Monday, September 19, 2016

አቶ ጌታቸው ረዳ የሸገር ካፌ ቆይታ …..



የኮሚኒኬሸን ሚኒሰትሩ አቶ ጌታቸው ረዳ በሸገር ካፌ ላይ ቀርበው ከእሸቴ አሰፋ ለቀረበላቸው ጥያቄ መልስ ሰጥተዋል፡፡ ጥያቄዎቹ የህዝብ መልሶቹ ግን የተለመዱ የኢህአዴግ ናቸው፡፡ ያሰገረሙኝን ብቻ ላካፍላችሁ፡፡
አቶ ጌታቸው ያለምንም ይሉኝታ ዳግም ተሃድሶ የታችኛውን ክፍል እንደሚጠራርግ ነግረውናል፡፡ ምክንያቱም መመረያ በሚል ሰበብ ህዝብ አያጉላሉ ያሉት እነርሱ በመሆናቸው የሚል አስቂኝ ሰበብ ሰጥተዋል፡፡ እግረ መንገዳቸውም ሚኒስትሮች እና ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከህግ በላይ እንዲሆኑም ፍላጎት አሳይተዋል፡፡ ሚኒስትሩ/ጠቅላይ ሚኒስተሩ ሲያዙ መመሪያ አይፈቅድም ይላሉ፡፡ እኔ እስከ ዛሬ ባለኝ ልምድ የመመሪያው ባለቤቶች እነዚያው ሚኒስትሮች መስለውኝ፡፡ መቼም እዚህ ሀገር ጉድ ሳይሰማ መሰከረም ስለማይጠባ በየመስሪያ ቤቱ ያሉ ኤክስፐርቶች መመሪያ የማውጣት ስልጣን ተሰጥቶ ከሆነ ልክ አይደሉም ሰልጣናቸውን ያለ አግባብ ሚኒሰትሮች እንዲሁም ጠቅላይ ሚኒስትሩን ለማሳቀቅ ሊጠቀሙበት ባልተገባ ነበር፡፡ ይህ ካልሆነ ግን እርሰ በእርሱ የሚጋጭ መመሪያ ያወጣ ሚኒስትር ያወጣውን መመሪያ ኤክስፐርት ቢያስታውሰው ክፋቱ አልታየኝም እና አቶ ጌታቸው በድጋሚ ቢያብራሩልን፡፡ በነገራቸን ላይ መመሪያ ደንብ የሚያከብሩና የሚያስከብሩ ሚኒስትሮች እና ጠቅላይ ሚኒስትር ነው የሚያስፈልገን፡፡ መቼም አቶ ሀይለማሪያም ደሳለኝን ያዘዙት እንቢ ያለ ኤክስፐርት ማን እንደሆነ ማወቅ ጥሩ ነበር፡፡ ይህ ኤክስፐርት አቶ መለስንም እንዲህ ይል ነበር? የሚል ጥያቄም ያጭራል፡፡ አቶ መለስ እንዲህ ብለዋል እየተባለ ባልወጣ መመሪያ እንተዳደር እንደነበር የሚዘነጋ አይደለም፡፡ ይህ ጉዳይ እኮ የቅርብ ጊዜ ነው፡፡
ሌላው አቶ ጌታቸው ረዳ ካለፈው ስህተታቸው መማር ያልቻሉት በሚዲያ በሚተላለፍ ውይይት ቃላት መረጣ አለመቻላቸው ወይም ፍላጎት ያለማሳየታቸው ነው፡፡ ጭራቅ እና አጋንንት መውደዳቸው እንደተጠበቀ ሆኖ ማለቴ ነው፡፡ ለምሳሌ “ህዝብ አሁን ካሉት 28 ካቢኔ ሚኒስትሮች ስንቱ ቢታሰር፣ ስንቱ ቢሰቀል እንደሚረካ አይገባኝም” ብለዋል፡፡ እኛ ይስቀሉ አላልንም፡፡ ነገር ግን እሰከሚገባኝ ድረስ ያለ አግባብ ከተሰቀሉበት ስልጣን ይውረዱ፡፡ ወርደው ባለጉዳይ ሆነው ይህችን ሀገር ይመልከቷት ነው የተባለው፡፡ እኔ እስከሚገባኝ ኢህአዴግ እስከ አሁን በፍፁም እንዲገባው የማይፈልገው ተጠያቂነት በውክልና አይተላለፍም ውክልና ለበታች ሰራተኛ ሲሰጥ ስራውን/ሃላፊነቱን ብቻ ነው፡፡ የተወከለው ሰራተኛ ካጠፋ የሚጠየቀው የወከለው ሃላፊ ነው፡፡ ይህ ሀሁ እንዲት ለሃያ አምስት ዓመት መረዳት ያቅታል፡፡ መቼም የጫካውን ዘመን እንርሳው ብዬ ነው፡፡
እሸቴ አሰፋ በግልፅ ያቀረበላቸው አንዱ ጥያቄ የአንድ ብሔር የበላይነት/የህወሃት የበላይነት አለ የሚል ቅሬታ አለ የሚል ነው፡፡ ይህ ጉዳይ በግምገማቸው ላይ ተነስቶ በስፋት ውይይት መደረጉ አቶ ጌታቸው ነግረውናል፡፡ የተነሳው የአንድ ብሔር /የትግራይ/ የበላይነት አለ የሚለው አንድ በጎ ነገር ሲሆን የተደረሰበት ነገርም ጥሩ ነው፡፡ አንዱን ኪራይ ስብሳቢ በሌላ ብሔር ኪራይ ስብሳቢ መተካት አይደለም፡፡ ህዝቡ እያለ ያለው ህውሃት ወርዶ በብአዴን ወይም በኦህዴድ ይተካ አይደለም፡፡ ሁላችሁም ውረዱ ነው፡፡ አሁን ያለው የህወሃት የበላይነት እንዲነግስ ያደረጉ አሁን ጥያቄያቸው በተራችን እኛ እንሁን ከመሆን ሊዘል አይችልም፡፡ የእኛ ጥያቄ ግን የዚህ ዓይነት ስርዓት አያስፈልገንም የሚል ነው፡፡
ከአንድ ብሔር የበላይነት ጋር ተያይዞ የተነሳው አንድ ቁልፍ ነገር የቁልፍ ቦታዎች ነገር ነው፡፡ ቁልፍ የሚባሉት ቦታዎች ለምን ቁልፍ ሆኑ? ሲባል ኪራይ ማደያ ሰለሆኑ ነው:: ምርጥ መልስ ነው፡፡ ያሳዝናል፡፡ አንድ የመንግሰት ተቋም ሃላፊ መሆን የራስን ግሳንግስ መሰብሰቢያ ስርዓት ከመገንባት የከፋ ውርደት ከየት ይመጣል፡፡ በኢትዮጵያ የሲቪል ሰርቪስ ታሪክ ሚኒስትር መሆን የራስን ቡድን መጥቀሚያ እንዲህ ዓይን ባወጣ መልኩ የሆነበት ጊዜ አሁን ብቻ ነው፡፡ ለምሳሌ የውጭ ጉዳይ ስራተኞች ምደባ ከብቃት ይልቅ በድርጅት ሰለሚሆን ኢህአዴግ አራት ድርጅቶች እንዲሁም በጨረፍታ ለአጋር ድርጅቶች ይታደላል፡፡ ከውጭ ጉዳያ ጋር ተያይዞ በቅርቡ የሰማሁት አንድ ነገር አለ፡፡ ህወሃት የውጭ ጉዳይ ሚኒሰትሩን ቦታ ቢይዝም ዋና ዋና የሚባሉትን ቦታዎች ለብአዴን/ብራሰልስ፣ እንግሊዝ፣ እስራኤል፣ወዘተ/ ለቋል የሚል ቅሬታ አለ፡፡ በአሜሪካ ግርማ ብሩም ቢሆን ከኦህዴድ  ይልቅ የሸዋ ሴረኝነቱ ይበልጣል ይሉታል- ህወሃቶች፡፡ ይህ እንግዲህ ህወሃቶች አሁን በያዙት የውጭ ጉዳይ ኪራይ ስብሳቢነት አልረኩም ማለት ነው፡፡ ይህን ለማስተካከልም ሙከራዎች አሉ ይባላል፡፡ መቼም ለምን ከፊት አልሆንም ካልሆነ በሰተቀር በሁሉም ቦታ እንዳሉ በግሌ አውቃለሁ፡፡
አቶ ጌታቸው ረዳ አንድ አሰቂኝ ምላሽ ሰጥተዋል “ጠቅላይ ሚኒስትሩ የከበቧቸው አማካሪዎች ወሳኝ አይደሉም” የሚል፡፡ እንደ ምሳሌም ያቀረቡት እራሳቸውን አማካሪ በነበሩበት ወቅት ወሳኝ አልነበርኩም በማለት ነው፡፡ እኛ የምናውቀው የጠቅላይ ሚኒስትሩ አማካሪ ቦታዎች በሶሰት ሊከፈሉ እንደሚችሉ ነው፡፡ አንደኛው የእውነት የማማከር ስራ የሚሰሩ በጠቅላይ ሚኒስትር ፅ/ቤት የተቀጠሩ ባለሞያዎች ናቸው፡፡ ሁለተኛው ደግሞ በሸተኞች እና ጡረታ እስኪወጡ ሊጠቀሙ የሚፈልጉ ሰዎች የሚገኙበት ነው፡፡ ይህ ምድብ እንደ ማግለያም ማገገሚያም ያገለግላል፡፡ የኤምባሲ ክፍት ቦታም እስኪገኝ መጠባበቂያም ሆኖ ያገለግላል፡፡ ሶሰተኛው ደግሞ ወሳኝ የሚባሉት የሚገኙበት ነው፡፡ በቁጥርም ውስን ናቸው፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትሩን በፓርቲ ማዕቀፍ መስመር በማስያዝ ውሳኔ የሚሰጡ ናቸው፡፡ ይህ ሶሰተኛው ቡድን አማካሪ በአቶ መለስ ዜናዊ ጊዜ አልነበሩም- ሊኖሩም አይችሉም፡፡ ሰውዬ በራሳቸው ወሳኝ ነበሩ፡፡ የተቀሩት ሁሉቱ ዓይነት አማካሪዎች ግን ድሮም የነበሩ ናቸው፡፡ ይህን ህዝቡ በደንብ ያውቀዋል ማን በየትኛው ምድብ እንዳለም ይታወቃል፡፡ ሰለዚህ የአቶ ጌታቸውን መልስ አልተቀበልነውም፡፡
ቸር ይግጠመን!!!

Saturday, September 3, 2016

የማሪያም መንገድ ሲዘጋ የገብሬሉ ይከፈታል ብለን ነበር!!!



አንድትን ፓርቲን ድንክ ለማድረግ ከመወሰናቸው በፊት አንድነት የሚከተለውን ሰላማዊ የትግል ስልታ፤ ሰላማዊ የሰለጠነ የስልጣን ሽግግር እንዲቀበሉ በተደጋጋሚ አሳሰብን ነበር፡፡ ከመሃከላችን እየመረጡ ማስር ትግሉን እንደማያዳክመው ይልቁንም እንደሚያጠነክረው ነግረናቸዋል፡፡ ከከፋም ትግሉ ወደ ሌላ ደረጃ እንደሚያሸጋግረው በቅርብ ላገኘናቸው ሁሉ ነግረናል፡፡ መግለጫዎች አውጠተን አቋማችን ህዝብ እንዲረዳው አድርገናል፡፡ የመንግሰት ተቋማት ህዝብን እንዲያገለግሉ፣ ከተሰጣቸው ህዝብን የማገልገል ሃላፊነት ውጭ እንዳይንቀሳቀሱ የበኩላችን ለማድረግ ሞክረናል፡፡ ማነኛውም ያደረግናቸው እንቅስቃሴዎች ከፍርሃት ተቆጥሮብናል፡፡ ከሁሉም በላይ በምን ያመጣሉ ትዕቢት የፈለጉትን አድርገዋል፡፡ ይህ እንዲሆን በውስጣችን ታቅፈናቸው የነበሩትን ጭንጋፎች ተሳትፎ የሚያሳንሰው አይደለም፡፡ ይህም ቢሆን ግን ገዢው ፓርቲ በማይመለከተው የፓርቲ የውስጥ ጉዳይ ገብቶ ህገወጥ እርምጃ የፖሊስ ሰራዊት በማሰማራት ወስዶዋል፡፡ ዛሬ በሰላማዊ ትግል ጥላ ስር ለውጥ እናመጣለን ሲሉ የነበሩ ወጣቶች በማነኛውም መንግድ ለውጥ ለማምጣት ቆርጠው ተነስተዋል፡፡ ተገፍተው የገቡበት መሆኑን ስለምናውቅ ምርጫቸውን ማክበር ብቻ ሳይሆን በባርነት ከመኖር ሞትን መምረጥ የሰው ልጅ ትክክለኛ ምርጫ ነው ብለን እናከብራቸዋለን፡፡
የታፈነ ህዝብ ለመተንፈስ የሚያደርገው የዚህ ዓመት ህዝባዊ እንቅስቃሴ በምንም መመዘኛ ሰህተት ሊሆን አይችልም፡፡ ጥያቄዎቹን በየቦታው ያስነሱት ጉዳዮች የተለያዩ ቢመስሉም መንግሰት እንደሚለው የመልካም አስተዳደር ጉድለት አይደለም፡፡ የህዝብ ጥያቄ ያልገባው መንግሰት ደግሞ መልሱን ሊያገኘው እንደማይችል ደግመን ደጋግመን ተናግረናል፡፡ በየቦታው የተነሳውን ህዝባዊ ንቅናቄ ተከትሎ መንግሰት ህገወጥ እርምጃዎችን መውሰዱን ቀጥሎበታል፡፡
መንግሰት በቅርቡ እያደረገ ያለው ዜጎችን መቅጠፍ በምንም መመዘኛ ቀለም አልተሰጠውም እንጂ ከቀይ ሽብር- ነጭ ሸብር የሚለይ አይደለም፡፡ በሃያ አንደኛው ክፍለ ዘመን የፖለቲካ ልዮነቶች በውይይት እና ህዝብ በሚመርጠው መስመር መፈታት አለበት ተብሎ በሚታመንበት ጊዜ መንግሰት ገዳይ ጥይቶቸን በሰላማዊ ዜጎች ላይ እየረጨ ይገኛል፡፡ ይህ መቼም ቢሆን ከተጠያቂነት የሚያድን አይደለም፡፡ የህዝብ መተንፈሻ የሚባሉትን መሰመሮች ሁሉ የዘጋ መንግሰት ህዝብ ለምን አደባባይ ወጣችሁ ብሎ ለመግደል የሚያስችል ስልጣን ማንም አልሰጠውም፡፡ ነገር ግን ጊዚያዊ ማዘዣውን ተጠቅሞ በተግባር ዜጎችን እየገደለ ይገኛል፡፡ ይባስ ብሎ ከነብስ ወከፍ መሳሪያ አልፎ የቡድን መሳሪያዎች፣ በእኔ ግምት ለውጭ ወራሪ ሀይል የተዘጋጀን መከላከያ አንቀሳቅሶ የህዝብን ድምፅ ለማፈን እየተንቀሳቀሰ መሆኑን ለሚታዘብ ወቅቱ የመንግሰት የእብደት ደረጃ ልክ ያለፈበት እንደሆነ ለመረዳት አያስቸግርም፡፡
የኢትዮጵያ ህዝብ ከሰሜን እስከ ደቡብ፣ ከምዕራብ እሰከ ምስራቅ የጠየቀው ለሰው ልጅ የሚገባውን ነፃነት እና ክብር ነው፡፡ መንግሰት ደግሞ ሆዳችሁን ከሞላቸሁ ፎቅ፣ ባቡር እና መኪና መንገድ ካያችሁ መች አነሳችሁ የሚል ይመስላል፡፡ በቅርቡ ጠቅላይ ሚኒስትር ሰብሰበው ለወጣቶች የሚነግሩት በሙሉ ሆድ ሰለሚሞላበት መንገድ ነው፡፡ ወጣቱ በአደረጃጀት ካልገባ ማግኘት እንደማይቻል ያስረዱት ደግሞ የስፖርትና ወጣቶች ሚኒሰትር መስሪያ ቤት የወጣት አደረጃጀት ሃላፊ ናቸው የተባሉ ሰው ናቸው፡፡ በሀገራችን ያለው የተፈቀደ አደረጃጀት መንግሰትን ለማወደስ የተቋቋሙት የወጣቶችና የሴቶች ሊጎች ናቸው፡፡ እነዚህ አደረጃጀቶች ገዢው ፓርቲ ሲየስነጥስ እንባቸው የሚመጣ ናቸው፡፡ እነዚህ ደግሞ የወጣቱን ችግር ሊናገሩ አይችሉም፡፡ ከጠቅላይ ሚኒስትሩ ጋር በወጣት ሰም ስብሰባ ተቀመጡ የተባሉ ሰዎች አብዛኞቹ በእውነት ይናገራሉ ተብለው የሚጠበቁ እንዳልሆነ ብዞዎች የተሰማሙበት ነው፡፡ እነዚህ ተሰብሳቢዎች ቢያንስ እድሜያቸው የወጣት አይደለም፡፡ ወጣት ያልሆነ የወጣት ችግር አያውቅም ማለት ሳይሆን በዚህ ስብሰባ ለመካፈል ለሚከፈል አበል ለማግኘት ሲሉ ወጣቶችን ትተው እራሳቸውን መርጠው የመጡ ሰዎች ናቸው፡፡ በዚህ በትንሹ ያልታመኑ በትልቁ ሊታመኑ አይችሉም፡፡
ጠቅላይ ሚኒሰትሩ የምር ውይይት ማድረግ ከፈለጉ የወጣቶችና ሰፖርቲ ሚኒስትሩ ሬዲዋን ሁሴን ስብሰባ ላይ የነገራቸውን የሚናግሩ ወጣቶችን መሰብሰብ ሳይሆን በአዲስ አበባ እና በየክልሉ ከተሞች ሰላማዊ ሰልፍ ሊወጡ ፈልገው የተከለከሉትን ወጣቶች ወይም ደግሞ የደህንነት ሰራተኞች በየጊዜው እያፈሱ በእስር ቤት የሚያጉሩዋቸውን ወጣቶች ማናገር አለባቸው፡፡ ለምሳሌ እነ አንጋው ተገኝ እና ጓደኖቹን ከጎንደር፣ እነ ስንታየሁ ቸኮል፣ ወይንሸት ሰለሺ  ከአዲስ አበባ፣ እነ ምርቱ ጉታ ከአዳማ፣ እነ ዘሪሁን ገሰሰ ከወሎ፣ ወዘተ ጠርተው ምን ጎደለባችሁ? ማለት ነበረባቸው፡፡ ለነገሩ እንጂ ጉዳዩ ከወጣቶቹ ጋር የሚያልቅ አይደለም፡፡ ጠቅላይ ሚኒስተሩ እና ጓዶቻቸው የምር ለዚህች ሀገር መፍትሔ የመፈለግ ፍላጎት ካላቸው ከማን ጋር መነጋገር እንዳለባቸው ይጠፋቸዋል ብዬ አላምንም፡፡
ዛሬ በጫካ የሚገኙት የሰላማዊ ትግል መስመር ሲዘጋ ወደ ትጥቅ ትግል የገቡት ልጆች በምንም መመዛኛ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ለወጣቶቹ እንደገለፁት በውይይት የሚገኘውን ውጤት ዘንግተው እና በድንጋይ ውርወራ መንግሰት ለመገልበጥ ፈልገው አይደለም፡፡ ይልቁንም መንግሰታቸው ውይይት ሰለሚፈራ እና በተወያየበት ሁሉ በጉልበት አንበርክኮ ለመውጣት ሰለሚፈልግ ነው፡፡ አሁንም በከተማ በድንጋይ ውርወራ መንግሰት ፋታ ለመከልከል የተዘጋጁ ወጣቶች መንግሰት ባዘጋጀው አደረጃጀቶች/ፎረሞች ብቻ እንዲሳተፉ በመምከር መፍትሔ አይገኝም፡፡ የተለያየ አስተሳሰብ ያላች ወጣቶች ሊደራጁበት የሚችሉበት መንገድ መከፈት አለበት፡፡ ትላንት ለእስር የተዳረገቸው የአንድነት አባል የነበረችው ወይንሸት ሰለሺ  በኢህአዴግ ወጣት አደረጃጀት የነበረች ቀጥሎም የባለ ራዕይ ወጣቶች አባል የነበረች ነች፡፡ በሲቪል ሶሳይቲነት ይንቀሳቀስ የነበረው ባለራዕይ ወጣቶች መንቀሳቀስ ሲከለከል አንድነት ተቀላቅላ ስርዓቱን ለመለወጥ ቆርጣ ተነሳች፡፡ ለዚህም ብላ አንድነትን ተቀላቀለች፡፡ አንድነት በህገወጥ መንገድ ሲፈርስ ደግሞ በፌስ ቡክ ትግል የምታደርግ ንቁ ወጣት ነች፡፡ በእኔ እምነት ወይነሸት ላይ የሚያቀርቡት አንድም ወንጀል የለም፡፡ ወንጀለኞች ቢወነጅሏት ለልጇ ዲሞክራሲያዊት ሀገር ለመመስረት ባደረገቸው ጥረት ነው፡፡ ለሆዴ አላድርም ነፃነት ይበልጥብኛል ሰለአለች ብቻ ነው፡፡
አሁንም ጥሪያችን መንግሰት የማሪያሙን መንገድ ክፍት ያድርግ በነፃነት መደራጃት የምንችልበትን መንገድ ክፍት ማድረጉን ማረጋገጫ ይስጠን፣ ከዚያ የኢትዮጵያ ህዝብ ምን እንደሚያደርግ ያውቃል፡፡ በአዲስ አበባ የተኮለኮሉ ኮብል እስቶኖችን መናፈቅ ትቶ በውይይት ወደ መፍትሔ ይገባል፡፡ ለመጀመር በአዲስ አበባ የወጣትና ሴቶች ፎረም አባል ያልሆኑ የአዲስ አበባ ልጆችን ለማነጋገር ከወሰኑ ትልቅ እርምጃ ነው፡፡ ክቡር ጠቅላይ ሚኒሰትር ስራ ላለማብዛት እኛ የዞን ዘጠኝ ወጣቶችን ወክለናል ያነጋግሩዋቸው፡፡
መልካም አዲስ ዓመት በተለመደው ሁኔታ ሳይሆን ለለውጥ የእውነትም አዲስ ዓመት ማድረግ የሁላችንም ሃላፊነት መሆኑን መዘንጋት የለብንም፡፡ ክብር ህይወታቸውን ለሰጡ ጀግኖቻችን ….
ቸር ይግጠመን!!!!!

Tuesday, August 16, 2016

የኢትዮጵያ ትንሣኤ እንዴት? ከሸግግር መንግሰት እሰከ ጠብመንጃ አፈሙዝ!!!!



ኢትዮጵያችን ከሰሞኑ ድርስ የዲሞክራሲ እርጉዝ የሆነች ይመስላል፡፡ በሰላማዊ መንገድ ለውጥ ለምንፈልግ ሰዎች መንግሰት የፖለቲካ ማሻሻያ በማድረግ ሁላችንም አሸናፊ ሆነን የምንወጣበት ዲሞክራሲያዊ ስርዓት እናገኝ ይሆን ብለን እየጠበቅን ነው፡፡ የለም ገዢው ፓርቲ አብቅቶለታል በውስጥም በስብሷል ከውጭም ጫናው በርትቷል ፈንግለን እንጥለዋለን የሚሉም አሉ፡፡ ሌሎች ደግሞ አንድ ዓይነት ውጥረት ተፈጠረ በተባለ ቁጥር “የሸግግር መንግሰት” አቀንቃኞች ናቸው፡፡ እነዚህን ሶስት የዲሞክራሲ ፅንስ ማዋለጃ መንገዶችን በአጭር በአጭሩ ለማየት እሞክራለሁ፡፡ የግሌን አቋም የያዝኩበትን መስመር ትንሸ ሰፋ አድረጌ እምለከታለሁ፡፡
የሸግግር መንግሰት ማቋቋም
ይህን ሃሳብ የሚያቀነቅኑ ግለሰቦችም ሆኑ ቡድኖች ይህ ሃሳብ ተግባራዊ ሊሆን የሚችለው መቼ እንደሆነ የተረዱት አይመስለኝም፡፡ የዚህ ሃሳብ ተግባራዊ መሆን የሚችለው በኢህአዴግ መቃብር ላይ ብቻ ነው ብዬ ባልፍ በቂ ነበር፡፡ የኢህአዴግ መቃብር ደግሞ ከዚህ ቀጥሎ በምንመለከተው ሁኔታ የሚሆን ሰለሚሆን “የሽግግር መንግሸት” ለብቻው የሚቆም አማራጭ አይደለም፡፡ ገዢው ፓርቲ የሸግግር መንግስት ለሚባል አካል ስልጣኑን አስረክቦ ቢለቅ እኔም የምታዘበው ይመስለኛል፡፡ ጠቅላይ ሚኒሰትሩ ወግ ቢደርሳቸው የዚህን ያህል የተዓማኒነት ችግር ያለበት መንግሰት እየመራሁ ነው ከሚሉ፣ ፓርላማውም ወግ ደርሶች ጫና ቢያሳድር፣ “ፓርላማው”ን በትኖ አዲስ ምርጫ በህገ መንግሰቱ አንቀፅ 60 መሰረት እንዲከናወን ማድረግ ይችል ነበር፡፡ ለዚህ አልታደልም፡፡ ከዚህ የተለየ ህጋዊ ስርዓት “የሸግግር መንግሰት” ለመመስረት የሚስችል መንገድ የለም፡፡
በጣም ግልፅ ለመሆን ከዚህም ከዚያ በሚውጣጣ የቡድን እና ግለሰቦች ስብስብ “የሸግግር መንግስት” ይመስረት የሚሉ ሰዎች ያላቸውን የቡድን ውክልና ወይም ደግሞ ግለሰባዊ እውቅና መሰረት አድርገው ስልጣን በአቋራጭ የሚፈልጉ ናቸው፡፡ እመኑኝ እነዚህ ሰዎች በዚህ መስመር ሰልጣን ቢያገኙ ያገኙትን ስልጣን በቀጣይ በሚደረግ ምርጫ ስልጣናቸውን ቢያጡ አሜን ብለው የሚቀበሉ አይሆኑም፡፡ ሰለዚህ በእኔ እምነት “የሸግግር መንግስት ይቋቋም” በሚለው አልስማማ፡፡
ኢህአዴግ በስብሷል የስርዓት ለውጥ መደረግ አለበት
በዚህ ጉዳይ ኢህአዴጎች ባይስማሙ ብዙ ወገን ሊስማማ ይችላል፡፡ ይህን ስርዓት በስብሰሃልና ዞርበል እያልን ከሆነ በጉልበትና በጉልበት ብቻ የሚሆን ነው፡፡ ይህ ጉልበት ደግሞ አንድም በታጠቁ ኃይሎች፣ ወይም ደግሞ ህዝባዊ አመፅን ተከትሎ በሚመጣ የሰርዓት መፍረስ የሚገኝ ውጤት ነው፡፡ መንግሰት አሁን በያዘው ሁኔታ እሳቱን እያዳፈነ፣ የተዳፈነውን እሳት ግን ጭድ ስር እየደበቀ የሚቀጥል ከሆነ አይቀሬው ህዝባዊ ማዕበል እሳት ሆኖ ይበላዋል፡፡ ይህ እሳት ኢህአዴግን ብቻ ሳይሆን እኛም ከእሳቱ ብንተርፍ ወላፈኑ እይለቀንም፡፡ ይህ በሰላማዊ ሽግግር ሊታለፍ ካልቻለ ቀላል የማይባል ቀውስ በሀገራችን እንደሚያስከትል ግልፅ ነው፡፡ ይህ አማራጭ በትጥቅ የሚንቀሳቀሱ ኃይሎች እና ምንአልባት ህዝባዊ አመፅን በመምራት ላይ ያሉ ቡድኖች/ግለሰቦች በሚያደርጉት ስምምነት ቀጣይ የሀገሪቱ እጣ ፈንታ እንዴት ይሁን ብለው ሊነጋገሩ ይችላሉ፡፡ ኢህአዴግ-ሻቢያ- ኦነግ በለንደን እንዳደረጉት ማለት ነው፡፡ ከመንግሰት ጋር ይህ ውይይት ሊደረግ አይችልም፡፡ ሰለዚህ በዚህ አማራጭ ላይ ብዙ ማለት የሚቻል አይመሰለኝም፣ የአሸናፊዎች ፍትህ መስጫ ነው የሚሆነው፡፡ ምን አልባት በዚህ ወቅት እነዚህ አሸናፊ ኃይሎች የሚያቋቁሙት “የሸግግር መንግስት” አንደኛው ትክክለኛው አማራጭ የሚሆን ሲሆን እንደከዚህ ቀደሙ የኢህአዴግ የሽግግር መንግሰት መጪው የሸግግር መንግሰትም አግላይ ላለመሆኑ ምንም ዋስትና ሊኖረን አይችለም፡፡
ባጭሩ በሀይል የስርዓት ለውጥ ይደረግ ሲባል ኢህአዴግ ምንም ታሪክ እንደማይተርፈው መረዳት ያለበት ይሆናል፡፡ በሰፈረው ቁና መሰፈሩ ላይቀር የሚችልበት እድል ሰፊ ነው፡፡ ኢህአዴግ እና ኢህአዴጋዊያን ይህ ክፉ ቀን እንዳይመጣ ከዚህ ቀጥሎ የቀረበውን የፖለቲካ ማሻሻያ በማድረግ ሀገሪቱን ህዝብንም ሆነ እራሳቸውን እንዲጠብቁ መምከር እፈልጋለሁ፡፡
የፖለቲካ ማሻሻያ ማድረግ
አሁን ባለንበት ወቅት በሁሉም ወገን ተቀባይነት ማግኘት ያለበት ሃሣብ ነው ብዬ የማምነው፡፡ አሁን የደረስንበትን ቀውስ ሳናባብስ ነገር ግን ስር ነቀል የፖለቲካ ማሻሻያ በማድረግ ወደምንፈልገው ዲሞክራሲያው ስርዓት ልንሸጋገር እንችላለን የሚል እምነት አለኝ፡፡ ይህ የፖለቲካ ማሻሻያ የሚገኘው ግን አሁን የተጀመሩት ህዝባዊ እንቅስቃሴዎች ተጠናክረው ቀጥለው መንግሰት በልመና/በችሮታ የሚሰጠው ሳይሆን ለዚህች ሀገር መፍትሔ የሚያመጣ መንገድ ነው ብሎ አምኖ ሲቀበለው እና በሂደቱ በቅንነት ሲሳተፍ ነው፡፡ ከመንግሰት በተፃራሪ የቆምን ሀይሎችም የእኛ ብቻ ነው ልክ ከሚለው ግትር አቋም መለሳለስ ሲችሉ እና አንበረከክነው ከሚለው አስተሳሰብ ስንወጣ ነው፡፡
ይህ የፖለቲካ ማሻሻያ ለማድረግ በዋነኝነት ከመንግሰት ውጭ ያሉ ሀይሎች ችግሩ አሁን በስራ ላይ ያለው ህገመንግሰት ተቀዶ መጣል አለበት ከሚለው ፅንፍ ወጥተወ ሰላማዊ ሽግግር ለማድረግ እንደመነሻ የሚያገለግል እጅግ ጠቃሚ የሆነ የፖለቲካ ሰነድ መሆኑን አምኖ መቀበል ያስፈልጋል፡፡ ይህ ሲሆን ገዢው ፓርቲ በተለይ (የድል አጥቢያ አርበኞች ሳይሆኑ) በትግሉ ወቅት ከፍተኛ መስዋዕትነት የከፈሉበት ህገመንግሰት ተቀባይነት በማግኘቱ ደስተኞች ሰለሚሆኑ ሂደቱን የተሳካ ያደርገዋል፡፡ ይህም ሆኖ ህገመንግሰቱ ሊሻሻል የሚችል መሆኑ የማሻሻያ አንቀፆች ያሉት ስለሆነ በሂደት የሚሻሻልበት ሂደት መኖሩን መቀበል ደግሞ ለተቃዋሚዎች ተሰፋን የሚያጭር ይሆናል፡፡
ይህ የፖለቲካ ማሻሻያ በሚከናወንበት ጊዜ ሁሉ አሁን በስልጣን ላይ ያለው መንግሰት በመደበኛ የእለት ከእለት ስራው ላይ እንዲቆይ በመስማማት ሀገሪቱ ወደ ሌላ ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ቀውስ እንዳትገባ በማድረግ በስልጣን ላይ ያሉትም ቢሆኑ በስልጣን ላይቀጥሉ ቢችሉ የሰነልቦና ዝግጅ ማድረጊያ ጊዜ ያገኛሉ፡፡ ከገዢው ፓርቲ ውጪ ያሉ በሀገር ውስጥም በውጭ የሚገኙ ስልጣን የሚፈልጉ ሀይሎችም ለስልጣን የሚያበቃቸውን በቂ ዝግጅት ከህዝቡ ጋር በማድረግ እራሳቸውን ለማዘጋጀት በቂ ጊዜ ያገኛሉ፡፡ ማን ስልጣኑን ይይዛል የሚለውን ህዝብ ይወስናል፡፡
የፖለቲካ ማሻሻያ ሂደቱን ሊመራ የሚችል ገለልተኛ የሆነ የሸግግር ሂደቱን የሚመራ “የሽግግር ኮሚሽን” የሚቋቋም ሲሆን ይህ ኮሚሽን በዋነኝነት በሀገሪቱ የፖለቲካ ምዕዳሩን ሊያሻሽሉ የሚችሉ ልዮልዮ ደንቦችን እና መመሪያዎችን እንዲወጡ በማድረግ፣ አፋኝ ህጎችን በመሻር/ወይም በምክር ቤቱ እንዲሻሩ በማድረግ ህዝቡ በፖለቲካው በንቃት እንዲሳተፍ ማድረግ ይጠበቅበታል፡፡
ይህ ማሻሻያ በልመና የሚገኝ ባለመሆኑ መንግሰት ወደ ትክክለኛውም አማረጭ እሲገባ ድረስ አሁን ያለው ህዝባዊ እንቢተኝነት እና “በቃ” የሚለው ህዝባዊ እንቅስቃሴ ተጠናክሮ እንዲቀጥል በማድረግ መንግሰት ይህን አስፈላጊ የፖለቲካ ማሻሻያ እንዲቀበል ማሰገደድ የግድ ይላል፡፡ ምንአልባትም መንግሰት በራሴ አፈታዋለሁ በሚል በሚጠራቸው “ህዝባዊ መድረኮች” ሁሉ በመገኘት ይህን የፖለቲካ ማሻሻያ እንዲያደርግ ግፊት ማድረግ ያስፈልጋል፡፡ መንግሰት “ሕዝባዊ” ብሎ የሚጠራች መድረኮች በአብዛኛው የፓርቲው አባላትና ጥቂት ጥቅመኞች እንደሆኑ በመረዳት በስብሰባው ላይ ሌሎች እንዲገኙ ጥረት ማድረግ ተገኝተውም ድምፃቸውን እንዲያሰሙ ማድረግ ያስፈልጋል፡፡

አሁን በመደረግ ላይ ያሉ እንቅስቃሴዎች መንግሰት ላይ የፈጠሩት ጫና ያለ ቢሆንም መንግሰት በተገቢው መንገድ ምላሻ ለመሰጠት በሚያስገድድ መልክ እንዳልሆኑ መገንዘብ ይቻላል፡፡ ለምሣሌ ሰላማዊ ሰልፍም ሆኖ ተቃውሞ በተደረገ ማግስት መንግሰት በዚህ ተቃውሞ ላይ የተሳተፉ ዜጎችን እየገደለና በየቤቱ እየዞረ እየለቀመ በማስር ከስራ በማፈናቀል እንቅስቃሴውን ማፈን እንደ አንድ ታክቲክ እየተጠቀመ ስለሆነ ማነኛውም የህዝብ ጥያቄ (ትክክል ባይሆን) ከመንግሰት ወገን መልስ ከመስጠት አልፎ ጥያቄውን በማቅረብ የተሳተፉ ወይም የመሩ ሰዎችን ማሰረን፣ ከስራ መባረርን መቃወም ሲከፋም እንዳይታሰሩ መከላከል፡፡ ከታሰሩም በታሰሩበት ቦታ በመገኘት ተቃውሞ መቀጠል፣ እስኪፈቱ ድረስ በፈረቃ በቦታው በመገኝት ተቃውሞ ከፍ እንዲል ማድረግ ያስፈልጋል፡፡
መንግሰት አሁን የግድ የሚያስፈልገውን የፖለቲካ ማሻሻያ እስኪቀበል ድረስ የተቀናጀ ህዝባዊ እንቅስቃሴ ማድረግ ህዝባዊ እንቅስቃሴው ከጊዜ ወደጊዜ አድማሱን እያሰፈ ረጅም ጊዜ የሚወሰድ የስራና ትምህርት ማቆም አድማ ማድረግ ሊጨምር ይችላል፡፡ መንግሰት በዚህ ላይ በሚሳተፉ ሰዎች ላይ በሚወሰድ እርምጅ በመቃውም ከላይ በተገለፀው መልኩ ተቃውሞን ማስፋት፡፡
በማነኛውም ጊዜ ሆነ ቦታ በሚደረጉ እንቅስቃሴዎች በማነኛውም ዜጋ ላይ ምንም ዓይነት ጉዳት እንዳይደርስ ጥንቃቄ ማድረግ፤በተለያየ ምክንያት የዚህ ዓይነት ችግሮች ሲፈጠሩ ማጋለጥና ህጋዊ እርምጃ እንዲወሰድ ህዝቡ እንዲተባበር ማድረግ፡፡ መንግሰት ይህን ሰበብ በማድረግ በሰው ህይወት ላይ አደጋ እንዳያደርስ፣ በሰው ህይውት ላይ ለሚደርሱ ጉዳቶች ሃላፊነቱን እንዲወሰድ ማድረግ፡፡
ኢትዮጵያዊያን በዘርና ሃይማኖት ተቧድነው ይጣላሉ ብሎ መገመት አስቸጋሪ ቢሆን መንግሰትን ጨምሮ የተለያዩ ሀይሎች ለቡድናዊ ፍላጎታቸው ማስፈፀሚያ አንድን የህብረተሰብ ክፍል እንደሰብዓዊ ከላለ ለመጠቀም መሞከራቸው አይቀርም፡፡ ማነኛውም ህዝባዊ እንቅስቃሴ በሚደረግበት ወቅት ከፍተኛ ጥንቃቄ ማድረግ እና ኢትዮጵያዊነታችን ከብሔር ማንነታችን ጋር በምንም ሁኔታ የማይጋጭ መሆኑን ማስመስከር ይጠበቅብናል፡፡ በተለይ ኢትዮጵያዊ ልሂቃን ይህን ጉዳይ ለፖለቲካ ጥቅም ከማዋል እራሳችንን በማራቅ ታሪክ መስራት ይጠበቅብናል፡፡

Tuesday, July 19, 2016

ከግል እና ከመንግሰት ትምህርት ቤት በጥራት ማን ይሻለል?



በዛሬው ፅሁፌ በቅርቡ በዘመቻ መልክ የሚካሄደውን የግል ትምህርት ቤቶች ውግዘት አሰመልክቶ አንድ አንድ ሃሳቦች መሰንዘር እፈልጋለሁ፡፡ ይህ የግል አስተያየት በቅጡ ውይይት ማደረግ የሚፈልግ ካለ በይፋ መድረክ ላይ መነጋገር የምችልበት በፅኑ የማምንበት አቋም ነው፡፡ በተለይ በቴሌቪዥን “ማያ” በሚባል ፕሮግራም ላይ ሲቀርብ የነበረው ተከታታይ የግል ትምህርት ዘርፍ ጠል የሆነ አቀራረብ ፕሮግራሙን አስቀያሚ አድርጎታል ብዬ እንዳምን አድርጎኛል፡፡ በዚህ አጋጣሚ የፕሮግራሙ አቅራቢ ልጁን የትኛው የመንግሰት ትምህርት ቤት እንደሚያስተምር በይፋ ለህዝብ እንዲገልፅ እጠይቃለሁ፡፡ ያለበለዚያ ግን ልጁን የግል ትምህርት ቤት እየለካ የዚህን ዓይነት ፕሮግራም ማዘጋጀት አሰነዋሪ ነው፡፡ ልጅ ከሌለው ደግሞ በዚህ ደረጃ በማያውቀው ጉዳይ ባይገባ ይመከራል፡፡ እደግመዋለሁ “ልጆቹን የት የመንግሰት ትምህርት ቤት እንደሚያስተምር ለህዝብ በይፋ መግለፅ እና ምሳሌ መሆን ይኖርበታል”፡፡
በመጀመሪያ ከግልና ከመንግሰት ትምህርት ቤት የቱ ይሻላል? ከባድ ጥያቄ አይደለም፡፡ በብዙ እጥፍ የግል ትምህርት ቤት ይሻላል፡፡ ለምን? ብሎ በመጠየቅ እና ተገቢውን መልስ በመስጠት የመንግሰት ትምህርት ቤቶች ወደ ግል ትምህርት ቤቶች ደረጃ ለማሳደግ የሚደረግ ጥረት ካለ ይህን ለማሳካት ይረዳል የሚል እምነት አለኝ፡፡
በእኔ እምነት የግል ትምህርት ቤቶች በሚከተሉት ሁኔታዎች የተሻሉ ናቸው፤
1)  የወላጅ - ትምህርት ቤት መገናኛ መፅኃፍ ማዘጋጀት እና መጠቀም፡፡ ይህ የግንኙነት መስመር የዕለት ከዕለት ነው፡፡ የልጆች ትምህርት ቤት ወሎን፤ ምን የቤት ስራ እንደተሰጠ፣ ልጆች በዕለቱ በምን ዓይነት ሁኔታ ውስጥ እንደነበሩ፣ ጤናቸውን ጨምሮ፣ ሌሎች ጠቃሚ መረጃዎችን መምህር ለወላጅ መልዕክት ይልካል፡፡ ወላጅ መልዕከቱን ማየቱን በፊርማው ያረጋግጣል፡፡ በዚህ ሁኔታ ወላጆች ልጆቻቸውን እንዲከታተሉ የሚያደርጉ ሲሆን የመንግሰት ትምህርት ቤቶች የዚህ ዓይነት ስርዓት ያላቸው መኖራቸውን አላውቅም፡፡ መንግስት የወላጅ ትምህርት ቤት የግንኙነት የሚያጠናክር ማስታወሻ መፅኃፍ በማዘጋጀት እና ተግባራዊነቱን በመከታተል በቀላሉ ሊያደረገው የሚችል ቀላል ግን እጅግ አስፈላጊ ነገር ነው፡፡ ወላጆች/የወላጅ ኮሚቴዎች በወርና በሶሰት ወር ከሚያደርጉት ሰብሰባ እጅጉን የተሻለ ነው፡፡

2)  የግል ትምህርት ቤቶች የእንግሊዘኛ ቋንቋን በተሸለ ሁኔታ ሰለሚያስተምሩ ቋንቁ የሚችሉ ልጆች ደግሞ ማነኛውንም የመረጃ ምንጭ በቀላሉ እንዲጠቀሙ ያደርጋቸዋል፡፡ በዚህ ዘመን ደግሞ መረጃ የእውቀት መሰረት ነው፡፡ ይህንን እጅግ አስፈላጊ የእውቀት መሰረት የሆነን ቋንቋ ወላጆች ለምን ትኩረት ሰጡት ብሎ ክስ የሚያቀርቡ የመንግሰት ትምህርት ቤቶች ዳይሬክተሮች ትምህርት ምን ማለት እንደሆነ የገባቸው አይመሰለኝም፡፡ እዚህ ነጥብ ላይ አንድ የግል ምሳሌ መግለፅ እፈለግጋለሁ፡፡ ልጆቼን ከማስተምርበት ትምህርት ቤት ልጆቾ “በአማርኛ” ወይስ “በእንግሊዘኛ” እንዲማሩ ይፈልጋሉ? ምክንያቶን ያስቀምጡ የሚል እና ሌሎች መጠይቆች ቀረቡልኝ፡፡ ይህን ጥያቄ ከልጄ ጋር መወያየት ስለነበረብኝ ተነጋገርን፡፡ በእንግሊዘኛ መማር እንደሚፈልግ አስረግጦ ነገረኝ - በወቅቱ የአምስተኛ ክፍል ተማሪ ነበር፡፡ ለምን ብዬ ሰጠይቀው “ዓለም አቀፍ” መሆን ሰለምፈልግ አለኝ፡፡ ከዚህ የተሸለ መልስ እኔም አልነበረኝም እና ይህንኑ ሞልቼ ላኩኝ፡፡ አሁን በዘማቻ የተያዘው ነገር “በአፍ መፍቻ ቋንቋ” በሚል ፈሊጥ ልጆቻችን በአማርኛ ይማሩ የሚል የጥቂቶች ጩኽት በመርዝ የተቀባ መሆኑን ለማወቅ ነብይ መሆን አያሰፈልግም፡፡ አዲስ አበባ የአፍ መፍቻ ቋንቋ አማርኛ ነው ያለው ማነው? ወላጆች የአፍ መፍቻ ቋንቋ የሚሉት ካላቸው ልጆችን የት ማስተማር እንዳለባቸው መወሰን ያለባቸው እነርሱ ናቸው፡፡ ከላይ በጠቀስኩት የቴሌቪዝን ፕሮግራም ላይ አንድ የግል ትምህርት ቤት ተወካይ ፈራ ተባ እያለች “የአፋር ልጅ” በምን ይማር? አማርኛ አይችልም ብላለለች፡፡ እኔም እላለሁ በአዲስ አበባ “ሶማሌም” አለ፣ “ኦሮሞ” አለ፣ “ትግሬ” አለ፣ ወዘተ ለምን ሲባል አማርኛ ብቻ እንባላለን፡፡ ከዚህ ጋር በተያያዘ በግል ትምህርት ቤቶች ተለጠፈ የሚባሉት ማስጠንቀቂያዎችን ይመለከታል፡፡ “አማርኛ መናገርና  …… ያስቀጣል” የሚለው ሲሆን መልዕክቱ በዚህ መልክ ባይለጠፍ ጥሩ ነው፡፡ ልጆቻችን ግን የእንግሊዘኛ ቋንቋ ለማዳበር ያላቸው አንዱና ዋነኛው ቦታ በትምህርት ቤት ውስጥ እንግሊዘኛ ቋንቋን እንዲጠቀሙ በማበረታት/በማስገደድም ነው፡፡ ይህን በጎ ነገር አይቶ ማስጠንቀቂያው እንዲስተካከል ከመምከር ይልቅ ይህንን በመጥፎ ጎኑ በመተረክ የግል ትምህርት ቤቶችን ማሸማቀቅ ምን ያህል ይጠቅማል? ስንት ወላጆች ልጆቻቸው ቋንቋ እንዲለምዱ ቤት ውስጥ መርዳት ይችላሉ? ለማነኛውም ወላጆች በፍፁም ያልተሳሳትነው፤ ነገር ግን የመንግሰት ትምህርት ቤት ዳይሬክተር ነን ብለው በቴሌቪዥን የቀረቡት ሰዎች እና አቅራቢው ጭምር የተሳሳቱት “እንግሊዘኛ ቋንቋ” ልጆቻችን እንዲማሩ ስንወስን ይህ ችሎታ ለማህበራዊም ሆነ ለተፈጥሮ ሳይንስ አውቀት ለማግኘት መሰረት ሰለሆነ ነው፡፡ በግሌ ኢትዮጵያ ውስጥ ዩኒቨርስቲዎች የሚያስተምሩት በአማርኛ ቢሆኑ ልጆቼን በአማርኛ ብቻ ለማስተማር፣ በኦሮምኛ ቢሆን ኦሮምኛ ለማስተማር ብዙ ላልቸገረ እችላለሁ፡፡ ግን ልጄ ዓለምአቀፍ እሆናለሁ ሲለኝ በፍፁም አይቻልም ብዬ ልሞግተው አልችልም፡፡ ምርጫ የልጆች ሲሆን ይህን ምርጫ ማገዝ የእኛ የወላጆች መሆኑን ማወቅ ይኖርብናል፡፡ እስኪ ባለፉት 20 ዓመታት በአፍ መፍቻ ቋንቋ ተምረው ምደርን ያንቀጠቀጡ ልጆች በምሳሌነት አቅርቡልን፡፡
3)  የግል ትምህርት ቤቶች ለተማሪዎች ተጨማሪ የመርጃ መፅኃፍት ያቀርባሉ(ከህንድ፣ ከእንግሊዝ፣ ከአሜሪካ ወዘተ)፡፡ በዚህ መስመር የሚታየው ነገር መሰረቱ ምቀኝነት የሚመስል ነው፡፡ በግል እምነቴ ሰታንዳርድ ማለት ዝቅተኛው እንጂ ከዝቅተኛው የሚበልጥ ክልክል ነው ማለት አይመስለኝ፡፡ የግል ትምህርት ቤቶች ለተማሪዎች የሚሰጡት ትምህርት ከተቀመጠው ስታንዳርድ አንሶ ከተገኘ ተጠያቂነት መኖር አለበት፡፡ ከዚያ ከበለጠ ግን ያነሰውን እንዴት ከፍ እናድርግ ከሚለው ሃሳብ ይልቅ እንዴት ከፍ ያለውን የግል ትምህርት ቤት ውጤት እናውርድ አሳፋሪ የሆነ ነገረ ነው፡፡ እያዩ ፈንገስ “ርሃብህ የሚነሳው፣ የጎረቤትህን መጥገብ ሲያይ ከሆነ ርሃብህ ምቀኝነት ነው” ብሎናል፡፡ አሁንም በቅጡ ተጨማሪ የትምህርት መርጃ መፅሃፍት እና ሌሎች ቁሶችን ማቅረብ መከልከል ተገቢ አይደለም፡፡ ወላጆች ልጆቻቸው በመንግሰት ትምህርት ቤት ከሚሰጠው ያነሰ ትምሀርት እያገኙ ተጨንቀው ተጠበው በውድ ዋጋ ያስተምራሉ ማለት የወላጆችን ውሳኔ እና የውሳኔ መስጠት አቅም መናቅ ነው፡፡ በዚህ ጉዳይ በጣም የሚያስገርመው የትምህርት ቢሮ ተወካይ፣ ሃላፊ ሆነው የሚፎክሩብን ሰዎች አለቆቻቸው ልጆቻቸውን የት እንደሚያስተምሩ የማያውቁ ይመስላል፡፡ ከዚህ አንፃር በመግቢያዬ ላይ ያቀረብኩ ጥያቄ ለትምህርት ቢሮ ሃላፊም ማቅረብ እፈልጋለሁ፡፡ ክብሩ በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የትምህርት ቢሮ ሃላፊ ልጆን የትኛው የመንግሰት ትምህርት ቤት እንደሚልኩ ቢነግሩን?
4)  የግል ትምሀርት ቤቶች በአብዛኛው በዲግሪ ደረጃ የተመረቁ ናቸው፡፡ ይህ ደግሞ ለትምሀርት ጥረት ወሳኝ ግብዓት ነው፡፡ የመምህራን ጥራት በተመለከተ ትምህርት ቢሮ መምህራን በሙሉ ከመምህራን ማስልጠኛ መውጣት አለባቸው ይላል፡፡ በሀገራችን መመህራን ማስልጠኛ የሚገቡት በትምህርት ውጤታቸው በምን ዓይነት ደረጃ ያሉት እንደሆኑ ይታወቃል፡፡ እነዚህ መምህራን በሌሎች ዮኒቨርሲት ከሚመረቁት ምሩቃን በተወሰኑ የፔዳጎጂ ትምህርት ልዩነት እንዳላቸው ይታወቃል፡፡ ይህን ክፍተት በአጭር ጊዜ ስልጠና በመሙላለት ምሩቃኑን አስተማሪ ማድረግ ግን ይቻላል፡፡ ለዚህ ትክክለኛ ማሳያው በዩኒቨርሲቲ ከፍተኛ ውጤት የሚያመጡ (ሰቃይ) ተማሪዎች በአስተማሪነት አይሰለጥኑም ነገር ግን ዩኒቨርስቲ በአስተማሪነት አሰቀርቶ አስተማሪ ያደርጋቸውል፡፡ በዩኒቨርሲት እያሰተማሩ ሌላ ቦታ ማስተማር አይችሉም ማለት ሰህተት ነው፡፡ እነዚህን ተመራቂዎች በተወሰነ ደረጃ ማስልጠን ያስፈልጋል በሚለው መስማማት ይቻላል፡፡
5)  በግል ትምህርት ቤቶች የሚማሩ በአንድ ክፍል የሚገኙ ሁሉም ተማሪዎች ተመሳሳይ ትምሀርት መማራቸውን ለመከታተል የሚረዳ እና ተከታታይ ምዘና ለማድረግ የሚያግዝ ወርክ ሽቶች በየዕለቱ ያገኛሉ፡፡ ወላቸጆችም ይህን ለመከታተል የሚችሉበት አስራር አለ፡፡ ይህ አስራር ለተማሪዎች እጅግ ጠቃሚ የማጥኛ ዘዴም ጭምር ነው፡፡ ይህ በወላጆች ተሳትፎም ቢሆን በመንግሰት ትምህርት ቤቶች ቢተገበር እጅግ ጠቃሚ ነው፡፡ ይህን ማንም ሲቃወም አላያሁም ግን ወደ መንግሰት ትምህርት ቤት እንዴት ይምጣ ? የሚለው ሲነሳ አልሰማሁም፡፡
6)  በግል ትምህርት ቤቶች እሰከ አሁን ባለኝ መረጃ በአንድ ክፍል ውስጥ ከ30 ተማሪ በላይ የለም፡፡ ይህ መምህሩ ተማሪዎቹን ለመከታተል እና ለመርዳት ያግዘዋል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ ረዳት መምህራን አሉ፡፡ በመንግሰት ትምህርት ቤት እሰከ አሁን ያልተሳካው በክፍል 50 ተማሪ ማድረግ ነው፡፡ ይህ በመምህሩ ላይ የሚፈጥረው ጫና እንደተጠበቀ ሆኖ ለክትትልም አይመችም፡፡
7)  በግል ትምህርት ቤቶች ተማሪ ከትምህርት ቤት በፍፁም መቅረት አይቻለም፡፡ ታሞ የቀረ የህከምና ማስረጃ ማቅረብ ግዴታ ሲሆን ወላጆች የልጃቸውን ከትምህርት ቤት መቅረቱን በእለቱ በስልክ ተደውሎ ምክንያት ይጠየቃሉ፡፡ ይህ ክትትል ልጆች በመሃል አልባሌ ቦታ እንዳይውሉ ያግዛል፡፡ በተደጋጋሚ የሚቀር ተማሪ ከትምህርት ቤቱ ይባረራል፡፡ ሰለሚከፍል ተብሎ ትምህርት ቤት አይቆይም ይህ ክትትል መቼም በመንግሰት ትምህርት ቤት ለማድረግ የሰልክ በጀት ብቻ ነው የሚያስፈልገው፡፡

ከላይ የዘረዘርኳቸው ነጥቦች በጎ በጎዎች ናቸው፡፡ ብዙ ችግሮች እንዳሉ አውቃለሁ፡፡ ወደዚያ ዝርዝር ያልገባሁት የፕሮግራም አቅራቢዎች በበቂ ለመክሰሻነት ያቀረቡት በመሆኑ ነው፡፡ እዚህ ግን መነሳት ያለበት የግል ትምሀርት ቤቶች እጅግ አሳሳቢ የሆነ የቦታ ችግር አለባቸው፡፡ ሰፊ ቦታ ለማግኘት አጅግ ውድ የሆነ የቤት ኪራይ መክፈል ስለሚኖርባቸው የትምህርት ክፍያዎች በአብዛኛው ኢትዮጵያዊ ከመክፈል አቅም በላይ እየሆኑ ሲሆን ወላጆች ይህን ለማሟላት ሲሉ በከፍተኛ ጭንቀት ላይ መሆናቸው ይታወቃል፡፡ መንግሰት የምር ለዜጎች ጭንቅና ለአዲሱ ትውልድ መፍትሔ ለማምጣት የሚጨነቅ ከሆነ ለመንገሰት ትምህርት ቤቶች እንደሚያደርገው ሁሉ ለግል ትምህርት ቤቶችም በዝቅተኛ ዋጋ ወይም ደግሞ በነፃ የትምህርት ቤት መገንቢያ ቦታ ሊሰጣቸው ይገባል፡፡ ለምሳሌ በነፃ ለትምህርት ቤት ግንባታ የተሰጠ ቦታ በምንም መልኩ ወደሌላ ቢዝነስ የማይለወጥ እንዲሆን የሚያስችል ህግ ሊያወጣ ይችላል፡፡ ከዚህም በላይ በነፃ ቦታ ያገኙ የግል ትምሀርት ቤቶች የተወሰኑ ተማሪዎችን ከዝቅተኛ የህብረተሰብ ክፍል በነፃ እንዲያስተምሩ ሊያስገድድ ይችላል፡፡ ይህ መንግሰት በእጁ ያለ የግል ዘርፉን ሊያግዝበት የሚችልበት ነው፡፡ ተመቸኝ ብሎ በቴሌቨዠን ቀርቦ ግን ተገቢ ያልሆነ ክስ መስጠት ግን ብዙ ጥቅም የለውም፡፡ አሁን በግል ትምህርት ቤቶች ላይ የተያዘው ዘመቻ በምንም መልኩ የመንግሰት ትምህርት ቤቶችን አያጠናክርም፡፡ ይልቁንም ወላጆች በመንግሰት ቁጥጥር ወደማይደረግባቸው “ኮሚኒቲ” ትምህርት ቤቶች እንዲያዘነብሎ፣ ካልሆነም ውጭ ልከው እንዲያስተምሩ ከመገፋፋት ውጭ ትርፍ የሚኖረው አይደለም፡፡ ለማነኛውም ሁላችንም የመንግሰት ትምህርት ቤቶች እንዲት ወደ ግል ትምህርት ቤቶች የጥራት ደረጃ ይድረሱ ለሚለው ጠጠር ብንወረውር የተሻለ ነው፡፡ የግሎቹን እንዴት ወደ መንግሰት ትምህርት ቤቶች ደረጃ እናውርዳቸው ከማለት ይልቅ፡፡