Tuesday, April 21, 2015

ክርክር አምስት መልካም አስተዳደርና የህግ የበላይነት ግርማ ሠይፉ ማሩ



girmaseifu32@yahoo.com; girmaseifu.blogspot.com
ተሳታፊዎች
·         ወልዴ ዳና  እና ሰለሞን ታፈስ             ከአትፓ  
·         ዋሰይሁን ተሰፋዬ ወንዶሰን ተሾመ        ከኢዴፓ
·         ይድነቃቸው  ከበደ                          ከሰማያዊ
·         ብርሃኑ በርሄ እና ደጀኔ                     ከመድረክ
·         አሰቴር ማሞ እና አባይ ፀሓዬ              ከኢህአዴግ
የሚያዚያ ዘጠኝ ቀን 2007 ክርክር እንዳበቃ አንድ አንድ ነዋሪዎች አስተያየት በሚል በኢትቪ የቀረበው ዜና አስቂኝ ነበር፡፡ በመጀመሪያ ፕሮግራሙ በተላለፈ እለት እንዴት አድርገው ይህን ሊሉ ቻሉ? የሚለው ዋነኛ ጥያቄ ነው፡፡ ምርጫ ቦርድ ገለልተኛ ፓርቲ ነው (ተሳስቼ አይደለም ሃሳብ የሰጠች የአዲስ አበባ ነዋሪ ነች እንዲህ ያለችው)፣  ሰማያዊ ፓርቲ የአባይ ግድብን ማጣጣል ተገቢ አይደለም ተብሎዋል.፤ የብሔሮችን እኩሉነትን የማይቀበል ሰማያዊ ፓርቲ፤ ወዘተ የሚሉ አስተያየቶች የሚያሳዩት ሰማያዊ ፓርቲ ላይ የተያዘው ዘመቻ ግቡ ምን እንደሆነ እየቆየን እንደምናየው ነው፡፡ ከዚህ ሁሉ በላይ ግን የሚከረፋው ኢቲቪ የሚባል የመንግሰት የሚዲያ ተቋም ይህን ያህል መውረዱ ብቻ ሳይሆን ለዚህ ተሳታፊ የሚሆኑ ሰዎች ያለማጣታችን ነው፡፡ ቢፈልጉ ፎረም የፈለጉትን ሊሆኑ ይቸላሉ ….. ይህች ሀገር ትንሳኤ የምታገኘው የዚህ ዓይነት ውርድት አንቢ የሚል የሀቅ፣ የነፃነት ሠራዊት ሲበዛ ነው፡፡
ከመንግሰቱ ሀይለማሪያም ቀጥሎ በኢትዮጵያ ከፍተኛውን ስልጣን የያዘው ማን ነው? ቢባል መለስ ዜናዊ ያለ ልክ ሊሆን ቢችልም አሁን ግን ጠቅላይ ሚኒስትር ሀይለማሪያም ናችው ብሎ ማንም ስህተት አይሰራም፤ ከጠቅላይ ሚኒሰትሩ በለይ ፈላጭ ቆራጭ የሆነ ስልጣን ያለውን ሰው የመድረኩ ተከራካሪ በይፋ ተናግረዋል፡፡ የስልጣኑን ዝርዝር የሚታወቅ ስለሆነ መዘርዘር አያሰፈልግም ብሎኛል አንድ ወዳጄ፡፡ ይደር በሚል!!!!
ኢህአዴግ ለክርክር ይዞ የቀረበው አቶ አባይ ፀሃዬ የመልካም አስተዳደርና የህግ የበላይነት ክርክር ላይ በግንባር ቀደምነት ይገኛሉ ብዬ አልገመትኩም፡፡ እነዚህ ሁለት ጥንድ ርዕሶች የራሳቸው ጌቶች አላቸው፡፡ አንደኛው እንደገመትኩት ወ/ሮ አስቴር ሲሆኑ ሁለተኛው ደግሞ የፍትህ ሚኒስትሩ አቶ ጌታቸው አምባዬ ይሆናሉ ብዬ ነበር፡፡ ብአዴን በዚህ ቦታ የሚያስቀምጣቸው ሰዎች የተሳካላቸው አልመሰለኝም፡፡ በአምስት ዓመት አንዴ በሚመጣ በህዝብ ፊት አንደበተ ርዕቱነት፣ታጋሽነትን፣ ወዘተ ሊፈተንበት የሚችል የአደባባይ መድረክ የፍትህ ሚኒሰትሩ ሊያገኙት አልቻሉም፡፡ የዚህ ውስጠ ወይራ አቶ ጌታቸው አይችሉም ብቻ ሳይሆን እርሳቸው በህግ የበላይነት ዙሪያ ከህውሃት ኢህአዴግ የበለጠ የማስረዳት የባለቤትነት ጉዳይም ጭምር ነው የሚመስለው፡፡
ሌላው ውስጠ ወይረ በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ማዕረግ የሲቪል ሰርቪስ ሚኒስቴር ሚኒስትር የሆኑት የኦህዴድ “ዋና” ሰው ወ/ሮ አስቴር ማሞ ቀደም ሲል የኮርፖሬሸን ስራ አስኪያጅ አሁን በተፈጠረው የቡድን አመራር የጠቅላይ ሚኒስትር አማካሪ ዋና ተከራካሪነት እርሳቸው በምክትልነት ተከራካሪነት ቀርበው አይተናቸዋል፡፡ አንድ አንድ ጊዜ የኦሮሞ ልጆች ለምሳሌ ወዳጄ ሰለሞን ስዩም ትልቅ ህዝብ ትንሽ ፓርቲ የሚለውን ኦህዴድ አግኝቼዋለሁ፡፡ ለማነኛውም የጎንደር አማርኛ የሚናገሩት ወ/ሮ አስቴር ማሞ ይህ የደረጃ ጉዳይ ነው ለምን? እንዲህ ይሆናል አላሉም አይሉምም፡፡ ፓርቲያቸው በመደባቸው ቦታ ይስራሉ፣ ይታዘዛሉ፡፡ እምቢ የሚባል ነገረ ቦታ የለውም፡፡
እስከ አሁን ባሉት ክርክሮች ያሰጠላኙ ነገሮች መካከል ኢህድግም ሆኑ ተቃዋሚዎች እንኳን አደረሳችሁ ለአምስተኛው ሀገራዊ ምርጫ የሚሉት ቀልድ፣ ኢህአደግ በግሉ አማራጭ የሌላቸው ተቃዋሚዎች እና ተቃዋሚዎች በሙሉ ደግሞ ብንመረጥ እንዲህ እናደርጋለን ብሎ መዋሸት ዋና ዋናዎቹ ናቸው፡፡
በዚህ ክርክር ነጥብ ያሰቆጠሩት ተከራካሪዎች የኢዴፓው ዋስይሁን እና የሰማያዊ ይድነቃቸው ቢሆኑም የኢህአዴግ ተከራካሪዎች ትኩረት ያደረጉት ግን በሰማያዊ እና በመድረክ ላይ ነበር፡፡ ለምሳሌ ሰማያዊና መድረክ ሀገር የመምራት ብቃት አላችሁ? የሚል ጥያቄ በኢህአዴግ ሲቀርብባቸው ኢዴፓ ይህ ጥያቄ ሊቀርብለት አልቻለም፡፡ ከዚህ ተደጋጋሚ ኢዴፓን በለውሳስ የማለፍ ሰሜት ኢህአዴግ በሚቀጥለው ምርጫ የኢዴፓ ውጤት ምንም ይሁን ምን ለኢዴፓ የሆነ ቦታ ለማጋራት ፍላጎት ያለው ይመስላል፡፡ ተራ ግምት ሊሆን ይችላል፡፡ ብሳሳትም ልክም ብሆን ምንም የተለየ ነገር አይኖርም፡፡ ኢዴፓዎች በልደቱ በኩል ያተረፉት ነገር ቢኖር በእንደዚህ ዓይነት ህዝባዊ መድረኮች በኢህአዴጎች አለመዘርጠጥን ነው፡፡ ይህ ለነገሩ የፓርቲዎች ምክር ቤት አባላት በሙሉ የጋራ ጥቅም ሳይሆን አይቀርም፡፡ አትፓ መቼም ከዚህ ዘለፋ የሚድነው ሀገር ለመምራት ባለው ብቃቱ አይመስለኝም፤ የፓርቲዎች ምክር ቤት አባል በመሆኑ ይመስለኛል፡፡
የአትፓ ባለቤት አቶ አስፋው ጌታቸው ከዚህ በፊት የለገስኩትን ምክር ብጤ ሰምቶ ከክርክሩ ዞር ቢልም የተለወጡት ሰዎች ፓርቲው ሲገለጥ ያሉትን አባላት ጥንካሬ ለማወቅ የሚረዳን ሆኖ አግኝቸዋለሁ፡፡ የአትፓ ተወካይ ከፖለቲካ ይልቅ እንዲሁ ከአምሳያ ወዳጆቻቸው ጋር በመሆን በፀሎት ሊረዱን ቢሞክሩ የተሻለ ነበር የሚል የግል አስተያየት አለኝ፡፡ ለነገሩ ፀሎት ቅን ልቦና ይጠይቃል፡፡ የፀሎት ትሩፋት ከራስ አልፎ ለሌላው እንዲተርፍ ካሰፈለገ ማለቴ ነው፡፡ ያለበለዚያ እንኳን አደረሳችሁ ለ2007 ምርጫ ለመባባል አይመስለኝም፡፡ የአትፓ ተወካይ ሰፋ ያለ የአድሎዎ ዝርዝር የገለፁ ሲሆን እርሳች አባል የሆኑበት የዓይማኖት ድርጅት ለስራ ቅጥር አንኳን ችግር እንዳለው ተናግረዋል፡፡ ሌላውን ሁሉ ትተው የአትፓ ተወካይ ሌቦችና ወንጀለኞች ጌታ በሆኑበት እስር ቤት፤ የፖለቲካ እሰረኞች ላይ የሚደርሰውን ግፍ ማንሳታቸው ለወሰዱት 19 ደቂቃ ከፓርቲው ከሚጠበቀው በላይ ሆኖ አግኝቼዋለሁ፡፡ ከማርሸ ቀያሪ ነኝ ከሚለው አትፓ ምንም ስለማልጠብቅ፣ ይህን እንደጥሩ ነጥብ አድርጌ ዘገባዬን አብቅቻለሁ፡፡
ኢዴፓ የመልካም አስተዳደር መመዘኛ ነጥቦችን አስቀምጦ አቶ አባይ ፀሀዬንም በዚሁ መስፈርት መሰረት እንዲፈሱ አድርጎዋቸዋል፡፡ ኢዴፓ የእነዚህ መሰፈርቶች ፈልሳፊ ባይሆን እንኳን ኢህአዴግ በነዚህ ዓለም አቀፍ መስፈርቶች መውደቁን ለማሳየት ተጠቅሞበታል፡፡ ወደ ዝርዝሩ መግባት ባልፈልግም ኢህአዴግ እነዚህን መሰፈርቶች በየመስሪያ ቤቱ መግቢያ ላይ የለጠፋቸው ቢሆንም አንዳቻውንም በተግባር አንደማያውል የአገልግሎት ፈላጊው ህዝብ ምስክር ነው፡፡
ለሲቪል ሰርቪስ ሰራተኛ ግልፅ ወገንተኝነቱን በተደጋጋሚ የሚገልፀው ኢዴፓ የሲቪል ሰርቪሱን ድክመት በግልፅ አስቀምጦዋል፡፡ ሲቪል ሰርቪሱ በእውነትም የአቅመ ቢሶች መጠራቀሚያ እንደሆነ በግልፅ ተከራካሪው ለማሰቀመጥ ሞክሮዋል፡፡ የሰቪል ሰርቪስ ሰረተኛው አቅም በፈቀደ ድጋፍ የሚደረግለት እንጂ በሰራበት ልክ የሚከፈለው እንዳልሆነ ጭምር የተመሰከረለት ነው፡፡ ተደጓሚ አንጂ በስራው ልክ የማይከፈለው፣ በአብዮታዊ ዲሞክራሲ መፍስስ ግዴታው የሆነ እንደሆነ መረዳት የሚያስችል ክርክር ነበር፡፡ ኢዴፓ እነዚህ ክርክሮች ይህን መስመር እንዲይዙ እና በምክትል ጠቅላይ ሚኒሰትር ማዕረግ ያሉት የኢህአዴግ ተከራካሪ እንዲፎርሹ እድል ስጥቷቸዋል፡፡ ምን ዋጋ አለው ሲቪል ሰርቪሱ ይህን ክርክር መሰረት አድርጎ ይወስናል የሚል እምነት የለኝም፡፡ ሁለም እንደሚያቀው የሲቪል ሰርቪስ ጠንካራው ሰራተኛ በአብዮታዊ ዲሞክራሲ መስመር አልገባም ብሎ መንግሰታዊ ያልሆኑ ተቋሞች ውስጥ ሲገባ እነዚህን ተቋሞች የኪራይ ስብሰቢ መታጎሪያ ተብለው ተፈርጀዋል፡፡
ኢዴፓዎች የሱማሌን ጦርነት ከኢህአዴግ ጎን ቆመው ከደገፉበት ቀን ጀምሮ አንገት ያስደፋቸውን የሀገር መረጋጋት በሚቃረን መልኩ ይህች ሀገር የተረጋጋች ነች ማለት አይቻለም ብለው ወደ ትክክለኛው ግምገማ ቀርበዋል፡፡ እዚህም እዚያም የታጠቀ ሀይል እየተንቀሳቀሰ ነው በሚል ሙግት አቅርበዋል፡፡ ኢህአዲጎች እዚህም እዚያም ያለ ቡድን ብለው ለማጣጣል ቢሞክሩም ችግሩን ማመናቸው ግን አልቀረም፡፡ ህወሓት በደርግ ጥቂት ወንደበዴዎች ይባል እንደነበረው ማለት ነው፡፡
ኢዴፓዎች ኢህአዴግ ሰለ መልካም አስተዳድርና የህግ የበላይነት ለማውራት የሞራል ልዕልና እንደሌለው ከማሳሰብ በተጨማሪ  በህግ አምላክ ብሎ የሚያምን ህዝብ በህግ ላይ እምነት ያጠበት ወቅት መሆኑን በጥድፊያ አስቀምጠዋል፡፡ ፍትህ አደጋ ላይ የወደቀበት ከደርግም ከንጉሱ ጊዜ የባሰ ነው በሚል ነው የገለፁት፡፡ ይህ አገላለፅ አቶ አባይ ፀሃዬን ከምንም በላይ ያስቆጣቸው ቢሆንም፡፡ ፍርድ ቤት አሽንጉሊት ከመባል ያለፈ ምን ይባል? ከዚህ በላይ የት ይውረድ? ብለው ሞግተዋል፡፡ መንግሰት ደግሞ ፍርድ ቤት የፈታውን የሚያስር ከሆነ ከዚህ በላይ ምን ዓይነት ጣልቃ ገብነት ነው የፈለገው? ብለውም ለህዝብ ለማሳየት ሞክረዋል፡፡ ባጠቃላይ ሲታይ የህግ የበላይነት ሳይሆን የፖለቲካ እና የገንዘብ የበላይነት የነገሰበት ነው፡፡ ፖለቲካና ገንዘብ ያለው የፈለገውን ለማድረግ የሚችልበት ሀገር ነው፡፡ የሙስና ዜናዎች ዘግናኝ ሆኖዋል፡፡ ስንት ትከፍላለህ ጉዳይ ለማስፈፀም መደበኛ የስራ ሂደት ሆኖዋል ሲሉ ለህዝቡ አቅርበዋል፡፡ ለዚህም ነው ኢህአዴግ ስለ ህግ የበላይነት እና መልካም አስተዳደር ለማውራት የሞራልም ሆነ የህግ ልዕልና የለው የምንለው ብለው ትንፋሽ እያጠራቸው አሰረድተውል፡፡ ለዚህ ነው እኛም ቤት ሆነን ምርጫችን ያልሆነውን ኢዴፓ ኮፍያ አንስተን ልክ ልክ ነገረልን ያልነው፡፡  ኢዴፓ ቢመረጥ ይህን ይህን እናደርጋለን የሚለውን ፌዝ ትተን ማለት ነው፡፡ ኢዴፓ ግን ከሁሉም በተሻለ እንደዚህም የምር ተናግሮ በቀጣዩ መንግሰት አንድ ነገር ሊያገኝ የሚችል ነው የሚል ተሰፋ አለኝ፡፡ በችሎታ ሳይሆን በችሮታ፡፡
ሰማያዊ ፓርቲ ክርክር የነበረበት ከተሰጠው ርዕስ ጋር ብቻ ሳይሆን ከአወያዩ ጋዜጠኛ ጭምር እንደነበር ለመረዳት አሰቸጋሪ አልነበረም፡፡ ይህን ጋዜጠኛ በቀጣዩ ቀን ደግሞ በሌላ አንድ ለአንድ በሚል ፕሮግራመ ከኢዴፓ የህዝብ ግንኙነት ጋር ክርክር ሲያደርግ አድምጨው ዶክተር መረራ ተማሪዬ የሚሉት ጋዜጠኛ ሊብራል ዲሞክራሲን በዚህ ደረጃ አስረድተው ከሆነ ያስመረቁት ለትምህርት ክፍሉም ነው ያዘንኩለት፡፡ የሰማያዊ ተከራካሪ ከዚህ ጋዜጠኛ አረዳድ ጋርም ጭምር ነበር ክርክር የገባው የሚል እምነት አለኝ፡፡ አንባቢ ይፍረደኝ ሊብራል ዲሞክራሲ ለጥቂት ባለሀብቶች የቆመ ነው የሚል መፅኃፍ የት ነው ያነበበው? የአብዮታዊ ዲሞክራሲ መፅሃፍ እንዲህ የሚል እንደሆነ አውቃለሁ፡፡ ይህ ደግሞ እውነት አይደለም፡፡ ይህ ጋዜጠኛ አነስተኛ ደሞዝ ወለል መወሰን ከሊብራል ዲሞክራሲ አስተሳሰብ የወጣ ነው ብሎ ያምናል፡፡ ጋዜጠኛው 2 ከመቶ የሚሆኑ ሀብታሞች ያሉበት ዓለም ብርቅ ለምን እንደሆነበት አይገባኝም፡፡ በዓለም ላይ ያሉ ጥቂት ነገሮች ሀብታሞች ብቻ አይደለም፡፡ ለምሳሌ በዓለም ላይ ያሉ ባለስልጣኞች ዜሮ ነጥብ አንድ አይሆኖም፡፡ በዓለም ላይ ያሉ ፓይለቶችም እንዲሁ ትንሽ ናቸው፡፡ እንዲህ ብሎ መቀጠል ይቻላል፡፡
ለሰማያዊ ፓርቲ የኢዴፓ ከፊት ቀድሞ የመልካም አስተዳደር መስፈርቶች እና የኢህአዴግ ድክሞቶች ማቅረቡ ሰማያዊ ፓርቲ ቀሪውን የኢህአዴግ ዘባተሎ ለማስረዳት እድል የሰጠው ይመስለኛል፡፡ የይድነቃቸው ጮሌነትም ይህን ለመጠቀም የረዳው ይመስለኛል፡፡ ይህን ክርክር ከህግ አግባብ ውጭ በእስር የሚማቅቁ ወንድሞችና እህቶች ካልተነሱቡት፣ ለደሞዝ እንጂ ለውጤት የሚሰራ ሲቪል ሰርቪስ እንደሌለን ካልተዘከረበት ምን ክርክር ሊባል ይችላል? ሰማያዊ ፓርቲ ተወካይ ይድነቃቸው እነዚህን ነጥቦች በማንሳት ተሳክቶለታል፡፡ በማግሰቱ በጋዜጣዊ መግለጫ የታጀበው “የድንኩ አንድነት” መግለጫንም የጠራው አስተያየት የተገኘው ከሰማያዊ ፓርቲ ነው፡፡ ኢቲቪዎች ካሜራ ይዘው ድንገት “ድንኩ አንድነት” ሰፈር ተገኝተው አቶ ትዕግሰቱ አወሉን የማሪያም ብቅል እንደበላ ሲያንተባትቡት ውለዋል፡፡ ፍርድ ቤትም እንደሚሄዱ ነግረውናል፡፡ ሌባን ሌባ ብለን ፍርድ ቤት መሄድ የምንፈራ እንዳልሆንን አቶ ትዕግሰቱ አጉሉም ቢሆን በደንብ ያውቀናል፡፡ አንድነት የፈሪ ሰፈር እንዳልሆነ ብቻ ሳይሆን የአጉል ጀብደኛም ሰፈር እንዳልነበር፡፡ አጉል ጀብደኛ ቢኖረን ትዕግሰቱ በየመሸታ ቤቱ ሲያንቃርር ሊገጥመው የሚችለውን ያውቅ ነበር፡፡ መርዕ እንዳለን ያውቃል ስለዚህ ማሰፈራሪያ እንደማንፈራ ብቻ ሳይሆን እንደማናሰፈራራም ያውቃል፡፡
ሰማያዊ ሰለብሔራዊ መግባባት ያነሳው ጉዳይ አቶ አባይ ፀሃዬን ቢያበሳጭም አሁንም እውነት መሆኑን መካድ አይቻልም፡፡ ከደርግ ጊዜ በላይ ታጣቂ ያለባት ሀገር ኢትዮጵያ ብቶሆንም የቀዝቃዛው ጦርነት በዓለም ላይ አለመኖር እና የፀረ ሸብር ህብረት በኢትዮጵያ ዙረያ ባሉ ሀገራት ተመሳሳይ መሆን ለመንግሰት የፈጠረለት ምቹ ሁኔታ መግባባት አለ እንድንል የሚያሰገድድ አይደለም፡፡ ይህ በፍፁም ኢህዴግን ሊያበሳጭ አይገባም፡፡ በዕትመት ምክንያት ዘግይቶ የደረሰኝ ሪፖርተር ጋዜጣ 11 ሰዎች ከጋምቤላ አካባቢ የህዳሴ ግድብ ላይ ጉዳት ሊያደርሱ ሲሉ ተይዘው ተፈረደባቸው የሚል ነበር፡፡ ይህ መልዕክቱ ምን ማለት ነው? ልማት ሊያፈርስ የሚፈልግ ጥቅሙ የተነካበት ቡድን አለ ማለት ነው፡፡
ሰማያዊ ፓርቲ ብትመርጡን እንዲህ እናደርጋለን የሚል ፌዝ ውስጥ መግባቱን አልወደድኩለትም፡፡ በተለይ ወዳጄ ይድነቃቸው አንድነት ፓርቲ ሰለ ምርጫ ሲሰብክ በማህበራዊ ድረ ገፅ ያወርድብን የነበረውን የጭቃ ጅራፍ ሳስታወሰ እና አሁን ምረጡን ብሎ እስክስታ በአንድ ራስ ሁለት ምላስ ዓይነት ነው የሚመስለው፡፡ ለማነኛውም ይድነቃቸው ማዕከላዊ ትሄዳለህ የሚል ዳኛ ባለበት ሀገር የህግ የበላይነት አለ እንድንል አያስብልም ያላትን ነጥብ በደንብ በአደባባይ ሲያቀርብ አንጀቴን ቂቤ አርሶታል፡፡ ይህች ነጥብ መቼም የኢህአዴጎችን ወዳጅ ዳንኤል ብርሃኔን እንኳን ጥፍር ስር ለመሸሸግ የገፋፋች ናት፡፡ ይህ ዳኛ በዚህ አባባሉ ፋውል ነጥብ የሚያዝበት ይመስለኛል፡፡
ለማነኛውም ይድነቃቸው  ምርጥ ምርጥ ነጥቦች አንስቶዋል፡፡ ከፓርቲ ገደብ ወጥቶ ተከራክሮዋል፡፡ ይድነቃቸው ከኢህአዴግ ጋር ብቻ ሳይሆን ከአወያዩ ጋርም ጭምር ነበር ግብ ግብ የገጠመው፡፡ ውሳኔ የተሰጠበትን ጉዳይ ሁሉ በፍርድ ቤት ተይዞዋል እያለ ለማቋረጥ ያደረገውን ጥረት አክሽፎበታል፡፡ ሰለ አባይ ግድብ መዋጮ ያነሳት ነጥብ ወደፊት ሰለማዊ ሰልፍ በሰማያዊ ላይ ልታስጠራ ትችላለች፡፡ ይህ የአንድ አንድ ነዋሪዎች አስተያየት ነው፡፡
መድረክ በአቶ ብርሃኑ በርሄ ዓለም አቀፍ ሪፖርት እንደማስረጃ በማቅረብ የጀመረ ሲሆን ይህ አቀራረቭ ህዝቡ ይህች ሀገር በመልካም አስተዳደርና የህግ የበላይነት ያለችበትን ደረጃ ከዓለም አቀፍ መስፈርት ደረጃ አንፃር እንዲያውቅ፣ የሚያውቀውም እንዲያስታውስ የረዳ ነው፡፡ አንደ ጠንከር ያለ ሃሰብም አንሰተዋል ይህች ሀገር ሰው እንደሌላት አንድ ሰው ይህን ሁሉ ስልጣን የያዘበት ሁኔት ለምንድነው? በሚል ጠይቀዋል፡፡ ይህ ግለሰብም በምክር ቤት ስብሰባ ብዙ ጊዜ ሰዎች የሚያውቁት የአቶ መለስ አጃቢ ጋርደ አድርገው የሚያውቁት ቢሆንም በትክክል ግን ከአቶ መለስ ዜናዊ ጀርባ የሚቀመጠው አቶ አስመላሽ ገ/ስላሴ የምክር ቤቱ ዋነኛ መሃንዲስ ነው፡፡
የመድረኩ ሌላኛው ተከራካሪ በገቡበት ጥቂት ደቂቃም ቢሆን የኢህአዴግን ታንክና ባንክ በደንብ አድርገው በጥድፊያ ገልፀዋል፡፡ ይህ ነው የሚባል የተማረ ሰው ሳይዝ ታንክና ክላሽ ይዞ ሀገር ለመምራት የቻለው ኢህአዴግ፣ መድረክን ሀገር ልትመሩ አትችሉም ማለቱን አጣጥለውታል፡፡ እንደ እውነቱ ከሆነ ኢህአዴግ ሀገር የሚመራው ኢትዮጵያዊ ከሆነ መሪው የፖለቲካ ፓርቲ ማንም ቢሆን ሀገር የሚመራበትን መንገድ የሚቀይስ ይጠፋል ማለቱ ሁሉም እንደራሱ በር ዘግቶ ለሌብነት ይመክራል ብሎ ስለሚያስብ ነው፡፡ ለመስረቅ ካልሆነ ሀገር ለመምራት ኢትዮጵያዊያን ከየትም ከኢህአዴግም ሰፈር ጨምሮ እንደሚኖሩ ያለማወቅ ነው፡፡
የኢህአዴግ ጉምቱ ፖለቲከኛ አቶ አባይ ፀሀዬ የኢዴፓው ጎረምሳ በተደረጃ መልክ ባቀረበው የመልካም አስተዳድር መመዘኛ መስመር እንዲቀርቡ ያስገደዳቸው ሲሆን፣ በዚህም ምክንያት ተዘጋጅተው የመጡበትን ዋና ዋና ነጥብ ማቅረብ አልቻሉም፡፡ የተዘጋጁት የኢህአዴግን ስኬት እና አሁን የሚታየውን ጉድለት በማቅረብ ጉድለቱን እንዴት አርመው ለቀጣይ እንደሚገዙን ህዝቡን ለማማለል ቢሆንም እንደቀልድ የጀመሩት የመልካም አስተዳድር መስፈርቶች ብሎ የኢዴፓ ተከራካሪ ያቀረበላቸውን ነጥብ በማብራራትና በመከላክል ጊዜውን ጨርሰውታል፡፡ ኢህአዴግ በእነዚህ መመዘኛወች ከአሰር ሁለት የሚያገኝበት አንድም ቦታ ሳይኖር ለቀጣይ ምርጫ እራሱን ማጨቱ እረሱ አስገራሚ ነው የሆነብኝ፡፡
ኢህአዴግ ሀገራዊ መግባባት ደርሰናል ያለባቸው ነጥቦች በሙሉ ከዚህ በፊት የኢትዮጵያ ህዝብ የተጣላባቸው አልነበሩም፡፡ ድህነት ሰርዓቶች የጫኑብን እንጂ እንደህዝብ ተሰማምተን ይዘነው አናውቅም፡፡ የብሔር ግጭትም ለግል የፖለቲካ ስልጣን የሚሮጡ ፖለቲከኞች እንጂ የህዝብ አጀንዳ አይደለም፡፡ ሰላምን የማይሻ በሽፍትነት የሚጠቀም የነበረ ሲሆን ሽፍታ መንግሰት ሆኖ መዝረፍ ከቻለ ሽፍትነት ሊያምረው አይችለም፡፡ ለማነኛውም ኢህአዴግ ያመነው የሙስና መስፋፋት ብቻ ከስልጣኑ በፈቃደኝነት እንዲለቅ የሚያደርገው ቢሆንም ይህን ለማድረግ ፍላጎት የሌለው ብቻ ሳይሆን ምን ላድርግ? እነዚህም ሰዎች ከማህበረሰቡ የመጡ ናቸው፡፡ ኢህአዴግ የመላዕክት ስብስብ አይደለሙ በሚል ፌዝ አልፈውታል፡፡
ሃያ አራት ዓመት መልካም አስተዳደርና የህግ የበላይነት ማረጋገጥ ያልቻለ ቡድን በስልጣን ለመቀጠል ፍላጎቱ ለከት ማጣቱን ስንታዘብ እና ባለፉት ሰድስት ዓመታት ቦኮአራምን ማስታገስ አልቻለም ተብሎ ስልጣን እንዲለቅ የተደረጉትን የናይጄሪያ ፕሬዝደንት ስናይ ቅናት እርር ድብን ቢያደርገን አይገርምም፡፡ ለማነኛውም ኢህአዴግ በቀጣይ ምርጫ ብቻውን እሮጦ ብቻውን እንደሚገባ ቢረጋገጥም ይህም ደግሞ እንደ ህዝብ አማራጭ ከለከልከን ብሎ ሆ ብሎ የሚነሳ ህዝብ ከሌለ ተገቢው መንግሰት ነው ብለን ለመቀበል አንቸገርም፡፡ ለኢትዮጵያ ህዝብ የሚመጥነው መንግሰት ለጊዜው ኢህአዴግ እና ኢህአዴግ ብቻ ነው፡፡ ለማንኛውም የእለት ፍጆታ ችግር አስመልክተው ወ/ሮ አስቴር ማሞ ስለ ውሃ ችግር ሲያወሩ እንስራ የያዘች አንዲት ኢትዬጵያዊ ምሰኪን ሴት ታየችኝ፣ በሁለት ሺ ሁለት 3000 ሜጋ ዋት አለን ያለው ኢህአዴግ በሁለት ሺ ሶሰት መጀመሪያ 2000 ሜጋ ዋት ነው ያለው በቀጣዩ አምስት ዓመት 10000 ይደርሳል ብለው ዛሬ በአሰር ዓመት 3000 ሜጋ ዋት ያለመኖሩን ሊያስተባብሉን ይሞክራሉ፡፡ ታዲይ የኢትዮጵያ ህዝብ ይህን ውሸት ከተቀበለ ኢህአዴግ ይመጥነዋል ማለት ሰህተት ይሆናል፡፡
ከዚህ በላይ የኢህአዴግን ዘባተሎ የተጠና ፕሮፓጋንዳ ማቅረብ ተገቢ አልመሰለኝም እና የዛሬውን በዚሁ ላብቃ፡፡


No comments:

Post a Comment