመር ፕሮፓጋንዳ እንድንዋኝ እየተደረግ ነው፡፡ በእውነት እንመልከት ከተባለ የዘርዑ ክህሸን መሰመር ከሻቢያ “የኤርትራ ነፃ ሀገር” መሆንን ከመፈፀም ያለፈ ግብ ነበረው ብለን እንድናምን የሚያደርግ ነገር ጠፍቶብናል፡፡ ልብ ወለድ በሚል ቢሆንም “የሱፍ አበባ” በሚል የተፃፈው መፅኃፍም ከዚህ የተለየ እንዲገባኝ አያደርግም፡፡ ለማነኛውም የብሔር ብሔረሰብ ጥንቅሩን ያልጠበቀውን የኢሕአፓ አመራር ከጅምሩ ስናይ በእርግጥ እነዚህ ሰዎች የተደራጁት ሻቢያና ወያኔ እንዲጠናከሩ መሰመር ለማበጀት ነው? የሚል ጥያቄ ያጭራል፡፡ አሁንም በጅምላ ፍረጃውን ትተን በግልፅ እንወያይበት የታሪክ ሰዎች ከፕሮፓጋንዳው ወጥተው፣ በዚሁ መስመር በተሰራው ሚዛን ሳይሆነ፤ በምሁራዊ እይታ እንዲገመግሙት መጠየቅ ይኖርብናል፡፡ የታጋይ ደም ይጮሃል በሁሉም መስመር ያለ ነው፡፡ በነጭም በቀይም፣ በሌሎቹም የእርስ በእርስ ጦርነቶች፡፡
ይህ የግል አስተያየቴ እንደሆነ ታውቁ በመጨረሻም መፅኃፉ ውስጥ የተፃፉት የተለያዩ ፅሁፎች የተፃፉበት ቀን በጣም የተለያየ በመሆኑ ምክንያት የተፃፉበት ቀን ቢያንስ ዓመተ ምህረቱ ቢገለፅ ጥሩ ይመሰለኛል፡፡ ሌላው ደግሞ ብዙ ቦታ በዚህ ጉዳይ ወደፊት እፅፋለሁ እየተባለ ታልፎዋል፡፡ ለፀኃፊው ጉዳዮቹን ለማስታወስ ከመርዳት ወጭ በአሁኑ ሰዓት መፅኃፉ ውስጥ ያላቸው ፋይዳ አልታየኝም፡፡ አንዳንድ ቦታዎች ላይ የሚታዩት የዓመት ምህረት ስህተቶች መታረም ይኖርባቸዋል፡፡
አቶ አሰፋ ጫቦ በማመሰገን ቸር ይግጠመን እላለሁ፡፡