Sunday, March 16, 2014

የአፍሪካ መሪዎችና አፍሪካዊያን ግርማ ሠይፉ ማሩ



በቅርቡ ለስብሰባ የመካከለኛ አፍሪካ በምትገኘው ካሜሩን ዋና ከተማ ያውንዴ ተገኝቼ ነበር፡፡ ያውንዴ በነበርኩበት ጊዜም አጋጣሚ ሆኖ ማርች 8 ዓለም አቀፍ የሴቶች ቀን የሚከበርበት ስለነበር አከባበሩን አሰመልክቶ የአፍሪካ መሪዎች እንዴት በዓል እንደሚያከብሩ ለመታዘብ ዕድል ሰጥቶኛል፡፡ ለአምባገነንት የሚጠቀሙበት መመሪያም አንድ መሆኑን ለማወቅ ጊዜ የሚወስድ አልነበረም፡፡ በዚህ አጋጣሚ ደግሞ ከጎረቤት ሀገር ተሳታፊዎች ጋር ለመገናኘት እና ለመወያየት ዕድል አግኝቼ ነበር፡፡ በተለይ ከኤርትራዊ ወንድሞቻችን እና እህቶች ጋር የነበረን ቆይታ ከእነርሱ  ከራሳቸው በስተቀር ከኢትዮጵያ የሚለያቸው ነገር የሚያውቅ እንደሌለ አፍጥጦ የሚታይ ሀቅ ነበር፡፡  ከሱማሊያ ከመጣው ወጣት ጋር የነበረን ውይይትም በፍፁም የማይታመን ነበር፡፡ የእኛ ጎምቱ ባለስልጣናት አብረውን ካሉት ጋር እንዴት እንደሚያጋጩን ሲያስላስሉ እዚያ ማዶ ያሉት ግን የእኛ ናፍቆት አላቸው፤ የአብሮነትን ጥቅም በደንብ ተረድተውት እንዴት እንደሚሆን ግን ግራ የተጋቡ ይመስላሉ፡፡ ይህን መፈላለግ ለመግለፅ ግን ከአንድ ጥግ ወደ ሌላ ጥግ መሄድ ለምን እንዳስፈለገን ተወያይተን የደረስንበት በእኛ በህዝቦች መካከል  ምንም የሚያለያይ ነገር እንደሌለ ነው፡፡ ለአብሮነታችን ግን አምባገነኖችን ከመክስስ በዘለለ ሁላችን የበኩላችንን ማድረግ ይኖርበናል፡፡
እንደ መግቢያ
የማርች 8 ባህል በካሜሮን ከተማ ያውንዴ ድል ባለ ሁኔታ ሲከበር የዓይን ምስክር ሆኜ ተመልክቻለሁ፡፡ ባህሉ ያለ ብዙ ወንዶች ተሳትፎ የሀገሪቱ ቀዳማዊ እመቤት በተገኙበት የተከበረ ሲሆን በእኛ ሀገር ለቀዳማዊ እመቤት በዚህ ደረጃ የደህንነት ጥበቃ ሲደረግ አይቼም ሰምቼም አላውቅም፡፡ የባሰ አለ ሀገር አትልቀቅ የሚባለው ይኼን ጊዜ ይመስለኛል፡፡ የማርች 8 በዓልን ለማድምቅ የወጡት ሴቶች እንደኛው ሀገር በመስሪያ ቤት ተደራጅተው የወጡ ሲሆን፤ ከበዓሉ በኋላ ግን እንደ እኛዎቹ ሴቶች ወደቤታቸው ነጠላቸውን በአናታቸው ላይ አድርገው ጠውልገው ሲመለሱ አላያሁም፡፡ በየደረሱበት አረፍ ብለው ቢራ እየተጎነጩ ሲመሽም ተሳክረው በየጎዳናው ሲደንሱ አጀብ የሚያሰኝ ነበር፡፡ ይኼ ነው እኩልነት ብዬ ታዝቤያቸው መጥቻለው፡፡ የሰልፉ ዝግጅት፣ የጦር ሰራዊት ጋጋታው፣ ወዘተ… በሀገራችን የሴቶች ሊግ የሚያደርገው ዓይነት እና በመንግሰት የሚደገፉ ሰልፉች ጋር አንድ ሲሆንብኝ ተሳስቼ መስቀል አደባባይ የተገኘው እንጂ በዚህ ሁሉ ኪሎ ሜትር ርቀት ልዩነት በዚህ ደረጃ መመሳሰል ይኖራል ብዬ ለማመን እራሴን ተጠራጠርኩ፡፡
ኢትዮጵያ (ከኤርትራ እና ያለ ኤርትራ)
ኤርትራዊያን ብዬ ለመፃፍ ወይም ለመጥራት የምር ምቾት አይስጠኝም፡፡ ያራቅኳቸው እኔም ከኢህአዴጎች ጋር ሆኜ አንድ አይደለንም የሚለውን የመደገፍ ሰሜት እየመጣብኝ ይፈታተነኛል፡፡ እንደዚያም ሆኖ ግን አሁን ያለውን እውነት ለመቀበል ስል እንደ ሁለት ሀገር አድርጌ ለመፃፍ እገደዳለሁ፡፡ ልቤ ግን ይህን እያለኝ አይደለም፡፡ ኢትዮጵያ ያለ ኤርትራ፤ ኤርትራም ያለ ኢትዮጵያ መኖር እንደሚችሉ ባሳለፍናቸው ሃያ ዓመታት በላይ የተረጋገጠ እና የተመዘገበ እውነት ነው፡፡ ነገር ግን አብረን ብንሆ ከዚህ የተሻለ ልንሆን እንደምንችል ከምን ጊዜውም የበለጠ አሁን የተሰማን ይመስለኛል፡፡ እኛ ከተከዚ ደቡብ የምንገኝ ህዝቦች አስመራ፣ ምፅዋ ሄደን ለመዝናናት ቢያስፈልግም ሰርተን ለመኖር ከኢሳያስ መሞት ቀጥሎ ከዚህ ከእኛ ሰፈር የአብዮታዊ ዲሞክራሲ መፍረስ የግድ የሚለን ይመስለኛል፡፡ ይህ “ጦርነትም ሰላምም የለም” በሚል ግርግዳ ታጥረን መኖራችን፤ ከአሰመራም ከአዲስ አበባም በኩል የመራራቅን ግድግዳ እያጠናከረ እንደሚሄድ ግን ምንም ጥርጥር የለውም፡፡ በዚሁ ከቀጠልን አዲሱ ትውልድ የእኛን ያህል አስመራንም ሆነ ምፅዋን የመጎብኘት ጉጉቱ ባያድርበት መገረም አይኖርብንም፡፡ በተለይ በአሰመራ በኩል አዲስ ታሪክ በመስራት ፕሮጀክት ውስጥ ኤርትራ በጎረቤት ሀገሯ ኢትዮጵያ ቅኝ ተይዛ እንደነበረ በሰፊው ተፅፎ እየተሰጠ እንደሚሆን መጠራጠር አያስፈልግም፡፡ ከአቶ መለስ እና ጓዶቻቸው በስተቀር እኛም ሳናውቅ አንድ በቅኝ የገዛነው ሀገር እንዳለን በአስመራ በኩል ይመዘገብ ይሆናል፡፡ አቶ መለስ ፅፈውታል ተብሎ የሚታመነው “ኤርትራ ከየት ወዴት?`` የሚለው መፅኃፍ ኢትዮጵያን ቅኝ ገዢ አድርጎ ነው የሚያቀርበው፡፡ የኤርትራ ጉዳይም ከቅኝ ግዣት ነፃ የመውጣት ነው ብለው ነው የደመደሙት፡፡ ለዚህም ነው ኤርትራ ነፃ ሀገር እንድትሆን ቀድመው ደብዳቤ የፃፉት፡፡ እርግጠኛ ነኝ በኢትዮጵያ በኩል ያለው ታሪክ ኤርትራ ከእናት ሀገሯ መገንጠሏን የሚነግር እንጂ በቅኝ ይዘናት የነበረን ሀገር እንዳስረከብን አይደለም፡፡ ለምሳሌ እንግሊዝ ኬኒያን ለቃ እንደወጣችው ዓይነት ማለት ነው፡፡ ለምሳሌ ደቡብ ሱዳን ከሱዳን ተገነጠለች እንጂ ከሱዳን ቅኝ ግዛት አይደለም ነፃ የወጣችው፡፡
የዚህ ፅሁፍ ዓላማም ይህ እየተጠናከረ ወደ አዲሱ ትውልድ በመሄድ ላይ ያለውን የሚያራርቅ ግንብ የኢሳያስንም ሆነ የእኛን አብዮታዊ ዲሞክራሲ ሞትና ግብዓተ መሬት ሳይጠብቅ ህዝብ ለህዝብ በሚደረግ ግንኙነት እንዲጠናከር ማድረግ እንዳለብን ከውስጤ ስለተሰማኝ ፍላጎቱና አቅሙ ላላቸው ሰዎች እረ ጎበዝ አንደ እንበል ለማለት ነው፡፡ ይህን እንዴት ማድረግ ይኖርብናል የሚለው ብዙ ሰዎች ብዙ የሚሉት ነገር እንደሚኖር ባምንም በእኔ ግምት በቅርቡ መጀመር ያለባቸው ብዬ የማምናቸው በማህበራዊም ሆነ በመደበኛ ሚዲያ ወጣቱ ትውልድ በሁለቱ ሀገሮች መካከል ያለውን የባሕል፣ የቋንቋ፣ የሰነልቦና፣ ወዘተ አንድነት የሚያሳዩና አዲሱን ትውልድ ከቀድሞ ጋር የሚያስተሳስሩ ሰራዎችን መስራት የግድ ይለናል፡፡ እንደዚህ ዓይነት ሰራዎች በፍፁም በአንድ ወገን ብቻ የሚሰሩ መሆን የለባቸውም፡፡ የኢየትዮጵያና የኤርትራ ቴሌቭዝኖች እንዲህ ዓይነት መልካም ሰራ ቢጠበቅባቸውም የማያምርባቸው ስለሆነ ከውጭ የሚተላለፉ ለምሳሌ ኢሳት እና “ኢቢሴ” በዚህ ጉዳይ ላይ ቢሰሩ የሚጠቀሙ እንጂ የሚጎዱ አይመስለኝም፡፡ እነዚህ ተግባራት በፍፁም ከፖለቲካ አመለካከት ጋር የሚገናኙ መሆን የለባቸውም፡፡
በውጭ የሚኖሩ ኢትዮጵያዊያን እና ኤርትራዊያን የጋራ ፎረሞችን በማዘጋጀት በአብሮነታችን ዙሪያ ምክክር በማድረግ ከእንደዚህ ዓይነት መድረኮች የሚገኙ ሃሳቦች በሰፊው ህዝቡ እንዲያውቀው በማድረግ የህዝብ ለህዝብ መቀራረብን ልናጎለብት ይገባ የሚል እምነት አለኝ፡፡ ፖለቲከኞች በፈጠሩት ግጭት ባለሞያዎች በሚገናኙበት መድረክ ላይ ለመሳተፍ አንድ ኤርትራዊ አውሮፓ ድረስ ተጉዞ ሶስት አራት ቀን መንገድ የሚያድርበት ቀን ለማሳጠር መሰረት መጣል ያለብን ይመስለኛል፡፡ ይህን ለማድረግ በመግቢያዬ ላይ እንዳልኩት የኢሳያስ መሞትና የአብዮታዊ ዲሞክራሲ መፍረስ ከጠበቅን የመለያየታችን ግንብ በልጆቻችን ውስጥ ሰርጾ መቼ አንድ ነበርን ሊሉን ይችላሉ፡፡

ኢትዮጵያና ሱማሊያ
ኢትዮጵያና ሱማሊያ በሱማሌ ቅኝ ገዜ የነበሩት በተለይ እንግሊዞች በቀበሩት የግጭት መንፈስ የተነሳ በተደጋጋሚ የድንበር ግጭት ብሎም ደም አፋሳሽ የሆነ ሙሉ ጦርነቶች ውስጥ ገብተን እንደነበር እሙን ነው፡፡ ይህን እውነት የምናውቅ የሁለት ሀገር ዜጎች ግን ካሜሮን ላይ ስንገናኝ እንደ ድሮ ሰፈር ልጅ በፍቅር ስንጫወት ነው የከረምነው፡፡ ከሱማሌው ተወካይ መሃመድ ጋር መጀመሪያ የተግባባነው ኢትዮጵያዊ መስሎን ነበር፡፡ እኔን እና መሃመድን የሚለየን መሃመድ ትንሽ  ትንሽ አማርኛ ይሞክራል እኔ ሱማልኛ ስለማልሞክር ይበልጠኛል ማለት ነው፤ መሃመድ ተግባቢ እና በደንብ እንደምናውቃቸው ሶማሊዎች ቴክኖሎጂ የሚወድ ነው፡፡ በእጁ የያዛት ብላክ ቤሪ ስልክ ሁሉንም ወሬ ታቀብለዋለች፡፡ መሃመድ እንደሚለው “ይህች ስልክ ሱማሌ ውስጥ በተለይ በአልሻባብ እጅ ከገባህ ሞት ታስከትላለች” ይላል በተደጋጋሚ፡፡ ቴክኖሎጂን እና ሌሎች የህዝብ መጠቀሚያዎችን በመከልከል አፍነው ሊገዙ የሚንቀሳቀሱ የአልሻባብ ሰዎች በፍፁም ምንጫቸው ሱማሌ እንዳልሆነ እና ከውጭ የመጣ አካራሪነት እንደሆነ ያምናል፡፡ በዚህ ሰበብ ግን በኢትዮጵያ በኩል እየተወሰደ ያለው እርምጃ በደንብ ታስቦበት ካልሆነ የህዝብ ለህዝብ ግንኙነትን እንደሚጎዳ አበክሮ ይናገራል፡፡ እርግጥ ነው አሁን ያለው መንግስት ደካማ ስለሆነ የኢትዮጵያ እርዳታ በተለይ ወታደራዊ ድጋፍ ይፈልጋል፤ እንደዚያም ሆኖ ግን ህዝቡ ይህን ሳይረዳ ይቀርና እንደ ወራሪ ሀይል በመቁጠር አልሻባብን ይቀላቀላል፡፡ ይህ ደግሞ ወደፊት ተባብረን እና ተደጋግፈን  የምንኖርበትን  ጊዜ ያርቀዋል ይላል፡፡ መሃመድ ከዚህ በፊት በኢትዮጵያና በሱማሊያ መካከል የተደረገውን ደም አፋሳሽ ጦርነት በታሪክነት ነው እንዲዘጋ የሚፈልገው፡፡ ይህ ጦርነት “ሁለት አንባገነኖች ንፁዓንን ያስፈጁበት በኋላ ደግሞ እነርሱ የተቃቀፉበት ነበር” ይላል መሃመድ፡፡ ሁለቱም አሁን የሉም ይህን ታሪክ አድርጎ ወደፊት መሄድ ነው ያለብን ነው የሚለው፡፡ በሃያ አንደኛው ክፍለ ዘመን ድንበር አርቴፊሻል ነው ብሎ ያምናል፡፡ ኢትዮጵያዊያኖች ባህር ዳር ሆነው ለመዝናናት ከሞምባሳ የእኛ ይቀርባል ይላል፤ ሶማሌዎችም ኢትዮጵያ ቤታችን ነው ብለው ያምናሉ እንደ መሃመድ እምነት፡፡ ኢትዮጵያዊያን ሁሉን ነገር ትተው በችግራችን ጊዜ እንደ ሀገራችን እንድንኖር ማድረጋቸው በፍፁም የሚረሳ ውለታ እንዳልሆነ ነው መሃመድ የሚተርከው፡፡
መሃመድ ይህን ሁሉ ባጫወተኝ ማግስት የኢትዮጵያ ጦር ወደ ደቡብ ጁባ ላንድ ሊገባ መሆኑን በተለመደ የመረጃ ቃራሚነቱ ሰምቶ ግርማ አሁንም የኢትዮጵያ ጦር ወደ ሶማሊያ መግባቱ ለህዝቡ በደንብ እንዲያውቀው ካልተደረገ መንግሰት ለመንግሰት ብቻ በሚደረግ ሰምምነት መሆኑ ችግሩን ከማባባስ አልፉ አልሻባብን ያጠናክራል የሚል ስጋት አለኝ ብሎ ፍርሃቱን አጋራኝ፡፡ እውነት ነው ደካማ የሱማሌ መንግሰት የሚያግዘው ጉልበተኛ ያስፈልገው ይሆናል፤ ለሀገር ዘላቂ ጥቅም ሲባል ግን ለአልሸባብ የሚወረወሩ ጥይቶች ሰላማዊ ዜጋ፣ ሴቶች እና ህፃናትን እንዳይጎዱ ጥንቃቄ መደረግ ይኖርበታል፡፡
ቸር ይግጠመን

No comments:

Post a Comment