Saturday, March 8, 2014

የኢህአዴግ አባል ድርጅቶች በእኔ ዕይታ ……. ግርማ ሠይፉ ማሩ



የኢህአዴግና ኣባል ድርጅቶችን እንደ ርዕሰ ጉዳይ ለማንሳት የገፋፋኝ የሰሞኑ የብአዴን መዝረክረክ ነው፡፡ ብአዴን ምን ነካው ብዬ ሃሳብ ለመሰንዘር ወስኜ ሳወጣ ሳወርድ ምን ያልተነካ የግንባር አባል ድርጅት ኖሮ ነው ብአዴን የምትለው የሚለው ሃሳብ ገዢ ሆኖ መጣብኝ፡፡ በዚህ መነሻም በነገር ቅደም ተከተል ሳይሆን ኢህአዴግ የሚባለውን ሚዛንና ቅርፅ የሌለውን ድርጅት በመመስረት ቅደም ተከተላቸው ለማየት ሞከርኩ፡፡
ሕወሓት ሁሉም እንደሚያውቀው አውራቸውን ካጡ በኋላ ዋና ስራቸው እራሳቸውን ወደ አንድ ፓርቲነት ለማሳደግ ደፋ ቀና ሲሉ እንደከረሙ እናውቃለን፡፡ የተሳካ ነገር መኖሩን የሚጠቁም ነገር የለም፡፡ ዛሬም ነገም ስብሰባ ነው፡፡ ባለሀብቶቹ ተሰብሰበው እባካችሁ ስብሰባ ቀንሱ ነው ያሉዋቸው፡፡ ህውሓት የአዲስ አበባና የመቀሌ ቡድን በመባል ይታወቃሉ፡፡ ይህም ሆኖ ግን የነፃ አውጪ ድርጅቱን የሚመሩት የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ክፍፍል የሚባል የለም ብለው ለየካቲት 11 መታሰቢያ በተዘጋጀ መፅሔት ላይ ቃለ ምልልስ መስጠታቸውን ይፋ ሆኖዋል፡፡ እኛም ሰምተናል መስማት ግን መስማማት እንዳልሆነ የታወቀ ነው፡፡ ይህ የሚያስታውሰን ነገር ቢኖር የጦጢትን አልበላሽምን ምን አመጣው ጫወታ ነው፡፡ ክፍፍል የለምን ምን አመጣው እንላለን፡፡ አንድ ግን ታውቆ ያደረ ነገር ቢኖር ህውሓት ሁሉ ነገሩን ለአቶ መለስ ሰጥቶ የነበረ ከመሆኑ አንፃር በተለይ በኢህዴግ ሰፈር አጀንዳ የማስቀመጡን ሰራ መስራት የሚችል ሆኖ አላገኘሁትም፡፡ አሁን ህውሓት ጥንካሬ አለው ከተባለ የፓርቲ ሳይሆን ኢ-ሕገ መንግሰታዊ በሆነ መስመር የመከላከያና የደህንነት መስሪያ ቤቱ ውስጥ ባሉት ቁልፍ ሰዎች የሚተማመን ከሆነ እና እነዚህም ቁልፍ ሰዎች ቢሆኑ ይህን መተማመኛ ሰጥተው ከሆነ ነው፡፡ ዘወተር ታማኝነታችን ለህገ መንግሰት ነው በሚሉት ቃላቸው ከታመኑ ደግሞ ጠቅላይ አዛዡ አቶ ኃይለማሪያም ደሳለኝ እንጂ የህውሓቱ መሪ አይሆኑም፡፡ ሰለዚህ ሕውሓት በአሁኑ ሰዓት በኢህአዴግ ውስጥ አጀንዳ አሰቀማጭነት ሚና የለውም የሚል አረዳድ ነው ያለኝ፡፡ ለዚህ ማሳያ የሚሆነው በፌዴራል መንግሰት በሚደረጉ ሹመቶች ውስጥ የህወሓት ሰዎች ከቦታ ቦታ ዝውውር እና የቀድሞ ታጋዮችን ወደፊት ከማምጣት የዘለለ አዲስ ፊት ማምጣት አልቻለም፡፡ ወጣቶቹ የህወሓት አፍቃሪ ልጆች በቢዝነሱ መስመር እንዲሁም ውስኪ በመጨለጡ እንጂ ንቁ ፖለቲከኛ የመሆን ፍላጎት ያላቸውን አይመስሉም፡፡ ባይሆን የዚህ ዓይነት ትንታግ ወጣቶች አረና ሰፈር ብቅብቅ ያሉ ይመስላሉ፡፡ እነ አብርሃ ደስታ የኢትዮጵያ አምላክ እንዲጠብቃቸው ፀሎት ሁሉ ያስፈልጋል፡፡ በትግል ከመተጋገዙ ጎን ለጎን ማለቴ ነው፡፡
በእውነቱ ከኢህአዴግ አባል ፓርቲዎች ውስጥ ተሰፋ ሳይበት የነበረው ብአዴን ሰሞኑን ምን እንደ ነካው ማወቅ አልቻልኩኝም፡፡ ለምን ተሰፋ ጣልክ ለሚለው ብዙ ማሳያ ቢኖረኝም በህውሓት ሰፈር ጠፍቶዋል ያልኩዋችሁን ወጣት አመራሮች ከስር ከስር ማየቴ እና ለውይየት ጋባዥ የሆኑ የቢሮ ሃላፊዎች ዋናው ሲሆን በተለይ ደግሞ በባህር ዳር ከተማ ላይ ዘለግ አድርገው ሃሰበው የሚሰሩት ሰራ ወደ ሌላ የአማራ ክልል ሊሄድ ይችላል የሚል ተሰፋ ስለነበረኝ ነው፡፡ ይሁን እንጂ በሰሞኑ ከየት መጣ ሳይባል አለምነው መኮንን የሚባል ካድሬ ከልጅነት እስከ እውቀት ሌሎች ሲሰድቡት የነበረውን እራሱ መቀበሉ ሳያንሰው የአማራን ህዝብ ሙልጭ አድርጎ ሲሳደብ ሰማነው፡፡ ያስታግሱታል ብሎም በተገቢው መንገድም ይቅርታ ጠይቆ ከሃላፊነቱ ይነሳል ብለን ስንጠብቅ ይባስ ተብሎ ሚዲያ ተሰጥቶት መግለጫ ሰጪ፤ ስለ ዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ሰኬት አብራሪ አድርገው አቀረቡት፡፡ ይህን ጊዜ የገባን ካድሬው የግል ባህሪው ሳይሆን የድርጅቱ አቋም ነው ብለን ወሰድን፡፡ የኢህአዴግ አባል ድርጅቶችም ይህን አባል ድርጅት ምንነው ጃል ማለት አልቻሉም፡፡ በኢህአዴግ ሰፈር ለምርጫ ዘመቻ ተቃዋሚዎች የቀየሱት ዘዴ ነው የሚል ማደናገሪያ ይዘው ቀርበዋል፡፡ አሁን ማን ይሙት አለምነው መኮንን የሚባል ካድሬ ሲሳደብ እንጂ በብአዴን ውስጥ መኖሩን ሰምተንም አይተንም አናውቅም፡፡ ይልቁንም የምናውቃቸው ተሰፋ የጣልንባቸው የተሳደቡ መስሎን ስናጣራ አልሰማንም እሰኪ እኛም እናጣራለን ብለውን ከዚያ በኋላ ስልክ ማንሳት ትተዋል፡፡ ተሰፋ የጣልንባቸውም ቢሆኑ ባይሳደቡም ወደውም ሆነ ተገደው ተባባሪ ናቸው፡፡
ሌላው በዚያው በብአዴን ሰፈር የተነሳው አሰቂኝ ነገር ደግሞ የህፃናት፣ወጣቶችና ሴቶች (ከጎልማሳና አዛውንት ወንዶች በስተቀር ልንለው እንችላለን) ሚኒስቴር ሚኒስትር የሆኑት ወ/ሮ ዘነቡ ታደሰ ደግሞ በፍፅሙ ከአንደ በዚህ ደረጃ ካለ ኢትዮጵያዊ በተለይ ከሴት በማይጠበቅ ሁኔታ ግብረሰዶማዊነት የሚደግፍ ፅሁፍ ካሰራጩ በኋላ እኔ አይደለሁም የማህበራዊ ድህረ ገፄ ቁልፍ ተሰብሮ ሌሎች ናቸው እንዲህ ጉድ የሰሩን የሚል ማስተባበያ ሰጡ ተባለ፣ ሌላው የከተማ ብአዴን አቶ ሽመልስ ከማል ደግም እዎ ተሰርቀው ነው አሉን፡፡ የመንግሰት ኮሚኒኬሽን ጉዳዮች መስሪያ ቤት የሚኒስትሮቻችን ማህበራዊ ድህረ ገፅ እንደሚመለከተው ያወቅሁት በዚህ ጉዳይ ነው፡፡ ሚኒስተሮቹ የማህበራዊ ድህረ ገፅ መድረኮችን መጠቀማቸው የሚበረታታ ቢሆንም በምንም ሁኔታ ግን ይህ የግል እንጂ የመንግሰት ሃላፊነት ሆኖ በመንግሰት ኮሚኒኬሽን መስሪያ ቤት በኩል መግለጫ የሚሰጥበት አይመስለኝም፡፡
እንግዲህ እነዚህ ብአዴኖች ናቸው ኢህአዴግ የሚባለውን የሰሩልን፡፡ ለህዝብ ሰሜት ሲባል አንድ ካድሬ ከስልጣን ሊያወርዱ የማይችሉ መሆናቸውን ሳሰብ ደከሙኝ፡፡ አንድ ነገር ግን ይታየኛል፡፡ አቶ አለምነው መኮንን በግላቸው ይቅርታ ጠይቀው ከፓርቲው ቢወጡ የበለጠ ሰላም ያገኛሉ የሚል እምነት አለኝ፡፡ ያለበለዚያ ግን በፍፁም ሰላም የሚሰጥ ሰህተት እንዳልሆነ አስምሬ መናገር እችላለሁ፡፡
ኦህዴድ ኢህአዴግን ከመሰረቱት አራት ፓርቲዎች በሶስተኛ ደረጃ የሚገኝ ቢሆንም ሰሞኑን የገባበት ውጥንቅጥ ግን ለብሔር ፓርቲ አደረጃጀት ትክክል አለመሆን ዋነኛ ማሳያ ነው፡፡ አንድ የብሔር ፓርቲ በተደላደለ ሁኔታ አመራር ለመምረጥና ለመተካት ምን ያህል ጊዜ ያስፈልገዋል? የኦሮሞ ህዝብ በቁመቱ ልክ በኢትዮጵያ ቦታ ሊሰጠው ይገባዋል የሚሉትን ሁሉ አንገት በሚያስደፋ ሁኔታ ኦህዴድ ድርጅቱን የሚመራ ሰው መሰየም አቅቶት ሲዋትት ቆይቶ በስንት ምጥ አሁንም እዚያው በዚያው ሽግሽግ አድርገው ኦህዴድ ዲሞክራሲያዊ በሆነ ሁኔታ የፓርቲውን መሪ መረጠ አሉን፡፡ ዲሞክራሲያዊ የሚለውን ምን አመጣው ? የጦጢት ነገር እዚህም ትዝ ቢለንም አይገርምም ለማነኛውም ግን በድርጅታዊ አሰራር የሚለው ግን ሳይፃፍ አንብበነዋል፡፡ እንደዚያም ሆኖ ግን ይህ ፅሁፍ እያሰናዳው እያለ ክልሉ አሁንም ርዕስ መስተዳድር የለውም፡፡ የክልሉ ምክትል ርዕስ መስተዳድር የቀድሞ የድሬዳዋ ከንቲባ አሁንም በፓረቲው ውስጥ ዋናም ምክትልም ሳይሆን በሞግዚትነት እሰከሚቀጥለው ምርጫ እንዲያሻግሩ የታጩ ይመስለኛል፡፡ ከዚህ በፊት የሰጠሁትን ግምቴን ለማጠናከር አቶ አባዱላ ገመዳ ወደ ክልል ሊመለሱ እንደሚችሉ ይሰማኛል ወይም በምክትል ጠቅላይ ሚኒሰትር ማዕረግ የሲቪል ሰርቪስ ሚኒስትሩ  አቶ ሙክታር ከደር እንደ ከሚል ስልጣን ከነሙሉ ክብሩና ጥቅሙ ጋር የክልል ፕሬዝዳንት ሊሆኑ ይችላሉ፡፡ በነገራችን ላይ በኢህአዴግ ውስጥ ያለው የኮታ ፖለቲካ በሁሉም ሰፈር አለ፡፡ በኦሮሚያም ቢሆን የዚህ እና የዚያ ዞን የሚል የጦዘ ፖለቲካ አለ፡፡ ይህ ሁሉ ሲሆን ግን የሁለት ሺ ሁለት ምርጫ ይዞት የሚመጣውን ማዕበል ገና ያወቀ የለም፡፡ ለማነኛውም የሰላም እንዲሆን ሁላችንም በመቻቻል መንፈስ መስራት ይኖርብናል፡፡
እንግዲህ ሁሉም ፓርቲዎች እኩል ናቸው ካልን እስከ አሁን ሶስት አራተኛ የሚሆነውን አይተናል ቀሪውን አንድ አራተኛ የያዘው የደቡብ ህዝቦች ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ/ደህዴን ሲሆን ይህ ሱሙ በአቅጣጫ የተሰየመ ፓርቲ መሪው አቶ ኃይለማሪያም ደሳለኝ የአሁኑ ጠቅላይ ሚኒሰትር ሲሆኑ ኢህአዴግን በመመስረት መጨረሻ ቢሆንም በትረ ስልጣን ለመያዝ ግን እድለኛ የሆነ ንቅናቄ ነው፡፡ ኢትዮጵያዊያኖች በጋራ አንድ ቤት ሊኖራቸው ይገባል ይቻላልም ብለን ስንሞግት አይችልም በብሔር መደራጀት ነው ለዚህች ሀገር መፍትሔው የሚለን ኢህአዴግ ከአምሳ ሰድስት በላይ የሆኑ ብሔሮችን በአንድ ላይ በደቡብ ንቅናቄ ሲያደራጅ እና በዚህ ምክንያት የሚታየውን የአሰተሳሰብ ተቃርኖ የሚረዳ ኢትዮጵያዊ አለ ብሎ አያምንም፡፡ ሲዳማዎች በሰማችን ጥሩን ደቡብ አቅጣጫ ነው ያሉት እንደተጠበቀ ሆኖ ማለቴ ነው፡፡
በነገራችን ላይ የብሔራቸው ተወላጅ ስልጣን ላይ ሲወጣ የሚደሰቱ ሰዎች እንዳሉ ይታወቃል፡፡ ትግሬ ሲሾም ደስ የሚለው ትግሬ ይኖራል፤ ኦሮሞ ሲሾም ደስ የሚለው ኦሮሞ ሊኖር ይችላል፤ ሌሎችም እንዲሁ፡፡ በዚህ ስሌት ከሄድን በአቶ ኃይለማሪም ደሳለኝ ጠቅላይ ሚኒስትር መሆን ደስ የሚለው ወላይታ ሊኖር እንደሚችል ባውቅም በምንም መመዛኛ ግን ይህ ሌሎችን የደቡብ ክልል በሚባለው የታቀፉትን ብሔሮች የሚያስደስት እንዳልሆነ እርግጠኛ መሆን አለብን፡፡ ስልጣን የሚያዘው በብቃት ሳይሆን  እንደ ኢህአዴግ ሰሌት በዙር ከሆነ በደቡብ ውስጥ ያሉት ብሔሮች በተለይ እንደ ሲዳማ፣ጉራጌ ከምባታ ኮታቸውን ጨርሰዋል ማለት ነው፡፡ ይህ በምንም ስሌት ተቀባይነት ያለው አይደለም፡፡ ደህዴን ኢህአዴግ ወደ ህብረብሔራዊ ፓርቲ መቀየር ከፈለገ እንዴት ማድረግ እንዳለበት ለሙከራ የተሰራ ድርጅት መሆኑ ይታወቃል፡፡ ለዚህ ስልጣንም የበቃው በውስጡ ባለው ተቃርኖ ምክንያት የያዘውን ስልጣን በማነኛውም ወቅት ቁጭ አድርግ ሲባል ቁጭ ያደርጋል በሚል ስሌት መስረት እንደሆነ እንጠረጥራለን፡፡
የእነዚህ አራት ፓርቲዎች ሰብሰብ ኢህአዴግ የሚባለውን ግንባር እንደፈጠረልን ይታወቃል፡፡ የዚህ ሁሉ መሃንዲስ የነበሩት  ከኋላ ሆነው መሪውን ለመያዝ ሲለፉ ሲተጉ የነበሩት “ባለራዕዩ” መሪ አሁን የለሙ፡፡ መሪያቻው በቀየሱላቸው መስመር ይሂዱ አይሂዱ እንደሆነ ጊዜ የሚነግረን ቢሆንም፡፡ አሁን የምንሰማቸው አንድ አንድ ነገሮች ግን ይህን የሚያሳዩ አይዳሉም፡፡ ሁሉም የኢህአዴግ አባል ድርጅቶች በፈለጉት እና በታያቸው መንገድ እየሄዱ እንደሆነ ይታያል፡፡ ፓርቲዎቹ ከኢህአዴግ ምክር ቤት በወረዳ አጀንዳ መሰረት ተወያየተው መወሰን ትተዋል፡፡ በማዕከላዊ መንግሰት ደረጃም ሟቹን ጥላ ከለላ አድርገው እንደልባቸው ሲሆኑ የነበሩትም ቢሆን ጣሪያው እንደተቀደደበት ሰው ፍሳሹ አስቸገረን እያሉ ሁሁ ሲሉ እየሰማን ነው፡፡ ከዚህ በፊት ተቃዋሚውን ጎራ ምንም ሳይደግፉት ይልቁንም ሲገፉት ቆይተው አሁን ግን ምን እየሰራችሁ ነው ማለት ጀምረዋል፡፡
ሊነጋ የሚመሰል ድቅድቅ ጨለማ ሀሉም ጋ ይታያል ….. ተሰፋ መቁረጥ እንዳይመጣ መጠንከር አለብን፡፡ ኢህአዴግ ግን እንደ ግንባር አንድ ቃል የሚናገር አይመስልም አጣባቂ ሙጫ የነበሩትን “ባለራዕይ” መሪውን አጥቶ ጎዳና ተዳዳሪ የሆነ ይመስለኛል፡፡
ቸር ይግጠመን፡፡

No comments:

Post a Comment