Monday, October 31, 2016

የአሰቸኳይ ጊዜ አዋጅ ብርቅ ነው!!!




የአስቸኳይ ጊዜው ሴክፌታሪያት አዋጁ ግቡን መቷል ብለው መግለጫ መስጠታቸውን ሰምተናል፡፡ ይህ አዋጅ በአጭሩ ዝም ጭጭ አድርጎ ለመግዛት የተቀየሰ ዘዴ ነው ለምንል ሰዎች ዜጎች ዝም ጭጭ እንዲሉ ተደርጓል ማለት ነው፡፡ አሰገራሚው ነገር መስከረም 1967 “መለኮታዊ ንጉስ” የሚባሉትን አውርዶ አስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ደርግ ለምን አወጀ ብለው የሚከሱ፣ ሲከፋም በዚሁ ምክንያት ነው ጫካ የገባነው ብለው የሚፎክሮ የዲሞክራሲ አርበኞች በህይወት እያሉ አሁን “ዲሞክራሲያዊ” የተባለ የአስቸኳይ ጊዚ አዋጅ አውጀውልናል፡፡ ይህ አዋጅ በቴሌቪዥን ሲነበብ አደመጥኩት ክልከላዎቹ በሙሉ ድሮም በህግ የተፈቀዱ በተግባር ግን የማይቻሉ የነበሩ ናቸው፡፡ ለማረጋገጥ በጋዜጣ የወጣውን በጥሞና ደግሜ ደግሜ አነበብኩት ብዙዎች መመሪያው “ክልክል” ያላቸው ድሮም ወደፊትም ክልክል ናቸው፡፡ ለምሣሌ ንብረት ማውደም፣ ሰው መግደል፣ ያልተፈቀደ የሠራዊት ዩኒፎርም መልበስ፣ ህገወጥ ቅስቀሳዎች፣ ወዘተ በሙሉ መቼም ያልተፈቀዱ ወደፊትም የማይፈቀዱ ክልከላዎች ናቸው፡፡ ተፈቅደው ነገር ግን በተግባር ያልነበሩት የአደባባይ ሠልፍ እና ስብሰባ ዋነኛዎቹ ሲሆኑ፣ እጅግ ብዙዎቹ ክልከላዎች በሀገሪቱ በነበረው ህዝባዊ እንቅስቃሴ ወቅት ገዢዎችን አንጀት ያሳረሩ ድርጊቶቸን ዝርዝር ለማወቅ ከመጥቀማቸው ውጭ ፋያዳቸው አይታየኝም፡፡
በአዋጁ ውስጥ አስደናቂ ሊባሉ የሚችሉት ግን ማየት መስማት የሚከለክሉት የመጀመሪያዎቹ አንቀፅ ላይ የሰፈሩት ክልከላዎች ናቸው፡፡ መለኮታዊ ንጉስ አውርዶ እንዴት ሰልፍ ተከለከልን ያሉ ታጋዮች ለዚህ ነው ዓይናችን የጠፋው አካላችን የጎደለው ያሉ ሁሉ በተገኙበት ስብሰባ ይህን ማድረግ አስገራሚ ሆኖ በታሪክ ይመዘገባል፡፡
አዋጁን ተከትሎ በሚዲያ የሚተላለፉት ነገሮች ደግሞ የበለጠ አስደማሚ ናቸው፡፡ አንድ አንድ ነዋሪዎች በመባል የሚታወቁ አስተያየት ሰጪዎች አዋጁ ዘገየ፣ ለልማታችን ያስፈልገናል፣ ወዘተ የሚሉ አሰተያየቶች ሰጥተዋል፡፡ ማለት የፈለጉት ለእኛ ብቻ ሳይሆን ለአስተያየት ሰጪዎችም ሆነ አስተያየት ሰብሳቢዎች ግልፅ አይመሰለኝም፡፡ ሕገ መንግሰታዊ ስርዓት ይከበር እያልን፣ በአስቸኳይ አዋጅ መብታችን ተገድቦ ይኑር ማለት ትርጉሙ አይገባም፡፡ ግራ ገብቷቸው ግራ የሚያጋቡ የዚህ ዓይነት አስተያየት ሰጪዎችና ሰብሳቢዎች ያሉበት ሀገር ውስጠ ነው የምንገኘው፡፡
ተንታኞች ተብዬዎቹ ደግሞ አዋጁ ምንም አያስገርምም ሁሉም ሀገሮች የሚያደርጉት ነው በሚል ፈረንሳይን፣ ቱርክን፣ አሜሪካን የመሳሰሉ ሀገሮችን በመጥቀስ አስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ብርቅ ነው እንዴ!! እያሉን ይገኛሉ፡፡ ይህን አዋጅ ልዩ የሚያደርገው ደግሞ አዋጁ ሲዘጋጅ ልምድ የተወሰደበት ሀገር አለመጠቀሱ ነው፡፡ ይህን እኛም እንዳንጠረጥር አዋጁን ያዘጋጀው ማንም ይሁን ማን ደረጃውን ያልጠበቀ ዝርክርክ መሆኑን ግን አለመግለፅ ትዝብት ላይ ይጥላል፡፡ ይህን አዋጅ ሰመለከት ይህ ካቢኔ ተብዬው ሀገሪቱን የሚገዛው ቡድን ያለውን አቅም ለመረዳት ችያለሁ፡፡ በምንም ሁኔታ በአስቸኳይ ደረጃውን የጠበቀ መግለጫ ማውጣት እንደማይችል፤ ይህን ዓይነት የባለሞያ ስራ ሊያግዝ የሚችል የባለሞያ ስብስብ እንደሌለው ጭምር ተረድቻለሁ፡፡ አዋጁን መታወጁን ጠቅላይ ሚኒስትሩ የገለፁ ዕለት ዝርዝሩን እንደደረስን እናቀርባለን የሚለው የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን የተደጋገመ ማስታወቂያ የሰለቸው ልጄ ስብሰባውን በእንግሊዘኛ ነው እንዴ ያደረጉት? ብሎኛል:: ይህ በሙሉ የሚያሳየው አሰቸኳይ ጊዜ አዋጁ፣ ደንብ፣ መመሪያ፣ ፕሮግራም እየተባለ የሚወጡት በሙሉ ደረጃቸውን ያልጠበቁ መሆናቸው ነው፡፡ “ነበር” በሚል መፅኃፍ ውስጥ ደርጎች መግለጫ እንዴት ያወጡ እንደነበር የተፃፈውን ስመለከት በዚያ ቀውጢ ወቅት ከዚህም ከዚያ የተሰባሰቡ ወታደሮች የሰሩትን መስራት የማይችል ሃያ አምሰት ዓመት በስልጣን ላይ የቆየ መንግሰት እንዴት አሳዛኝ እንደሆነ አንባቢ ሊፈርድ ይችላል፡፡
በነገራችን ላይ ከቅዳሜ ጀምሮ የሚፀና አዋጅ እሁድ ለምን ታወጀ? ሰኞ ምክር ቤቱ ሰለሚከፈት በዝርዝር አዘጋጅተው ለምን ምክር ቤቱ ሲከፈት አላቀረቡትም? የሚሉና የመሳሰሉትን ጥያቄዎች ማንሳት ይቻላል፡፡ በእኔ እምነት ከቅዳሜ ጀምሮ የፀና ይሆናል የሚል ህገወጥ አካሄድ የመረጡት ምክር ቤት በሌለበት የታወጀ በማሰመሰል፣ በአርባ ስምንት ሰዓት ውስጥ ለምክር ቤት አቅርቡ የሚለውን ህገ መንግሰታዊ ድንጋጌ ለመጣስ እንደሆነ ግልፅ ነው፡፡ ይህን በማድረግ በሁለተኛው አማራጭ አሰራ አምስት ቀን ማግኘት የቻሉ ሲሆን ባገኙት አስራ አምስት ቀን የዝግጅት ጊዜ ውስጥም የሚሰሩትን ሰራ ጥራት ለማስጠበቅ አልቻሉም፡፡
አዋጁ ዋና ዓላማው አስፈራርቶ መግዛት ስለሆነ ከሞላ ጎደል ሊሳካለት ይችላል የሚባለው ለመፍራት በተዘጋጁት ላይ ብቻ ነው፡፡ ነፃነት ወይም ሞት ብሎ ለተነሳ ግን ይህ አዋጅ ምን ይቀንሰበታል? ብዬ ጠይቄ መልሱ ምንም የሚል ነው የሆነብኝ፡፡ ለማነኛውም ይህ አሰቸኳይ ጊዜ አዋጅ ህወሃት/ኢህአዴግ በውስጡ እፈጥራለሁ ላለው “ጥልቅ ተሃድሶ”  ይሁን “ፈርሶ መሰራት” በአባላቱ መካከል ሊፈጠር ለሚችል ቀውስ መቆጣጠሪያ ለማድረግ ነው በሚል በተሰፋ ለመሞላት ለሚፈልጉት ተሰፋ ከሰጣቸውም ተሳስቼም ቢሆን ይህ ተሰፋ ዕውን ቢሆን ደስ ይለኛል፡፡
መልካም የአስቸኳይ ጊዜ ይሁንልን!!!!

ለኢትዮጵያ ፖለቲካ መሪነት ተቃዋሚ መሆን ብቻ አይበቃም!!!




በሀገሩ ጉዳይ  እገሌ ያገባዋል እገሌ አያገባውም ማለት ተገቢ ነው ብዬ አላምንም፡፡ ነገር ግን መሃንዲሰ ሀኪም መሆን እንደሌለበት ሁሉ የሚያገባን በምን በምን ጉዳይ መሆኑ ተለይቶ መታወቅ እና የበለጠ ውጤታማ የምንሆንበትን መምረጥ ተገቢ ይመስለኛል፡፡ በኢትዮጵያ ሀገራችን ፖለቲካ ውስጥ ሁሉም ያገባዋል ነገር ግን በምን ደረጃ ሃላፊነት ሊወስድ ይችላል በሚባለው ጉዳይ ግን ዝርዝር መታወቅ ይኖርበታል፡፡ እገሌ ማን ነው? ተብሎ መጠየቅ ይኖርበታል፡፡ ይህ መጠይቅ ደግሞ በተለይ መቅረብ ያለበት በአንድ ቡድን ውስጥ ሆኖ በአንድ ማዕቀፍ ለመስራት ለሚፈልግ ሰው የግድ ነው፡፡ ሀገራችን ኢትዮጵያ ከፍተኛ የፖለቲካ አመራር ችግር አለባት፡፡ ተቃዋሚ መሆን ብቻ ለፖለቲካ መሪነት አያበቃም፡፡ ብቃት ያለው የፖለቲካ መሪ እንዳይኖረን ካደረጉት ነገሮች ዋነኛው እስከ ዛሬ በፖለቲካ ፓርቲ ውስጥ ለመሳተፍ እራሳቸውን ያዘጋጁ ሁሉ ከስሜት አልፈው የፖለቲካ አመራር ማፍራት ትክክለኛ የፖለቲካ ፓርቲ ተግባር ነው ብለው አምነው ያለማወቃቸው ነው፡፡ አሁንም ቢሆን ይህ ትልቅ ኃላፊነት ለፖለቲካ ፓርቲዎች የተተወ እንደሆነ የሚረዱ አይመስለኝም፡፡ ይልቁንም የፖለቲካ ፓርቲዎች ሰልፍ መጥራት፣ መግለጫ ማውጣት እና ከፍ ሲል ጋዜጣ ማሳተም ትልቁ የፓርቲ ስራ ይመስላቸዋል፡፡ የሚገርመው አንዳንዶቹ መደበኛ ትምህርታቸውን እንኳን ፓርቲ እንደያስተምራቸው የሚፈልጉ ናቸው፡፡ ለዛሬው መደበኛ ትምህርታቸውን ፓርቲ እንዲያስተምራቸው የሚፈልጉትን ምስኪኖች ሳይሆኑ እራሳቸውን የፖለቲካ መሪ አድርገው ያስቀመጡ ልሂቃን ላይ ብቻ ማተኮር ነው የምፈልገው፡፡
ሁሉም እንደሚረዳው የኢትዮጵያ ፖለቲካ ፓርቲ ምስረታ በእነ ኢህአፓ እና መኢሶን የተጀመረ ሲሆን ከዚያ በኋላ ብዙ ፓርቲዎች በወቅቱ የነበረውን የስልጣን ክፍተት ለመሙላት መደራጀት በሚል ሲደራጁ እንደ ነበር ይታወሳል፡፡ የዚህ ታሪክ ባለቤቶች አሁንም በኢትዮጵያ ፖለቲካ ውስጥ ዋናዎቹ ተዋናዮች ናቸው፡፡ ሲደክማቸው እያረፉ፣ መልካም አጋጣሚ የተገኘ ሲመስላቸው ብቅ እያሉ ዛሬ ደርሰናል፡፡ በቅርቡ ትዝታችን ሁሉንም ኢትዮጵያዊ ከሀገር ውስጥም ሆነ ከውጭ ከፍተኛ ንቅናቄ የፈጠረው የቅንጅት መንፈስ ነው፡፡ ይህ መንፈስ ምን ዓይነት እንደነበር ለታሪክ እንዲተው የምንፈልግ ብንኖርም አሁንም የዚህ መንፈስ ተከታዮች አሉ፡፡ በኢትዮጵያ የፖለቲካ እንቅስቀሴ ውስጥ ከኢህአፓ መንፈስ ቀጥሎ ከፍተኛ ህዝባዊ ንቅናቄ የፈጠረ መንፈስ የቅንጅት መንፈስ ነው ቢባል የሚቀየም አይኖርም፡፡
ቅንጅትን ከሁሉም በላይ በህዝቡ ዘንድ ተደማጭነት እንዲኖረው ካደረጉት ነገሮች አንዱ ህዝቡ በግንባር የሚያያቸው መሪዎች ከጥቂቶቹ በስተቀር ፕሮፌሰር፣ ዶክተር፣ ኢንጅነር፣ ወዘተ በሚባሉ ማዕረጎች የሚጠሩ ነበሩ፡፡ የተማረ ይግደለኝ የሚባለው ዓይነት መሆኑ ነው፡፡ ይህ መንፈስ ታዲያ ዛሬም የሞተ አልመሰለኝም፡፡ ኢንጀነር የሚል ማዕረግ ከዩኒቨርሲቲ ውጭ በእለት ከእለት ኑሮ መጠሪያ ሲሆን ይህ ዘመን የመጀመሪያ ይመስለኛል፡፡ ይህን ፉርሽ ነገር “መንግሰት” ተብዬውም ተከትሎ “ኢንጅነር” እገሌ እያለ መጥራት ሙያ አድርጎታል፡፡ የተማራ ይግደለኝ መንፈስ አልሞተም ያልኩበት ምክንያት ዛሬም ከዚህ በፊት በተቃዋሚ ፓርቲ ፖለቲካ አፍራሽ ሚና የነበራቸው ሁሉ ድንገት ክፍተት ከተገኘ ብለው ጥፋታቸውን ለማረም ሳይሆን ጥፋታቸውን አድሰው ለመድገም እየተንቀሳቀሱ እንደሆነ በመስማቴ ነው፡፡
በሀገራችን በሚፈጠር ችግር ከእድሜያቸውም አንፃር ሸምግልና የሚገባቸው ሁሉ ዛሬም በፓርቲ ፖለቲካ ውስጥ ሆነው እራሳቸውን ለስልጣን ሲያጩ ማየት የእውነት ያማል፡፡ ያለፈውን ፓርቲያችሁን ምን አደረጋችሁት? የሰባሰባችሁትን ወጣት ምን በላው? ወዘተ ብሎ የሚጠይቃቸው ያለ አይመስለኝም፡፡ ይልቁንም እነርሱ ከሰሻ እና ፈራጅ ሆነው መድረኩን የክፋታቸውን ጥላ አጥልተውበታል፡፡
በኢትዮጵያ ፖለቲካ ከአሁን በኋላ የከዚህ ቀደም የፖለቲካ ሂሳቡን ሳያወራርድ ኢንጂነር፣ ዶክተር የሚል ማዕረግ ይዘው ለጡረታ ጊዜ የሚንቀሳቀሱትን አቤት የሚላቸው ካገኙ ይገርመኛል፡፡ የኢህአዴግ መተካካት ምኞት ሆኖ ቢቀርም፣ በተቃዋሚ ጎራ መሪዎች መተካት ባይችሉም በራሳቸው ተነሳሸነት ሃላፊነት ለመውሰድ ለሚመጣ አዲስ ኃይል ቦታ መልቀቅ የግድ ነው፡፡ ቦታ ልቀቁ ሲባል ስልጣኑን ብቻ አይደለም፣ ትግሉንም ጭምር ነው፡፡ እሰከ ዛሬ ላደረጉት ሙከራ ክብር በመስጠት የነበራቸውን ረጅም የትግል ታሪክ በመፅኃፍ መልክ ለትውልድ በታሪክ መልክ በታማኝነት ማሰቀመጥ ይጠበቅባቸዋል፡፡ ይህ ለራሳቸውም ቢሆን ምን ያህል ታማኝ እንደሆኑ ሌላው እንዲረዳቸው እድል ይስጣል፡፡
ከኢትዮጵያ ፖለቲካ ጡረታ መውጣት ካለባቸው ሰዎች አንዱ እና ዋነኛው ግዛቸው ሸፈራው (ኢ/ር) ነው፡፡ በፌስ ቡክ ላይ “በቅንጅት መንፈስ በሚል ፓርቲ ለመመሰረት መንገድ ላይ ያለው ግዛቸው ለአንድነት መፍረስ ያሰቀመጠውን የመሰረት ድንጋይ እረስቶት ፓርቲ በማፍረስ ኢህድግን ብቻ ይከሳል፡፡ እሱ ቢረሳው እኛ ግን አንረሳውም እና ……. ከአሁን በኋላ የፓርቲ ፖለቲካ ቢቀርበት ምከሩት” ብዬ ለጥፌ ነበር፡፡ ፌስ ቡክ ላይ ባያየውም በደንብ እንደሰማው መረጃው አለኝ፡፡ ግዛቸው በቅንጅት ጊዜ የተጫወታቸው ሚናዎች በወቅቱ በነበረበት ጊዜ የሚገመገም ቢሆንም አንድነትን በመስራችነት እና በመሪነት ሲያገለግል ምን ሰርቶ ምን አድርጎ ፓርቲውን እንዳፈረሰ ማስረዳት ይኖርበታል፡፡ ይህን በቅጡ ሳይወጣ ዛሬም የፖለቲካ ፓርቲ መስርቶ መሪ ሊሆን ያሰባል፡፡ የሚገርመው “እኔ ከሞትኩ ሰርዶ አይብቀል” እንዳለቸው አህያ አንድነትን በመሪነት ከሚያፈርስ ሚዲያ ጋር ቀርቦ እራሱን ሲከስ የነበረ ጀግና፣ በአንድነት ንቅናቄ ላይ ቀዝቃዛ ውሃ መቸለሱን ረስቶ ዛሬም ፖለቲካ መጫወት ያምረዋል፡፡ ግዛቸው ፓርቲ ካማረው ከትዕግሰቱ አወሉ ጋር ተሰማምቶ መሰራት ነው ያለበት፡፡ ይህን ለማድረግ የሬዲዮ ፋናው ብሩክ ሊረዳው እንደሚችል እገምታለሁ፡፡ ምክንያቱም የትዕግሰቱ አወሉ ቡድን ከምርጫ ቦርድ ድጋፍ ያገኘው “ግዛቸው ከስልጣን የተነሳው በህጋዊ መንገድ አይደለም” የሚለው መከራከሪያ አቅርቦ ነው፡፡ ግዛቸው “በፈቃዴ ነው የለቀቅሁት” ብሎ ቃሉን ለመስጠት ዳተኛ መሆኑ ብቻ ሳይሆን “በሀሰት ከኃላፊነቴ እንደለቅ የተገደድኩት ፋይናንስ በባንክ ይሁን ስላልኩ ነው” ብሎ ራሱን ጭምር በሬዲዮ ፋና ቀርቦ ከሶዋል፡፡ አንድነት ፓርቲ ከማንም ፓርቲ በተሻለ የፋይናንስ ስርዓት እንዳለው እያወቀ ቢሆንም ክፋቱን እወነት ሊያሸንፈው አልቻለም፡፡ ከዚህ ዓይነት ክፉ ሰው ጋር የፖለቲካ ማህበር አይደለም እንዴት ሌላ ማህበራዊ ኑሮ ይታሰባል፡፡ ያለፈውንም ይቅር ይበለን!!
ከግዛቸው ጋር የፓርቲ ምስረታ ጥንስስ ላይ ያለ ሁሉ /ለጊዜው ስም አልጠራም/ በዝርዝር እራሳችሁን ማየት ይኖርባችኋል፡፡ ከደርግ የማይሻል የለም ተብሎ የመጣው ህወሃት/ኢህአዴግ ደርግን በአፈና አስንቆታል፡፡ እናንተም ከዚህ መሻላችሁን በእውነት ቀድማችሁ አስመስክሩ፡፡ ሀገራችን የወላድ መሃን የሆነችበት ወቅት ላይ እንገኛለን እና በጥንካሬ መሪ ለመፍጠር አስበን መስራት እንዳለብን ማወቅ ይኖርብናል፡፡
ቸር ይግጠመን!!


Monday, October 24, 2016

የፕሬዝዳንት ሙላቱ ሪፖርት እና የፋና ውይይት……..



ታሪከኛው የ2007 ምርጫ ተጠናቆ ገዢው ፓርቲ `መንግሰት` መስርቻለሁ ባለ ማግስት በተጀመረ ህዝባዊ እንቅስቃሴ ሲናወጥ የከረመው መንግስት የሁለተኛ ዓመት ስራውን ለመጀመር ማሟሻ ንግግር የሚያደርጉት ፕሬዝዳንት ሙላቱ ተሾመ መሰከረም 30/2009 ንግግር አድርገዋል፡፡ ተከትሎም የግንባሩ ልሣን ፋና ብሮድካሰቲንግ ማስመሰያ ውይይት አዘጋጅቷል፡፡ ከፕሬዝዳንቱ ሪፖርት እና ከፋና ውይይት ምን እንጠብቅ የሚል ጥያቄ ለራሴ አቅርቤ ትዝብቴን አሰቀምጫለሁ፡፡ የፕሬዝዳንቱ የመክፈቻ ንግግር እና የፋና የውይየትት ፕሮግራም በተለመደው መስመር ማዘናጋት እና አሁንም ገዢው ፓርቲ ህወሃት/ኢህአዴግ መሆኑን አረጋግጦ ማለፍ ነው፡፡ የተወሰኑ ነጥቦችን አንስተን ለመመልከት እንሞክር፡፡
እንደ መነሻም በሰሞኑ ለነበረው የህዝባዊ እንቅስቃሴ ሞተር ለነበረው ወጣት ትውልድ ማዘናጊያ የሚሆን 10 ቢሊዮን ብር መመደቡን አብሰረዋል የዚህ ዓመት በጀት ጉዳይ በሰኔ 30 መጠናቀቁን የሚያስታውስ ሰው ያለ አልመሰላቸውም፡፡ ቀደም ሲል የኦሮሚያ ፕሬዝዳንት የነበሩት አቶ ሙክታርም ለኦሮሚያ ቀወስ 3 ቢሊዮን በጀት ዓመቱ ሊጠናቀቅ ሶሰት ወር ሲቀረው ለወጣቱ ሰራ ፈጠራ መድነበናል ብለው ነበር፡፡ ይህ በጀት የኦሮሚያን ችግርም አላበረደም አቶ ሙክታርንም በስልጣን ሊያቆይ አልቻለም፡፡ 10 ቢሊዮን ብር በጀት የወጣቱን ጥያቄ ለመመለስ የወሰዱትን እርምጃ በአስገራሚነቱ ተወዳዳሪ ሊኖረው አይችልም፡፡ ምን ማለት ነው “ወያኔ ይውደም!!” ብሎ መፈክር ለሚያሰማ ወጣት መልሱ “አርፈህ ወደ ስራ ግባ!!” እንደማለት ነው፡፡ ወጣቱ የጠየቀው የስርዓት ለውጥ ነው፡፡ የስርዓት ለውጥ የሚያመጣውን ማነኛውንም እድል የስራ ዕድልን ጨምሮ ለማየት ይፈልጋል፡፡ 25 ዓመት ተሞክሮ ያልተሳካለት አብዮታዊ ዲሞክራሲ ትንተና መልስ እንደማይሰጠው ነው ወጣቱ የተናገረው፡፡ ለዚህ መልስ መስጫው መንገድ ተዘዋዋሪ የብድር ገንዘብ ተዘጋጅቶዋል የሚል ፌዝ ያዘለ መልስ ያስቃል፡፡ ህወሃት/ኢህአዴግ ጉዳዩን የምር እንዳልያዙት የሚያስታውቀው በቅርቡ ሬዲዮ ፋና በጠራው ስብሰባ ላይ የተጋበዙት የወጣቶች ተወካይ የኢህአዴግ አደረጃጀት ወጣት ናቸው፡፡ እነዚህ ወጣቶች ሰልፍ አልወጡም ጥያቄም አላቀረቡም፡፡ ይልቁንም ጥያቄ ያነሱትን ወጣቶች ፀረ-ሰላም እያሉ የሚከሱ ቡድን ተወካይ ናቸው፡፡ ምን አልባትም የተመደበው በጀት ለዚህ ቡድን ሊያገለግል ይችላል፡፡ በዚህ ጉዳይ ላይ ከአንድ ጓደኛዬ ጋር ስናወራ ይህ የስርዓቱ ትክክለኛ መገለጫ ነው፣ ችግሮች የሚፈቱት በገንዘብ ይመስላቸዋል፡፡ ሙሰኛ ስርዓት ህዝብንም ሙሰኛ አድርጎ በማየት በገንዘብ ለመደለል ይሞክራል ነው ያለኝ፡፡ እኔም ተሰማምቼበታለሁ፡፡ ገንዘብ ካለ በሰማይ መንገድ አለ ከሚል የዘራፊዎች ቡድን ከዚህ የተሻለ የመፍትሔ አቅጣጫ አይገኝም፡፡ የወጣቱ ጥያቄ የስርዓት ለውጥ ነው፡፡ መልሱም እንዴት በተረጋጋ ሁኔታ የስርዓት ለውጥ እናምጣ የሚለው ነው፡፡ መልሱን ከወጣቱ ጋር በግልጽ መወያየት ነው፡፡ ወጣቱ ተወካይ የለውም እንዳትሉን ከዚህ በፊት እንደዳልኩት እኔ ዞን ዘጠኝ የሚባሉትን ወጣቶች ወክያለሁ ……. ሌላም መጨመር ይቻላል፡፡ ከፎረም ውጭ ……
በፕሬዝዳንቱ ንግግር ውስጥ ትኩረት አግኝቶ በተለያየ መንገድም ትኩረት የሳባው የምርጫ ህግ ማሻሻል የሚመለከተው ነው፡፡ የምርጫ ህግ ማሻሻል ሲባል ብዙ ሰው “ህገ መንግሰት ማሻሻል” መሆኑንም ዘንግቶታል፡፡ ከብዙዎቹ አንዱ ፕሬዝዳንት ሙላቱ ናቸው፡፡ የኢትዮጵያ ህገ መንግሰት አንቀፅ 54/2 በአንድ ምርጫ ክልል አብላጫ ድምፅ ያገኘ ያሸንፋል በሚለው መስረት ይመረጣል ነው የሚለው፡፡ ሰለዚህ ሌላ የምርጫ ስርዓት ማድረግ አይቻልም፡፡ ህገ መንግሰቱ ሳይሻሻል ማለት ነው፡፡ ሌላው ህወሃት/ኢህአዴግ ማስተላለፍ የፈለገውን መልዕክት ብዙ ሰው የተቀበለው ይመስለኛል፡፡ ይህ መልዕክት “ህውሃት/ኢህአዴግ እና አጋሮች አሸንፈዋል” የሚለው ነው፡፡  ይህ ማለት ግን “ሁሉም ሰው መርጦናል ማለት አይደለም” የሚለውን መልዕክት ነው፡፡ ይህ ደግሞ ምርጫው ነፃ፣ ፍትሃዊና ታማኝነት ነበረው ለማለት ነው፡፡ በኢትዮጵያ ውስጥ የሚያስፈልገው ነፃ፣ ፍትሃዊ፣ ግልፅነት ያለው ምርጫ እንጂ የምርጫ ስርዓት ለውጥ አይደለም፡፡ የምርጫ ስርዓት ለውጥ የሚጠቅመው በቢሮ ቁጭ ብለው የፓርቲ ሰርተፊኬት እና ማህተም በፌስታል ይዘው የብሄር ተወካይ ነን በሚል የውክልና ስልጣን ለማግኘት ለሚፈልጉ ጥቂት ግለሰቦች ነው፡፡ አሁን ባለው ምርጫ ስርዓት ኢትዮጵያ ውስጥ የብዙሃን ፓርቲ ስርዓትን ማረጋገጥ ይቻላል፡፡ ከዚህ የተለይ የምርጫ ህግ የሚመክሩን የውጭ አማካሪዎችም ሆኑ ኢትዮጵያዊያን ልሂቃን በኢህአዴግ ምርጫ አሸንፊያለሁ ችግሩ የምርጫ ስርዓቱ ነው በሚለው መታለላቸውን ማስታወስ ይኖርብኛል፡፡ በመደራጅት መብት ስም ማንም ሱሰኛ የፓርቲ ሰርተፊኬት ይዞ ዕጩ የሀገር መሪ ቡድን ነኝ ሲል ዝም ሊባል አይገባም፡፡ በምርጫ ስርዓት ማሻሻል ሰምም የህዝብ ውክልና ማገኘት ዕድል ሊመቻች አይገባም፡፡
በኢትዮጵያ ሀገራችን ውይይት አጅግ በጣም አስፈላጊ እና በእጅጉ የጎደለን የሰልጣኔ መንገድ እንደሆነ ይስማኛል፡፡ ውይይት ሲባል ደግሞ ገዢዎች ንግግር ሲያደርጉ የሚያዳምጣቸውን የፎረም ተወካዮች ሰብሰቦ ሲሞጋገሱ መዋያም መድረክ አይደለም፡፡ ውይይት ሲባል ሃሳብ ተለዋውጦ የሃሳብ ሽግሽግ ለማድረግ መዘጋጀትንም ይጠይቀል፡፡ የሃሳብ ሽግሽግ የሚደረግበት የውይይት መድረክ ሀገራችን በእጅጉ ያስፈጋታል፡፡ በሰብሰባ ውስጥ የህዝብ ሰሜት የሚኮረክሩ ንግግሮች ከተደረጉ በኋላ ሹሞች ያሻቸውን በማጠቃለያነት ተናግረው፣ ሲፈልጉም ዘለፋ አክለውበት ምን ታመጣላችሁ፣ ከቻላችሁ ተደራጅታችሁ እራሳቸሁን አጠናክራችሁ መጥታችሁ ግጠሙን በሚል ፉከራ የሚጠናቀቅ መሆን የለበትም፡፡ ይህ ዓይነቱ መድረክ የውይይት ሳይሆን የፉከራና ቀረርቶ ነው ሊባል የሚችለው፡፡ ተጠናክሮ መጥቶ ለመጋጠም የሕወሃት/ኢህአዴግ ምክር አስፈላጊ አይመስለኝም፡፡ መጋጠሚያ ቦታውን እና የመጋጠሚያ ህጉን ማስተካክል ነው፡፡ የብረት ቦክስ ይዞ ሜዳ እየገቡ ባዶ እጅ ያለን ተጋጣሚ ማድማትና ማቁሰል ጉብዝና ሳይሆን ህገወጥ መሆን እና ውንብድና ነው፡፡
ሌላው የሪፖርቱ አስገራሚ ነጥብ የዜጎች መፈናቀል የሚመለከተው ነው፡፡ ዜጎችን ማፈናቀሉ ትክክል እንዳልሆነ ተገንዝቢያለሁ ያለ የሚመስለው ገዢው ፓርቲና መንግሰት በተዘዋዋሪ ማፈናቀል እቀጥላለሁ ነገር ግን የሚሰጠውን ካሳ ከጊዜው የዋጋ ንረት፣ የምርት ዋጋ እና ምርታማነት እድገት ጋር ተገናዝቦ ይሻሻላል የሚል መግለጫ እየሰጠ ይገኛል፡፡ አታፈናቅሉኝ ያለን ዜጋ ዋጋ ጨምረን እናፈናቅልህ እያሉት ነው፡፡ ህውሃት/ኢህአዴግ ችግሩን ከመስረቱ መፍታት ሳይሆን አሁንም ዙሪያ ጥምጥም መሄድ መርጠዋል፡፡ የህዝቡ ጥያቄ የመሬት ባለቤትነት ጥያቄ መልስ ያግኝ ነው፡፡ የያዘውን መሬት ለልማት ሲባል እንዴት እና በምን ዓይነት ሁኔታ እንደሚለቅ በኋላ የሚደረስበት የውይይት ነጥብ ነው፡፡ ይህ ጉዳይ እንደ ምርጫ ሰርዓቱ ህገ መንግሰታዊ ጉዳይ ነው፡፡ ገዢው ፓርተ የመሬት ነገር በመቃብሬ የሚለውን ነገር ወደ ጎን ትቶ መሬት ለባለመሬቱ ማስተላለፍ ይኖርበታል፡፡ ቀሪውን ስንደርስ የምንጫወታው ይሆናል …… ድልድዩን ሰንደርስ እንሻገራለን እንደሚባለው መሆኑ ነው፡፡
የህወሃት/ኢህአዴግ ጥልቅ ተሃድሶ ፍልስፍና ፈርሶ እስከ መሰራት እንደማይደርስ አቶ አባይ ፀሃዬ ነግረውናል ባይነግሩንም የሚታወቅ ሀቅ ነው፡፡ ፈረሰው ይሁን፣ በአሸዋ ላይ ፓርቲያቸውን መስራት የእነርሱ ምርጫ ነው፣ ይህን ምርጫቸውን የምናከብርላቸው ቢሆንም አሁንም የኢትዮጵያን ህዝብ በካበኔ ሹም ሽር ለመሸንገል ተጨፈኑ እናሞኛችሁ ብሎ ማሰብ መፍትሄ ፍለጋ እና ችግሩን መረዳት ላይ እጅግ ልዮነት እንዳለን ማሳያ ነው፡፡ የኢህአዴግ ካቢኔ ማንንም ይዞ ቢመጣ መስመሩን እስከ አላስተካከለ እና በመድበለ ፓርቲ ስርዓት ውስጥ ቁጥጥር የሚደረግበት ካልሆነ ትርጉም የሌለው ድካም ነው፡፡ ምን አልባትም በራሳቸው ስር ሌላ አኩራፊ ከመጨመር ውጭ የተለየ ፋይዳ አይኖረውም፡፡ አቶ ጁነዲን ሳዶን የመሰለ የአብዮታዊ ዲሞክራሲ ፈላስፋ (በሀገር ውስጥ እያለ) አሁን በግልፅ ምንም ስልጣን አልነበረኝም ስልጣኑ የህወሃት ነው ማለቱን ማስታወስ ያስፈልጋል፡፡ ተራው የማን ነው? መጠበቅ ነው፡፡
በመጨረሻ በቅርቡ ይወጣል የሚባለውን “የኦሮሚያን ልዩ ጥቅም በአዲስ አበባ” የሚመለከት አዋጅ ነው፡፡ ይህ አዋጅ ምን ያህል የተደከመበት ቢሆን ህወሃት/ኢህአዴግ በለመደው መልኩ አዋጅ አድርጎ ካወጣ በኃላ ንትርክ የሚፈጥር እንደሚሆን ይጠበቃል፡፡ ቢያንስ በቅርቡ ይወጣል ሲባል እንኳን ለህዝብ ለውይይት የሚረዱ አንኳር ነጥቦችን ማጋራት አልቻሉም፡፡ ጉዳዮንም የኦሮሚያ ክልል ብቻ በማድረግ የአዲስ አበባ ነዋሪ ግብር ከፋይ ምንም መረጃ እንዲኖረው እየተደረገ አይደለም፡፡ ሰለዚህ ይህ አዋጅ ምን ይዞ ይመጣል ወደፊት የምናየው ነው፡፡ ፕሬዝዳንቱ ግን በቅርቡ ይታወጃል ብለዋል ….. ቅርብ መቼ ነው? በነገራቸን ላይ ሀረሪ ክልል በሚባለው ውስጥስ ቢሆን ኦሮሚያ ልዩ ጥቅም አያስፈልጋትም ትላላችሁ፡፡ ወይም ክልሉ ለኦሮሚያ ተሰጥቶ የሀረሪ ልዩ ጥቅም የሚባል ነገር በሃሳባችሁ መጥቶ አያውቅም፡፡ እጅግ በቁጥር አነስተኛ የሆኑ ሀረሪዎች ሁልጊዜ አሸናፊ የሚሆኑበት ምርጫ ኢትዮጵያችን ውስጥ ላለው አሳፋሪ የምርጫ አፈፃፀም ጉልዕ ማሳያ ነው፡፡ ሰለምርጫ ከላይ ያነሳሁትን ነጥብ እዚህም ማስታወስ የግድ ይላል፡፡ አዲስ አበባ መቼ ነው በነዋሪዎች ቀጥተኛ ምርጫ ከንቲባ የምትመርጠው የሚል ጥያቄ አሁንም አለኝ፡፡
ይህ ፅሁፍ በምንም መልኩ ከአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ጋር እንደማይጋጭ እራሴን ሳንሱር አድርጌ ነው የፃፍኩት፣ቢጋጭም ይጋጭ ብዬ ለጥፌዋለሁ፡፡
ቸር ይግጠመን!!!!

Monday, September 19, 2016

አቶ ጌታቸው ረዳ የሸገር ካፌ ቆይታ …..



የኮሚኒኬሸን ሚኒሰትሩ አቶ ጌታቸው ረዳ በሸገር ካፌ ላይ ቀርበው ከእሸቴ አሰፋ ለቀረበላቸው ጥያቄ መልስ ሰጥተዋል፡፡ ጥያቄዎቹ የህዝብ መልሶቹ ግን የተለመዱ የኢህአዴግ ናቸው፡፡ ያሰገረሙኝን ብቻ ላካፍላችሁ፡፡
አቶ ጌታቸው ያለምንም ይሉኝታ ዳግም ተሃድሶ የታችኛውን ክፍል እንደሚጠራርግ ነግረውናል፡፡ ምክንያቱም መመረያ በሚል ሰበብ ህዝብ አያጉላሉ ያሉት እነርሱ በመሆናቸው የሚል አስቂኝ ሰበብ ሰጥተዋል፡፡ እግረ መንገዳቸውም ሚኒስትሮች እና ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከህግ በላይ እንዲሆኑም ፍላጎት አሳይተዋል፡፡ ሚኒስትሩ/ጠቅላይ ሚኒስተሩ ሲያዙ መመሪያ አይፈቅድም ይላሉ፡፡ እኔ እስከ ዛሬ ባለኝ ልምድ የመመሪያው ባለቤቶች እነዚያው ሚኒስትሮች መስለውኝ፡፡ መቼም እዚህ ሀገር ጉድ ሳይሰማ መሰከረም ስለማይጠባ በየመስሪያ ቤቱ ያሉ ኤክስፐርቶች መመሪያ የማውጣት ስልጣን ተሰጥቶ ከሆነ ልክ አይደሉም ሰልጣናቸውን ያለ አግባብ ሚኒሰትሮች እንዲሁም ጠቅላይ ሚኒስትሩን ለማሳቀቅ ሊጠቀሙበት ባልተገባ ነበር፡፡ ይህ ካልሆነ ግን እርሰ በእርሱ የሚጋጭ መመሪያ ያወጣ ሚኒስትር ያወጣውን መመሪያ ኤክስፐርት ቢያስታውሰው ክፋቱ አልታየኝም እና አቶ ጌታቸው በድጋሚ ቢያብራሩልን፡፡ በነገራቸን ላይ መመሪያ ደንብ የሚያከብሩና የሚያስከብሩ ሚኒስትሮች እና ጠቅላይ ሚኒስትር ነው የሚያስፈልገን፡፡ መቼም አቶ ሀይለማሪያም ደሳለኝን ያዘዙት እንቢ ያለ ኤክስፐርት ማን እንደሆነ ማወቅ ጥሩ ነበር፡፡ ይህ ኤክስፐርት አቶ መለስንም እንዲህ ይል ነበር? የሚል ጥያቄም ያጭራል፡፡ አቶ መለስ እንዲህ ብለዋል እየተባለ ባልወጣ መመሪያ እንተዳደር እንደነበር የሚዘነጋ አይደለም፡፡ ይህ ጉዳይ እኮ የቅርብ ጊዜ ነው፡፡
ሌላው አቶ ጌታቸው ረዳ ካለፈው ስህተታቸው መማር ያልቻሉት በሚዲያ በሚተላለፍ ውይይት ቃላት መረጣ አለመቻላቸው ወይም ፍላጎት ያለማሳየታቸው ነው፡፡ ጭራቅ እና አጋንንት መውደዳቸው እንደተጠበቀ ሆኖ ማለቴ ነው፡፡ ለምሳሌ “ህዝብ አሁን ካሉት 28 ካቢኔ ሚኒስትሮች ስንቱ ቢታሰር፣ ስንቱ ቢሰቀል እንደሚረካ አይገባኝም” ብለዋል፡፡ እኛ ይስቀሉ አላልንም፡፡ ነገር ግን እሰከሚገባኝ ድረስ ያለ አግባብ ከተሰቀሉበት ስልጣን ይውረዱ፡፡ ወርደው ባለጉዳይ ሆነው ይህችን ሀገር ይመልከቷት ነው የተባለው፡፡ እኔ እስከሚገባኝ ኢህአዴግ እስከ አሁን በፍፁም እንዲገባው የማይፈልገው ተጠያቂነት በውክልና አይተላለፍም ውክልና ለበታች ሰራተኛ ሲሰጥ ስራውን/ሃላፊነቱን ብቻ ነው፡፡ የተወከለው ሰራተኛ ካጠፋ የሚጠየቀው የወከለው ሃላፊ ነው፡፡ ይህ ሀሁ እንዲት ለሃያ አምስት ዓመት መረዳት ያቅታል፡፡ መቼም የጫካውን ዘመን እንርሳው ብዬ ነው፡፡
እሸቴ አሰፋ በግልፅ ያቀረበላቸው አንዱ ጥያቄ የአንድ ብሔር የበላይነት/የህወሃት የበላይነት አለ የሚል ቅሬታ አለ የሚል ነው፡፡ ይህ ጉዳይ በግምገማቸው ላይ ተነስቶ በስፋት ውይይት መደረጉ አቶ ጌታቸው ነግረውናል፡፡ የተነሳው የአንድ ብሔር /የትግራይ/ የበላይነት አለ የሚለው አንድ በጎ ነገር ሲሆን የተደረሰበት ነገርም ጥሩ ነው፡፡ አንዱን ኪራይ ስብሳቢ በሌላ ብሔር ኪራይ ስብሳቢ መተካት አይደለም፡፡ ህዝቡ እያለ ያለው ህውሃት ወርዶ በብአዴን ወይም በኦህዴድ ይተካ አይደለም፡፡ ሁላችሁም ውረዱ ነው፡፡ አሁን ያለው የህወሃት የበላይነት እንዲነግስ ያደረጉ አሁን ጥያቄያቸው በተራችን እኛ እንሁን ከመሆን ሊዘል አይችልም፡፡ የእኛ ጥያቄ ግን የዚህ ዓይነት ስርዓት አያስፈልገንም የሚል ነው፡፡
ከአንድ ብሔር የበላይነት ጋር ተያይዞ የተነሳው አንድ ቁልፍ ነገር የቁልፍ ቦታዎች ነገር ነው፡፡ ቁልፍ የሚባሉት ቦታዎች ለምን ቁልፍ ሆኑ? ሲባል ኪራይ ማደያ ሰለሆኑ ነው:: ምርጥ መልስ ነው፡፡ ያሳዝናል፡፡ አንድ የመንግሰት ተቋም ሃላፊ መሆን የራስን ግሳንግስ መሰብሰቢያ ስርዓት ከመገንባት የከፋ ውርደት ከየት ይመጣል፡፡ በኢትዮጵያ የሲቪል ሰርቪስ ታሪክ ሚኒስትር መሆን የራስን ቡድን መጥቀሚያ እንዲህ ዓይን ባወጣ መልኩ የሆነበት ጊዜ አሁን ብቻ ነው፡፡ ለምሳሌ የውጭ ጉዳይ ስራተኞች ምደባ ከብቃት ይልቅ በድርጅት ሰለሚሆን ኢህአዴግ አራት ድርጅቶች እንዲሁም በጨረፍታ ለአጋር ድርጅቶች ይታደላል፡፡ ከውጭ ጉዳያ ጋር ተያይዞ በቅርቡ የሰማሁት አንድ ነገር አለ፡፡ ህወሃት የውጭ ጉዳይ ሚኒሰትሩን ቦታ ቢይዝም ዋና ዋና የሚባሉትን ቦታዎች ለብአዴን/ብራሰልስ፣ እንግሊዝ፣ እስራኤል፣ወዘተ/ ለቋል የሚል ቅሬታ አለ፡፡ በአሜሪካ ግርማ ብሩም ቢሆን ከኦህዴድ  ይልቅ የሸዋ ሴረኝነቱ ይበልጣል ይሉታል- ህወሃቶች፡፡ ይህ እንግዲህ ህወሃቶች አሁን በያዙት የውጭ ጉዳይ ኪራይ ስብሳቢነት አልረኩም ማለት ነው፡፡ ይህን ለማስተካከልም ሙከራዎች አሉ ይባላል፡፡ መቼም ለምን ከፊት አልሆንም ካልሆነ በሰተቀር በሁሉም ቦታ እንዳሉ በግሌ አውቃለሁ፡፡
አቶ ጌታቸው ረዳ አንድ አሰቂኝ ምላሽ ሰጥተዋል “ጠቅላይ ሚኒስትሩ የከበቧቸው አማካሪዎች ወሳኝ አይደሉም” የሚል፡፡ እንደ ምሳሌም ያቀረቡት እራሳቸውን አማካሪ በነበሩበት ወቅት ወሳኝ አልነበርኩም በማለት ነው፡፡ እኛ የምናውቀው የጠቅላይ ሚኒስትሩ አማካሪ ቦታዎች በሶሰት ሊከፈሉ እንደሚችሉ ነው፡፡ አንደኛው የእውነት የማማከር ስራ የሚሰሩ በጠቅላይ ሚኒስትር ፅ/ቤት የተቀጠሩ ባለሞያዎች ናቸው፡፡ ሁለተኛው ደግሞ በሸተኞች እና ጡረታ እስኪወጡ ሊጠቀሙ የሚፈልጉ ሰዎች የሚገኙበት ነው፡፡ ይህ ምድብ እንደ ማግለያም ማገገሚያም ያገለግላል፡፡ የኤምባሲ ክፍት ቦታም እስኪገኝ መጠባበቂያም ሆኖ ያገለግላል፡፡ ሶሰተኛው ደግሞ ወሳኝ የሚባሉት የሚገኙበት ነው፡፡ በቁጥርም ውስን ናቸው፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትሩን በፓርቲ ማዕቀፍ መስመር በማስያዝ ውሳኔ የሚሰጡ ናቸው፡፡ ይህ ሶሰተኛው ቡድን አማካሪ በአቶ መለስ ዜናዊ ጊዜ አልነበሩም- ሊኖሩም አይችሉም፡፡ ሰውዬ በራሳቸው ወሳኝ ነበሩ፡፡ የተቀሩት ሁሉቱ ዓይነት አማካሪዎች ግን ድሮም የነበሩ ናቸው፡፡ ይህን ህዝቡ በደንብ ያውቀዋል ማን በየትኛው ምድብ እንዳለም ይታወቃል፡፡ ሰለዚህ የአቶ ጌታቸውን መልስ አልተቀበልነውም፡፡
ቸር ይግጠመን!!!

Saturday, September 3, 2016

የማሪያም መንገድ ሲዘጋ የገብሬሉ ይከፈታል ብለን ነበር!!!



አንድትን ፓርቲን ድንክ ለማድረግ ከመወሰናቸው በፊት አንድነት የሚከተለውን ሰላማዊ የትግል ስልታ፤ ሰላማዊ የሰለጠነ የስልጣን ሽግግር እንዲቀበሉ በተደጋጋሚ አሳሰብን ነበር፡፡ ከመሃከላችን እየመረጡ ማስር ትግሉን እንደማያዳክመው ይልቁንም እንደሚያጠነክረው ነግረናቸዋል፡፡ ከከፋም ትግሉ ወደ ሌላ ደረጃ እንደሚያሸጋግረው በቅርብ ላገኘናቸው ሁሉ ነግረናል፡፡ መግለጫዎች አውጠተን አቋማችን ህዝብ እንዲረዳው አድርገናል፡፡ የመንግሰት ተቋማት ህዝብን እንዲያገለግሉ፣ ከተሰጣቸው ህዝብን የማገልገል ሃላፊነት ውጭ እንዳይንቀሳቀሱ የበኩላችን ለማድረግ ሞክረናል፡፡ ማነኛውም ያደረግናቸው እንቅስቃሴዎች ከፍርሃት ተቆጥሮብናል፡፡ ከሁሉም በላይ በምን ያመጣሉ ትዕቢት የፈለጉትን አድርገዋል፡፡ ይህ እንዲሆን በውስጣችን ታቅፈናቸው የነበሩትን ጭንጋፎች ተሳትፎ የሚያሳንሰው አይደለም፡፡ ይህም ቢሆን ግን ገዢው ፓርቲ በማይመለከተው የፓርቲ የውስጥ ጉዳይ ገብቶ ህገወጥ እርምጃ የፖሊስ ሰራዊት በማሰማራት ወስዶዋል፡፡ ዛሬ በሰላማዊ ትግል ጥላ ስር ለውጥ እናመጣለን ሲሉ የነበሩ ወጣቶች በማነኛውም መንግድ ለውጥ ለማምጣት ቆርጠው ተነስተዋል፡፡ ተገፍተው የገቡበት መሆኑን ስለምናውቅ ምርጫቸውን ማክበር ብቻ ሳይሆን በባርነት ከመኖር ሞትን መምረጥ የሰው ልጅ ትክክለኛ ምርጫ ነው ብለን እናከብራቸዋለን፡፡
የታፈነ ህዝብ ለመተንፈስ የሚያደርገው የዚህ ዓመት ህዝባዊ እንቅስቃሴ በምንም መመዘኛ ሰህተት ሊሆን አይችልም፡፡ ጥያቄዎቹን በየቦታው ያስነሱት ጉዳዮች የተለያዩ ቢመስሉም መንግሰት እንደሚለው የመልካም አስተዳደር ጉድለት አይደለም፡፡ የህዝብ ጥያቄ ያልገባው መንግሰት ደግሞ መልሱን ሊያገኘው እንደማይችል ደግመን ደጋግመን ተናግረናል፡፡ በየቦታው የተነሳውን ህዝባዊ ንቅናቄ ተከትሎ መንግሰት ህገወጥ እርምጃዎችን መውሰዱን ቀጥሎበታል፡፡
መንግሰት በቅርቡ እያደረገ ያለው ዜጎችን መቅጠፍ በምንም መመዘኛ ቀለም አልተሰጠውም እንጂ ከቀይ ሽብር- ነጭ ሸብር የሚለይ አይደለም፡፡ በሃያ አንደኛው ክፍለ ዘመን የፖለቲካ ልዮነቶች በውይይት እና ህዝብ በሚመርጠው መስመር መፈታት አለበት ተብሎ በሚታመንበት ጊዜ መንግሰት ገዳይ ጥይቶቸን በሰላማዊ ዜጎች ላይ እየረጨ ይገኛል፡፡ ይህ መቼም ቢሆን ከተጠያቂነት የሚያድን አይደለም፡፡ የህዝብ መተንፈሻ የሚባሉትን መሰመሮች ሁሉ የዘጋ መንግሰት ህዝብ ለምን አደባባይ ወጣችሁ ብሎ ለመግደል የሚያስችል ስልጣን ማንም አልሰጠውም፡፡ ነገር ግን ጊዚያዊ ማዘዣውን ተጠቅሞ በተግባር ዜጎችን እየገደለ ይገኛል፡፡ ይባስ ብሎ ከነብስ ወከፍ መሳሪያ አልፎ የቡድን መሳሪያዎች፣ በእኔ ግምት ለውጭ ወራሪ ሀይል የተዘጋጀን መከላከያ አንቀሳቅሶ የህዝብን ድምፅ ለማፈን እየተንቀሳቀሰ መሆኑን ለሚታዘብ ወቅቱ የመንግሰት የእብደት ደረጃ ልክ ያለፈበት እንደሆነ ለመረዳት አያስቸግርም፡፡
የኢትዮጵያ ህዝብ ከሰሜን እስከ ደቡብ፣ ከምዕራብ እሰከ ምስራቅ የጠየቀው ለሰው ልጅ የሚገባውን ነፃነት እና ክብር ነው፡፡ መንግሰት ደግሞ ሆዳችሁን ከሞላቸሁ ፎቅ፣ ባቡር እና መኪና መንገድ ካያችሁ መች አነሳችሁ የሚል ይመስላል፡፡ በቅርቡ ጠቅላይ ሚኒስትር ሰብሰበው ለወጣቶች የሚነግሩት በሙሉ ሆድ ሰለሚሞላበት መንገድ ነው፡፡ ወጣቱ በአደረጃጀት ካልገባ ማግኘት እንደማይቻል ያስረዱት ደግሞ የስፖርትና ወጣቶች ሚኒሰትር መስሪያ ቤት የወጣት አደረጃጀት ሃላፊ ናቸው የተባሉ ሰው ናቸው፡፡ በሀገራችን ያለው የተፈቀደ አደረጃጀት መንግሰትን ለማወደስ የተቋቋሙት የወጣቶችና የሴቶች ሊጎች ናቸው፡፡ እነዚህ አደረጃጀቶች ገዢው ፓርቲ ሲየስነጥስ እንባቸው የሚመጣ ናቸው፡፡ እነዚህ ደግሞ የወጣቱን ችግር ሊናገሩ አይችሉም፡፡ ከጠቅላይ ሚኒስትሩ ጋር በወጣት ሰም ስብሰባ ተቀመጡ የተባሉ ሰዎች አብዛኞቹ በእውነት ይናገራሉ ተብለው የሚጠበቁ እንዳልሆነ ብዞዎች የተሰማሙበት ነው፡፡ እነዚህ ተሰብሳቢዎች ቢያንስ እድሜያቸው የወጣት አይደለም፡፡ ወጣት ያልሆነ የወጣት ችግር አያውቅም ማለት ሳይሆን በዚህ ስብሰባ ለመካፈል ለሚከፈል አበል ለማግኘት ሲሉ ወጣቶችን ትተው እራሳቸውን መርጠው የመጡ ሰዎች ናቸው፡፡ በዚህ በትንሹ ያልታመኑ በትልቁ ሊታመኑ አይችሉም፡፡
ጠቅላይ ሚኒሰትሩ የምር ውይይት ማድረግ ከፈለጉ የወጣቶችና ሰፖርቲ ሚኒስትሩ ሬዲዋን ሁሴን ስብሰባ ላይ የነገራቸውን የሚናግሩ ወጣቶችን መሰብሰብ ሳይሆን በአዲስ አበባ እና በየክልሉ ከተሞች ሰላማዊ ሰልፍ ሊወጡ ፈልገው የተከለከሉትን ወጣቶች ወይም ደግሞ የደህንነት ሰራተኞች በየጊዜው እያፈሱ በእስር ቤት የሚያጉሩዋቸውን ወጣቶች ማናገር አለባቸው፡፡ ለምሳሌ እነ አንጋው ተገኝ እና ጓደኖቹን ከጎንደር፣ እነ ስንታየሁ ቸኮል፣ ወይንሸት ሰለሺ  ከአዲስ አበባ፣ እነ ምርቱ ጉታ ከአዳማ፣ እነ ዘሪሁን ገሰሰ ከወሎ፣ ወዘተ ጠርተው ምን ጎደለባችሁ? ማለት ነበረባቸው፡፡ ለነገሩ እንጂ ጉዳዩ ከወጣቶቹ ጋር የሚያልቅ አይደለም፡፡ ጠቅላይ ሚኒስተሩ እና ጓዶቻቸው የምር ለዚህች ሀገር መፍትሔ የመፈለግ ፍላጎት ካላቸው ከማን ጋር መነጋገር እንዳለባቸው ይጠፋቸዋል ብዬ አላምንም፡፡
ዛሬ በጫካ የሚገኙት የሰላማዊ ትግል መስመር ሲዘጋ ወደ ትጥቅ ትግል የገቡት ልጆች በምንም መመዛኛ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ለወጣቶቹ እንደገለፁት በውይይት የሚገኘውን ውጤት ዘንግተው እና በድንጋይ ውርወራ መንግሰት ለመገልበጥ ፈልገው አይደለም፡፡ ይልቁንም መንግሰታቸው ውይይት ሰለሚፈራ እና በተወያየበት ሁሉ በጉልበት አንበርክኮ ለመውጣት ሰለሚፈልግ ነው፡፡ አሁንም በከተማ በድንጋይ ውርወራ መንግሰት ፋታ ለመከልከል የተዘጋጁ ወጣቶች መንግሰት ባዘጋጀው አደረጃጀቶች/ፎረሞች ብቻ እንዲሳተፉ በመምከር መፍትሔ አይገኝም፡፡ የተለያየ አስተሳሰብ ያላች ወጣቶች ሊደራጁበት የሚችሉበት መንገድ መከፈት አለበት፡፡ ትላንት ለእስር የተዳረገቸው የአንድነት አባል የነበረችው ወይንሸት ሰለሺ  በኢህአዴግ ወጣት አደረጃጀት የነበረች ቀጥሎም የባለ ራዕይ ወጣቶች አባል የነበረች ነች፡፡ በሲቪል ሶሳይቲነት ይንቀሳቀስ የነበረው ባለራዕይ ወጣቶች መንቀሳቀስ ሲከለከል አንድነት ተቀላቅላ ስርዓቱን ለመለወጥ ቆርጣ ተነሳች፡፡ ለዚህም ብላ አንድነትን ተቀላቀለች፡፡ አንድነት በህገወጥ መንገድ ሲፈርስ ደግሞ በፌስ ቡክ ትግል የምታደርግ ንቁ ወጣት ነች፡፡ በእኔ እምነት ወይነሸት ላይ የሚያቀርቡት አንድም ወንጀል የለም፡፡ ወንጀለኞች ቢወነጅሏት ለልጇ ዲሞክራሲያዊት ሀገር ለመመስረት ባደረገቸው ጥረት ነው፡፡ ለሆዴ አላድርም ነፃነት ይበልጥብኛል ሰለአለች ብቻ ነው፡፡
አሁንም ጥሪያችን መንግሰት የማሪያሙን መንገድ ክፍት ያድርግ በነፃነት መደራጃት የምንችልበትን መንገድ ክፍት ማድረጉን ማረጋገጫ ይስጠን፣ ከዚያ የኢትዮጵያ ህዝብ ምን እንደሚያደርግ ያውቃል፡፡ በአዲስ አበባ የተኮለኮሉ ኮብል እስቶኖችን መናፈቅ ትቶ በውይይት ወደ መፍትሔ ይገባል፡፡ ለመጀመር በአዲስ አበባ የወጣትና ሴቶች ፎረም አባል ያልሆኑ የአዲስ አበባ ልጆችን ለማነጋገር ከወሰኑ ትልቅ እርምጃ ነው፡፡ ክቡር ጠቅላይ ሚኒሰትር ስራ ላለማብዛት እኛ የዞን ዘጠኝ ወጣቶችን ወክለናል ያነጋግሩዋቸው፡፡
መልካም አዲስ ዓመት በተለመደው ሁኔታ ሳይሆን ለለውጥ የእውነትም አዲስ ዓመት ማድረግ የሁላችንም ሃላፊነት መሆኑን መዘንጋት የለብንም፡፡ ክብር ህይወታቸውን ለሰጡ ጀግኖቻችን ….
ቸር ይግጠመን!!!!!