Monday, April 27, 2015

ክርክር 6፡ ኢህአዴግ እና 1997 ስብርባሪዎች!!!!

በዛሬው ሰድስተኛ ዙር የምርጫ ተብዬ ክርክር ጉዳዩ በመሰረተ ልማት ላይ ያተኮረ ነው፡፡ ኢህአዴግ ጎምቱ ያላቸውን ሹሞቹን ለክርክር ይዞ የቀረበበት ቢሆንም ለእኔ ግን ትኩረቴን የሳበው የተከራከሩበት ርዕስ ሳይሆን ተከራካሪዎቹ ሰዎች እና ፓርቲዎች ናቸው፡፡ ማለት የፈለኩት የመሰረተ ልማት በሚል ርዕስ ክርክር ስመለከት የተገነዘብኩት ጉዳይ ቢኖር ኢህአዴግ ክርክር እያደረገ ያለው የዛሬ አስር ዓመት ለሚዲያ ክርክር ድመቅት ይሰጥ ከነበረው ከቅንጅት ስብርባሪ ጋር አንደሆነ ተረዳሁኝ፡፡ ህብረትም ቢሆን አሁን በመድረክ በኩል በድሮ ግርማ ሞገሱ አይታይም፡፡ እውነቱን ለመናገር አሁን በክርክሩ ላይ የሚገኙት ሰዎች ኢህአዴግ በልኩ የሰራቸው፤ በእግራቸው ገመድ የተበጀላቸው ጭምር ናቸው፡፡ ምንም ቢሉ ማንም ምንም የማይሰማቸው፡፡
ኢዴፓ በ1997 ከተቀናቃኙ መኢህአድ ጋር ያለውን የውስጥ ግብ ግብ ቅንጅት የሚባል ፓርቲ እውን እንዳይሆን በማድረግ፣ አንድ አንዶቹን በግል ታሪካዊ የፖለቲካ ዋጋ አስከፍሎ አሁን ባለበት ደረጃ ይገኛል፡፡ ይህ የኢዴፓ አመራር ውሳኔ ኢትዮጵያ ሀገራችንም በመድበለ ፓርቲ ስርዓት ግንባታ ዋጋ እየከፈለች እንድትገኝ አድርጓል፡፡ በሁለት ሺ ሰባት ምርጫ ኢዴፓ እንደ ፓርቲ መንግሰት እንደማይሆን ቢታወቅም ወደፊት ፓርቲስ ይሆናል ወይ? የሚል ጥያቄ ሁሉ ማንሳት የግድ የሚል ነው፡፡ ይህ በፍፁም ሟርት አይያደለም በምድር የሚታይ ሀቅ ነው፡፡ ለማነኛውም ኢዴፓ የዛሬ አሰር ዓመት በ1997 ክርክር የቅንጅት ፈርጥ ሆኖ ክርክሩን ያደመቀ ቢሆንም ዛሬ ይህን ሊያደርግ አልተቻለውም፡፡ ኢህአዴጎች በጥርስና ጥፍራቸው ቅንጅትን ሲያፈርሱ ያተረፉት ሽራፊ ኢዴፓ አሰር ዓመት አፈር ልሶ መነሳት ሳይችል ቀርቷል፡፡ አሁንም በምድር ላይ እየዳከረ ይገኛል፡፡
ኢዴፓ ማህተም አላደርግም በማለት ያፈረሰውን ቅንጅት ቢያንስ በፍረስራሽ በቅጡ እንዳይሰራ ያደረገው ደግሞ አቶ አየለ ጫሚሶ ነው፡፡ መቼም ይህን ሰም የማያውቅ ያለ አይመስለኝም፡፡ “ቅንጅት”  በአቶ አየለ ጫሚሶ ተወክሎ ቅንጅት ቢመረጥ እንዲህ ያደርጋል ይህን ይፈጥራል ሲሉን እኛ የምናወቀው የ1997 ቅንጅት የሌለ መሆኑን፤ የፈለግነው ቅንጅት እንዳይኖር የተሰራው “ቅንጅት” እንኳን ለኢትዮጵያ ህዝብ የሚጠቅም አጀንዳ አይደለም እንደ ድርጅትም ቁመናውን አስተካክሎ የሚሄድ እነዳልሆን እናውቃለን፡፡ እውነቱን ለመናገር እነርሱም በሚዲያ ቀርበው አይተናቸዋል፡፡ ለማነኛውም ይሉሹን በሰማሽ ገበያ ባልወጣሽ የሚባለው የዚህ ዓይነቱ ድርጊት ነው፡፡ የቅንጅት ምልክት የነበረው ሁለት ጣት አሁንም “ቅንጅት” ለሚባው ድርጅት ቢሰጥም በተግባር ግን በስራ ላይ እንደሌለ ይታወቃል፡፡ ትዝ ይላችሁ እንደሆን “ጣት እንቆርጣለን” እስክንባል ድርስ ይህች አስማተኛ ምልክት የዛሬ አስር ዓመት የሰራቸው ስራ በእውነት ግሩም ድንቅ ነበር፡፡ የእኛን ቅንጅት ነብስ ይማር ብለናል፡፡
መድረክ አሁን ባለው ቁመና የ1997 ህብረት ሰዎች በተወሰነ ደረጃ ቢይዝም ህብረትን የሚያክል አይደለም፡፡ በነገራችን ላይ ከምርጫ በኋላ ቅንጅት የሚባል እንዳይኖር የአሁኖቹ መድረኮች ያላቸው ጥላቻ ቀላል አይደለም፡፡ ፕሮፌሰር በየነ ጴጥሮስ አሁንም ቢሆን ከቅንጅት መንፈስ ጋር ግብ ግብ ላይ እንዳለ ማወቅ የፈለገ የ1997 ጫወታ አንስቶ መሞከር ነው፡፡ በሌሎቹም የህብረት አባል ድርጅቶች እሰከ ፓርላማ የደረሰ ደባ በቅንጅት ላይ እንደሚሰራበት የሚታወቅ ነው፡፡ የዚህ ደባ ባለቤቶች አሁንም የመድረክ አባሎችና አመራሮች ናቸው፡፡ መድረክ አንድነትን ከሚጠላበት አንዱ ምክንያት በአንድነት ውስጥ የሚታየው የቅንጅት መንፈስ ጭምር ነው፡፡ የአሁኖቹ አመራሮች ከአንድነት ጋር ሲነነጋገሩ የሚሰማቸው ሰሜት በ1997 ህብረት ሆነው ከቅንጅት ጋር የሚያደርጉት ውይይት/ክርክር ነው፡፡ በክርክሩ ውስጥ ሁሌም ጠልፉ መጣል አለ!! የኢትዮጵያ ፖለቲከኞች ልዬ ችሎታ፡፡
አሁን ደግሞብ በብረት ሰንሰለት ተይዞ የሚገኘው ሰማያዊ ፓርቲ ነው፡፡ ሰማያዊ የት ድረስ ይጓዛል? አላውቅም፡፡ ሰማያዊ ፓርቲም ቢሆን የቅንጅት አብዛኛውን አመራርና አባል ይዞ የተመሰረተው አንድነት ፓርቲ ስባሪ ነው፡፡ ስለዚህ የቅንጅት አካል እንደነበር ማወቅ ያስፈልጋል፡፡  በሁለት ሺ ሁለት ምርጫ አንድነትን ምርጫው ላይ ውጤታማ እንዳይሆን ከኢህአዴግ ባልተናነሰ ገትረው የያዙት ልጆች ሳይዘገዩ በአምስተኛ ዓመቱ የምርጫ ፈተና ከኢህአዴግ ጋር እንዴት እንደሆነ እየቀመሱት ነው፡፡ በሆነ ባልሆነው ሰማያዊ የሚለው መንግሰትም ከሰማያዊ አልላቀቅ ብሎ ምን ሊያደርግ እንደሚችል እየተጠበቀ ነው፡፡ የኢህአዴግ ትልቅ ግብ በዚህ ምርጫ መንግሰት መመስረት የሚመስለው ካለ ተሳስቷል፡፡ ሰማያዊን ለማዋረድ ነው የሚሰራው፡፡ በኢቲቪ በሰማያዊ ላይ የተያዘው ዘመቻ የአንድ አንድ የህግ ባለሞያዎች ተብዬ አስተያየት ጥፍራችን ውስጥ እንድንደበቅ የሚያደርግ ነው፡፡ እረ በህግ መባል ያለባቸው ናቸው፡፡
ሌሎች ተሳታፊ ፓርቲዎችን ትተን ከላይ የዘረዘርናቸው ፓርቲዎችን ስንመለከት ኢህአዴግ የዛሬ አስር ዓመት ሰንገው ይዘውት ከነበሩ አሁን ግን ምንም ማድረግ ከማይችሉ ደካማ ስብርባሪ ፓርቲዎች ጋር ተራ ገብቶ እየተጫወተ ነው፡፡ ሁሌም እንደምለው ኢህአዴግ ብጤዎቹን በትክክል መርጦዋል፡፡ ከዚህ ከፍ ያለ ጫወታ አይችልም፡፡ ከዚህ ከፍ ካለ ኢህአዴግ ቀልድ አያውቅም ለሰፊው ህዝብ ጥቅም ሲል ታንክም ባንክም ለመጠቀም ወደኋላ የሚል አይደለም፡፡ አሁን ለጊዜው በቁጥጥር ስር ያሉ ሚዲያዎች እና ሆዳሞች ይበቁታል፡፡ ታንክ አያስፈልግም ማለቴ ነው፡፡ ሚዲያና ሆዳሙን ለመጥቀም ያህል ባንክ ይጠቀም ይሆናል፡፡

ቸር ይግጠመን!!!!!

No comments:

Post a Comment