Wednesday, April 2, 2014

የኑሮ ውድነት ሽክም የጫነብን ማን ይሆን? ግርማ ሠይፉ ማሩ



በሀገራችን የኑሮ ውድነት ከእለት እለት እየከፋ የድሃውን ህዝብ ጉስቁልና እያበዛ እንደሆነ ነጋሪ የሚያስፈልግ አይመስለኝም፡፡ በቤተ መንግሰትና አካባቢ የሚኖሩት ይህ ጉዳይ አይመለከታቸውም፡፡ ለዚህ የኑሮ ውድነት አንዱ እና ዋነኛው ምክንያት የዋጋ ንረት መሆኑን ብዙዎች ይረዳሉ የሚል እምነት አለኝ፡፡ ዛሬ ለፅሁፌ ዋና ማጠንጠኛም የማደርገው የዋጋ ንረት ምንስዔው ምን እንደሆነ በተለይ የመንግሰት ሚና ከዚህ አንፃር ምን እንደሆነ ማስረዳት ነው፡፡
በእኔ አረዳድ በአቅርቦት እጥረት ምክንያት የሚከሰት የዋጋ ንረት አቅርቦቱ ሲሻሻል እንደሚቀንስ በሀገራችን እንደ ሲሚንቶ ያለ ጉልዕ ማስረጃ ማቅረብ አይቻልም፡፡ ከወጣበት ጣራ ወርዶ ትክክለኛም ባይሆን ጥሩ የሚባል ደረጃ ደርሶዋል፡፡ ጊዜው መቼ እንደሆነ ባላስታውሰውም በደርግ መንግሰት ማስታወቂያ ሚኒስትር የሚታተም አንድ መፅሄት “ወደ ላይ ተወርውራ የቀረች ኳስ” ብሎ በሀገራችን ዋጋ ከናረ የማይመለስ ነገር እንደሆነ መጣጥፍ ማቅረቡ ትዝ ይለኛል፡፡ እንደምሳሌ የተጠቀመው ግን አንድ ብር የነበረ ውስኪ ሦሰት ብር ገባ የጠርሙስ ውስኪ ዋጋ ቢቀንስም የመለኪያው አልቀንስ አለ የሚል ነበር፡፡ ይህ ግን የኛ ችግር አይመስለኝም፡፡ የእኛ ችግር ስኳር ቢቀንስ፤ ዱቄት ቢቀንስ፤ ወዘተ የሻይና የኬክ ብሎም የዳቦና ማኪያቶ ዋጋ ይቀንሳል የሚል ተሰፋ የለንም፡፡ ተስፋችን ለምን ጠፋ? ማን አጠፋው? የዚህ ፅሁፍ ማጠንጠኛ ይሆናል፡፡
ገዢው ፓርቲ ኢህአዴግ ወደ መቃብር ካልወረደ ወይም አሁን ያሉተ ሰዎች መቃብር ከመውረዳቸው በፊት የዚህችን ሀገር የመሬት ስሪት የሚለውጥ ነገር ለህዝብ ይዘው በመቅረብ ይህን ጉዳይ ከህገ መንግሰት ድንጋጌነት ማውጣት የሚችሉበትን ዕድል ካልተጠቀሙና ተሰፋ ካልሰጡን ተሰፋችንን ያጠፋው ኢህአዴግ መሆኑ ግልፅ ይሆናል፡፡ አሁን ባለው ሁኔታ ገዢው ፓርቲም እንደሚያምነው አብዛኛው ሌባ የተሰባሰበው በመሬት ዙሪያ ነው፡፡ መሬት የመንግሰት ነው፡፡ በፍፁም የህዝብ አይደለም፡፡ በፓርቲ ተመርጠው በመንግሰት የተሾሙት ሌቦች እንደፈለጉ የሚያዙበት የሀብታቸው ምንጭ ነው፡፡ ይህ እንዴት ዋጋ ያንራል ማለት ተገቢ ነው፡፡ ዋጋ ማናር ብቻ አይደለም ህይወትም ያስከፍላል፡፡ አለማየሁ አቶምሳን ልብ ይሏል!!
መንግሰት ዜጎችን እያፈናቀለ በሊዝ የሚቸበችበው መሬት አሁን ባለው ሁኔታ እስከ ሰላሳ ሺ ብር በካሬ ሜትር እየተከፈለበት ነው፡፡ በአዲስ አበባችን፡፡ ይህን በሰላሣ ሺ ብር በካሬ ሜትር የሚገዙ ሰዎች የገንዘብ ምንጫቸው ምንድነው? ብለን መጠየቅ ይኖርብናል፡፡ በህጋዊ መንገድ ያገኘውን ገንዘብ በካሬ ለባዶ መሬት (ወርቅ ውስጡ የሌለ ማለት ነው) ይህን ያህል ገንዘብ ከከፈለ፤ ይህን ገንዘብ ለማስመለስ ግልፅ የሆነው ህጋዊ መስመር መሬቱ ላይ ለሚገነባው ቤት ከፍተኛ ዋጋ መጠየቅ ነው፡፡ ይህ ቤት በሽያጭም ይሁን በኪራይ ውድ ይሆናል ስለዚህ እዚህ ቤት ውስጥ የሚሰጥ አገልግሎት ወይም የሚሸጥ ዕቃም ቢያንስ የቤት ኪራዩን መሸፈን ይኖርበታል፡፡ ስለዚህ ዋጋውን መጨመር የግድ ይላል፡፡ ይህ ትንተና የሚሰራው አዲስ በሚሰሩ በሊዝ ለተገዙ ቤቶች ነው የሚል የዋህ አይጠፋም፡፡ ነገር ግን ቤት አከራዮች አዲሶቹ ዋጋ ሲጨምሩ የድሮዎችም ይህንኑ ተከትለው ነው የኪራይ ዋጋ የሚጨምሩት፡፡ ለምሳሌ በአዲስ አበባ ከተማ ሰርቪስ ቤት በሁለት መቶ ብር ተከራይቶ መኖር የቅርብ ጊዜ ትዝታ ቢሆንም በአሁኑ ሰዓት በምንም ዓይነት አንድ ሰርቪስ ቤት ከሺ አምሰት መቶ በታች ማግኘት አይቻልም፡፡ ከገቢያችን አንፃር ማሰተካከያ ቢሰራለት ይህ ዋጋ አሜሪካን አገር እንኳን እንዲህ ዓይነት ዋጋ የለም፡፡
በቅርቡ ከአንደ ጓደኛዬ ጋር የመኖሪያ ቤት ገንብተው የሚሸጡ ሪል ኤስቴቶች አካባቢ ጎራ ብለን ነበር፡፡ እነዘህ ቤት ገንቢዎች ዋጋቸው በፍፁም በሀገር ውስጥ የምንኖር ዜጎችን ያማከለ አይደለም፤ ቤታችንን መንግሰት አይሰራልንም የምንል ዜጎችም ብንኖርም እጃችን ተጠምዝዞ መንግሰትን ደጅ እንድንጠና የሚያደርግ ነው፡፡ ለእነዚህ ቤቶች መወደድ አንዱ ምክንያት የመንግሰት የሊዝ ፖሊስ እንደሆነ መረዳት ብዙ እውቀት የሚጠይቅ አይደለም፡፡ ከዚህ በተጨማሪ እነዚህ ቤት ገንቢዎች ከቤት ገዢዎች የተጨማሪ እሴት ታክስ ሰብሰበው ለመንግሰት ገቢ ያደርጋሉ፡፡ ከቤቱ ዋጋ አስራ አምሰት ከመቶውን የያዘው ለመንግሰት የሚከፈለው ታክስ ነው፡፡ ሌላው የታዘብኩት ነገር ደግሞ ለዋጋ ንረቱ ከሊዝና ታክስ በተጨማሪ ሌላ አቁስል ምክንያት መኖሩ ነው፡፡ ከጋደኛዬ ጋር ቤቱን መግዛት እንዳለብን ከምታግባባን የሽያጭ ሰራተኛ ማዶ ሌላ ሽያጭ ሰራተኛ ሁለት ሴቶችን ከፊት ለፊቷ አሰቀምጣ ቤቱን እንዲገዙ በተመሳሳይ ዝርዝር መረጃ ሰጥታ የማግባባት ሰራዋን ሰታጠናቅቅ፤ በዋጋው ውድነት ብስጭት በማለት የተለያየ ሃሳብ መሰንዘር ይጅምራሉ አንዷ ግን እንደ መፍትሔ ሃሣብ አቅረበች “አንገዛም ማለት አለብን!!” አለች፡፡ ልክ ነበረች ገዢ ሲጠፋ ዋጋ መቀነስ የታወቀ የንግድ ሰርዓት ውስጥ የሚወሰድ እርምጃ ነው፡፡ ትክክለኛ የገበያ ህግ በሚሰራበት ሀገር ማለቴ ነው፡፡ ጓደኛዋ ግን በዚህ መፍትሔ አልተስማማችም እንዲህ አለች “ምን መሰለሽ እዚህ ሀገር ብዙ በህገወጥ መንገድ ገንዘብ የሚያገኙ ሰዎች አሉ፤ እነርሱ ደግሞ በህገወጥ መንገድ ያገኙትን ገንዘብ ህጋዊ ማድረጊያ መንገዳቸው አንዱ ቤት መግዛ ነው” ብላ ተጨማሪውን የዋጋ ንረት ምንጭ ነካችው፡፡
ቤት ገንቢዎች ለምን ቤቱን አስወደዱት ብዬ እንደማልከሳቸው ማወቅ አለባቸው ግን በፍፁም ልክ ያልሆነ ነገር በእግረ መንገድ ላስቀምጥ “ይህን ያህል ካሬ ሜትር ቤት በዚይን ያህል ዋጋ” ብለው ማስታወቂያ ሰርተው ለመግዛት የሚሄደው ሰው ግን የሚያገኘው ሰባ ከመቶ አይሆንም፡፡ ምን ነው ? ሲባል ለመኪና ማቆሚያ፤ ለመተላለፊያ፤ ለሊፍት፤ ለጋራ አገልግሎት፤ ወዘተ የሚሉ ቦታዎች ተደምረውበታል ይባላል፡፡ ይህ ምን ያህል ቤት ፈላጊዎችን እንደሚያሳስት ግን ከሻጮቹም የተሰወረ አይደለም፡፡ ማስታወቂያው ሀቅን መሰረት ያድርግ!! ለቤት ገንቢዎች በእግረ መንገድ ያለኝ ምክር ነው፡፡
በዚህች ሀገር የገበያ ህግ እንዳይሰራ እነዚህ ህገወጦች በቀጥታ በጉቦ፣ አገልግሎት በመንፈግ የሚያደርሱብን ጉዳት አልበቃ ብሎዋቸው ሰርቀው ያገኙትን ገንዘብ ህጋዊ ለማድረግ ምስኪን ዜጎች ማረፊያ እንዳይኖረን የሚያደርጉት አስተዋፅኦ እንዲሁም ለዚህም ዋነኛው ተባባሪ በውድ መሬት የሚቸበችበው መንግሰት መሆኑ ታሰቦኝ፤ እንደ አዲሰ እውቅት መብገን ጀመርኩና እናንተም ትበግኑ ዘንድ ነው ይህን ላካፍላችሁ የወደድኩት፡፡ እንግዲ ይህ ገፊ ምክንያት ሆኖን የመሬት ሰሪቱ በዕለት ከዕለት ኑሮዋችን መጥቶ እያሰቃየን ነው ብልን ለለውጥ ካልተነሳን፣ ሌላ ምን በቂ ምክንያት ነው የምንጠብቅው? የሚለው ጥያቄ በእንጥልጥል የሚቆይ ነው፡፡
በህጋዊ መንገድ መሬት የሚፈልጉ ሰዎችም ከህገወጦቹ ጋር ነው ግብ ግብ የሚያያዙት፡፡ ለዚህም ዋናው ምክንያት የቁጥ ቁጥ መሬት አቅርቦት ፖሊስ ነው፡፡ መንግስት የመሬት አቅርቦቱን ሆን ብሎ እያሳጠረ፤ ሌቦቹ እንዲመቻቸው ዕድል እንዲፈጠር እያደረገ ነው፡፡ መሬት በመግቢያዬ እንዳልኳችሁ የመንግሰት ነው እንጂ በፍፁም የህዝብ አይደለም፤ ህዝብማ በመንግሰት እጅ በተያዘ መሬት ሰበብ የሻይና ማኪያቶ ዋጋ ላይ ጭምር ጫና የሚፈጥር ሆኖበታል፡፡ የዚህ መሬትን በመንግስት እጅ የማቆየት ፖሊስ ዋናው ገፊ ምክንያት ፖለቲካም መሆኑን መዘንጋት የለብንም፡፡ መሬቱን ይዞ የሊዝ ሂሣብ ሳይከፍል፣ ተጨማሪ እሴት ታክስ ሳይኖርበት፣ ግብዓቶችን ከቀረጥ ነፃ አሰገብቶ ኮንዶሚኒየም በርካሽ እሰራላሁ እያለ ለዚህም በስልጣን መቆየት አለብን እያለ ይገኛል፡፡ ገዢው ፓርቲ፡፡ ዋናው ፖለቲካዊ ግቡ በስልጣ ገዢውን ፓርቲ ማቆየት ነው፡፡ ይህ ገዢ ፓርቲ በስልጣን ላይ ከቆየ ገዢ መደቦች እየሰረቁ ገንዘብ ያገኛሉ፤ በስርቆት ያገኙትን ገንዘብ ደግሞ በውድም ቢሆን መሬት በመግዛት ዘላቂ ጥቅማቸውን የሚያስጠብቅላቸው በኢኮኖሚ ደንዳና የሆነ ሰርዓት ይገነባል ብለው ያምናሉ፡፡ ይህች ፍልሰፍና ግን የብዙሃኑን ተጠቃሚነት በጎዳ መልኩ ስለሆነ እየተሰራ ያላው በምንም መልኩ ሊሳካ የሚችል አይደለም፡፡ በአሸዋ ላይ የተሰራ ቤት ዓይነት  ነው፡፡ አውሎ ንፋስ አይጠብቅም ትንሽ ንፋስ ጠራርጎ ያፈርሰዋል፡፡ ልብ መግዛት ያለብን ይመስለኛል፡፡
ፅሁፌን ከዘጋው በኋላ ዋጋው በአቅርቦት መሻሻል ይቀንሳል ብለን ተሰፋ ያደረግነው ሰኳርም ቢሆን የዋጋ ጭማሪ ያደረገ መሆኑን በሬዲዮ ሰማው፡፡ ይህ ምንም አያስገርምም፡፡ የሚያስገርመው መግለጫ የሰጡት ኃላፊ ማብራሪያ ነው፡፡ የዋጋ ጭማሪ የሚባል ነገር የለም፡፡ ነገር ግን ለትራንስፖርት ተብሎ ዘጠና አምሰት ሳንቲም በኪሎ ተጨመረ እንጂ፤ የዚህ ምክንያት ደግሞ ቀደም ብሎ ሰኳሩ ከውጭ ስለሚመጣ ከጅቡቲ በቀጥታ ይገባ ስለነበር ነው፡፡ በማለት ቀደም ሲል ስኳር የትራንሰፖርት ወጪ የለበትም የሚል መንፈስ ያለው መግለጫ ሰጡ፡፡ ይህ መግለጫ ህዝቡን እንዴት እንደናቁት ከማሳየት ውጪ አንድም የእውቀትና እውነት መሰረት የለውም፡፡ የዋጋ ጭማሪ አይደለም የትራንሰፖርት ነው!! ምን የሚሉት ፌዝ ነው፡፡ ዋጋ እንዴት ነው የሚተመነው? ፋብሪካው ይህ የመጀመሪያ ምርቱ ነው? እሰከዛሬ ትራንስፖርት ማን ነበር የሚሸፍነው? መግለጫውንም ሁሉንም ትተን አሁንም ቢሆን በተጨመረው ዋጋ ስኳሩ የታለ ነው? ያለው ጭማሪውን ዋጋም ጨምሮ ይገዛል፡፡ የሌለው ድሮ ከሚገዛው መጠን ቀንሶ ይገዛል፡፡ በተለይ የመንግሰት ሰራተኛው በቅርቡ የትራንሰፖርት ዋጋ ተጨመረበት፣ አሁን ደግሞ የስኳር ማጓጓዣ ተጨመረበት፣ ቀጥሎ ስኳርን ተከትሎ ዳቦ ይጨምራል ወዘተ.. ደሞዝ ግን እንዳለች ነው፡፡ መፍትሔው ልጆችን ስኳር ለጤና ጥሩ አይደለም ብሎ ማስተው ነው፡፡ ዳቦ እንዴት ተብሎ ይከለከል ይሆን?
ታስታውሱ እንደሆነ የተለያዩ ምክንያቶችን እየደረደረ ዋጋ ይጨምር የነበረው ሙገር ሲምንቶ ፋብሪካ አሁን ዋጋ መቀነሱን ማስታወቂያ ከፍሎ እየነገረን ነው፡፡ ምክንያቱም የመንግሰት ያልሆኑ ተወዳዳሪዎች ስለመጡበት እና እየመጡበት ስለሆነ ነው፡፡ ስኳር ይህን እድል እንዳያገኝ ማዕቀብ ያደረገብን መንግሰት ነው፡፡ ሁሉም ፋብሪካ እኔ እስራለሁ ብሎ፡፡ ቢሰራውም ዋጋ አይቀንስም፡፡ ለምን? የሚታለብ ላም ነው ይለናል፡፡ ስለዚህ ይህን የኑሮ ውድነት የጫነብን እየጫነብንም ያለው፣ በመንግሰት ስም የተቀመጠው የአብዮታዊ ዲሞክራሲ ዘራፊ ቡድን ነው፡፡ ቸር ይግጠመን፡፡

Sunday, March 23, 2014

በግፊያ የሚነሱ አሉ…… በግፊያ የማይነሱትስ?



ግርማ ሠይፉ ማሩ
ለዚህ ፅሁፍ የሚሆን ርዕስ ያቀበለኝ ዶክተር ምህረት ደበበ ነው፡፡ በቅርቡ ብዙዎች “የተቆለፈበት ቁልፍ” በሚለው መፅሃፉ ነው የምናውቀው፡፡ ከዚያ በኋላም በሸገር ሬዲዮ ከመዓዛ ብሩ ጋር በሚያደርጋቸው ውይይቶች ሬዲዮ እንዳንዘጋ ከሚያደርጉን ጥቂት ሰዎች አንዱ ሆኖዋል፡፡ የኤፍ.ኤም ሬዲዮ ጣቢያዎች የደፋሮች መፈንጫ ሆነው ባሉበት በዚህ አስቸጋሪ ጊዜ ለልብ የሚሆን መልዕክት ከሚያስተላልፉልን አንዱ እንግዳ እንደ ነበር መመስከር ግድ ይለኛል፡፡ በቅርቡ ታዲያ ብዙዎቻችን በግፊ ካልተነሳን በስተቀር ተልዕኮ ኖሮን የምናሳካው ነገር እጅግ አነስተኛ ወይም የሌለ መሆኑን ሲነግረን ነበር፡፡ ይህንን መልዕክት ተንተርሼ ነው ለዛሬ በተለያየ መልኩ በግፊ ሰለመነሳት ለማንሳት እና ሲከፋም ተገፍተው የማይነሱም መብዛታቸው ይህችን ሀገር ምን ያህል ከባድ ፈተና እንደተጋረጠባት ለማሳየት የምሞክረው፡፡
የፖለቲካ ፓርቲዎችና ምርጫ ቦርድ
ምርጫ ቦርድ አሉኝ ብሎ ከሚላቸው 75 ፓርቲዎች ግማሾቹን ደግሞ ደግሞ የሚቆጥራቸው ቢሆኑም ራዕይ ኖሯቸው ሊደርሱበት ወደሚፈልጉት ግብ እንዴት እንደሚደርሱ ሃስበው ይህን ወደ ተግባር ለመቀየር የሚሰሩ ፓርቲዎች ቢቆጠሩ የአንድ እጅ ጣት አይሞሉም፡፡ እነዚህ ፓርቲዎች የሚንቀሳቀሱት ወይ ገዢው ፓርቲ አበል አለ ብሎ ሲጠራቸው፣ አሊያም አንድ የፖለቲካ ትርፍ የሚያስገኝ ኩነት ተገኘ ሲባሉ ነው፡፡ አብዛኞቹ ግን መኖራቸው የሚታወቀው ምርጫ የሚባል ነገር ሲመጣ ነው፡፡ በዚያን ሰሞን አለን ለማለትም ገፊ የሚሆነው ምክንያት ምርጫ ቦርድ የሚያድላት ገንዘብ ሳትሆን አትቀርም፡፡ ከዘህ ውጭ ሌላ ብዙ ገፊ ምክንያት ብናስብም ለእኔ በተግባር የገጠመኝ ግን ከፓርቲ መዝገብ ላለመሰረዝ ምርጫ መወዳደር የግድ ስለሚል ነው፡፡ መሰረዝ የማይፈልጉበትን ምክንያት ግን እዚህ ማንሳት ተገቢ አይደለም በሚል ባልፈው መረጥኩ፡፡ ላነሳው ያልፈለኩት ጉዳይ በእውነቱ ዋነኛው ገፊ ምክንያት እንደሆነ ግን ይታወቃል፡፡ ለአንባቢያን አይመጥንም በሚል ነው የማልፈው፡፡
በግፊ የሚነሱ ፓርቲዎች ለዚህች ሀገር የመድበለ ፓርቲ ሰርዓት ግንባታ የሚመጥኑ እንዳልሆኑ እነርሱም ያውቃሉ ህዝቡም ያውቃል፡፡ ገዢው ፓርቲም በደንብ አውቆ ከግፊ ውጪ እንዳይነሱ ቆመው እንዲከርሙ ያደርጋቸዋል፡፡ ዋናው ግን ቆመው ለመክረም የወሰኑት እራሳቸው መሆናቸውን ሳንዘነጋ ነው፡፡ በኢህአዴግ ማሳበብ ማቆም ይኖርባቸዋል፤ ይኖርብናል፡፡ ለውጥ ለማምጣት ከሆነ ግን ከግፊ ወጥተን በራስ ተነሳሽነት በልምድ ከተሰመረው መስመር ውጭ መንቀሳቀስ ግድ ይላል፡፡
የምርጫ ቦርድ መስሪያ ቤት በተደጋጋሚ ለልዩ ልዩ ጉዳይ ጎራ ብዬ አውቃለሁ፡፡ የሚፈልጉትን ሠራተኛ በመንግሰት የስራ ሰዓት ማግኘት ዘበት ነው፡፡ የቦርዱ አባላት በቋሚ ሰራተኛነት መገኘት ባይኖርባቸው በቀጠሮ ሊገኙ ይችላሉ፡፡ ምን ያደርጋል ቢገኙስ መፍትሔ የሚባል ነገር ሊሰጡ የሚችሉ አይደሉም፡፡ ዝም ብሎ ምርጫ ቦርድን ለመክሰስ እንዳይሆን ማሳያ ላቅርብ፡፡ ነጋዴ ችግር ሲገጥመው ንግድ ሚኒስትር እንደሚሄደው እኛም እንደ ፖለቲካ ፓርቲ ችግር ገጥሞናል መፍትሔ ስጡን ብለን የምንሄደው ምርጫ ቦርድ ነው፡፡ ፖሊስ በየመንገዱ የፖለቲካ ስራ ልንስራ እየከለከለን ነው፤ አዳራሽ የሚያከራዩ ሰዎች ፈቃድ ይሉናል ፈቃድ ሰጪ አካል ደግሞ የለም ምን እናድርግ፤ ማተሚያ ቤት የንግድ ፈቃድ አምጡ ይላል እኛ ነጋዴ አይደለንም ይህን ጉዳይ በአዋጅ መሰረት መፍትሔ ስጡን፤ ወዘተ. ለምርጫ ቦርድ በግንባር ቀርበን ያቀረብናቸው ጥያቄዎች ናቸው፤ አንድም መፍትሔ የለም፡፡ መልሳቸው አነጋግረን መልስ እንሰጣችኋለን ይሉናል፡፡ መልስ ግን የለም፡፡ ይልቁንም በአውራ ፓርቲ መኖር ተገቢነት ላይ በሚቀርብ የገዢው ፓርቲ መድረክ ላይ በተሳታፊነት ይገኛሉ፡፡ ስለዚህ ምርጫ ቦርድ በግፊም አይነሳም ወይም ገፊውን ይመርጣል ማለት ነው፡፡ ምርጫ ቦርድ በአሰተዳደራዊ መስመር አልፈታ ሲለን ነው እንግዲህ ሌላ ተቋም ለመፈተሽ ወደ ፍርድ ቤት የተሄደው፡፡ ፍርድ ቤቶቻችን በግፊ ይነሱ አይንሱ እዚህ ማንሳት አያስፈልግም፡፡ ይደር ብለን እንለፍ፡፡

መንግስት /አሰፈፃሚ አካል
መንግሰት የሚባለው አካል ሰራውን የሚያሰራው የሲቪል ሰርቪስ ወይም የመንግሰት ሰራተኞች በመባል በሚታወቁት በአብዛኛው የባለሞያዎች ስብስብ ነው፡፡ በአብዛኛው እነዚህ ሰራተኞች ጠዋት 2፡30 ወደ ሰራ ገብተው ማታ 11፡30 ከስራ የሚወጡ መሆናቸውን ከግንዛቤ አስገብተን (በቀን ሰምንት ሰዓት ማለት ነው) ይህን ሁሉ ሰዓት በስራ ገበታቸው ተገኝተው የተጣለባቸውን ሃላፊነት ሲከውኑ ነው የሚውሉት ብለን ስናስብ ግን መልሱ አዎንታዊ እንዳልሆነ እንረዳለን፡፡ ለዚህም ነው መንግስት የሚባል አካል የመልካም አስተዳደር ማሻሻያ መርዓ ግብር ብሎ የሚዳክረው፡፡ ግን ለምንድነው እነዚህ ሲቪል ሰርቪስ አገልግሎት የሚሰጡ ሰራተኞች በግፊ ካልሆነ በስተቀር የሚጠበቅባቸውን አገልግሎት ለመስጠት ዳተኛ የሆኑት ማለት ይኖርብናል፡፡ ለማነኛውም ያለግፊ የሚሰሩ ከተሰመረላቸው መስመር ወጥተው የሚያገለግሉ የሉም ማለት አይደለም፡፡ የአብዛኛው መገለጫ ግን በግፊ መነሳት መሆኑ ነው፡፡ ሁላችንም እንደምናውቀው መንግሰት የሚባለውን አካል የሚያዋቅረው እና የሚመራው ደግሞ ገዢው ፓርቲ ነው፡፡ ገዢው ፓርቲ ደግሞ እንቅስቃሴው ጎልቶ የሚታየው ልክ እንደተቃዋሚዎቹ ሁሉ በምርጫ ሰሞን መሆኑ ነው፡፡ ለገዢው ፓርቲ ገፊው ምርጫ የሚሆነው ግን እንደ አብዛኛዎቹ ተቃዋሚዎች ከምርጫ ቦርድ የሚያገኘው ገንዘብ አይደለም፡፡ ከምርጫ ቦርድ የሚያገኘውን ገንዘብ ከህግ አግባብ ውጭ በምርጫ ቦርድ በኩል ለሌሎች ፓርቲዎች እንደሚያድለው እናውቃለን፡፡ ለገዢው ፓርቲ ምርጫ ገፊ የሚሆነው ለመግዛት የሚያስችለውን ውጤት አግኝቻለሁ ብሎ አለማቀፍ ማህበረሰቡን ለማሳመን እንዲቻለው በማሰብ ነው፡፡ ለዚህም ህዝቡን በልማት ስም የልማት አርበኛ ነኝ ብሎ ድምፅ ለማግኘት ያስችለኛል ያለውን ከመሰረት ድንጋይ ማስቀመጥ እስከ የልማት ሰራዎች ሳይጠናቀቁም ቢሆን ምርቃ ለማድረግ ደፋ ቀና የሚለው፡፡ እንግዲህ ሰሞኑን በምርጫ ግፊ እነዚህን ክስተቶች እስኪያነገሸግሸን እንሰማለን፡፡ በነገራችን ላይ የ1997 ምርጫ ውጤትን ተከትሎ ምርጫ እንደዋዛ የማይመለከተው ገዢ ፓርቲ በግፊ የሚሰራቸውንም ቢሆን ህዝቡ አሁን ድረስ እድሜ ለቅንጅት እንደሚል መረጃ አለን፡፡ በተለይ በጉራጌ ዞን ከቅንጅትም አልፎ የአንዳንድ ቅንጅት ግንባር ቀደም ሰዎችን ስም በማንሳት ነው በአካባቢያቸው ሰለሚጀመሩ ልማቶች ምስጋና የሚያቀርቡት፡፡ አዲስ አበባም ቢሆንም ወጣቱን ከአደገኛ ቦዘኔ ከሚል ፍረጃ በማንኛውም ሁኔታ ወጣቱን መያዝ ወደሚል ገዢውን ፓርቲ ያሸጋገረ ገፊ ጉዳይ ምርጫ ነው፡፡ ይህ ወጣቱን የማቀፍ አቅጣጫ አሁንም ተጠናክሮ የቀጠለ ነው፡፡
ገዢው ፓርቲ ግን በግፊ የሚነሳና ቁም ነገር የሚሰራ ነው ተብሎ በብዙዎች ዘንድ አይወሰድም፡፡ በነገራችን ላይ በግፊ የሚነሱ ሰዎችም ቢሆኑ የተለየ ነገር ያደርጋሉ ተብሎ አይጠበቅም፡፡ ገዢው ፓርቲም የሰዎች ስብስብ ነው፡፡ ዶክተር ምህረት ደበበ እንደነገረን ከሆነ “በግፊ የሚነሱ ሰዎች ሰራ ሲቀጠሩ እንዲያከናውኑ ከተሰመረላቸው መስመር ዘለግ አድርገው ሰራ ለመስራት ብዙም ተነሳሸነት የላቸውም፡፡ ስለዚህ ልዩ ፈጠራ በማድረግ ሰራን ለማሻሻል አቅም የላቻውም፡፡ ሰራቸውንም ለመስራት ሁልጊዜ ጎትጓች ይፈልጋሉ በጉትጎታ ደግሞ ፈጠራ የለም፡፡” ነው የሚለው፡፡ ገዢው ፓርቲ ደግሞ የሰዎች ስብስብ ነው ብለናል፡፡ እነዚህ አባላቱ ደግሞ አብዛኞቹ ሰለግል ነፃነት ግድ የሌላቸው ብሎም የሚያደርጉት ነገር ሁሉ በግምገማ እና ግምገማን ተከትሎ በሚከተላቸው ቁንጥጫ ፍርሃት የሚንቀሳቀሱ ናቸው፡፡ ከነዚህ በግፊ ከሚንቀሳቀሱ አባላት ደግሞ አዲስ ነገር መጠበቅ የዋህነት ነው፤ ፈጠራ ከነፃነት የሚመነጭ መሆኑን ልብ ይሏል፡፡
በግፊ የሚነሱ ቡድኖችም ሆኑ ግለሰቦች እሰከተሰመረላቸው መስመር ድረስ ሊሰሩ እንደሚችሉ እሙን ነው፤ ይህም የሚሆነው ገፊው አካል ወይም ሁኔታ በሚያደርሰው የግፊት መጠን እና ገፊው በተገፊው ላይ ባለው ኃይል የሚወሰን መሆኑን መረዳት ይኖርበናል፡፡ የሚገርመው ግን ሀገራችን የሚያስፈልጋት ያለ ግፊ የሚሰሩ ሰዎችና ተቋማት ቢሆንም አሁን ግን በግፊም በደንብ የማይሰሩ ሲከፋ ደግሞ በግፊም የማይነሱ መብዛታቸው ነው፡፡
ስንቶቻችን የሰዓት ፊርማ ባይኖር በሰራ ሰዓት በስራ ቦታችን እንገኛለን? ብሔራዊ የሆኑ የበዓል ቀናት ቅዳሜና እሁድ ሲውሉ የማይበሳጭ ስንቱ ነው? የስራና የፋይናንስ ሪፖርት ማቅረቢያ ጊዜ ባይኖር ሪፖርት የሚባል ነገር ይኖራል ወይ? ተማሪዎች ፈተና ባይኖር ለዕውቀት ብሎ ጥናት ይኖር ነበር ወይ? ወዘተ ብለን ስንጠይቅ በሁሉም መስክ ግፊት የግድ የሚለን ጉዳይ ሆኖዋል፡፡ ይኼ ሁሉ ሆኖ ግን የማይንቀሳቀስ ብዙ ሰው እንዳለ ሳይዘነጋ፡፡
በሀገራችን ጭቆናው በዝቶብኛል የሚለው ዜጋ እጅግ ብዙ ነው፤ ይህ የጭቆና መብዛት ገፊ ሆኖ እምቢ ለነፃነቴ ብሎ ግን የሚነሰው እዚህ ግባ የሚባል አይደለም ነፃነትን ለማግኘት ከጭቆና መብዛት የተሻለ ገፊ ሁኔታ ከየት ሊመጣ ይችላል፡፡ በእኔ እምነት ጭቆና እምቢ የሚባልበት መንገድ አንዱ የምርጫ ካርድ መውሰድ ሲሆን፤ የምርጫ ካርድ ወስዶ የሚመርጠው አማራጭ ካጣ ደግሞ ካርዱን ቤቱ ይዞ በመቀመጥ ጨቋኞችን እምቢ ማለት የግድ የሚል ይመስለኛል፡፡ አብዛኛው ግን አማራጭ ከሌለ ካርድ መውሰድ ምን መልዕክት እንዳለው አይረዳም፡፡ ሌሎችም ጭቆና እምቢ የሚባልባቸው መንገዶች እንዳሉ ባለመዘንጋት ነው፡፡ እምቢኝ ብሎ ቤት ከመቀመጥ ጅምሮ ጎዳና ወጥቶ እምቢ ብሎ እስከመጮህ፡፡ እምቢኝ ለማለት ግፊው አልበቃንም ወይም ቢገፉንም አንነሳም ብለናል ማለት ነው፡፡
በግፊ አልነሳ ያሉትን የህብረተሰብ ክፍሎች፣ ግለሰቦች፣ ቡድኖች፣ አካለት ወዘተ ለመዘርዘር በሃሳቤ ቢመጣም ወደ ዝርዝሩ ገብቼ መሄድ አልፈቀድኩም እሰኪ ይህን ፅሁፍ ለማንበብ እድል የገጠማቸሁ ሁሉ እራሳችሁን ገምግሙት፡፡ በራሳችሁ ተነሳሽነት የምትንቀሳቀሱ ፣ በግፊ የምትነሱ መሆኑን ወይም በግፊም ቢሆን ለመነሳት ባትሪያችሁን የጨረሳችሁ መሆኑን ፈትሹ መልሱን ስታገኙ ቢያንስ በዚህ ዓመት ካላችሁበት አንድ ደረጃ ከፍ ለማድረግ ተግባራዊ እንቅስቃሴ ውስጥ ለመግባት ውሳኔ አድርጉ ግፊን እምቢ በሉ፡፡
ቸር ይግጠመን!!!

Sunday, March 16, 2014

ዜና ውህደት



ዛሬ በመኢህአድ ፅ/ቤት የመኢህአድ እና የአንድነት ፓርቲ የብሔራዊ ምክር ቤት አባላት የጋራ ስብሰባ አድርገው አንድ ወሳኝ ምዕራፍ ላይ ደርሰዋል፡፡ ይህውም ለቀጣይ ሐሙስ መጋቢት 11/2004 ዓ/ም የቅድመ ውህደት ሰምምነት እንዲደረግ እስከ አሁን ውህደቱን ለማዘግየት የተወሰደው ጊዜ ከበቂ በላይ በመሆኑ አጅግ አጭር በሆነ ጊዜ ውስጥ ይህን ጉዳይ አጠናቆ የጋራ ጉባዔውን የሚያመቻች ኮሚቴም በእለቱ ይፋ እንዲደረግ ከስምምነት ተደርሶዋል፡፡ እነዚህ ሁለት ፓርቲዎች ውህድ በሚሆኑበት ወቅት ፈታኝ ይሆናሉ የተባሉ የፕሮገራም እና የደንብ ልዮነቶች የሚባሉት ውሕዱን ፓርቲ የተሻለ ደንብና ፕሮግራም እንዲኖረው ከማድረግ የዘለለ ውህደቱን ለማዘግየት ምክንያት እንዳይደሉ መግባባት ላይ ተደርሶዋል፡፡  የውህዱን ፓርቲ ስያሜ በተመለከተም ተሳታፊዎቹ በአዲስ መሆን እንዳለበት እና ይህም ተጠንቶ ለጠቅላላ ጉባኤ ቀርቦ የሚወሰን እንደሆነ ግንዛቤ ተይዞዋል፡፡ ትልቁ ነጥብ የነበረው በሁለቱም ፓርቲዎች በኩል አመራሮች በምንም ሁኔታ ውህደቱን ለማዘግየት ቢሞክሩ አባላት ተዋሕደው አመራሮች ተንጠልጥለው እንደሚቀሩ በተደጋጋሚ የገለፁ ሲሆን ይህም በከፍተኛ ጭብጨባ ድጋፍ አግኝቶዋል፡፡ እውነት እውነት እላችኋለው ይህ ጉዳይ ከሁለት ወር ባልበለጠ ጊዜ እውን ይሆናል የሚል እምነት አለኝ፡፡ ይህ ከሆነ ደግሞ የፈረሰው ቅንጅት ሶስት አራተኛው እንደተመለሰ ይሰማኛል፡፡ ቸር ወሬ ያሰማን፡፡ የመጋቢት 11 ሰው ይበለን፡፡

የአፍሪካ መሪዎችና አፍሪካዊያን ግርማ ሠይፉ ማሩ



በቅርቡ ለስብሰባ የመካከለኛ አፍሪካ በምትገኘው ካሜሩን ዋና ከተማ ያውንዴ ተገኝቼ ነበር፡፡ ያውንዴ በነበርኩበት ጊዜም አጋጣሚ ሆኖ ማርች 8 ዓለም አቀፍ የሴቶች ቀን የሚከበርበት ስለነበር አከባበሩን አሰመልክቶ የአፍሪካ መሪዎች እንዴት በዓል እንደሚያከብሩ ለመታዘብ ዕድል ሰጥቶኛል፡፡ ለአምባገነንት የሚጠቀሙበት መመሪያም አንድ መሆኑን ለማወቅ ጊዜ የሚወስድ አልነበረም፡፡ በዚህ አጋጣሚ ደግሞ ከጎረቤት ሀገር ተሳታፊዎች ጋር ለመገናኘት እና ለመወያየት ዕድል አግኝቼ ነበር፡፡ በተለይ ከኤርትራዊ ወንድሞቻችን እና እህቶች ጋር የነበረን ቆይታ ከእነርሱ  ከራሳቸው በስተቀር ከኢትዮጵያ የሚለያቸው ነገር የሚያውቅ እንደሌለ አፍጥጦ የሚታይ ሀቅ ነበር፡፡  ከሱማሊያ ከመጣው ወጣት ጋር የነበረን ውይይትም በፍፁም የማይታመን ነበር፡፡ የእኛ ጎምቱ ባለስልጣናት አብረውን ካሉት ጋር እንዴት እንደሚያጋጩን ሲያስላስሉ እዚያ ማዶ ያሉት ግን የእኛ ናፍቆት አላቸው፤ የአብሮነትን ጥቅም በደንብ ተረድተውት እንዴት እንደሚሆን ግን ግራ የተጋቡ ይመስላሉ፡፡ ይህን መፈላለግ ለመግለፅ ግን ከአንድ ጥግ ወደ ሌላ ጥግ መሄድ ለምን እንዳስፈለገን ተወያይተን የደረስንበት በእኛ በህዝቦች መካከል  ምንም የሚያለያይ ነገር እንደሌለ ነው፡፡ ለአብሮነታችን ግን አምባገነኖችን ከመክስስ በዘለለ ሁላችን የበኩላችንን ማድረግ ይኖርበናል፡፡
እንደ መግቢያ
የማርች 8 ባህል በካሜሮን ከተማ ያውንዴ ድል ባለ ሁኔታ ሲከበር የዓይን ምስክር ሆኜ ተመልክቻለሁ፡፡ ባህሉ ያለ ብዙ ወንዶች ተሳትፎ የሀገሪቱ ቀዳማዊ እመቤት በተገኙበት የተከበረ ሲሆን በእኛ ሀገር ለቀዳማዊ እመቤት በዚህ ደረጃ የደህንነት ጥበቃ ሲደረግ አይቼም ሰምቼም አላውቅም፡፡ የባሰ አለ ሀገር አትልቀቅ የሚባለው ይኼን ጊዜ ይመስለኛል፡፡ የማርች 8 በዓልን ለማድምቅ የወጡት ሴቶች እንደኛው ሀገር በመስሪያ ቤት ተደራጅተው የወጡ ሲሆን፤ ከበዓሉ በኋላ ግን እንደ እኛዎቹ ሴቶች ወደቤታቸው ነጠላቸውን በአናታቸው ላይ አድርገው ጠውልገው ሲመለሱ አላያሁም፡፡ በየደረሱበት አረፍ ብለው ቢራ እየተጎነጩ ሲመሽም ተሳክረው በየጎዳናው ሲደንሱ አጀብ የሚያሰኝ ነበር፡፡ ይኼ ነው እኩልነት ብዬ ታዝቤያቸው መጥቻለው፡፡ የሰልፉ ዝግጅት፣ የጦር ሰራዊት ጋጋታው፣ ወዘተ… በሀገራችን የሴቶች ሊግ የሚያደርገው ዓይነት እና በመንግሰት የሚደገፉ ሰልፉች ጋር አንድ ሲሆንብኝ ተሳስቼ መስቀል አደባባይ የተገኘው እንጂ በዚህ ሁሉ ኪሎ ሜትር ርቀት ልዩነት በዚህ ደረጃ መመሳሰል ይኖራል ብዬ ለማመን እራሴን ተጠራጠርኩ፡፡
ኢትዮጵያ (ከኤርትራ እና ያለ ኤርትራ)
ኤርትራዊያን ብዬ ለመፃፍ ወይም ለመጥራት የምር ምቾት አይስጠኝም፡፡ ያራቅኳቸው እኔም ከኢህአዴጎች ጋር ሆኜ አንድ አይደለንም የሚለውን የመደገፍ ሰሜት እየመጣብኝ ይፈታተነኛል፡፡ እንደዚያም ሆኖ ግን አሁን ያለውን እውነት ለመቀበል ስል እንደ ሁለት ሀገር አድርጌ ለመፃፍ እገደዳለሁ፡፡ ልቤ ግን ይህን እያለኝ አይደለም፡፡ ኢትዮጵያ ያለ ኤርትራ፤ ኤርትራም ያለ ኢትዮጵያ መኖር እንደሚችሉ ባሳለፍናቸው ሃያ ዓመታት በላይ የተረጋገጠ እና የተመዘገበ እውነት ነው፡፡ ነገር ግን አብረን ብንሆ ከዚህ የተሻለ ልንሆን እንደምንችል ከምን ጊዜውም የበለጠ አሁን የተሰማን ይመስለኛል፡፡ እኛ ከተከዚ ደቡብ የምንገኝ ህዝቦች አስመራ፣ ምፅዋ ሄደን ለመዝናናት ቢያስፈልግም ሰርተን ለመኖር ከኢሳያስ መሞት ቀጥሎ ከዚህ ከእኛ ሰፈር የአብዮታዊ ዲሞክራሲ መፍረስ የግድ የሚለን ይመስለኛል፡፡ ይህ “ጦርነትም ሰላምም የለም” በሚል ግርግዳ ታጥረን መኖራችን፤ ከአሰመራም ከአዲስ አበባም በኩል የመራራቅን ግድግዳ እያጠናከረ እንደሚሄድ ግን ምንም ጥርጥር የለውም፡፡ በዚሁ ከቀጠልን አዲሱ ትውልድ የእኛን ያህል አስመራንም ሆነ ምፅዋን የመጎብኘት ጉጉቱ ባያድርበት መገረም አይኖርብንም፡፡ በተለይ በአሰመራ በኩል አዲስ ታሪክ በመስራት ፕሮጀክት ውስጥ ኤርትራ በጎረቤት ሀገሯ ኢትዮጵያ ቅኝ ተይዛ እንደነበረ በሰፊው ተፅፎ እየተሰጠ እንደሚሆን መጠራጠር አያስፈልግም፡፡ ከአቶ መለስ እና ጓዶቻቸው በስተቀር እኛም ሳናውቅ አንድ በቅኝ የገዛነው ሀገር እንዳለን በአስመራ በኩል ይመዘገብ ይሆናል፡፡ አቶ መለስ ፅፈውታል ተብሎ የሚታመነው “ኤርትራ ከየት ወዴት?`` የሚለው መፅኃፍ ኢትዮጵያን ቅኝ ገዢ አድርጎ ነው የሚያቀርበው፡፡ የኤርትራ ጉዳይም ከቅኝ ግዣት ነፃ የመውጣት ነው ብለው ነው የደመደሙት፡፡ ለዚህም ነው ኤርትራ ነፃ ሀገር እንድትሆን ቀድመው ደብዳቤ የፃፉት፡፡ እርግጠኛ ነኝ በኢትዮጵያ በኩል ያለው ታሪክ ኤርትራ ከእናት ሀገሯ መገንጠሏን የሚነግር እንጂ በቅኝ ይዘናት የነበረን ሀገር እንዳስረከብን አይደለም፡፡ ለምሳሌ እንግሊዝ ኬኒያን ለቃ እንደወጣችው ዓይነት ማለት ነው፡፡ ለምሳሌ ደቡብ ሱዳን ከሱዳን ተገነጠለች እንጂ ከሱዳን ቅኝ ግዛት አይደለም ነፃ የወጣችው፡፡
የዚህ ፅሁፍ ዓላማም ይህ እየተጠናከረ ወደ አዲሱ ትውልድ በመሄድ ላይ ያለውን የሚያራርቅ ግንብ የኢሳያስንም ሆነ የእኛን አብዮታዊ ዲሞክራሲ ሞትና ግብዓተ መሬት ሳይጠብቅ ህዝብ ለህዝብ በሚደረግ ግንኙነት እንዲጠናከር ማድረግ እንዳለብን ከውስጤ ስለተሰማኝ ፍላጎቱና አቅሙ ላላቸው ሰዎች እረ ጎበዝ አንደ እንበል ለማለት ነው፡፡ ይህን እንዴት ማድረግ ይኖርብናል የሚለው ብዙ ሰዎች ብዙ የሚሉት ነገር እንደሚኖር ባምንም በእኔ ግምት በቅርቡ መጀመር ያለባቸው ብዬ የማምናቸው በማህበራዊም ሆነ በመደበኛ ሚዲያ ወጣቱ ትውልድ በሁለቱ ሀገሮች መካከል ያለውን የባሕል፣ የቋንቋ፣ የሰነልቦና፣ ወዘተ አንድነት የሚያሳዩና አዲሱን ትውልድ ከቀድሞ ጋር የሚያስተሳስሩ ሰራዎችን መስራት የግድ ይለናል፡፡ እንደዚህ ዓይነት ሰራዎች በፍፁም በአንድ ወገን ብቻ የሚሰሩ መሆን የለባቸውም፡፡ የኢየትዮጵያና የኤርትራ ቴሌቭዝኖች እንዲህ ዓይነት መልካም ሰራ ቢጠበቅባቸውም የማያምርባቸው ስለሆነ ከውጭ የሚተላለፉ ለምሳሌ ኢሳት እና “ኢቢሴ” በዚህ ጉዳይ ላይ ቢሰሩ የሚጠቀሙ እንጂ የሚጎዱ አይመስለኝም፡፡ እነዚህ ተግባራት በፍፁም ከፖለቲካ አመለካከት ጋር የሚገናኙ መሆን የለባቸውም፡፡
በውጭ የሚኖሩ ኢትዮጵያዊያን እና ኤርትራዊያን የጋራ ፎረሞችን በማዘጋጀት በአብሮነታችን ዙሪያ ምክክር በማድረግ ከእንደዚህ ዓይነት መድረኮች የሚገኙ ሃሳቦች በሰፊው ህዝቡ እንዲያውቀው በማድረግ የህዝብ ለህዝብ መቀራረብን ልናጎለብት ይገባ የሚል እምነት አለኝ፡፡ ፖለቲከኞች በፈጠሩት ግጭት ባለሞያዎች በሚገናኙበት መድረክ ላይ ለመሳተፍ አንድ ኤርትራዊ አውሮፓ ድረስ ተጉዞ ሶስት አራት ቀን መንገድ የሚያድርበት ቀን ለማሳጠር መሰረት መጣል ያለብን ይመስለኛል፡፡ ይህን ለማድረግ በመግቢያዬ ላይ እንዳልኩት የኢሳያስ መሞትና የአብዮታዊ ዲሞክራሲ መፍረስ ከጠበቅን የመለያየታችን ግንብ በልጆቻችን ውስጥ ሰርጾ መቼ አንድ ነበርን ሊሉን ይችላሉ፡፡

ኢትዮጵያና ሱማሊያ
ኢትዮጵያና ሱማሊያ በሱማሌ ቅኝ ገዜ የነበሩት በተለይ እንግሊዞች በቀበሩት የግጭት መንፈስ የተነሳ በተደጋጋሚ የድንበር ግጭት ብሎም ደም አፋሳሽ የሆነ ሙሉ ጦርነቶች ውስጥ ገብተን እንደነበር እሙን ነው፡፡ ይህን እውነት የምናውቅ የሁለት ሀገር ዜጎች ግን ካሜሮን ላይ ስንገናኝ እንደ ድሮ ሰፈር ልጅ በፍቅር ስንጫወት ነው የከረምነው፡፡ ከሱማሌው ተወካይ መሃመድ ጋር መጀመሪያ የተግባባነው ኢትዮጵያዊ መስሎን ነበር፡፡ እኔን እና መሃመድን የሚለየን መሃመድ ትንሽ  ትንሽ አማርኛ ይሞክራል እኔ ሱማልኛ ስለማልሞክር ይበልጠኛል ማለት ነው፤ መሃመድ ተግባቢ እና በደንብ እንደምናውቃቸው ሶማሊዎች ቴክኖሎጂ የሚወድ ነው፡፡ በእጁ የያዛት ብላክ ቤሪ ስልክ ሁሉንም ወሬ ታቀብለዋለች፡፡ መሃመድ እንደሚለው “ይህች ስልክ ሱማሌ ውስጥ በተለይ በአልሻባብ እጅ ከገባህ ሞት ታስከትላለች” ይላል በተደጋጋሚ፡፡ ቴክኖሎጂን እና ሌሎች የህዝብ መጠቀሚያዎችን በመከልከል አፍነው ሊገዙ የሚንቀሳቀሱ የአልሻባብ ሰዎች በፍፁም ምንጫቸው ሱማሌ እንዳልሆነ እና ከውጭ የመጣ አካራሪነት እንደሆነ ያምናል፡፡ በዚህ ሰበብ ግን በኢትዮጵያ በኩል እየተወሰደ ያለው እርምጃ በደንብ ታስቦበት ካልሆነ የህዝብ ለህዝብ ግንኙነትን እንደሚጎዳ አበክሮ ይናገራል፡፡ እርግጥ ነው አሁን ያለው መንግስት ደካማ ስለሆነ የኢትዮጵያ እርዳታ በተለይ ወታደራዊ ድጋፍ ይፈልጋል፤ እንደዚያም ሆኖ ግን ህዝቡ ይህን ሳይረዳ ይቀርና እንደ ወራሪ ሀይል በመቁጠር አልሻባብን ይቀላቀላል፡፡ ይህ ደግሞ ወደፊት ተባብረን እና ተደጋግፈን  የምንኖርበትን  ጊዜ ያርቀዋል ይላል፡፡ መሃመድ ከዚህ በፊት በኢትዮጵያና በሱማሊያ መካከል የተደረገውን ደም አፋሳሽ ጦርነት በታሪክነት ነው እንዲዘጋ የሚፈልገው፡፡ ይህ ጦርነት “ሁለት አንባገነኖች ንፁዓንን ያስፈጁበት በኋላ ደግሞ እነርሱ የተቃቀፉበት ነበር” ይላል መሃመድ፡፡ ሁለቱም አሁን የሉም ይህን ታሪክ አድርጎ ወደፊት መሄድ ነው ያለብን ነው የሚለው፡፡ በሃያ አንደኛው ክፍለ ዘመን ድንበር አርቴፊሻል ነው ብሎ ያምናል፡፡ ኢትዮጵያዊያኖች ባህር ዳር ሆነው ለመዝናናት ከሞምባሳ የእኛ ይቀርባል ይላል፤ ሶማሌዎችም ኢትዮጵያ ቤታችን ነው ብለው ያምናሉ እንደ መሃመድ እምነት፡፡ ኢትዮጵያዊያን ሁሉን ነገር ትተው በችግራችን ጊዜ እንደ ሀገራችን እንድንኖር ማድረጋቸው በፍፁም የሚረሳ ውለታ እንዳልሆነ ነው መሃመድ የሚተርከው፡፡
መሃመድ ይህን ሁሉ ባጫወተኝ ማግስት የኢትዮጵያ ጦር ወደ ደቡብ ጁባ ላንድ ሊገባ መሆኑን በተለመደ የመረጃ ቃራሚነቱ ሰምቶ ግርማ አሁንም የኢትዮጵያ ጦር ወደ ሶማሊያ መግባቱ ለህዝቡ በደንብ እንዲያውቀው ካልተደረገ መንግሰት ለመንግሰት ብቻ በሚደረግ ሰምምነት መሆኑ ችግሩን ከማባባስ አልፉ አልሻባብን ያጠናክራል የሚል ስጋት አለኝ ብሎ ፍርሃቱን አጋራኝ፡፡ እውነት ነው ደካማ የሱማሌ መንግሰት የሚያግዘው ጉልበተኛ ያስፈልገው ይሆናል፤ ለሀገር ዘላቂ ጥቅም ሲባል ግን ለአልሸባብ የሚወረወሩ ጥይቶች ሰላማዊ ዜጋ፣ ሴቶች እና ህፃናትን እንዳይጎዱ ጥንቃቄ መደረግ ይኖርበታል፡፡
ቸር ይግጠመን

Saturday, March 8, 2014

የኢህአዴግ አባል ድርጅቶች በእኔ ዕይታ ……. ግርማ ሠይፉ ማሩ



የኢህአዴግና ኣባል ድርጅቶችን እንደ ርዕሰ ጉዳይ ለማንሳት የገፋፋኝ የሰሞኑ የብአዴን መዝረክረክ ነው፡፡ ብአዴን ምን ነካው ብዬ ሃሳብ ለመሰንዘር ወስኜ ሳወጣ ሳወርድ ምን ያልተነካ የግንባር አባል ድርጅት ኖሮ ነው ብአዴን የምትለው የሚለው ሃሳብ ገዢ ሆኖ መጣብኝ፡፡ በዚህ መነሻም በነገር ቅደም ተከተል ሳይሆን ኢህአዴግ የሚባለውን ሚዛንና ቅርፅ የሌለውን ድርጅት በመመስረት ቅደም ተከተላቸው ለማየት ሞከርኩ፡፡
ሕወሓት ሁሉም እንደሚያውቀው አውራቸውን ካጡ በኋላ ዋና ስራቸው እራሳቸውን ወደ አንድ ፓርቲነት ለማሳደግ ደፋ ቀና ሲሉ እንደከረሙ እናውቃለን፡፡ የተሳካ ነገር መኖሩን የሚጠቁም ነገር የለም፡፡ ዛሬም ነገም ስብሰባ ነው፡፡ ባለሀብቶቹ ተሰብሰበው እባካችሁ ስብሰባ ቀንሱ ነው ያሉዋቸው፡፡ ህውሓት የአዲስ አበባና የመቀሌ ቡድን በመባል ይታወቃሉ፡፡ ይህም ሆኖ ግን የነፃ አውጪ ድርጅቱን የሚመሩት የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ክፍፍል የሚባል የለም ብለው ለየካቲት 11 መታሰቢያ በተዘጋጀ መፅሔት ላይ ቃለ ምልልስ መስጠታቸውን ይፋ ሆኖዋል፡፡ እኛም ሰምተናል መስማት ግን መስማማት እንዳልሆነ የታወቀ ነው፡፡ ይህ የሚያስታውሰን ነገር ቢኖር የጦጢትን አልበላሽምን ምን አመጣው ጫወታ ነው፡፡ ክፍፍል የለምን ምን አመጣው እንላለን፡፡ አንድ ግን ታውቆ ያደረ ነገር ቢኖር ህውሓት ሁሉ ነገሩን ለአቶ መለስ ሰጥቶ የነበረ ከመሆኑ አንፃር በተለይ በኢህዴግ ሰፈር አጀንዳ የማስቀመጡን ሰራ መስራት የሚችል ሆኖ አላገኘሁትም፡፡ አሁን ህውሓት ጥንካሬ አለው ከተባለ የፓርቲ ሳይሆን ኢ-ሕገ መንግሰታዊ በሆነ መስመር የመከላከያና የደህንነት መስሪያ ቤቱ ውስጥ ባሉት ቁልፍ ሰዎች የሚተማመን ከሆነ እና እነዚህም ቁልፍ ሰዎች ቢሆኑ ይህን መተማመኛ ሰጥተው ከሆነ ነው፡፡ ዘወተር ታማኝነታችን ለህገ መንግሰት ነው በሚሉት ቃላቸው ከታመኑ ደግሞ ጠቅላይ አዛዡ አቶ ኃይለማሪያም ደሳለኝ እንጂ የህውሓቱ መሪ አይሆኑም፡፡ ሰለዚህ ሕውሓት በአሁኑ ሰዓት በኢህአዴግ ውስጥ አጀንዳ አሰቀማጭነት ሚና የለውም የሚል አረዳድ ነው ያለኝ፡፡ ለዚህ ማሳያ የሚሆነው በፌዴራል መንግሰት በሚደረጉ ሹመቶች ውስጥ የህወሓት ሰዎች ከቦታ ቦታ ዝውውር እና የቀድሞ ታጋዮችን ወደፊት ከማምጣት የዘለለ አዲስ ፊት ማምጣት አልቻለም፡፡ ወጣቶቹ የህወሓት አፍቃሪ ልጆች በቢዝነሱ መስመር እንዲሁም ውስኪ በመጨለጡ እንጂ ንቁ ፖለቲከኛ የመሆን ፍላጎት ያላቸውን አይመስሉም፡፡ ባይሆን የዚህ ዓይነት ትንታግ ወጣቶች አረና ሰፈር ብቅብቅ ያሉ ይመስላሉ፡፡ እነ አብርሃ ደስታ የኢትዮጵያ አምላክ እንዲጠብቃቸው ፀሎት ሁሉ ያስፈልጋል፡፡ በትግል ከመተጋገዙ ጎን ለጎን ማለቴ ነው፡፡
በእውነቱ ከኢህአዴግ አባል ፓርቲዎች ውስጥ ተሰፋ ሳይበት የነበረው ብአዴን ሰሞኑን ምን እንደ ነካው ማወቅ አልቻልኩኝም፡፡ ለምን ተሰፋ ጣልክ ለሚለው ብዙ ማሳያ ቢኖረኝም በህውሓት ሰፈር ጠፍቶዋል ያልኩዋችሁን ወጣት አመራሮች ከስር ከስር ማየቴ እና ለውይየት ጋባዥ የሆኑ የቢሮ ሃላፊዎች ዋናው ሲሆን በተለይ ደግሞ በባህር ዳር ከተማ ላይ ዘለግ አድርገው ሃሰበው የሚሰሩት ሰራ ወደ ሌላ የአማራ ክልል ሊሄድ ይችላል የሚል ተሰፋ ስለነበረኝ ነው፡፡ ይሁን እንጂ በሰሞኑ ከየት መጣ ሳይባል አለምነው መኮንን የሚባል ካድሬ ከልጅነት እስከ እውቀት ሌሎች ሲሰድቡት የነበረውን እራሱ መቀበሉ ሳያንሰው የአማራን ህዝብ ሙልጭ አድርጎ ሲሳደብ ሰማነው፡፡ ያስታግሱታል ብሎም በተገቢው መንገድም ይቅርታ ጠይቆ ከሃላፊነቱ ይነሳል ብለን ስንጠብቅ ይባስ ተብሎ ሚዲያ ተሰጥቶት መግለጫ ሰጪ፤ ስለ ዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ሰኬት አብራሪ አድርገው አቀረቡት፡፡ ይህን ጊዜ የገባን ካድሬው የግል ባህሪው ሳይሆን የድርጅቱ አቋም ነው ብለን ወሰድን፡፡ የኢህአዴግ አባል ድርጅቶችም ይህን አባል ድርጅት ምንነው ጃል ማለት አልቻሉም፡፡ በኢህአዴግ ሰፈር ለምርጫ ዘመቻ ተቃዋሚዎች የቀየሱት ዘዴ ነው የሚል ማደናገሪያ ይዘው ቀርበዋል፡፡ አሁን ማን ይሙት አለምነው መኮንን የሚባል ካድሬ ሲሳደብ እንጂ በብአዴን ውስጥ መኖሩን ሰምተንም አይተንም አናውቅም፡፡ ይልቁንም የምናውቃቸው ተሰፋ የጣልንባቸው የተሳደቡ መስሎን ስናጣራ አልሰማንም እሰኪ እኛም እናጣራለን ብለውን ከዚያ በኋላ ስልክ ማንሳት ትተዋል፡፡ ተሰፋ የጣልንባቸውም ቢሆኑ ባይሳደቡም ወደውም ሆነ ተገደው ተባባሪ ናቸው፡፡
ሌላው በዚያው በብአዴን ሰፈር የተነሳው አሰቂኝ ነገር ደግሞ የህፃናት፣ወጣቶችና ሴቶች (ከጎልማሳና አዛውንት ወንዶች በስተቀር ልንለው እንችላለን) ሚኒስቴር ሚኒስትር የሆኑት ወ/ሮ ዘነቡ ታደሰ ደግሞ በፍፅሙ ከአንደ በዚህ ደረጃ ካለ ኢትዮጵያዊ በተለይ ከሴት በማይጠበቅ ሁኔታ ግብረሰዶማዊነት የሚደግፍ ፅሁፍ ካሰራጩ በኋላ እኔ አይደለሁም የማህበራዊ ድህረ ገፄ ቁልፍ ተሰብሮ ሌሎች ናቸው እንዲህ ጉድ የሰሩን የሚል ማስተባበያ ሰጡ ተባለ፣ ሌላው የከተማ ብአዴን አቶ ሽመልስ ከማል ደግም እዎ ተሰርቀው ነው አሉን፡፡ የመንግሰት ኮሚኒኬሽን ጉዳዮች መስሪያ ቤት የሚኒስትሮቻችን ማህበራዊ ድህረ ገፅ እንደሚመለከተው ያወቅሁት በዚህ ጉዳይ ነው፡፡ ሚኒስተሮቹ የማህበራዊ ድህረ ገፅ መድረኮችን መጠቀማቸው የሚበረታታ ቢሆንም በምንም ሁኔታ ግን ይህ የግል እንጂ የመንግሰት ሃላፊነት ሆኖ በመንግሰት ኮሚኒኬሽን መስሪያ ቤት በኩል መግለጫ የሚሰጥበት አይመስለኝም፡፡
እንግዲህ እነዚህ ብአዴኖች ናቸው ኢህአዴግ የሚባለውን የሰሩልን፡፡ ለህዝብ ሰሜት ሲባል አንድ ካድሬ ከስልጣን ሊያወርዱ የማይችሉ መሆናቸውን ሳሰብ ደከሙኝ፡፡ አንድ ነገር ግን ይታየኛል፡፡ አቶ አለምነው መኮንን በግላቸው ይቅርታ ጠይቀው ከፓርቲው ቢወጡ የበለጠ ሰላም ያገኛሉ የሚል እምነት አለኝ፡፡ ያለበለዚያ ግን በፍፁም ሰላም የሚሰጥ ሰህተት እንዳልሆነ አስምሬ መናገር እችላለሁ፡፡
ኦህዴድ ኢህአዴግን ከመሰረቱት አራት ፓርቲዎች በሶስተኛ ደረጃ የሚገኝ ቢሆንም ሰሞኑን የገባበት ውጥንቅጥ ግን ለብሔር ፓርቲ አደረጃጀት ትክክል አለመሆን ዋነኛ ማሳያ ነው፡፡ አንድ የብሔር ፓርቲ በተደላደለ ሁኔታ አመራር ለመምረጥና ለመተካት ምን ያህል ጊዜ ያስፈልገዋል? የኦሮሞ ህዝብ በቁመቱ ልክ በኢትዮጵያ ቦታ ሊሰጠው ይገባዋል የሚሉትን ሁሉ አንገት በሚያስደፋ ሁኔታ ኦህዴድ ድርጅቱን የሚመራ ሰው መሰየም አቅቶት ሲዋትት ቆይቶ በስንት ምጥ አሁንም እዚያው በዚያው ሽግሽግ አድርገው ኦህዴድ ዲሞክራሲያዊ በሆነ ሁኔታ የፓርቲውን መሪ መረጠ አሉን፡፡ ዲሞክራሲያዊ የሚለውን ምን አመጣው ? የጦጢት ነገር እዚህም ትዝ ቢለንም አይገርምም ለማነኛውም ግን በድርጅታዊ አሰራር የሚለው ግን ሳይፃፍ አንብበነዋል፡፡ እንደዚያም ሆኖ ግን ይህ ፅሁፍ እያሰናዳው እያለ ክልሉ አሁንም ርዕስ መስተዳድር የለውም፡፡ የክልሉ ምክትል ርዕስ መስተዳድር የቀድሞ የድሬዳዋ ከንቲባ አሁንም በፓረቲው ውስጥ ዋናም ምክትልም ሳይሆን በሞግዚትነት እሰከሚቀጥለው ምርጫ እንዲያሻግሩ የታጩ ይመስለኛል፡፡ ከዚህ በፊት የሰጠሁትን ግምቴን ለማጠናከር አቶ አባዱላ ገመዳ ወደ ክልል ሊመለሱ እንደሚችሉ ይሰማኛል ወይም በምክትል ጠቅላይ ሚኒሰትር ማዕረግ የሲቪል ሰርቪስ ሚኒስትሩ  አቶ ሙክታር ከደር እንደ ከሚል ስልጣን ከነሙሉ ክብሩና ጥቅሙ ጋር የክልል ፕሬዝዳንት ሊሆኑ ይችላሉ፡፡ በነገራችን ላይ በኢህአዴግ ውስጥ ያለው የኮታ ፖለቲካ በሁሉም ሰፈር አለ፡፡ በኦሮሚያም ቢሆን የዚህ እና የዚያ ዞን የሚል የጦዘ ፖለቲካ አለ፡፡ ይህ ሁሉ ሲሆን ግን የሁለት ሺ ሁለት ምርጫ ይዞት የሚመጣውን ማዕበል ገና ያወቀ የለም፡፡ ለማነኛውም የሰላም እንዲሆን ሁላችንም በመቻቻል መንፈስ መስራት ይኖርብናል፡፡
እንግዲህ ሁሉም ፓርቲዎች እኩል ናቸው ካልን እስከ አሁን ሶስት አራተኛ የሚሆነውን አይተናል ቀሪውን አንድ አራተኛ የያዘው የደቡብ ህዝቦች ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ/ደህዴን ሲሆን ይህ ሱሙ በአቅጣጫ የተሰየመ ፓርቲ መሪው አቶ ኃይለማሪያም ደሳለኝ የአሁኑ ጠቅላይ ሚኒሰትር ሲሆኑ ኢህአዴግን በመመስረት መጨረሻ ቢሆንም በትረ ስልጣን ለመያዝ ግን እድለኛ የሆነ ንቅናቄ ነው፡፡ ኢትዮጵያዊያኖች በጋራ አንድ ቤት ሊኖራቸው ይገባል ይቻላልም ብለን ስንሞግት አይችልም በብሔር መደራጀት ነው ለዚህች ሀገር መፍትሔው የሚለን ኢህአዴግ ከአምሳ ሰድስት በላይ የሆኑ ብሔሮችን በአንድ ላይ በደቡብ ንቅናቄ ሲያደራጅ እና በዚህ ምክንያት የሚታየውን የአሰተሳሰብ ተቃርኖ የሚረዳ ኢትዮጵያዊ አለ ብሎ አያምንም፡፡ ሲዳማዎች በሰማችን ጥሩን ደቡብ አቅጣጫ ነው ያሉት እንደተጠበቀ ሆኖ ማለቴ ነው፡፡
በነገራችን ላይ የብሔራቸው ተወላጅ ስልጣን ላይ ሲወጣ የሚደሰቱ ሰዎች እንዳሉ ይታወቃል፡፡ ትግሬ ሲሾም ደስ የሚለው ትግሬ ይኖራል፤ ኦሮሞ ሲሾም ደስ የሚለው ኦሮሞ ሊኖር ይችላል፤ ሌሎችም እንዲሁ፡፡ በዚህ ስሌት ከሄድን በአቶ ኃይለማሪም ደሳለኝ ጠቅላይ ሚኒስትር መሆን ደስ የሚለው ወላይታ ሊኖር እንደሚችል ባውቅም በምንም መመዛኛ ግን ይህ ሌሎችን የደቡብ ክልል በሚባለው የታቀፉትን ብሔሮች የሚያስደስት እንዳልሆነ እርግጠኛ መሆን አለብን፡፡ ስልጣን የሚያዘው በብቃት ሳይሆን  እንደ ኢህአዴግ ሰሌት በዙር ከሆነ በደቡብ ውስጥ ያሉት ብሔሮች በተለይ እንደ ሲዳማ፣ጉራጌ ከምባታ ኮታቸውን ጨርሰዋል ማለት ነው፡፡ ይህ በምንም ስሌት ተቀባይነት ያለው አይደለም፡፡ ደህዴን ኢህአዴግ ወደ ህብረብሔራዊ ፓርቲ መቀየር ከፈለገ እንዴት ማድረግ እንዳለበት ለሙከራ የተሰራ ድርጅት መሆኑ ይታወቃል፡፡ ለዚህ ስልጣንም የበቃው በውስጡ ባለው ተቃርኖ ምክንያት የያዘውን ስልጣን በማነኛውም ወቅት ቁጭ አድርግ ሲባል ቁጭ ያደርጋል በሚል ስሌት መስረት እንደሆነ እንጠረጥራለን፡፡
የእነዚህ አራት ፓርቲዎች ሰብሰብ ኢህአዴግ የሚባለውን ግንባር እንደፈጠረልን ይታወቃል፡፡ የዚህ ሁሉ መሃንዲስ የነበሩት  ከኋላ ሆነው መሪውን ለመያዝ ሲለፉ ሲተጉ የነበሩት “ባለራዕዩ” መሪ አሁን የለሙ፡፡ መሪያቻው በቀየሱላቸው መስመር ይሂዱ አይሂዱ እንደሆነ ጊዜ የሚነግረን ቢሆንም፡፡ አሁን የምንሰማቸው አንድ አንድ ነገሮች ግን ይህን የሚያሳዩ አይዳሉም፡፡ ሁሉም የኢህአዴግ አባል ድርጅቶች በፈለጉት እና በታያቸው መንገድ እየሄዱ እንደሆነ ይታያል፡፡ ፓርቲዎቹ ከኢህአዴግ ምክር ቤት በወረዳ አጀንዳ መሰረት ተወያየተው መወሰን ትተዋል፡፡ በማዕከላዊ መንግሰት ደረጃም ሟቹን ጥላ ከለላ አድርገው እንደልባቸው ሲሆኑ የነበሩትም ቢሆን ጣሪያው እንደተቀደደበት ሰው ፍሳሹ አስቸገረን እያሉ ሁሁ ሲሉ እየሰማን ነው፡፡ ከዚህ በፊት ተቃዋሚውን ጎራ ምንም ሳይደግፉት ይልቁንም ሲገፉት ቆይተው አሁን ግን ምን እየሰራችሁ ነው ማለት ጀምረዋል፡፡
ሊነጋ የሚመሰል ድቅድቅ ጨለማ ሀሉም ጋ ይታያል ….. ተሰፋ መቁረጥ እንዳይመጣ መጠንከር አለብን፡፡ ኢህአዴግ ግን እንደ ግንባር አንድ ቃል የሚናገር አይመስልም አጣባቂ ሙጫ የነበሩትን “ባለራዕይ” መሪውን አጥቶ ጎዳና ተዳዳሪ የሆነ ይመስለኛል፡፡
ቸር ይግጠመን፡፡