Tuesday, August 16, 2016

የኢትዮጵያ ትንሣኤ እንዴት? ከሸግግር መንግሰት እሰከ ጠብመንጃ አፈሙዝ!!!!



ኢትዮጵያችን ከሰሞኑ ድርስ የዲሞክራሲ እርጉዝ የሆነች ይመስላል፡፡ በሰላማዊ መንገድ ለውጥ ለምንፈልግ ሰዎች መንግሰት የፖለቲካ ማሻሻያ በማድረግ ሁላችንም አሸናፊ ሆነን የምንወጣበት ዲሞክራሲያዊ ስርዓት እናገኝ ይሆን ብለን እየጠበቅን ነው፡፡ የለም ገዢው ፓርቲ አብቅቶለታል በውስጥም በስብሷል ከውጭም ጫናው በርትቷል ፈንግለን እንጥለዋለን የሚሉም አሉ፡፡ ሌሎች ደግሞ አንድ ዓይነት ውጥረት ተፈጠረ በተባለ ቁጥር “የሸግግር መንግሰት” አቀንቃኞች ናቸው፡፡ እነዚህን ሶስት የዲሞክራሲ ፅንስ ማዋለጃ መንገዶችን በአጭር በአጭሩ ለማየት እሞክራለሁ፡፡ የግሌን አቋም የያዝኩበትን መስመር ትንሸ ሰፋ አድረጌ እምለከታለሁ፡፡
የሸግግር መንግሰት ማቋቋም
ይህን ሃሳብ የሚያቀነቅኑ ግለሰቦችም ሆኑ ቡድኖች ይህ ሃሳብ ተግባራዊ ሊሆን የሚችለው መቼ እንደሆነ የተረዱት አይመስለኝም፡፡ የዚህ ሃሳብ ተግባራዊ መሆን የሚችለው በኢህአዴግ መቃብር ላይ ብቻ ነው ብዬ ባልፍ በቂ ነበር፡፡ የኢህአዴግ መቃብር ደግሞ ከዚህ ቀጥሎ በምንመለከተው ሁኔታ የሚሆን ሰለሚሆን “የሽግግር መንግሸት” ለብቻው የሚቆም አማራጭ አይደለም፡፡ ገዢው ፓርቲ የሸግግር መንግስት ለሚባል አካል ስልጣኑን አስረክቦ ቢለቅ እኔም የምታዘበው ይመስለኛል፡፡ ጠቅላይ ሚኒሰትሩ ወግ ቢደርሳቸው የዚህን ያህል የተዓማኒነት ችግር ያለበት መንግሰት እየመራሁ ነው ከሚሉ፣ ፓርላማውም ወግ ደርሶች ጫና ቢያሳድር፣ “ፓርላማው”ን በትኖ አዲስ ምርጫ በህገ መንግሰቱ አንቀፅ 60 መሰረት እንዲከናወን ማድረግ ይችል ነበር፡፡ ለዚህ አልታደልም፡፡ ከዚህ የተለየ ህጋዊ ስርዓት “የሸግግር መንግሰት” ለመመስረት የሚስችል መንገድ የለም፡፡
በጣም ግልፅ ለመሆን ከዚህም ከዚያ በሚውጣጣ የቡድን እና ግለሰቦች ስብስብ “የሸግግር መንግስት” ይመስረት የሚሉ ሰዎች ያላቸውን የቡድን ውክልና ወይም ደግሞ ግለሰባዊ እውቅና መሰረት አድርገው ስልጣን በአቋራጭ የሚፈልጉ ናቸው፡፡ እመኑኝ እነዚህ ሰዎች በዚህ መስመር ሰልጣን ቢያገኙ ያገኙትን ስልጣን በቀጣይ በሚደረግ ምርጫ ስልጣናቸውን ቢያጡ አሜን ብለው የሚቀበሉ አይሆኑም፡፡ ሰለዚህ በእኔ እምነት “የሸግግር መንግስት ይቋቋም” በሚለው አልስማማ፡፡
ኢህአዴግ በስብሷል የስርዓት ለውጥ መደረግ አለበት
በዚህ ጉዳይ ኢህአዴጎች ባይስማሙ ብዙ ወገን ሊስማማ ይችላል፡፡ ይህን ስርዓት በስብሰሃልና ዞርበል እያልን ከሆነ በጉልበትና በጉልበት ብቻ የሚሆን ነው፡፡ ይህ ጉልበት ደግሞ አንድም በታጠቁ ኃይሎች፣ ወይም ደግሞ ህዝባዊ አመፅን ተከትሎ በሚመጣ የሰርዓት መፍረስ የሚገኝ ውጤት ነው፡፡ መንግሰት አሁን በያዘው ሁኔታ እሳቱን እያዳፈነ፣ የተዳፈነውን እሳት ግን ጭድ ስር እየደበቀ የሚቀጥል ከሆነ አይቀሬው ህዝባዊ ማዕበል እሳት ሆኖ ይበላዋል፡፡ ይህ እሳት ኢህአዴግን ብቻ ሳይሆን እኛም ከእሳቱ ብንተርፍ ወላፈኑ እይለቀንም፡፡ ይህ በሰላማዊ ሽግግር ሊታለፍ ካልቻለ ቀላል የማይባል ቀውስ በሀገራችን እንደሚያስከትል ግልፅ ነው፡፡ ይህ አማራጭ በትጥቅ የሚንቀሳቀሱ ኃይሎች እና ምንአልባት ህዝባዊ አመፅን በመምራት ላይ ያሉ ቡድኖች/ግለሰቦች በሚያደርጉት ስምምነት ቀጣይ የሀገሪቱ እጣ ፈንታ እንዴት ይሁን ብለው ሊነጋገሩ ይችላሉ፡፡ ኢህአዴግ-ሻቢያ- ኦነግ በለንደን እንዳደረጉት ማለት ነው፡፡ ከመንግሰት ጋር ይህ ውይይት ሊደረግ አይችልም፡፡ ሰለዚህ በዚህ አማራጭ ላይ ብዙ ማለት የሚቻል አይመሰለኝም፣ የአሸናፊዎች ፍትህ መስጫ ነው የሚሆነው፡፡ ምን አልባት በዚህ ወቅት እነዚህ አሸናፊ ኃይሎች የሚያቋቁሙት “የሸግግር መንግስት” አንደኛው ትክክለኛው አማራጭ የሚሆን ሲሆን እንደከዚህ ቀደሙ የኢህአዴግ የሽግግር መንግሰት መጪው የሸግግር መንግሰትም አግላይ ላለመሆኑ ምንም ዋስትና ሊኖረን አይችለም፡፡
ባጭሩ በሀይል የስርዓት ለውጥ ይደረግ ሲባል ኢህአዴግ ምንም ታሪክ እንደማይተርፈው መረዳት ያለበት ይሆናል፡፡ በሰፈረው ቁና መሰፈሩ ላይቀር የሚችልበት እድል ሰፊ ነው፡፡ ኢህአዴግ እና ኢህአዴጋዊያን ይህ ክፉ ቀን እንዳይመጣ ከዚህ ቀጥሎ የቀረበውን የፖለቲካ ማሻሻያ በማድረግ ሀገሪቱን ህዝብንም ሆነ እራሳቸውን እንዲጠብቁ መምከር እፈልጋለሁ፡፡
የፖለቲካ ማሻሻያ ማድረግ
አሁን ባለንበት ወቅት በሁሉም ወገን ተቀባይነት ማግኘት ያለበት ሃሣብ ነው ብዬ የማምነው፡፡ አሁን የደረስንበትን ቀውስ ሳናባብስ ነገር ግን ስር ነቀል የፖለቲካ ማሻሻያ በማድረግ ወደምንፈልገው ዲሞክራሲያው ስርዓት ልንሸጋገር እንችላለን የሚል እምነት አለኝ፡፡ ይህ የፖለቲካ ማሻሻያ የሚገኘው ግን አሁን የተጀመሩት ህዝባዊ እንቅስቃሴዎች ተጠናክረው ቀጥለው መንግሰት በልመና/በችሮታ የሚሰጠው ሳይሆን ለዚህች ሀገር መፍትሔ የሚያመጣ መንገድ ነው ብሎ አምኖ ሲቀበለው እና በሂደቱ በቅንነት ሲሳተፍ ነው፡፡ ከመንግሰት በተፃራሪ የቆምን ሀይሎችም የእኛ ብቻ ነው ልክ ከሚለው ግትር አቋም መለሳለስ ሲችሉ እና አንበረከክነው ከሚለው አስተሳሰብ ስንወጣ ነው፡፡
ይህ የፖለቲካ ማሻሻያ ለማድረግ በዋነኝነት ከመንግሰት ውጭ ያሉ ሀይሎች ችግሩ አሁን በስራ ላይ ያለው ህገመንግሰት ተቀዶ መጣል አለበት ከሚለው ፅንፍ ወጥተወ ሰላማዊ ሽግግር ለማድረግ እንደመነሻ የሚያገለግል እጅግ ጠቃሚ የሆነ የፖለቲካ ሰነድ መሆኑን አምኖ መቀበል ያስፈልጋል፡፡ ይህ ሲሆን ገዢው ፓርቲ በተለይ (የድል አጥቢያ አርበኞች ሳይሆኑ) በትግሉ ወቅት ከፍተኛ መስዋዕትነት የከፈሉበት ህገመንግሰት ተቀባይነት በማግኘቱ ደስተኞች ሰለሚሆኑ ሂደቱን የተሳካ ያደርገዋል፡፡ ይህም ሆኖ ህገመንግሰቱ ሊሻሻል የሚችል መሆኑ የማሻሻያ አንቀፆች ያሉት ስለሆነ በሂደት የሚሻሻልበት ሂደት መኖሩን መቀበል ደግሞ ለተቃዋሚዎች ተሰፋን የሚያጭር ይሆናል፡፡
ይህ የፖለቲካ ማሻሻያ በሚከናወንበት ጊዜ ሁሉ አሁን በስልጣን ላይ ያለው መንግሰት በመደበኛ የእለት ከእለት ስራው ላይ እንዲቆይ በመስማማት ሀገሪቱ ወደ ሌላ ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ቀውስ እንዳትገባ በማድረግ በስልጣን ላይ ያሉትም ቢሆኑ በስልጣን ላይቀጥሉ ቢችሉ የሰነልቦና ዝግጅ ማድረጊያ ጊዜ ያገኛሉ፡፡ ከገዢው ፓርቲ ውጪ ያሉ በሀገር ውስጥም በውጭ የሚገኙ ስልጣን የሚፈልጉ ሀይሎችም ለስልጣን የሚያበቃቸውን በቂ ዝግጅት ከህዝቡ ጋር በማድረግ እራሳቸውን ለማዘጋጀት በቂ ጊዜ ያገኛሉ፡፡ ማን ስልጣኑን ይይዛል የሚለውን ህዝብ ይወስናል፡፡
የፖለቲካ ማሻሻያ ሂደቱን ሊመራ የሚችል ገለልተኛ የሆነ የሸግግር ሂደቱን የሚመራ “የሽግግር ኮሚሽን” የሚቋቋም ሲሆን ይህ ኮሚሽን በዋነኝነት በሀገሪቱ የፖለቲካ ምዕዳሩን ሊያሻሽሉ የሚችሉ ልዮልዮ ደንቦችን እና መመሪያዎችን እንዲወጡ በማድረግ፣ አፋኝ ህጎችን በመሻር/ወይም በምክር ቤቱ እንዲሻሩ በማድረግ ህዝቡ በፖለቲካው በንቃት እንዲሳተፍ ማድረግ ይጠበቅበታል፡፡
ይህ ማሻሻያ በልመና የሚገኝ ባለመሆኑ መንግሰት ወደ ትክክለኛውም አማረጭ እሲገባ ድረስ አሁን ያለው ህዝባዊ እንቢተኝነት እና “በቃ” የሚለው ህዝባዊ እንቅስቃሴ ተጠናክሮ እንዲቀጥል በማድረግ መንግሰት ይህን አስፈላጊ የፖለቲካ ማሻሻያ እንዲቀበል ማሰገደድ የግድ ይላል፡፡ ምንአልባትም መንግሰት በራሴ አፈታዋለሁ በሚል በሚጠራቸው “ህዝባዊ መድረኮች” ሁሉ በመገኘት ይህን የፖለቲካ ማሻሻያ እንዲያደርግ ግፊት ማድረግ ያስፈልጋል፡፡ መንግሰት “ሕዝባዊ” ብሎ የሚጠራች መድረኮች በአብዛኛው የፓርቲው አባላትና ጥቂት ጥቅመኞች እንደሆኑ በመረዳት በስብሰባው ላይ ሌሎች እንዲገኙ ጥረት ማድረግ ተገኝተውም ድምፃቸውን እንዲያሰሙ ማድረግ ያስፈልጋል፡፡

አሁን በመደረግ ላይ ያሉ እንቅስቃሴዎች መንግሰት ላይ የፈጠሩት ጫና ያለ ቢሆንም መንግሰት በተገቢው መንገድ ምላሻ ለመሰጠት በሚያስገድድ መልክ እንዳልሆኑ መገንዘብ ይቻላል፡፡ ለምሣሌ ሰላማዊ ሰልፍም ሆኖ ተቃውሞ በተደረገ ማግስት መንግሰት በዚህ ተቃውሞ ላይ የተሳተፉ ዜጎችን እየገደለና በየቤቱ እየዞረ እየለቀመ በማስር ከስራ በማፈናቀል እንቅስቃሴውን ማፈን እንደ አንድ ታክቲክ እየተጠቀመ ስለሆነ ማነኛውም የህዝብ ጥያቄ (ትክክል ባይሆን) ከመንግሰት ወገን መልስ ከመስጠት አልፎ ጥያቄውን በማቅረብ የተሳተፉ ወይም የመሩ ሰዎችን ማሰረን፣ ከስራ መባረርን መቃወም ሲከፋም እንዳይታሰሩ መከላከል፡፡ ከታሰሩም በታሰሩበት ቦታ በመገኘት ተቃውሞ መቀጠል፣ እስኪፈቱ ድረስ በፈረቃ በቦታው በመገኝት ተቃውሞ ከፍ እንዲል ማድረግ ያስፈልጋል፡፡
መንግሰት አሁን የግድ የሚያስፈልገውን የፖለቲካ ማሻሻያ እስኪቀበል ድረስ የተቀናጀ ህዝባዊ እንቅስቃሴ ማድረግ ህዝባዊ እንቅስቃሴው ከጊዜ ወደጊዜ አድማሱን እያሰፈ ረጅም ጊዜ የሚወሰድ የስራና ትምህርት ማቆም አድማ ማድረግ ሊጨምር ይችላል፡፡ መንግሰት በዚህ ላይ በሚሳተፉ ሰዎች ላይ በሚወሰድ እርምጅ በመቃውም ከላይ በተገለፀው መልኩ ተቃውሞን ማስፋት፡፡
በማነኛውም ጊዜ ሆነ ቦታ በሚደረጉ እንቅስቃሴዎች በማነኛውም ዜጋ ላይ ምንም ዓይነት ጉዳት እንዳይደርስ ጥንቃቄ ማድረግ፤በተለያየ ምክንያት የዚህ ዓይነት ችግሮች ሲፈጠሩ ማጋለጥና ህጋዊ እርምጃ እንዲወሰድ ህዝቡ እንዲተባበር ማድረግ፡፡ መንግሰት ይህን ሰበብ በማድረግ በሰው ህይወት ላይ አደጋ እንዳያደርስ፣ በሰው ህይውት ላይ ለሚደርሱ ጉዳቶች ሃላፊነቱን እንዲወሰድ ማድረግ፡፡
ኢትዮጵያዊያን በዘርና ሃይማኖት ተቧድነው ይጣላሉ ብሎ መገመት አስቸጋሪ ቢሆን መንግሰትን ጨምሮ የተለያዩ ሀይሎች ለቡድናዊ ፍላጎታቸው ማስፈፀሚያ አንድን የህብረተሰብ ክፍል እንደሰብዓዊ ከላለ ለመጠቀም መሞከራቸው አይቀርም፡፡ ማነኛውም ህዝባዊ እንቅስቃሴ በሚደረግበት ወቅት ከፍተኛ ጥንቃቄ ማድረግ እና ኢትዮጵያዊነታችን ከብሔር ማንነታችን ጋር በምንም ሁኔታ የማይጋጭ መሆኑን ማስመስከር ይጠበቅብናል፡፡ በተለይ ኢትዮጵያዊ ልሂቃን ይህን ጉዳይ ለፖለቲካ ጥቅም ከማዋል እራሳችንን በማራቅ ታሪክ መስራት ይጠበቅብናል፡፡

Tuesday, July 19, 2016

ከግል እና ከመንግሰት ትምህርት ቤት በጥራት ማን ይሻለል?



በዛሬው ፅሁፌ በቅርቡ በዘመቻ መልክ የሚካሄደውን የግል ትምህርት ቤቶች ውግዘት አሰመልክቶ አንድ አንድ ሃሳቦች መሰንዘር እፈልጋለሁ፡፡ ይህ የግል አስተያየት በቅጡ ውይይት ማደረግ የሚፈልግ ካለ በይፋ መድረክ ላይ መነጋገር የምችልበት በፅኑ የማምንበት አቋም ነው፡፡ በተለይ በቴሌቪዥን “ማያ” በሚባል ፕሮግራም ላይ ሲቀርብ የነበረው ተከታታይ የግል ትምህርት ዘርፍ ጠል የሆነ አቀራረብ ፕሮግራሙን አስቀያሚ አድርጎታል ብዬ እንዳምን አድርጎኛል፡፡ በዚህ አጋጣሚ የፕሮግራሙ አቅራቢ ልጁን የትኛው የመንግሰት ትምህርት ቤት እንደሚያስተምር በይፋ ለህዝብ እንዲገልፅ እጠይቃለሁ፡፡ ያለበለዚያ ግን ልጁን የግል ትምህርት ቤት እየለካ የዚህን ዓይነት ፕሮግራም ማዘጋጀት አሰነዋሪ ነው፡፡ ልጅ ከሌለው ደግሞ በዚህ ደረጃ በማያውቀው ጉዳይ ባይገባ ይመከራል፡፡ እደግመዋለሁ “ልጆቹን የት የመንግሰት ትምህርት ቤት እንደሚያስተምር ለህዝብ በይፋ መግለፅ እና ምሳሌ መሆን ይኖርበታል”፡፡
በመጀመሪያ ከግልና ከመንግሰት ትምህርት ቤት የቱ ይሻላል? ከባድ ጥያቄ አይደለም፡፡ በብዙ እጥፍ የግል ትምህርት ቤት ይሻላል፡፡ ለምን? ብሎ በመጠየቅ እና ተገቢውን መልስ በመስጠት የመንግሰት ትምህርት ቤቶች ወደ ግል ትምህርት ቤቶች ደረጃ ለማሳደግ የሚደረግ ጥረት ካለ ይህን ለማሳካት ይረዳል የሚል እምነት አለኝ፡፡
በእኔ እምነት የግል ትምህርት ቤቶች በሚከተሉት ሁኔታዎች የተሻሉ ናቸው፤
1)  የወላጅ - ትምህርት ቤት መገናኛ መፅኃፍ ማዘጋጀት እና መጠቀም፡፡ ይህ የግንኙነት መስመር የዕለት ከዕለት ነው፡፡ የልጆች ትምህርት ቤት ወሎን፤ ምን የቤት ስራ እንደተሰጠ፣ ልጆች በዕለቱ በምን ዓይነት ሁኔታ ውስጥ እንደነበሩ፣ ጤናቸውን ጨምሮ፣ ሌሎች ጠቃሚ መረጃዎችን መምህር ለወላጅ መልዕክት ይልካል፡፡ ወላጅ መልዕከቱን ማየቱን በፊርማው ያረጋግጣል፡፡ በዚህ ሁኔታ ወላጆች ልጆቻቸውን እንዲከታተሉ የሚያደርጉ ሲሆን የመንግሰት ትምህርት ቤቶች የዚህ ዓይነት ስርዓት ያላቸው መኖራቸውን አላውቅም፡፡ መንግስት የወላጅ ትምህርት ቤት የግንኙነት የሚያጠናክር ማስታወሻ መፅኃፍ በማዘጋጀት እና ተግባራዊነቱን በመከታተል በቀላሉ ሊያደረገው የሚችል ቀላል ግን እጅግ አስፈላጊ ነገር ነው፡፡ ወላጆች/የወላጅ ኮሚቴዎች በወርና በሶሰት ወር ከሚያደርጉት ሰብሰባ እጅጉን የተሻለ ነው፡፡

2)  የግል ትምህርት ቤቶች የእንግሊዘኛ ቋንቋን በተሸለ ሁኔታ ሰለሚያስተምሩ ቋንቁ የሚችሉ ልጆች ደግሞ ማነኛውንም የመረጃ ምንጭ በቀላሉ እንዲጠቀሙ ያደርጋቸዋል፡፡ በዚህ ዘመን ደግሞ መረጃ የእውቀት መሰረት ነው፡፡ ይህንን እጅግ አስፈላጊ የእውቀት መሰረት የሆነን ቋንቋ ወላጆች ለምን ትኩረት ሰጡት ብሎ ክስ የሚያቀርቡ የመንግሰት ትምህርት ቤቶች ዳይሬክተሮች ትምህርት ምን ማለት እንደሆነ የገባቸው አይመሰለኝም፡፡ እዚህ ነጥብ ላይ አንድ የግል ምሳሌ መግለፅ እፈለግጋለሁ፡፡ ልጆቼን ከማስተምርበት ትምህርት ቤት ልጆቾ “በአማርኛ” ወይስ “በእንግሊዘኛ” እንዲማሩ ይፈልጋሉ? ምክንያቶን ያስቀምጡ የሚል እና ሌሎች መጠይቆች ቀረቡልኝ፡፡ ይህን ጥያቄ ከልጄ ጋር መወያየት ስለነበረብኝ ተነጋገርን፡፡ በእንግሊዘኛ መማር እንደሚፈልግ አስረግጦ ነገረኝ - በወቅቱ የአምስተኛ ክፍል ተማሪ ነበር፡፡ ለምን ብዬ ሰጠይቀው “ዓለም አቀፍ” መሆን ሰለምፈልግ አለኝ፡፡ ከዚህ የተሸለ መልስ እኔም አልነበረኝም እና ይህንኑ ሞልቼ ላኩኝ፡፡ አሁን በዘማቻ የተያዘው ነገር “በአፍ መፍቻ ቋንቋ” በሚል ፈሊጥ ልጆቻችን በአማርኛ ይማሩ የሚል የጥቂቶች ጩኽት በመርዝ የተቀባ መሆኑን ለማወቅ ነብይ መሆን አያሰፈልግም፡፡ አዲስ አበባ የአፍ መፍቻ ቋንቋ አማርኛ ነው ያለው ማነው? ወላጆች የአፍ መፍቻ ቋንቋ የሚሉት ካላቸው ልጆችን የት ማስተማር እንዳለባቸው መወሰን ያለባቸው እነርሱ ናቸው፡፡ ከላይ በጠቀስኩት የቴሌቪዝን ፕሮግራም ላይ አንድ የግል ትምህርት ቤት ተወካይ ፈራ ተባ እያለች “የአፋር ልጅ” በምን ይማር? አማርኛ አይችልም ብላለለች፡፡ እኔም እላለሁ በአዲስ አበባ “ሶማሌም” አለ፣ “ኦሮሞ” አለ፣ “ትግሬ” አለ፣ ወዘተ ለምን ሲባል አማርኛ ብቻ እንባላለን፡፡ ከዚህ ጋር በተያያዘ በግል ትምህርት ቤቶች ተለጠፈ የሚባሉት ማስጠንቀቂያዎችን ይመለከታል፡፡ “አማርኛ መናገርና  …… ያስቀጣል” የሚለው ሲሆን መልዕክቱ በዚህ መልክ ባይለጠፍ ጥሩ ነው፡፡ ልጆቻችን ግን የእንግሊዘኛ ቋንቋ ለማዳበር ያላቸው አንዱና ዋነኛው ቦታ በትምህርት ቤት ውስጥ እንግሊዘኛ ቋንቋን እንዲጠቀሙ በማበረታት/በማስገደድም ነው፡፡ ይህን በጎ ነገር አይቶ ማስጠንቀቂያው እንዲስተካከል ከመምከር ይልቅ ይህንን በመጥፎ ጎኑ በመተረክ የግል ትምህርት ቤቶችን ማሸማቀቅ ምን ያህል ይጠቅማል? ስንት ወላጆች ልጆቻቸው ቋንቋ እንዲለምዱ ቤት ውስጥ መርዳት ይችላሉ? ለማነኛውም ወላጆች በፍፁም ያልተሳሳትነው፤ ነገር ግን የመንግሰት ትምህርት ቤት ዳይሬክተር ነን ብለው በቴሌቪዥን የቀረቡት ሰዎች እና አቅራቢው ጭምር የተሳሳቱት “እንግሊዘኛ ቋንቋ” ልጆቻችን እንዲማሩ ስንወስን ይህ ችሎታ ለማህበራዊም ሆነ ለተፈጥሮ ሳይንስ አውቀት ለማግኘት መሰረት ሰለሆነ ነው፡፡ በግሌ ኢትዮጵያ ውስጥ ዩኒቨርስቲዎች የሚያስተምሩት በአማርኛ ቢሆኑ ልጆቼን በአማርኛ ብቻ ለማስተማር፣ በኦሮምኛ ቢሆን ኦሮምኛ ለማስተማር ብዙ ላልቸገረ እችላለሁ፡፡ ግን ልጄ ዓለምአቀፍ እሆናለሁ ሲለኝ በፍፁም አይቻልም ብዬ ልሞግተው አልችልም፡፡ ምርጫ የልጆች ሲሆን ይህን ምርጫ ማገዝ የእኛ የወላጆች መሆኑን ማወቅ ይኖርብናል፡፡ እስኪ ባለፉት 20 ዓመታት በአፍ መፍቻ ቋንቋ ተምረው ምደርን ያንቀጠቀጡ ልጆች በምሳሌነት አቅርቡልን፡፡
3)  የግል ትምህርት ቤቶች ለተማሪዎች ተጨማሪ የመርጃ መፅኃፍት ያቀርባሉ(ከህንድ፣ ከእንግሊዝ፣ ከአሜሪካ ወዘተ)፡፡ በዚህ መስመር የሚታየው ነገር መሰረቱ ምቀኝነት የሚመስል ነው፡፡ በግል እምነቴ ሰታንዳርድ ማለት ዝቅተኛው እንጂ ከዝቅተኛው የሚበልጥ ክልክል ነው ማለት አይመስለኝ፡፡ የግል ትምህርት ቤቶች ለተማሪዎች የሚሰጡት ትምህርት ከተቀመጠው ስታንዳርድ አንሶ ከተገኘ ተጠያቂነት መኖር አለበት፡፡ ከዚያ ከበለጠ ግን ያነሰውን እንዴት ከፍ እናድርግ ከሚለው ሃሳብ ይልቅ እንዴት ከፍ ያለውን የግል ትምህርት ቤት ውጤት እናውርድ አሳፋሪ የሆነ ነገረ ነው፡፡ እያዩ ፈንገስ “ርሃብህ የሚነሳው፣ የጎረቤትህን መጥገብ ሲያይ ከሆነ ርሃብህ ምቀኝነት ነው” ብሎናል፡፡ አሁንም በቅጡ ተጨማሪ የትምህርት መርጃ መፅሃፍት እና ሌሎች ቁሶችን ማቅረብ መከልከል ተገቢ አይደለም፡፡ ወላጆች ልጆቻቸው በመንግሰት ትምህርት ቤት ከሚሰጠው ያነሰ ትምሀርት እያገኙ ተጨንቀው ተጠበው በውድ ዋጋ ያስተምራሉ ማለት የወላጆችን ውሳኔ እና የውሳኔ መስጠት አቅም መናቅ ነው፡፡ በዚህ ጉዳይ በጣም የሚያስገርመው የትምህርት ቢሮ ተወካይ፣ ሃላፊ ሆነው የሚፎክሩብን ሰዎች አለቆቻቸው ልጆቻቸውን የት እንደሚያስተምሩ የማያውቁ ይመስላል፡፡ ከዚህ አንፃር በመግቢያዬ ላይ ያቀረብኩ ጥያቄ ለትምህርት ቢሮ ሃላፊም ማቅረብ እፈልጋለሁ፡፡ ክብሩ በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የትምህርት ቢሮ ሃላፊ ልጆን የትኛው የመንግሰት ትምህርት ቤት እንደሚልኩ ቢነግሩን?
4)  የግል ትምሀርት ቤቶች በአብዛኛው በዲግሪ ደረጃ የተመረቁ ናቸው፡፡ ይህ ደግሞ ለትምሀርት ጥረት ወሳኝ ግብዓት ነው፡፡ የመምህራን ጥራት በተመለከተ ትምህርት ቢሮ መምህራን በሙሉ ከመምህራን ማስልጠኛ መውጣት አለባቸው ይላል፡፡ በሀገራችን መመህራን ማስልጠኛ የሚገቡት በትምህርት ውጤታቸው በምን ዓይነት ደረጃ ያሉት እንደሆኑ ይታወቃል፡፡ እነዚህ መምህራን በሌሎች ዮኒቨርሲት ከሚመረቁት ምሩቃን በተወሰኑ የፔዳጎጂ ትምህርት ልዩነት እንዳላቸው ይታወቃል፡፡ ይህን ክፍተት በአጭር ጊዜ ስልጠና በመሙላለት ምሩቃኑን አስተማሪ ማድረግ ግን ይቻላል፡፡ ለዚህ ትክክለኛ ማሳያው በዩኒቨርሲቲ ከፍተኛ ውጤት የሚያመጡ (ሰቃይ) ተማሪዎች በአስተማሪነት አይሰለጥኑም ነገር ግን ዩኒቨርስቲ በአስተማሪነት አሰቀርቶ አስተማሪ ያደርጋቸውል፡፡ በዩኒቨርሲት እያሰተማሩ ሌላ ቦታ ማስተማር አይችሉም ማለት ሰህተት ነው፡፡ እነዚህን ተመራቂዎች በተወሰነ ደረጃ ማስልጠን ያስፈልጋል በሚለው መስማማት ይቻላል፡፡
5)  በግል ትምህርት ቤቶች የሚማሩ በአንድ ክፍል የሚገኙ ሁሉም ተማሪዎች ተመሳሳይ ትምሀርት መማራቸውን ለመከታተል የሚረዳ እና ተከታታይ ምዘና ለማድረግ የሚያግዝ ወርክ ሽቶች በየዕለቱ ያገኛሉ፡፡ ወላቸጆችም ይህን ለመከታተል የሚችሉበት አስራር አለ፡፡ ይህ አስራር ለተማሪዎች እጅግ ጠቃሚ የማጥኛ ዘዴም ጭምር ነው፡፡ ይህ በወላጆች ተሳትፎም ቢሆን በመንግሰት ትምህርት ቤቶች ቢተገበር እጅግ ጠቃሚ ነው፡፡ ይህን ማንም ሲቃወም አላያሁም ግን ወደ መንግሰት ትምህርት ቤት እንዴት ይምጣ ? የሚለው ሲነሳ አልሰማሁም፡፡
6)  በግል ትምህርት ቤቶች እሰከ አሁን ባለኝ መረጃ በአንድ ክፍል ውስጥ ከ30 ተማሪ በላይ የለም፡፡ ይህ መምህሩ ተማሪዎቹን ለመከታተል እና ለመርዳት ያግዘዋል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ ረዳት መምህራን አሉ፡፡ በመንግሰት ትምህርት ቤት እሰከ አሁን ያልተሳካው በክፍል 50 ተማሪ ማድረግ ነው፡፡ ይህ በመምህሩ ላይ የሚፈጥረው ጫና እንደተጠበቀ ሆኖ ለክትትልም አይመችም፡፡
7)  በግል ትምህርት ቤቶች ተማሪ ከትምህርት ቤት በፍፁም መቅረት አይቻለም፡፡ ታሞ የቀረ የህከምና ማስረጃ ማቅረብ ግዴታ ሲሆን ወላጆች የልጃቸውን ከትምህርት ቤት መቅረቱን በእለቱ በስልክ ተደውሎ ምክንያት ይጠየቃሉ፡፡ ይህ ክትትል ልጆች በመሃል አልባሌ ቦታ እንዳይውሉ ያግዛል፡፡ በተደጋጋሚ የሚቀር ተማሪ ከትምህርት ቤቱ ይባረራል፡፡ ሰለሚከፍል ተብሎ ትምህርት ቤት አይቆይም ይህ ክትትል መቼም በመንግሰት ትምህርት ቤት ለማድረግ የሰልክ በጀት ብቻ ነው የሚያስፈልገው፡፡

ከላይ የዘረዘርኳቸው ነጥቦች በጎ በጎዎች ናቸው፡፡ ብዙ ችግሮች እንዳሉ አውቃለሁ፡፡ ወደዚያ ዝርዝር ያልገባሁት የፕሮግራም አቅራቢዎች በበቂ ለመክሰሻነት ያቀረቡት በመሆኑ ነው፡፡ እዚህ ግን መነሳት ያለበት የግል ትምሀርት ቤቶች እጅግ አሳሳቢ የሆነ የቦታ ችግር አለባቸው፡፡ ሰፊ ቦታ ለማግኘት አጅግ ውድ የሆነ የቤት ኪራይ መክፈል ስለሚኖርባቸው የትምህርት ክፍያዎች በአብዛኛው ኢትዮጵያዊ ከመክፈል አቅም በላይ እየሆኑ ሲሆን ወላጆች ይህን ለማሟላት ሲሉ በከፍተኛ ጭንቀት ላይ መሆናቸው ይታወቃል፡፡ መንግሰት የምር ለዜጎች ጭንቅና ለአዲሱ ትውልድ መፍትሔ ለማምጣት የሚጨነቅ ከሆነ ለመንገሰት ትምህርት ቤቶች እንደሚያደርገው ሁሉ ለግል ትምህርት ቤቶችም በዝቅተኛ ዋጋ ወይም ደግሞ በነፃ የትምህርት ቤት መገንቢያ ቦታ ሊሰጣቸው ይገባል፡፡ ለምሳሌ በነፃ ለትምህርት ቤት ግንባታ የተሰጠ ቦታ በምንም መልኩ ወደሌላ ቢዝነስ የማይለወጥ እንዲሆን የሚያስችል ህግ ሊያወጣ ይችላል፡፡ ከዚህም በላይ በነፃ ቦታ ያገኙ የግል ትምሀርት ቤቶች የተወሰኑ ተማሪዎችን ከዝቅተኛ የህብረተሰብ ክፍል በነፃ እንዲያስተምሩ ሊያስገድድ ይችላል፡፡ ይህ መንግሰት በእጁ ያለ የግል ዘርፉን ሊያግዝበት የሚችልበት ነው፡፡ ተመቸኝ ብሎ በቴሌቨዠን ቀርቦ ግን ተገቢ ያልሆነ ክስ መስጠት ግን ብዙ ጥቅም የለውም፡፡ አሁን በግል ትምህርት ቤቶች ላይ የተያዘው ዘመቻ በምንም መልኩ የመንግሰት ትምህርት ቤቶችን አያጠናክርም፡፡ ይልቁንም ወላጆች በመንግሰት ቁጥጥር ወደማይደረግባቸው “ኮሚኒቲ” ትምህርት ቤቶች እንዲያዘነብሎ፣ ካልሆነም ውጭ ልከው እንዲያስተምሩ ከመገፋፋት ውጭ ትርፍ የሚኖረው አይደለም፡፡ ለማነኛውም ሁላችንም የመንግሰት ትምህርት ቤቶች እንዲት ወደ ግል ትምህርት ቤቶች የጥራት ደረጃ ይድረሱ ለሚለው ጠጠር ብንወረውር የተሻለ ነው፡፡ የግሎቹን እንዴት ወደ መንግሰት ትምህርት ቤቶች ደረጃ እናውርዳቸው ከማለት ይልቅ፡፡

Tuesday, July 5, 2016

ኮንዶሚኒየም፣ የዜጎች መኖሪያ ቤት ጉዳይ እና ፖለቲካ



አንድ ጊዜ አሜሪካን ሀገር በነበረ ስብሰባ ኮንዶሚኒየም ቤት ለማግኘት የተመዘገበው በውጭ የሚኖር ኢትዮጵያዊ ትክክል እንዳልሆነ ትንሽ ጠንከር ያለ ሃሳብ ሰጠው፡፡ በቂ ምክንያት ነበረኝ፣ አሁንም ልክ እንደሆንኩ ይስማኛል፡፡ ኮንዶሚኒየም የሚሰረው በመንግሰት ልዩ ድጋፍ “ለድሆች” በሚል ነበር፡፡ ነበር ያልኩት እየገቡ ያሉት እንማን እንደሆኑ በብዛት ስለሚታወቅ ነው፡፡ ስለዚ በውጭ የሚኖሩ ኢትዮጵያዊያን ደግሞ በአንፃራዊነት የተሻሉ ናቸው፡፡ ሰለዚህ በዚህ ውድድር ውስጥ መግባት የለባቸውም የሚለው አንዱ ለሰጠሁት ሃሳብ መነሻ ሲሆን፡፡ ዋነኛውም ግን መንግሰት በውጭ የሚኖሩ ኢትዮጵያዊያን/ትውልደ ኢትዮጵያዊያን ለማገዝ ፈልጎ ሳይሆን በዚሁ መስመር የውጭ ምንዛሬ ለማግኘት ነው፡፡ የሚሉ ሃሳቦች ነበሩኝ፡፡ ነገር ግን ሁሉም ከእውነቱ እና ከቀረበው አምክንዮ ይልቅ የግል ጥቅሙ በልጦበት እጅጉን ቅር ተሰኘ፡፡ ድሮም እኔ በውሸት ለማስደስት ሰለአልተዘጋጀሁ በግሌ ደስ አለኝ፡፡ ተዋወቅን ብል ነው ደስ የሚለኝ፡፡ ይህን አስመልክቶ በግል እንዲህ ዓይነት አቋም አትያዝ ውጭ ያሉት ሰዎች ቅር ይላቸዋል፣ ድጋፍም አይሰጡህም የሚሉ ምክር አዘል መልዕክቶች ደርሰውኛል፡፡ እውነቱ ግን ይህው ነበር፡፡ በግሌ የተለየ ድጋፍ ሰለማልፈልግ እውነቱን መናገር ምርጫያ ነበር፡፡
ሰሞኑን ደግሞ በሀገር ውስጥ ያሉ በመንግሰት ፍርጃ “ጥቅመኞች፣የኒዎ ሊብራል አቀንቃኞች፣ ወዘተ” የሚባሉት የእኔ ቢጤዎች ኮንዶሚኒየም ቤት ለማግኘት በ40/60 ቤት ተሰርቶ እንደሚሰጣቸው እንዲሁም በማህበር ተደራጅተው ሃምሳ ከመቶ (50/50) የግንባታ ወጪ በዝግ ሂስባ ካስቀመጡ በከተማው መሃል ለልማት ከሚነሱት ቦታዎች ቦታ ይሰጣችኋል ተብለው እጅግ ብዙ ገንዘብ እንዲቆጥቡ አማላይ ሃሳብ ቀረቦላቸው ተግባራዊ ሲያደርጉ ነበር፡፡
አብዛኛው ያለምንም ማንገራገር የመንግሰትን መግለጫ ሰምቶ ቁጠባ ጀመረ- ቁጠባ ከሚባል ያለውን ጥሪት ተበድሮ ጭምር ወደ ንግድ ባንክ አዞረ ማለት ይቀላል፡፡ በእሩጫ ውድድር አሯሯጭ እንደሚመደበው አንድ አሯሯጭ ዜናም አብሮ ቀረበ፤ “ቀድሞ ሙሉ የከፈለ ቅድሚያ ያገኛል” የሚል ወሬ ሚዲያውን ጨምሮ በልዩ ልዩ መስመር ተወራ፡፡ በእውነትም በአስር ሺዎች ሙሉ በሙሉ ከፈሉ፡፡ ለመክፈል ያልቻሉም የቻሉትን ያህል ለመክፈል ተረባረቡ፤ በተለይ አርባ ከመቶ ለማሟላት የሚችሉትን ሁሉ አደረጉ፡፡ አብዮታዊው ዲሞክራሲው መንግሰታችን “የእነዚህን ጥቅመኞች እና የኒዎ ሊብራሎችን” ገንዘብ ሰብሰቦ በእጁ አስገባ፡፡ በእጅ አዙር በቁጥጥር ስር አዋላቸው ነው መባል ያለበት፡፡
መንግሰት ገንዘቡን ለመሰለውና ለፖለቲካ ጥቅሜ ያዋጣኛል ባለው መስመር ተጠቀመበት፡፡ ይህን እውነት ከማመን ይልቅ ሁለት ሺ ለማይሞላ ቤት አሰር ሺዎች ይራኮታሉ፡፡ በዚህ አጋጣሚ መንግሰት በሚቀጥሉትም አምስት አመታት ቤት ሰርቶ እንደማያስረክብ የታመነ ነው፡፡ ለምሳሌ ባለፉ አስር ዓመታት መንግሰት መገንባት የቻለው 175 ሺ የማይበልጥ ሲሆን በቀጣይ አምስት ዓመታት የታቀደው ደግሞ 450 ሺ ቤት ለመገንባት ነው፡፡ እንደምታውቁት ፉከራ ነው፡፡ በመጨረሻው ልምድ አግኝተንበታል ነው የምንባል፡፡ ሚሊዮኖች ተመዝግበው እየጠበቁ ሌሎች ሚሊዮኖች ደግሞ የቤት ፈላጊ ሆነው በዚህ መስመር ቤት አገኛለሁ ማለት የእልም እንጀራ ይመስለኛል፡፡ ጥቂቶች ቤት አያገኙም እያልኩ እንዳልሆነ ሊሰመርበት ይገባል፡፡ ውጤቱን ግን ወደፊት እናየዋለን፡፡
በነገራችን ላይ መንግሰት ይህን ማድረግ የማይችል መሆኑን በደንብ ተረድተው በሪል ሰቴት ልማት ውስጥ የሚሰማሩ ኢንቨሰተሮችን በሆነው ባልሆነ እንዳይሳካላቸው መንገድ የሚዘገው መንግሰት መሆኑን ብዙዎች አይረዱም፡፡ ይልቁንም ከቤት አልሚዎች ጋር ከመንግሰት ጋር ተባብረው ፈጣሪ ኢንቨሰተሮችን ያዋክባሉ፡፡ ይሰቀል፣ በድንጋይ ይወገሩ የሚሉ ሞልተዋል፡፡ መንግሰት በዚህ ጊዜ ደግሞ ቤት እንዲያገኙ ፍላጎት እንዳለው መስሎ ቀርቦ ድብቅ ተልዕኮውን ያሳካል፡፡ መንግሰት ይህን የሚያደርገው የግል አልሚዎች በተሻለ መፈፀም ከቻሉ መሰታውት ሆነው እንደሚያጋልጡት ስለሚረዳ ነው፡፡ ቀደም ሲል የመሬት ዋጋ በማሰወደድ የግል አልሚዎችን ማሰወጣት በቂ ነው በሚል እየሰራ የነበረ ሲሆን፣ ይህ ግን በቂ አለመሆኑን በመረዳት በአሁኑ ጊዜ የግል አልሚዎች በፍፁም እንዳይሳካላቸው እያደረገ ይገኛል፡፡ ይህን ለመመልከት ግን በፍፁም ከግል ጥቅማችን እና ጉዳታችን ወጥተን ጉዳዩን በእውነት ለመመልከት ስንወሰን የሚገባን ሚስጥር ነው፡፡
መንግሰት ለቤት አልሚዎች መሬት በነፃ ሰጥቶ አልሚዎች በተመጣጣኝ ዋጋ ቤት እንዲያቀርቡ ለምን አይደራደርም? ይህማ የኒዎ ሊብራል አስተሳሰብ ነው፡፡ መንግሰት የእኔ ነው በሚለው መሬት ግለሰቦች ሊከብሩበት የሚል የምቀኛ አስተሳሰብ በውሰጣችን አለ፡፡ መንግሰት ይህን እየኮተኮተ ያሳድጋል፡፡ እኛ ከስር ከስር ውሃ እናጠጣለን፡፡ ተቃቅፈን በድህነት የመንግሰት ጥገኛ ሆነን እንኖራለን፡፡ መንግሰትም የሚፈልገው ሁላችንንም ግቡ-ውጡ በሚለን መስመር እንድንገኝ ነው፡፡ የምርጫ ሰሞን ኮንዶሚኒየም ጊቢዎች ውስጥ ያለውን ውክቢያና ጥርነፈ የተመለከተ ነፃነቱን በገንዘቡ አሳልፎ እንደሰጠ ይረዳል፡፡ ኮንዶሚኒየም ቤት ደርሶት ያከራየ ሁሉ ተከራይም ኢህአዴግን መምረጥ እንዳለበት ማሳሰቢያ የሚሰጡበት ወቅት ነው፡፡
በነገራችን ላይ በዚህ አጋጣሚ የአያት የመኖሪያ መንደር መስራች በግሌ በግፍ እንደተሰቃዩ ይሰማኛል፡፡ ባደረጉት ከፍተኛ አስተዋፅኦ በሀገራችን የቤት ልማት ውስጥ ማንም በሸፍፅ የማይሽርው አሻራ አኑረዋል፡፡ እጅግ ብዙዎችን ባለቤት/ባለሀገር አድርገዋል፡፡ ይህን የሚያክል የከተማ ክፍል ሲገነቡ ምንም ስህተት አልሰሩም ብዬ መከራከር የምችልበት መረጃ ባይኖረኝም፣ መንግሰት ይህን የሚያክል ከተማ ክፍል የመገንባት ሰራ ቢሰራ ሊያጠፋ የሚቸለውን ሳሰበው ይዘገንነኛል፡፡ ሰራ እና ሃሳብ ፈጣሪዎቻችንን ከመሸለም እና እውቅና ከመስጠት ይልቅ ወህኒ ማውረድ በፍፁም ተቀባይነት የለውም፡፡ ክብር ለሚገባው ክብር እንስጥ!!!!
ቸር ይግጠመን!!!!


Monday, June 27, 2016

ለዲሞክራሲ ስርዓት ምን ዓይነት ፓርቲ ያስፈልገናል?



በሀገራችን የዲሞክራሲያዊ ስርዓት ግንባታ የፖለቲካ ፓርቲዎች፣ የሲቪል ማህበራት እንዲሁም የሚዲያ ተሳትፎ አጅግ ወሳኝ እንደሆነ ሁሉም ይረዳዋል ማለት ባይቻልም በተለይ የፖለቲካ ፓርቲ አባል አመራር የሆኑ ሰዎች ይጠፋቸዋል ብሎ የሚገምት ላይኖር ይችላል፡፡ እውነቱ ግን ከዚህ የተለየ ነው፡፡ በአሁኑ ጊዜ የፖለቲካ ፓርቲ ውስጥ ሰዎች የሚሳተፉት በዋነኝነት በሀገራቸን የዲሞክራሲ ስርዓት ግንባታ ያላቸውን መዋጮ በማስላት ሳይሆን ገዢውን ፓርቲ በማስወገድ ላይ ብቻ ያጣነጠነ ይመስላል፡፡ ይህንንም ማድረግ የሚፈልጉት ደግሞ በትርፍ ጊዚያቸው ከስራ መልስ ወይም በጡረታ ጊዚያቸው ነው፡፡ ይህን ሲያደርጉ ደግሞ የብዙ ወጣቶች ጊዜና ጉልበት መስመር ባልያዘ አቅጣጫ እንደሚመሩ አይረዱም፡፡ ለነገሩ የወጣቶችን ጊዜ በማባከን እና የወጣቶችን ፍሬያማ ጊዜ በከንቱ በማባከን ገዢውን ፓርቲ የሚወዳደር የለም፡፡ በሰራ እናገኛለን ተሰፋ እና እራሳቸውን ከደህንነት ስጋት ለመጠበቅ ገዢውን ፓርቲ በምሽግነት ስለሚጠቀሙበት፡፡ ይህም ቢሆን ገዢው ፓርቲ ይህን ስለሚያደርግ ተቃዋሚዎች የወጣቶችን ጊዜ ያለአግባብ ማባከን አለብን የሚል ክርክር ሊገጥሙ አይገባም፡፡
በእኔ እምነት የፖለቲካ ፓርቲ አባል ሲኮን በተለይም አመራር ሲኮን በቀጣይ የመንግሰትን ስልጣን ለመያዝ መዘጋጀትን ይጠይቃል፡፡ በአሁኑ ወቅት በዚህ ልክ እራሳቸውን ያዘጋጁ የገዢው ፓርቲም ሆነ የተቃዋሚ ፓርቲ አባላት ማግኘት አስቸጋሪ ነው፡፡ ገዢው ፓርቲ ከሰበሰባቸው ሰባት ሚሊዮን አባላት ምርጥ ብሎ አውጥቶ አመራሩን መቀየር ባለመቻሉ ያሉትን የጡረታ ጊዜ እያራዘሙ 25 ዓመት ሞልቶታል፡፡ አሁንም ቢሆን በገዢው ፓርቲም ሰፈር ከፊት መጥተው ተሰፋ የሚደረግባቸው አይታዩም፡፡
በተቃዋሚ ጎራ ይህን ወሳኝ የፖለቲካ አመራር እና የመንግሰት ስልጣን ቁርኝትን ባለመረዳት ፓርቲ የመሰረቱ እና ለመመስረት የሚራወጡ ሰዎች ግባቸው እንደ ከዚህ ቀደሙ የጡረታ ወይም ደግሞ ከሰራ መልስ ጊዜ ማሳለፊያ ከማድረግ የዘለለ ፋይዳ ያላቸው አይመስለኝም፡፡ ከዚህ በፊት ይህን ለማሳካት አንድነት ፓርቲ ያዘጋጀውን ስትራቴክ ሰነድ መሰረት አድርጎ የመድረክ አመራሮችን “ሻዶ ካቢኔ” እናቋቁም ብሎ ጥያቄ ሲያቀርብ በግልፅ ለፖለቲካ ስልጣን የምናደርገውን ትግል በድብቅ ማድረግ የለብንም የሚለውን የአንድነትን ግልፅ አቋም በድብቅ በውስጣቸው ባለ ሰውር የስልጣን ጥም (ማን የካቢነዊ መሪ ይሆናል?) ሳይቀበሉት እና ሳይሳካ ቀርቷል፡፡ በዚህም መነሻ አንድነት ያቀረበውን የስትራቲጂክ ፕላን ሰነድ ሳይቀበሉት ቀሩ፣ቀጥሎም አንድነትን ገፍትረው አስወጡት፡፡ ለነጉሩ አንድነትም በዚህ ትብትብ ውስጥ ድንክ ሆኖ አይቆይም ነበር፡፡
አሁን ደግሞ በድጋሚ ማሳካት የሚፈልገው ዓላማ ምን እንደሆነ የማይታውቅ ከአንድነት ፓርቲ ፍርስራሽ “ነፃነት” የሚባል ፓርቲ መመስረቱን ሰምተናል፡፡ ለምስረታው ከፍተኛውን ሚና ሲጫወት የነበረው አቶ ብሩ ቢርመጂ በድንገት ከዚህ ዓለም በሞት ቢለይም የፓርቲው መሪ ሆኖ የተመረጠው ዶክተር ንጋት በእርግጥም የጃንሜዳ ልጅ ቢሆንም በሰሜን ሸዋነቱ በቀጣይ መድረክ ውስጥ ለሚታየው የአማራ ፓርቲ ክፍተት ማሟየ እንደሚሆን ግልፅ ነው፡፡
አንድነትን ገፍትሮ ያስወጣው የፕሮፌሰር በየነ አና የዶክተር መረራ መድረክ አሁን ለነፃነት ፓርቲ ምስረታ ሁሉን አቀፍ ድጋፍ በማድረግ ላይ ይገኛል፡፡ ይህ የሚያሳየን ኢትዮጵያ የፓርቲዎች እጥረት ስለአለባት የዜጎችን የመደራጀት ዲሞክራሲያዊ መብት ለመደገፍ ካላቸው ቀና አመለካካት ሳይሆን መድረክ የኢህአዴግ “ፎርጅድ ኮፒነቱን” ለማሳካት የጎደለውን የአማራ ፓርቲ ለመሙላት ብቻ ነው፡፡ መድረክ በትግራይ ዓረና ለህውሃት፣ በኦሮሚያ ኦፌኮ ለኦህዴ፣ በደቡብ የፕሮፌሰር በየነ ፓርቲዎች እና የሲዳማው ድርጅት ለደህዲን የተዘጋጁ ሲሆን ለብአዴን ግን የአቻ ፓርቲ ችግር ነበረበት፡፡ ከዚህ በፊት አንድነትን በውስጠ ታዋቂነትም ሲከፋም በይፋ የአማራ ፓርቲ አድርገው ይፈርጁ ሰለነበር ከአንድነት መውጣት በኋላ ይህ ክፍተት “ፎርጅድ ኮፒ” ለመሆን እንኳን አላሰቻላቸውም፡፡ አሁን ግን የነፃነት ፓርቲ መምጣት ከመኢህአድም ሆነ ከሰማያዊ ጋር ያላቸውን ስር የሰደደ ጥላቻ አስወግደው ከመሻረክ ይህን የአንድነት ፍራሽ በማሰገባት ድሮ አንድነት ሊውጠን ነው ከሚለው ስጋታቸው ወጥተው እኩያቸው የሆነ ፓርቲ እንዲያገኙ ይረዳቸዋል፡፡ ነፃነት ቢሮ የሌለው ማህተምና ፋይል በሰዎች መኖሪያ ቤት የሚገኝ፣ ይህ ነው የሚባል ድርጅታዊ ጥንካሬ የሌለው ፓርቲ ሰለሆነ ለመድረክ አባል ድርጅቶች የእኩዮች ጥምረት ይሆናል፡፡ “የፎርጅድ ኮፒ” ፕሮጀክት ክፍተትም ይሞላል፡፡ እንደሚታወቀው የፓርቲዎች ውህደት እኩል ሳይሆኑ በእኩልነት መንፈስ ይባላል፡፡
ለማነኛውም የኢትዮጵያ ህዝብ እውነተኛ የዲሞክራሲ ስርዓት እንዲኖር ይፈልጋል፡፡ ይህ ደግሞ የሚሆነው አውነትኛ የድርጅት አቅም ያላቸው አማራጭ የሚሆኑ፤ ህዝቡ ቢመርጣቸው የመንግሰት ሃላፊነት ተረክበው ሊያስተዳድሩት የሚችሉ፤ የፖለቲካ ፓርቲዎች ይፈልጋል፡፡ በግሌ አንድ ፓርቲ መንግሰት ብሆን የካቢኔ አባሎቼ እነ እገሌ ናቸው ብሎ ብቃት ያላቸው 30 ሰዎች የሚያሳየኝ ካለ አባል ለመሆን ዝግጁ ነኝ፡፡ አንድነት ውስጥ ይህን ማደረግ ስለሚቻል ነበር ለፖለቲካ ስልጣን የምንሰራው፣ ይህ በገዢው ፓርቲ አልተወደደም፡፡ በገዢው ፓርቲ ብቻ ሳይሆን ተቃዋሚ ነን በሚሉት ጭምር (ሰማያዊና መድረክን ጨምሮ) በተለይ ሰማያዊ በአንድነት ፍራሽ የሚጠነክር መስሎት ስለነበር፡፡ ነገሩ ግን የተገላቢጦሸ ነው የሆነው፡፡
አሁንም በኢትዮጵያ የዲሞክራሲ ስርዓት እንዲኖር ካስፈለገ፤ የሚፈጠረው ፓርቲ እንደ ኢህአዴግ አመራር የማይወጣው 7 ሚሊዮን አባል በመስብሰብ የመልካም አስተዳደር ችግር የሚፈጥሩ አባላትን በማብዛት ሳይሆን ምርጦች የሚሰበሰቡበት፣ ለጥቅም ሳይሆን “ለአቅመ መስጠት” የደረሱ፤በአውቀታቸው እና ከራሳቸውና ከቤተሰባቸው አልፈው ለዜጎች ኢኮኖሚያዊ፣ ማህበራዊ ፍትህ የሚጨነቁ ብቻ ሳይሆን አማራጭ መፍትፈሔ የሚያቀርቡ፣ በየደረጃው ለፖለቲካ አመራር የሚሰባሰቡበት መሆን ይኖርበታል፡፡ ሰለዚህ መስጠት የማይችሉ ለአቅመ መስጠት እስኪበቁ በደጋፊነት መቆየት ይኖርባቸዋል፡፡ መረዳት ያለባቸው የተቃዋሚ ፓርቲ አባልም ሳይሆኑ በዲሞክራሲ ስርዓት ተጠቃሚ ይሆናሉ፡፡ በዚህ የሚጠቀሙት የኢህአዴግ አባለት ጭምር ስለሚሆኑ፡፡
በተመሳሳይ ጠንካራ ሚዲያ እና ሲቪል ተቋማት መኖር አለባቸው፡፡ አርዳታ ለማሰጠት እና ለራሳቸው የስራ እድል ለመፍጠር የተደራጁ ሲቪል ማኅበራት፣ በዕትመት ለመቆየት ለዘብተኛ የሆኑ ሚዲያዎች ለዲሞክራሲ ስርዓት ግንባታ ፋይዳ የላቸውም፡፡ ይፍረሱ!!!!!

Monday, June 6, 2016

መድረክ ንጉሣዊ ነው እንዴ?



ለመድረክ ቅርብ የሆነ አንድ ወዳጄ የመድረክን የእሁድ ግንቦት 28/2008 ጉባዔን አስመልክቶ የነገረኝ ነገር መድረክ ንጉሣዊ ነው እንዴ? የሚል ጥያቄ እንዳነሳ አድርጎኛል፡፡ መቼም በመድረክ ስም ፓርላማ ስለነበርኩ ለመድረክ ቅርብ የምመሰላቸው ካሉ ተሳስተዋል፡፡ የመድረክ ስብሰባ እንደሚታወቀው ውሣኔ የሚሰጠው የጉባዔ አባላት ተሰብሰበው በውይየት አቋም ይዘው በነፃነት በሚሰጥ ድምፅ አይደለም፡፡ አባል ድርጅቶች አድማ መተው የሚመጡበት ነው፡፡ ሌላው በመድረክ ውስጥ ኃላፊነት የሚያዘው በአባል ድርጅቶች በዙር ነው፡፡ ከአባል ድርጅቶቹ ደግሞ የሚልኩትን መሪ ቀይረው የማያውቁት ደግሞ ፕሮፌስር በየነ እና ዶክተር መረራ ናቸው፡፡ አሁን ባለኝ መረጃ መሰረት መድረክን የመምራት ተራው የሀረና ነበር፡፡ ይህ ማለት ግን የስብሳቢነት ቦታው ለሀረና እንዲሲጠው ሀረና ለቦታ የሚያቀርበው ዕጩ ወሳኝነት አለው፡፡ ሰለዚህም ሀረና ያቀረበው ዕጩ ለመድረክ ሊቀመንበርነት አይደለም፣ ለምክትልም አይሆንም በሚል ቦታው በቃኝ ለማያውቁት ለፕሮፌሰር በየነ አንዲሰጥ ተደርጎ ዶክተር መረራም ምክትል ሆነው ቀጥለዋል፡፡
አቶ አስፋ ጫቦ በቅርቡ ባሳተመው መፅኃፍ ውስጥ የሸዋ ንግስና ከተመለሰ የእኛም መመለስ አለበት የሚል ስላቅ አቅርቦ ነበር፡፡ ፕሮፌሰር በየነም ቤተሰቦቻቸው በአካባቢው እንዲህ ዓይነት የንግሰና ጥያቄ ከመጠ ከሚጠይቁት ወገን ናቸው ስለሚባል፤ ይህ እስኪመጣ ድረስ መድረክን የንግስና መለማመጃ ያደረጉት መስለኝ፡፡ ይህ ካልሆነ ግን ብዙ ሙከራ አድርገው ያልተሳካላቸውን የአመራር ቦታ ቢቻል ፖለቲካውን ጭምር መተው ለምን ተቸገሩ?
ከወዳጄ ጋር ሰለምርጫው ስናወራ የፕሮፌሰሩ በተደጋጋሚ ከሚቀርብባቸው ከተቃዋሚ መሪነት እራሳቸውን ያግልሉ ጥያቄ ችላ ማለት ብቻ ሳይሆን ሃያም ሆነ ሰላሣ ሰዎች ድምፅ ሰጥተዋቸው በሃላፊነት የሚቆይቱ ባለፈው የሃላፊነት ዘመናቸው ምን ሰርተው ነው? የሚል ጥያቄ ለምን አያነሱም ነው፡፡ በፕሮፌሰር በየነ አመራር ወቅት መድረክ ምን ውጤት አስገኝቶ ያን ውጤት ለማስቀጠል ሲባል ነው የተሰጠው ሊባል የሚችል ውጤት አልታየም፡፡ በኦሮሚያ ለነበረው ህዝባው ንቅናቄ እንኳን በቂ ድጋፍ መስጠት ያልቻለ ስብሰብ እንደሆነ በስብሰባው ወቅት ጥያቄ ተነስቶበታል፡፡
የተነሳው ጥያቄም “በኦሮሚያ ለነበረው እንቅስቃሴ ኦፌኩ ብቻውን ለምን ተንቀሳቀሰ?” በሚል ነበር፡፡ መልሱ ግን የበለጠ አስደማሚ ነበር፡፡  “ኦሮሞዎች የተለየ ጉዳይ ስለነበረን ነው” የሚል እንደምታ ያለው መልስ ተሰጥቷል፡፡ አስገራሚው ነገር በአንድ ወቅት ሀብታሙ አያሌው  “ሰለ ኦሮሞ ችግር ለመናገር ኦሮሞ መሆን አያስፈልግም ሰው መሆን ይበቃል” ብሎ በሰጠው አስተያየት መድረክ አጀንዳ አድርጎት ኦሮሞ ያልሆነ የኦሮሞ ችግር አይገባውም የሚል መልስ ተሰጥቶ አንድነት እና ሀረና ታዲያ እዚህ ምን እንሰራለን? በሚል ስብሰባው ተቀውጦ እንደነበር የቅርብ ጊዜ ትዝታ ነው፡፡ አሁንም መድረኮች አብረን ነን ይበሉ እንጁ የትግሬው ችግር የሀረና፣ የኦሮሞ ችግር የኦፌኮ አድርገው በመያዝ ዳር ይዘው ተቀምጠዋል፡፡ በነገራችን ላይ መድረኮች አንድነትን ካስወጡ በኋላ የአማራ ተወካይ የሚያደርጉት ወይም የሚመስልላቸው ሳያገኙ እስከ አሁን አሉ፡፡ በቅርቡ የተመሰረተው የአንድነት ሽራፊ “ነፃነት” የሚባለው ፓርቲ ይህን ቀዳዳ ለመሙላት ተሰፋ ሳያደርጉ አይቀሩም፡፡ ወይም “ሰመያዊ” ፓርቲ ዓይኑ በጨው ታጥቦ ሊቀላቀላቸው ይችላል፡፡ የመድረክ አመራሮች ይህ ያለባቸውን የአማራ ወኪል ክፍተት በመሙላት “ፎርጂድ” የኢህአዴግ ኮፒ አደረጃጀት እንዲሳካ መጣራቸው የማይቀር ነው፡፡ ለህወሃት-ሀረና፣ ለኦህዴድ-ኦፌኮ፣ ለደህዴን-የበየነ ፓርቲዎች፣ ለብአዴን- ? ? ? ? - ፡፡ ክፍቱን ቦታ ለመሙላት እንግዲ ነፃነትና ሰማያዊ እድሉ አላቸው፡፡
የሀረና ልጆች በመድረኮች ፊት ዓይን የማይሞሉ ሆነው የተገኙት በመተካካት ፖሊሲ የቀድሞውን መሪ አቶ ገብሩ አስራትን ለዕጩነት ባለማቅረባቸው ነው፡፡ አስገራሚው ነገር በመድረክ አንፃር የተሻለ የውጭ ደጋፊ ያለው ሀረና ለክፉም ለደጉ በሚል የፋይናንስ ኮሚቴ ሃላፊነት እንደተሰጠው ተሰምቷል፡፡ በእርግጥ ዶክተር መረራም ከውጭ ድጋፍ ያለው ቢሆንም ድጋፉን በግል ከፈለገ ለኦፌኮ ካልሆነ ለመድረክ የማድረግ ፍላጎት የለውም፡፡ ለማነኛውም ፕሮፌሰሩ ሲመሩት ከነበሯቸው ድርጅቶች የተወሰኑትን “ምርጫ ቦርድ” ተብዬው ቢሰርዘውም በንግሰና በሚመስል መልኩ የመድረክን ሃላፊነት አለቅ ብለው ቀጥለው፡፡ ወይም ደግሞ አባላቱ በግድ ጭነውባቸዋል፡፡ በዚህ የሃላፊነት ዘመናቸው መቼም በቀጣይ ሊያድርጉት ያሰቡትን መርዓ ግብር በሆነ መልኩ ይፋ ያድርጋሉ ብለን እንጠብቃለን፡፡ በእኔ ግምት የመድረክ ሰዎች ይህን ኃለፊነት ይዘው መቆየት የፈለጉት በአንድ አጋጣሚ ኢህአዴግ ሸብረክ ቢል አለን!!! ለማለት ካልሆነ በስተቀር በተጠና ሰትራቴጂ ትግሉን መርተው መንግሰት ለመሆን አይደለም፡፡ እራሱን ለመንግሰትነት ያላዘጋጀ ፓርቲ/ሰብሰብ፣ ህዝቡን ለማድራጀት የማይተጋ ስብስብ ፋይዳው አይታየኝም፡፡
ሀገራዊ ሰብስብ ነኝ የሚል መድረክ ጠቅላላ ጉባዔ ሲያካሂድ በማህበራዊ ድረ ገጽ እንኳን የውይይት አጀንዳ አለመሆኑ አሳዝኖች ይህችን አካፈልኳቹ፤ እናንተስ ምን ታዘባችሁ፡፡ ከመድረክ ስብሰባ ተካፋዮች ዝርዝር እንጠብቃለን ….. ዘላለማዊ ስልጣን ….