Friday, March 7, 2014

የትራፊክ አደጋን ለመቀነስ በምሽት አትንዱ!! ዘመኑን መረዳት ያቃተው የሰነፍ ውሳኔ!!



በጥር አጋማሽ አካባቢ ምክር ቤቱ ለዕረፍተ ከመበተኑ በፊት አስቸኳይ ያላቸውን ጉዳዮች ለመጨረስ በሚል ከስዓት በኋላ በሰምንት ሰዓት ለመገናኘት ቀጠሮ ይዞ ምክር ቤቱ ሲበተን ወደ ቢሮዬ ተጠግቼ ምሳ ለመብላትና እግረ መንገዴንም በቢሮ አንድ አንድ ነገር አድርጌ ለመመለስ ሳዘግም ፒያሳ ላይ ያለው የትራፊክ ጭንቅንቅ መላወሻ ሲያሳጣኝ ፌቴን አዙሬ ወደ ጣይቱ ሆቴል አመራው፡፡ ብቻዬን ምግብ ቤት መመገብ ባልወድም የግዴን አንድ ጥግ ይዤ ቁጭ እንዳልኩ አንድ ሰው መጥቶ ቅር ካላለህ አብሬህ ብቀመጥ ብሎኝ ፈቃድ ሲጠይቀኝ በደስታ ብዬው አብረን ምሳ በላን፡፡ ጋበዘኝም! ግብዣውን ላለመቀበል  ስግደረደር አይዞህ አንተ ባለስልጣን አይደለህም ካንተ ምንም አልፈልግም ብሎ ካሰፈገገኝ በኋላ ወግ ጀመርን፡፡ እዚህም እዚያም እያልን ብዙ ጠቃሚ ውይይቶች ለማድረግ ዕድል አገኘሁ፡፡ እንዲህ ዓይነት አጋጣሚዎች ለእንደኔ ዓይነቱ መረጃ ቃራሚ ጠቃሚ ነው ብዬ ነው የምወስደው፡፡
ካነሳናቸው ጉዳዮች አንዱ በምሽት አገልግሎት እንዳይሰጡ የታገዱትን ሚኒባስ እና መስል መኪኖችን የሚመለከት ሲሆን፤ በዛሬ ፅሁፍ ይህን ርዕስ እንዳደርግ ጫና ያደረገብኝ ደግሞ ከዚሁ ጉዳይ ጋር ተዛማጅ የሆነ ዘግናኝ ዜና በጠዋት በመስማቴ ነው፡፡ ይህውም በምሽት የሚደረግ ትራንስፖርት አሁንም ባለመቆሙ፣ ይልቁንም በድብቅ በህገወጥ መንገድ የሚደረግ መሆኑ ያስከተለው አደጋ ነው፡፡ በጥር 27  ሊነጋ ሲል ከጎንደር አዲሰ አበባ ሰዎች ጭኖ ሊገባ ሲል ነጋ አልነጋ ብሎ ሲከንፍ ለጉዳያችን በፍጥነት እንደርሳለን ያሉ ሰድስት ሰዎች ወዲያውኑ ህይወታቸው ያለፈ ሲሆን፣ ብዙዎች ለከባድና ቀላል ጉዳት ተዳርገዋል፡፡ በሀገራችን በትራፊክ አደጋ ህይወታቸው የሚያልፈው ቁጥሩ አሁን እየቀረበ ካለው እንደሚልቅ ደግሞ አንድ ባለሞያ በማግስቱ በሚዲያ ሲናገሩ ሰማሁ፡፡ ከባድ ጉዳት ደርሶባቸው ከጥቂት ቀናት በኋላ ህይወታቸው የሚያልፍ ሰዎች በመረጃው ውስጥ እንደማይካተቱ ነው ያስረዱን፡፡ በሀገራቸን የሚከሰተው የትራፊክ አደጋ ዝቅ ብሎ የሚቀርበውም መረጃ ቢሆን በምንም መመዘኛ ተቀባይነት እንደሌለው ማንም ይስማማል፡፡ ዛሬ የትኩረት አቅጣጫ ማድረግ የፈለኩት ግን የምሽት ትራንስፖርት የተከለከለው በእርግጥ አደጋ ለመቀነስ ነው? ወይስ ሌላ ውስጠ ወይራ አለው?
በምሳ ላይ ያጫወቱኝ ግለሰብ እንደሚያምኑት ከሆነ በምሽት በሚኒባስ የሚደረግ ጉዞ የተከለከለው አንድም የቴክኒክም ሆነ የህግ መስረት ኖሮት ሳይሆን ይልቁንም በዋነኝነት ሚኒባሶች በሚሰሩበት መስመር የሚንቀሳቀሰው የትራንስፖርት አገልግሎት ሰጪ  “ሰላም ባስ” በመባል የሚታወቀው ድርጅት ባለቤትነቱ የኤፈርት ድርጅት ገቢ በመቀነሱ ነው የሚል ነው፡፡
ይህ ምንም እውነት የሌለው ግምት ወይም አሉባልታ ነገር ነው ተብሎ የማይተው ቢሆንም ግን ሚኒባስ ከ150 ኪሎ ሜትር በላይ መሄድ አይችልም ብሎ ብቃቱ ላይ ምስክርነት የሰጠው ማን ነው? አንድ ሚኒባስ ከአዲስ አበባ ናዝሬት ሶስት ጊዜ ደርሶ መልስ ሄደ ወይም ቀጥ ብሎ ባህርዳር፣ጎንደር ወይም ድሬዳዋ ሄደ ለውጡ ምን እንደሆነ የሚያስረዳኝ ሰው ፈልጌ ማግኘት አልቻልኩም፡፡ ሌላው አስገራሚ ጉዳይ ተመሳሳይ የሆኑ መኪኖች ነገር ግን ባለቤታቸው ግን መንግሰት ወይም የቱሪስት ድርጅት ከሆነ በፈለጉት መንገድንና ጊዜ መጓዝ የሚከለክላቸው የለም፡፡ ተመሳሳይ መኪና ባለቤቱ ብቻ ስለተለያየ እንዴትና ወዴት መሄድ እንዳለበት ገደብ ይጣልበታል፡፡ የቴክኒክ ብቃት ከሆነ ምክንያቱ በማንም ባለቤትነት ይያዝ እገዳው መፅናት ይኖርበታል፡፡
ብዙ ሰዎች በተለይ በኤፍ.አም ሬዲዮ ስልክ ተደውሎላቸው (ደውለው ማለት ስለሚከብደኝ ነው) በዚህ ጉዳይ የምሽት ጉዞ መከልከል እንዳለበት አበክረው የሚገልፁበት ምክንያታቸው በምሽት በሚደረግ ጉዞ በሚፈጠር አደጋ የተማረሩ የሚመስሉ ናቸው፡፡ እንደው ለነገሩ በቀን አደጋ ቢበዛ በቀንም ይከለከል ይሆን? ሀገራችንን ቀን ከሌሊት ሰርተንም ቢሆን ለውጥ ለማምጣት መድከም ሲኖርብን በቀጭን ትዕዛዝ በምሽት መስራት አይቻልም የሚባልበት ሀገር መሆኗ አስገራሚ ብቻ ሳይሆን አሳኝም ነው፡፡ በሚኒባስ ሳይሆን በአውቶሞቢል ሀገር እያቋረጡ መሄድ በሚቻልበት የቴክኖሎጂ እና የተሻለ የሚባል መንገድ ባለበት ዘመን የዚህ ዓይነት መመሪያ አስገራሚነቱን ያጎላዋል፡፡ ሚኒባሶች መብራት የተሰራላቸው በምሽት መጓዝ ስለሚችሉና ስለአለባቸው ጭምር ነው፡፡ የምሽት ጉዞ በተለይ በጥሩ የአየር ሁኔታ ላይ ለመኪናም ሆነ ለተጓዥ እጅግ ምቹ እንደሆነ የሚታመን ነው፡፡ የየምሽት ጉዞ የሚፈልጋቸውን ጥንቃቄዎች መደረጋቸውን ማረጋገጥ ብቻ ነው የሚያስፈልገው፡፡ በምሽት ተጉዞ፣ በቀጣዩ ቀን ጉዳዩን አጠናቆ በቀጣዩ ምሽት ወደ ቤቱ ተመልሶ ወደ ስራ ለመግባት የሚተጋን ሰው ከዚህ ትጋት የሚያደናቅፉ የኤፍ.ኤም ጀግኖች ተዉ የሚላቸው መኖር አለበት፡፡ ያለበለዚያ ግን እንደሚባለውም የገዢዎች ንብረት እና ተጠቃሚነትን የሚነኩ ድርጅቶች እጅ አለበት የሚባለውን ለማመን እንገደዳለን፡፡
ይህንን ሀሳብ ሳቀርብ በምሽት ጉዞ የሚደርስ አደጋን መከላከያው መንገድ ጉዞውን ማስቀረት አይደለም ከሚል መነሻ እንጂ በምሽት ጉዞ ላይ ምንም ዓይነት ቁጥጥር መደረግ የለበትም ከሚል መነሻ አይደለም፡፡ በምሽት መስራትም ሆነ መጓዝ የሚፈልጉ ዜጎች መብታቸው ሊከበርላቸው ይገባል፡፡ ይህ መብት ፀኃይ ስለ አለችና ስለሌለች መሆን የለበትም፡፡ ጉዞው በህግ የሚገዛና ስርዓት ያለው ይልቁንም የዜጎችን ደህንነት በሚያረጋግጥ ደረጃ ላይ መሆኑን መቆጣጠር በሚያስችል መስመር ላይ መሆን ይኖርበታል፡፡ ለምሳሌ አንድ ሚኒባስ 12 ሰው መጫን ካለበት ከ12 ስው በላይ ጭኖ ቢገኝ የሚቀጣው ባለመኪናው ብቻ ሳይሆን በትርፍ ለመጫን ፈቃደኛ የሆነው 13ኛ ሰው ሲከፋም ይህን በመመልከት ምን ይደረግ ብለው ዝም ያሉት ሌሎቹ ተሳፋሪዎች ጭምር መሆን ይኖርባቸዋል፡፡ ይህን ማድረግ ስንችል ሰርዓት ያላው አገልግሎት ሰጪ ብቻ ሳይሆን ሰርዓት ያለው ተገልጋይም ማፍራት ይቻላል፡፡ ሌላው የፍጥነት ገደብ መቆጣጠሪያ ቴክኖሎጂ የመኪና ባለንብረቶች እንዲያስገጥሙ ማድረግ አሁን ባይቻልም፣ መንግሰት በየመቶ ኪሎሜትር ቲኬት መቁረጫ ማሽኖችን በማስቀመጥ አሽከርካረዎች የደረሱበትን ሰዓት በመመልከት ከፍጥነት ገደብ ውጭ የተጓዙት ላይ ተገቢው ህጋዊ እርምጃ እንዲወሰድ ማድረግ ይቻላል፡፡ ይህ ቴክኖሎጂ በየባንኮችና ቢሮዎች ወረፋ ለመያዣነት አገልግሎት እየሰጠ የሚገኝ ማሽን ዓይነት ሊሆን ይችላል፡፡ ሌላው አሽከርሪዎች በጉዞ ላይ የሚጠቀሙተን ጫትና ሌሎች ደባል ሱሶች እንዲያቆሙ በፍፁም ቁርጠኝነት መመሪያውን ለመተግበር በመወሰን እንጂ፤ ሰራ የምትሰሩት ፀኃይ ስትኖር ብቻ ነው የሚለውን የሰነፍ መንገድ ተገቢ ነው ለማለት ያስቸግራል፡፡ ችግር ብልዓትን ይፈጥራል የሚለውን ብሂል ከመተግበር እና ዜጎችን ቴክኖሎጂ ለመጠቀምና ለፈጠራ ከማንቃት ወደ ቁጥጥር ማድለት የመንግሰትን ደካማነት እንጂ ለዜጎች ሃሳቢነትን አያሳይም፡፡

አሁን በማን አለብኝነት ወይም ደግሞ ከአንድ ሰፈር በተፈጠረ የጥቅም ግጭት ምክንያት በተሰጠ ጥቅሻ ብዙ መቶ ሺ ብር አውጥተው ሰርተን እናድጋለን ቤተሰቦቻችንን እናስተዳድራለን ብለው ወደ ትራንስፖርት ዘርፍ የገቡተን ዜጎች እጅግ አሳዝኖዋል፡፡ ይህ ብቻም አይደለም መንግሰት ሊወስዳቸው የሚችላቸው ቁጥጥሮች እና የሚያወጣቸው መመሪያዎች ተገማችነት የሌላቸው በመሆናቸው በማነኛውም የስራ ዘርፍ ተሰማርቶ መስራት አደገኛ ነው ወደሚል መደምደሚያ የሚወስድ ነው፡፡ ብዙ ወጣቶች ይህን ተማምነው ከውጭ መጥተው ሰራ የጀመሩ ቢሆንም አሁን ደግሞ በኪሳራ ሸጠው ወደ ውጭ ለስደት ተሰጋጅተዋል፡፡ በዚህ ገንዘብ ትልቁ ልጄን ውጪ ልኬ መኪናው የሚያመጣውን ያህል እርሱ ይልክልኛል ብለው ያጫወቱኝ ጎልማሳ አሉ፡፡ የመንግሰታችን መልስ ይሞክሩት እንደሚሆን አለመጠርጠር ነው፡፡
በዚህ አጋጣሚ ባለንብረቶች የምሽት ጉዞ ንብረታቸውን ሲያሰማሩ የሾፌሮችን ብቃትና የመኪናቸውን ደህንነት እያረጋገጠ ሰምሪት የሚሰጥ አንድ ማህበር በማቋቋም ንብረታቸውን በህገወጥ መንገድ ለአደጋ እና እንዲሁም ዜጎችን አደጋ ላይ የሚጥል አገልግሎት እንዲቆም ለመተባበር ዝግጁ መሆናቸውን ማሳየት እና በህገወጥ መንገድ የተጣለባቸውን የምሽት አገልግሎት የመስጠት መብት ለማስከበር መንቀሳቀስ ይኖርባቸዋል፡፡ መንግሰትም ከፍተኛ ንብረት ወጥቶበት የተገነቡት መንገዶች 24 ሰዓት አገልግሎት የሚሰጡበትን መንገድ ለማመቻቸት ከክልከላ የተሻለ ዘዴ ለመቀየስ መስራት ይኖርበታል፡፡ ክልከላው የሰነፍ መንገድ ነው፡፡ 
ይህን ፅሁፍ እንድከትብ ያነሳሳኝ የጥር 27/2006 አደጋ መሆኑን በመግቢያዬ ገልጫለሁ፡፡ ስለዚህም ይህ መኪና ከጎንደር ተነስቶ አዲስ አበባ ሊገባ 20 ኪሎሜትር ሲቀረው ነው የተገለበጠው፤ የተገለበጠውም ሳይነጋ ትራፊክ ሳይዘው ለመግባት በሚያደርገው ጥረት እና በነበረው ፍጥነት ምክንያት ነው፡፡ ይህን ሁሉ ኪሎ ሜትር አቋርጦ የተጣለውን ክልከላ ጥሶ ሲመጣ መቆጣጠር ማሰቆም ያልተቻለው ለምንድነው? በዚህ ሁሉ መንገድ የነበሩ ይህን መመሪያ እንዲያስከብሩ ኃላፊነት የተሰጣቸው ክፍሎች ሁሉ በህግ መጠየቅ ይኖርባቸዋል፡፡ በሹፌር ላይ ጥፋቱን አላኮ መቆም የለበትም፡፡ ይህ በጥቅሻ እንቅስቃሴን ማስቆምና ማሰቀጠል ተጠያቂነት ሊኖርበት ይገባል፡፡ የዜጎች ህይወት በከንቱ እንዲጠፋ ምክንያት የሆኑት ሁሉ ለህግ እንዲቀርቡ ሁሉም ይጩኽ፡፡
በመጨረሻም እንደነገሩ የምንፅፋቸው ፅሁፎች አንባቢ እንዳላቸው እርግጠኛ ብሆንም የሚመለከታቸው አካላትም እንደሚያነቡት የሚያሳይ ሁለት የእግረመንገድ ነጥብ ላንሳ፡፡  በአንድ ወቅት ቃሊቲ ሄጄ ባነበብኩት ማሰታወቂያ መሰረት በመንግሰት ሀብት የብአዴን በዓል እንደሚከበር ገልጬ ነበር፡፡ የካቲት 2/2006 አንዱዓለም አረጌን ለመጠየቅ ሲሄድ ምንም ዓይነት ማስታወቂያ በሩ ላይ መለጠፍ ክልክል መሆኑን አንብቤ መጥቻላው፡፡ ይህ የሚያሳየው ፅሁፉን እንዳነበቡት ሲሆን የወሰዱት እርምጃ ግን የመንግሰትን ንብረት ለፓርቲ መጠቀሚያ እንዳይውል ማድረግ ሳይሆን አሁንም የመከልከል ዜዴያቸውን ነው የተጠቀሙት፡፡ የሰነፉን መንገድ፡፡
ሌላው ለፅሁፋችን ተነባቢነት ማሳያው አቶ አሰራት ጣሴ በአዲስ ጉዳይ ላይ ባሰፈሩት ሀሳብ ምክንያት ፍርድ ቤት ደፍረዋል ተብለው ለእስር መዳረጋቸውን ነው፡፡ ፍርድ ቤቶች ሊማሩ የሚገባ የነበረው፤ የዘገየ ፍትህ እንደተነፈገ ይቆጠራል የሚለውን ወርቃማ አባባል ሲሆን በተቃራኒው ከመንግሰታቸው ባልተለየ የማስፈራሪያ ዘዴያቸውን ተግባራዊ አድርገዋል፡፡ በዚህ ጉዳይ ትላንት የተሰጠውን ውሳኔ መሰረት አድርጌ ሳምንት እመለስበታለሁ፡፡
ለማነኛውም የዚህ ፅሁፍ አንባቢ የሆናችሁ የትራንስፖርት ዘርፍ ሹሞች ሀገራችን ኢትዮጵያ ሃያ አራት ሰዓት ሰርተን ዓለም ከደረሰበት ለመድረስ ብዙ እንደሚቀረን ተገንዝባችሁ ለሰራ የሚያነሳሳ ዘዴ እንድታሰቡ አደራ እላለሁ፡፡ ያለበለዚያ የትራፊክ አደጋን ለመቀነስ የቀኑንም ትራንሰፖርት አስቁሙና የትራፊክ አደጋ በመቀነስ ከዓለም አንደኛ ለመሆን ሞክሩ፡፡ በትራንስፖርት ኤኮኖሚክስ ከአደጋ ነፃ የሚባለው ዜሮ ርቀት ነው፡፡
ቸር ይግጠመን

No comments:

Post a Comment