Sunday, March 16, 2014

የአፍሪካ መሪዎችና አፍሪካዊያን ግርማ ሠይፉ ማሩ



በቅርቡ ለስብሰባ የመካከለኛ አፍሪካ በምትገኘው ካሜሩን ዋና ከተማ ያውንዴ ተገኝቼ ነበር፡፡ ያውንዴ በነበርኩበት ጊዜም አጋጣሚ ሆኖ ማርች 8 ዓለም አቀፍ የሴቶች ቀን የሚከበርበት ስለነበር አከባበሩን አሰመልክቶ የአፍሪካ መሪዎች እንዴት በዓል እንደሚያከብሩ ለመታዘብ ዕድል ሰጥቶኛል፡፡ ለአምባገነንት የሚጠቀሙበት መመሪያም አንድ መሆኑን ለማወቅ ጊዜ የሚወስድ አልነበረም፡፡ በዚህ አጋጣሚ ደግሞ ከጎረቤት ሀገር ተሳታፊዎች ጋር ለመገናኘት እና ለመወያየት ዕድል አግኝቼ ነበር፡፡ በተለይ ከኤርትራዊ ወንድሞቻችን እና እህቶች ጋር የነበረን ቆይታ ከእነርሱ  ከራሳቸው በስተቀር ከኢትዮጵያ የሚለያቸው ነገር የሚያውቅ እንደሌለ አፍጥጦ የሚታይ ሀቅ ነበር፡፡  ከሱማሊያ ከመጣው ወጣት ጋር የነበረን ውይይትም በፍፁም የማይታመን ነበር፡፡ የእኛ ጎምቱ ባለስልጣናት አብረውን ካሉት ጋር እንዴት እንደሚያጋጩን ሲያስላስሉ እዚያ ማዶ ያሉት ግን የእኛ ናፍቆት አላቸው፤ የአብሮነትን ጥቅም በደንብ ተረድተውት እንዴት እንደሚሆን ግን ግራ የተጋቡ ይመስላሉ፡፡ ይህን መፈላለግ ለመግለፅ ግን ከአንድ ጥግ ወደ ሌላ ጥግ መሄድ ለምን እንዳስፈለገን ተወያይተን የደረስንበት በእኛ በህዝቦች መካከል  ምንም የሚያለያይ ነገር እንደሌለ ነው፡፡ ለአብሮነታችን ግን አምባገነኖችን ከመክስስ በዘለለ ሁላችን የበኩላችንን ማድረግ ይኖርበናል፡፡
እንደ መግቢያ
የማርች 8 ባህል በካሜሮን ከተማ ያውንዴ ድል ባለ ሁኔታ ሲከበር የዓይን ምስክር ሆኜ ተመልክቻለሁ፡፡ ባህሉ ያለ ብዙ ወንዶች ተሳትፎ የሀገሪቱ ቀዳማዊ እመቤት በተገኙበት የተከበረ ሲሆን በእኛ ሀገር ለቀዳማዊ እመቤት በዚህ ደረጃ የደህንነት ጥበቃ ሲደረግ አይቼም ሰምቼም አላውቅም፡፡ የባሰ አለ ሀገር አትልቀቅ የሚባለው ይኼን ጊዜ ይመስለኛል፡፡ የማርች 8 በዓልን ለማድምቅ የወጡት ሴቶች እንደኛው ሀገር በመስሪያ ቤት ተደራጅተው የወጡ ሲሆን፤ ከበዓሉ በኋላ ግን እንደ እኛዎቹ ሴቶች ወደቤታቸው ነጠላቸውን በአናታቸው ላይ አድርገው ጠውልገው ሲመለሱ አላያሁም፡፡ በየደረሱበት አረፍ ብለው ቢራ እየተጎነጩ ሲመሽም ተሳክረው በየጎዳናው ሲደንሱ አጀብ የሚያሰኝ ነበር፡፡ ይኼ ነው እኩልነት ብዬ ታዝቤያቸው መጥቻለው፡፡ የሰልፉ ዝግጅት፣ የጦር ሰራዊት ጋጋታው፣ ወዘተ… በሀገራችን የሴቶች ሊግ የሚያደርገው ዓይነት እና በመንግሰት የሚደገፉ ሰልፉች ጋር አንድ ሲሆንብኝ ተሳስቼ መስቀል አደባባይ የተገኘው እንጂ በዚህ ሁሉ ኪሎ ሜትር ርቀት ልዩነት በዚህ ደረጃ መመሳሰል ይኖራል ብዬ ለማመን እራሴን ተጠራጠርኩ፡፡
ኢትዮጵያ (ከኤርትራ እና ያለ ኤርትራ)
ኤርትራዊያን ብዬ ለመፃፍ ወይም ለመጥራት የምር ምቾት አይስጠኝም፡፡ ያራቅኳቸው እኔም ከኢህአዴጎች ጋር ሆኜ አንድ አይደለንም የሚለውን የመደገፍ ሰሜት እየመጣብኝ ይፈታተነኛል፡፡ እንደዚያም ሆኖ ግን አሁን ያለውን እውነት ለመቀበል ስል እንደ ሁለት ሀገር አድርጌ ለመፃፍ እገደዳለሁ፡፡ ልቤ ግን ይህን እያለኝ አይደለም፡፡ ኢትዮጵያ ያለ ኤርትራ፤ ኤርትራም ያለ ኢትዮጵያ መኖር እንደሚችሉ ባሳለፍናቸው ሃያ ዓመታት በላይ የተረጋገጠ እና የተመዘገበ እውነት ነው፡፡ ነገር ግን አብረን ብንሆ ከዚህ የተሻለ ልንሆን እንደምንችል ከምን ጊዜውም የበለጠ አሁን የተሰማን ይመስለኛል፡፡ እኛ ከተከዚ ደቡብ የምንገኝ ህዝቦች አስመራ፣ ምፅዋ ሄደን ለመዝናናት ቢያስፈልግም ሰርተን ለመኖር ከኢሳያስ መሞት ቀጥሎ ከዚህ ከእኛ ሰፈር የአብዮታዊ ዲሞክራሲ መፍረስ የግድ የሚለን ይመስለኛል፡፡ ይህ “ጦርነትም ሰላምም የለም” በሚል ግርግዳ ታጥረን መኖራችን፤ ከአሰመራም ከአዲስ አበባም በኩል የመራራቅን ግድግዳ እያጠናከረ እንደሚሄድ ግን ምንም ጥርጥር የለውም፡፡ በዚሁ ከቀጠልን አዲሱ ትውልድ የእኛን ያህል አስመራንም ሆነ ምፅዋን የመጎብኘት ጉጉቱ ባያድርበት መገረም አይኖርብንም፡፡ በተለይ በአሰመራ በኩል አዲስ ታሪክ በመስራት ፕሮጀክት ውስጥ ኤርትራ በጎረቤት ሀገሯ ኢትዮጵያ ቅኝ ተይዛ እንደነበረ በሰፊው ተፅፎ እየተሰጠ እንደሚሆን መጠራጠር አያስፈልግም፡፡ ከአቶ መለስ እና ጓዶቻቸው በስተቀር እኛም ሳናውቅ አንድ በቅኝ የገዛነው ሀገር እንዳለን በአስመራ በኩል ይመዘገብ ይሆናል፡፡ አቶ መለስ ፅፈውታል ተብሎ የሚታመነው “ኤርትራ ከየት ወዴት?`` የሚለው መፅኃፍ ኢትዮጵያን ቅኝ ገዢ አድርጎ ነው የሚያቀርበው፡፡ የኤርትራ ጉዳይም ከቅኝ ግዣት ነፃ የመውጣት ነው ብለው ነው የደመደሙት፡፡ ለዚህም ነው ኤርትራ ነፃ ሀገር እንድትሆን ቀድመው ደብዳቤ የፃፉት፡፡ እርግጠኛ ነኝ በኢትዮጵያ በኩል ያለው ታሪክ ኤርትራ ከእናት ሀገሯ መገንጠሏን የሚነግር እንጂ በቅኝ ይዘናት የነበረን ሀገር እንዳስረከብን አይደለም፡፡ ለምሳሌ እንግሊዝ ኬኒያን ለቃ እንደወጣችው ዓይነት ማለት ነው፡፡ ለምሳሌ ደቡብ ሱዳን ከሱዳን ተገነጠለች እንጂ ከሱዳን ቅኝ ግዛት አይደለም ነፃ የወጣችው፡፡
የዚህ ፅሁፍ ዓላማም ይህ እየተጠናከረ ወደ አዲሱ ትውልድ በመሄድ ላይ ያለውን የሚያራርቅ ግንብ የኢሳያስንም ሆነ የእኛን አብዮታዊ ዲሞክራሲ ሞትና ግብዓተ መሬት ሳይጠብቅ ህዝብ ለህዝብ በሚደረግ ግንኙነት እንዲጠናከር ማድረግ እንዳለብን ከውስጤ ስለተሰማኝ ፍላጎቱና አቅሙ ላላቸው ሰዎች እረ ጎበዝ አንደ እንበል ለማለት ነው፡፡ ይህን እንዴት ማድረግ ይኖርብናል የሚለው ብዙ ሰዎች ብዙ የሚሉት ነገር እንደሚኖር ባምንም በእኔ ግምት በቅርቡ መጀመር ያለባቸው ብዬ የማምናቸው በማህበራዊም ሆነ በመደበኛ ሚዲያ ወጣቱ ትውልድ በሁለቱ ሀገሮች መካከል ያለውን የባሕል፣ የቋንቋ፣ የሰነልቦና፣ ወዘተ አንድነት የሚያሳዩና አዲሱን ትውልድ ከቀድሞ ጋር የሚያስተሳስሩ ሰራዎችን መስራት የግድ ይለናል፡፡ እንደዚህ ዓይነት ሰራዎች በፍፁም በአንድ ወገን ብቻ የሚሰሩ መሆን የለባቸውም፡፡ የኢየትዮጵያና የኤርትራ ቴሌቭዝኖች እንዲህ ዓይነት መልካም ሰራ ቢጠበቅባቸውም የማያምርባቸው ስለሆነ ከውጭ የሚተላለፉ ለምሳሌ ኢሳት እና “ኢቢሴ” በዚህ ጉዳይ ላይ ቢሰሩ የሚጠቀሙ እንጂ የሚጎዱ አይመስለኝም፡፡ እነዚህ ተግባራት በፍፁም ከፖለቲካ አመለካከት ጋር የሚገናኙ መሆን የለባቸውም፡፡
በውጭ የሚኖሩ ኢትዮጵያዊያን እና ኤርትራዊያን የጋራ ፎረሞችን በማዘጋጀት በአብሮነታችን ዙሪያ ምክክር በማድረግ ከእንደዚህ ዓይነት መድረኮች የሚገኙ ሃሳቦች በሰፊው ህዝቡ እንዲያውቀው በማድረግ የህዝብ ለህዝብ መቀራረብን ልናጎለብት ይገባ የሚል እምነት አለኝ፡፡ ፖለቲከኞች በፈጠሩት ግጭት ባለሞያዎች በሚገናኙበት መድረክ ላይ ለመሳተፍ አንድ ኤርትራዊ አውሮፓ ድረስ ተጉዞ ሶስት አራት ቀን መንገድ የሚያድርበት ቀን ለማሳጠር መሰረት መጣል ያለብን ይመስለኛል፡፡ ይህን ለማድረግ በመግቢያዬ ላይ እንዳልኩት የኢሳያስ መሞትና የአብዮታዊ ዲሞክራሲ መፍረስ ከጠበቅን የመለያየታችን ግንብ በልጆቻችን ውስጥ ሰርጾ መቼ አንድ ነበርን ሊሉን ይችላሉ፡፡

ኢትዮጵያና ሱማሊያ
ኢትዮጵያና ሱማሊያ በሱማሌ ቅኝ ገዜ የነበሩት በተለይ እንግሊዞች በቀበሩት የግጭት መንፈስ የተነሳ በተደጋጋሚ የድንበር ግጭት ብሎም ደም አፋሳሽ የሆነ ሙሉ ጦርነቶች ውስጥ ገብተን እንደነበር እሙን ነው፡፡ ይህን እውነት የምናውቅ የሁለት ሀገር ዜጎች ግን ካሜሮን ላይ ስንገናኝ እንደ ድሮ ሰፈር ልጅ በፍቅር ስንጫወት ነው የከረምነው፡፡ ከሱማሌው ተወካይ መሃመድ ጋር መጀመሪያ የተግባባነው ኢትዮጵያዊ መስሎን ነበር፡፡ እኔን እና መሃመድን የሚለየን መሃመድ ትንሽ  ትንሽ አማርኛ ይሞክራል እኔ ሱማልኛ ስለማልሞክር ይበልጠኛል ማለት ነው፤ መሃመድ ተግባቢ እና በደንብ እንደምናውቃቸው ሶማሊዎች ቴክኖሎጂ የሚወድ ነው፡፡ በእጁ የያዛት ብላክ ቤሪ ስልክ ሁሉንም ወሬ ታቀብለዋለች፡፡ መሃመድ እንደሚለው “ይህች ስልክ ሱማሌ ውስጥ በተለይ በአልሻባብ እጅ ከገባህ ሞት ታስከትላለች” ይላል በተደጋጋሚ፡፡ ቴክኖሎጂን እና ሌሎች የህዝብ መጠቀሚያዎችን በመከልከል አፍነው ሊገዙ የሚንቀሳቀሱ የአልሻባብ ሰዎች በፍፁም ምንጫቸው ሱማሌ እንዳልሆነ እና ከውጭ የመጣ አካራሪነት እንደሆነ ያምናል፡፡ በዚህ ሰበብ ግን በኢትዮጵያ በኩል እየተወሰደ ያለው እርምጃ በደንብ ታስቦበት ካልሆነ የህዝብ ለህዝብ ግንኙነትን እንደሚጎዳ አበክሮ ይናገራል፡፡ እርግጥ ነው አሁን ያለው መንግስት ደካማ ስለሆነ የኢትዮጵያ እርዳታ በተለይ ወታደራዊ ድጋፍ ይፈልጋል፤ እንደዚያም ሆኖ ግን ህዝቡ ይህን ሳይረዳ ይቀርና እንደ ወራሪ ሀይል በመቁጠር አልሻባብን ይቀላቀላል፡፡ ይህ ደግሞ ወደፊት ተባብረን እና ተደጋግፈን  የምንኖርበትን  ጊዜ ያርቀዋል ይላል፡፡ መሃመድ ከዚህ በፊት በኢትዮጵያና በሱማሊያ መካከል የተደረገውን ደም አፋሳሽ ጦርነት በታሪክነት ነው እንዲዘጋ የሚፈልገው፡፡ ይህ ጦርነት “ሁለት አንባገነኖች ንፁዓንን ያስፈጁበት በኋላ ደግሞ እነርሱ የተቃቀፉበት ነበር” ይላል መሃመድ፡፡ ሁለቱም አሁን የሉም ይህን ታሪክ አድርጎ ወደፊት መሄድ ነው ያለብን ነው የሚለው፡፡ በሃያ አንደኛው ክፍለ ዘመን ድንበር አርቴፊሻል ነው ብሎ ያምናል፡፡ ኢትዮጵያዊያኖች ባህር ዳር ሆነው ለመዝናናት ከሞምባሳ የእኛ ይቀርባል ይላል፤ ሶማሌዎችም ኢትዮጵያ ቤታችን ነው ብለው ያምናሉ እንደ መሃመድ እምነት፡፡ ኢትዮጵያዊያን ሁሉን ነገር ትተው በችግራችን ጊዜ እንደ ሀገራችን እንድንኖር ማድረጋቸው በፍፁም የሚረሳ ውለታ እንዳልሆነ ነው መሃመድ የሚተርከው፡፡
መሃመድ ይህን ሁሉ ባጫወተኝ ማግስት የኢትዮጵያ ጦር ወደ ደቡብ ጁባ ላንድ ሊገባ መሆኑን በተለመደ የመረጃ ቃራሚነቱ ሰምቶ ግርማ አሁንም የኢትዮጵያ ጦር ወደ ሶማሊያ መግባቱ ለህዝቡ በደንብ እንዲያውቀው ካልተደረገ መንግሰት ለመንግሰት ብቻ በሚደረግ ሰምምነት መሆኑ ችግሩን ከማባባስ አልፉ አልሻባብን ያጠናክራል የሚል ስጋት አለኝ ብሎ ፍርሃቱን አጋራኝ፡፡ እውነት ነው ደካማ የሱማሌ መንግሰት የሚያግዘው ጉልበተኛ ያስፈልገው ይሆናል፤ ለሀገር ዘላቂ ጥቅም ሲባል ግን ለአልሸባብ የሚወረወሩ ጥይቶች ሰላማዊ ዜጋ፣ ሴቶች እና ህፃናትን እንዳይጎዱ ጥንቃቄ መደረግ ይኖርበታል፡፡
ቸር ይግጠመን

Saturday, March 8, 2014

የኢህአዴግ አባል ድርጅቶች በእኔ ዕይታ ……. ግርማ ሠይፉ ማሩ



የኢህአዴግና ኣባል ድርጅቶችን እንደ ርዕሰ ጉዳይ ለማንሳት የገፋፋኝ የሰሞኑ የብአዴን መዝረክረክ ነው፡፡ ብአዴን ምን ነካው ብዬ ሃሳብ ለመሰንዘር ወስኜ ሳወጣ ሳወርድ ምን ያልተነካ የግንባር አባል ድርጅት ኖሮ ነው ብአዴን የምትለው የሚለው ሃሳብ ገዢ ሆኖ መጣብኝ፡፡ በዚህ መነሻም በነገር ቅደም ተከተል ሳይሆን ኢህአዴግ የሚባለውን ሚዛንና ቅርፅ የሌለውን ድርጅት በመመስረት ቅደም ተከተላቸው ለማየት ሞከርኩ፡፡
ሕወሓት ሁሉም እንደሚያውቀው አውራቸውን ካጡ በኋላ ዋና ስራቸው እራሳቸውን ወደ አንድ ፓርቲነት ለማሳደግ ደፋ ቀና ሲሉ እንደከረሙ እናውቃለን፡፡ የተሳካ ነገር መኖሩን የሚጠቁም ነገር የለም፡፡ ዛሬም ነገም ስብሰባ ነው፡፡ ባለሀብቶቹ ተሰብሰበው እባካችሁ ስብሰባ ቀንሱ ነው ያሉዋቸው፡፡ ህውሓት የአዲስ አበባና የመቀሌ ቡድን በመባል ይታወቃሉ፡፡ ይህም ሆኖ ግን የነፃ አውጪ ድርጅቱን የሚመሩት የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ክፍፍል የሚባል የለም ብለው ለየካቲት 11 መታሰቢያ በተዘጋጀ መፅሔት ላይ ቃለ ምልልስ መስጠታቸውን ይፋ ሆኖዋል፡፡ እኛም ሰምተናል መስማት ግን መስማማት እንዳልሆነ የታወቀ ነው፡፡ ይህ የሚያስታውሰን ነገር ቢኖር የጦጢትን አልበላሽምን ምን አመጣው ጫወታ ነው፡፡ ክፍፍል የለምን ምን አመጣው እንላለን፡፡ አንድ ግን ታውቆ ያደረ ነገር ቢኖር ህውሓት ሁሉ ነገሩን ለአቶ መለስ ሰጥቶ የነበረ ከመሆኑ አንፃር በተለይ በኢህዴግ ሰፈር አጀንዳ የማስቀመጡን ሰራ መስራት የሚችል ሆኖ አላገኘሁትም፡፡ አሁን ህውሓት ጥንካሬ አለው ከተባለ የፓርቲ ሳይሆን ኢ-ሕገ መንግሰታዊ በሆነ መስመር የመከላከያና የደህንነት መስሪያ ቤቱ ውስጥ ባሉት ቁልፍ ሰዎች የሚተማመን ከሆነ እና እነዚህም ቁልፍ ሰዎች ቢሆኑ ይህን መተማመኛ ሰጥተው ከሆነ ነው፡፡ ዘወተር ታማኝነታችን ለህገ መንግሰት ነው በሚሉት ቃላቸው ከታመኑ ደግሞ ጠቅላይ አዛዡ አቶ ኃይለማሪያም ደሳለኝ እንጂ የህውሓቱ መሪ አይሆኑም፡፡ ሰለዚህ ሕውሓት በአሁኑ ሰዓት በኢህአዴግ ውስጥ አጀንዳ አሰቀማጭነት ሚና የለውም የሚል አረዳድ ነው ያለኝ፡፡ ለዚህ ማሳያ የሚሆነው በፌዴራል መንግሰት በሚደረጉ ሹመቶች ውስጥ የህወሓት ሰዎች ከቦታ ቦታ ዝውውር እና የቀድሞ ታጋዮችን ወደፊት ከማምጣት የዘለለ አዲስ ፊት ማምጣት አልቻለም፡፡ ወጣቶቹ የህወሓት አፍቃሪ ልጆች በቢዝነሱ መስመር እንዲሁም ውስኪ በመጨለጡ እንጂ ንቁ ፖለቲከኛ የመሆን ፍላጎት ያላቸውን አይመስሉም፡፡ ባይሆን የዚህ ዓይነት ትንታግ ወጣቶች አረና ሰፈር ብቅብቅ ያሉ ይመስላሉ፡፡ እነ አብርሃ ደስታ የኢትዮጵያ አምላክ እንዲጠብቃቸው ፀሎት ሁሉ ያስፈልጋል፡፡ በትግል ከመተጋገዙ ጎን ለጎን ማለቴ ነው፡፡
በእውነቱ ከኢህአዴግ አባል ፓርቲዎች ውስጥ ተሰፋ ሳይበት የነበረው ብአዴን ሰሞኑን ምን እንደ ነካው ማወቅ አልቻልኩኝም፡፡ ለምን ተሰፋ ጣልክ ለሚለው ብዙ ማሳያ ቢኖረኝም በህውሓት ሰፈር ጠፍቶዋል ያልኩዋችሁን ወጣት አመራሮች ከስር ከስር ማየቴ እና ለውይየት ጋባዥ የሆኑ የቢሮ ሃላፊዎች ዋናው ሲሆን በተለይ ደግሞ በባህር ዳር ከተማ ላይ ዘለግ አድርገው ሃሰበው የሚሰሩት ሰራ ወደ ሌላ የአማራ ክልል ሊሄድ ይችላል የሚል ተሰፋ ስለነበረኝ ነው፡፡ ይሁን እንጂ በሰሞኑ ከየት መጣ ሳይባል አለምነው መኮንን የሚባል ካድሬ ከልጅነት እስከ እውቀት ሌሎች ሲሰድቡት የነበረውን እራሱ መቀበሉ ሳያንሰው የአማራን ህዝብ ሙልጭ አድርጎ ሲሳደብ ሰማነው፡፡ ያስታግሱታል ብሎም በተገቢው መንገድም ይቅርታ ጠይቆ ከሃላፊነቱ ይነሳል ብለን ስንጠብቅ ይባስ ተብሎ ሚዲያ ተሰጥቶት መግለጫ ሰጪ፤ ስለ ዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ሰኬት አብራሪ አድርገው አቀረቡት፡፡ ይህን ጊዜ የገባን ካድሬው የግል ባህሪው ሳይሆን የድርጅቱ አቋም ነው ብለን ወሰድን፡፡ የኢህአዴግ አባል ድርጅቶችም ይህን አባል ድርጅት ምንነው ጃል ማለት አልቻሉም፡፡ በኢህአዴግ ሰፈር ለምርጫ ዘመቻ ተቃዋሚዎች የቀየሱት ዘዴ ነው የሚል ማደናገሪያ ይዘው ቀርበዋል፡፡ አሁን ማን ይሙት አለምነው መኮንን የሚባል ካድሬ ሲሳደብ እንጂ በብአዴን ውስጥ መኖሩን ሰምተንም አይተንም አናውቅም፡፡ ይልቁንም የምናውቃቸው ተሰፋ የጣልንባቸው የተሳደቡ መስሎን ስናጣራ አልሰማንም እሰኪ እኛም እናጣራለን ብለውን ከዚያ በኋላ ስልክ ማንሳት ትተዋል፡፡ ተሰፋ የጣልንባቸውም ቢሆኑ ባይሳደቡም ወደውም ሆነ ተገደው ተባባሪ ናቸው፡፡
ሌላው በዚያው በብአዴን ሰፈር የተነሳው አሰቂኝ ነገር ደግሞ የህፃናት፣ወጣቶችና ሴቶች (ከጎልማሳና አዛውንት ወንዶች በስተቀር ልንለው እንችላለን) ሚኒስቴር ሚኒስትር የሆኑት ወ/ሮ ዘነቡ ታደሰ ደግሞ በፍፅሙ ከአንደ በዚህ ደረጃ ካለ ኢትዮጵያዊ በተለይ ከሴት በማይጠበቅ ሁኔታ ግብረሰዶማዊነት የሚደግፍ ፅሁፍ ካሰራጩ በኋላ እኔ አይደለሁም የማህበራዊ ድህረ ገፄ ቁልፍ ተሰብሮ ሌሎች ናቸው እንዲህ ጉድ የሰሩን የሚል ማስተባበያ ሰጡ ተባለ፣ ሌላው የከተማ ብአዴን አቶ ሽመልስ ከማል ደግም እዎ ተሰርቀው ነው አሉን፡፡ የመንግሰት ኮሚኒኬሽን ጉዳዮች መስሪያ ቤት የሚኒስትሮቻችን ማህበራዊ ድህረ ገፅ እንደሚመለከተው ያወቅሁት በዚህ ጉዳይ ነው፡፡ ሚኒስተሮቹ የማህበራዊ ድህረ ገፅ መድረኮችን መጠቀማቸው የሚበረታታ ቢሆንም በምንም ሁኔታ ግን ይህ የግል እንጂ የመንግሰት ሃላፊነት ሆኖ በመንግሰት ኮሚኒኬሽን መስሪያ ቤት በኩል መግለጫ የሚሰጥበት አይመስለኝም፡፡
እንግዲህ እነዚህ ብአዴኖች ናቸው ኢህአዴግ የሚባለውን የሰሩልን፡፡ ለህዝብ ሰሜት ሲባል አንድ ካድሬ ከስልጣን ሊያወርዱ የማይችሉ መሆናቸውን ሳሰብ ደከሙኝ፡፡ አንድ ነገር ግን ይታየኛል፡፡ አቶ አለምነው መኮንን በግላቸው ይቅርታ ጠይቀው ከፓርቲው ቢወጡ የበለጠ ሰላም ያገኛሉ የሚል እምነት አለኝ፡፡ ያለበለዚያ ግን በፍፁም ሰላም የሚሰጥ ሰህተት እንዳልሆነ አስምሬ መናገር እችላለሁ፡፡
ኦህዴድ ኢህአዴግን ከመሰረቱት አራት ፓርቲዎች በሶስተኛ ደረጃ የሚገኝ ቢሆንም ሰሞኑን የገባበት ውጥንቅጥ ግን ለብሔር ፓርቲ አደረጃጀት ትክክል አለመሆን ዋነኛ ማሳያ ነው፡፡ አንድ የብሔር ፓርቲ በተደላደለ ሁኔታ አመራር ለመምረጥና ለመተካት ምን ያህል ጊዜ ያስፈልገዋል? የኦሮሞ ህዝብ በቁመቱ ልክ በኢትዮጵያ ቦታ ሊሰጠው ይገባዋል የሚሉትን ሁሉ አንገት በሚያስደፋ ሁኔታ ኦህዴድ ድርጅቱን የሚመራ ሰው መሰየም አቅቶት ሲዋትት ቆይቶ በስንት ምጥ አሁንም እዚያው በዚያው ሽግሽግ አድርገው ኦህዴድ ዲሞክራሲያዊ በሆነ ሁኔታ የፓርቲውን መሪ መረጠ አሉን፡፡ ዲሞክራሲያዊ የሚለውን ምን አመጣው ? የጦጢት ነገር እዚህም ትዝ ቢለንም አይገርምም ለማነኛውም ግን በድርጅታዊ አሰራር የሚለው ግን ሳይፃፍ አንብበነዋል፡፡ እንደዚያም ሆኖ ግን ይህ ፅሁፍ እያሰናዳው እያለ ክልሉ አሁንም ርዕስ መስተዳድር የለውም፡፡ የክልሉ ምክትል ርዕስ መስተዳድር የቀድሞ የድሬዳዋ ከንቲባ አሁንም በፓረቲው ውስጥ ዋናም ምክትልም ሳይሆን በሞግዚትነት እሰከሚቀጥለው ምርጫ እንዲያሻግሩ የታጩ ይመስለኛል፡፡ ከዚህ በፊት የሰጠሁትን ግምቴን ለማጠናከር አቶ አባዱላ ገመዳ ወደ ክልል ሊመለሱ እንደሚችሉ ይሰማኛል ወይም በምክትል ጠቅላይ ሚኒሰትር ማዕረግ የሲቪል ሰርቪስ ሚኒስትሩ  አቶ ሙክታር ከደር እንደ ከሚል ስልጣን ከነሙሉ ክብሩና ጥቅሙ ጋር የክልል ፕሬዝዳንት ሊሆኑ ይችላሉ፡፡ በነገራችን ላይ በኢህአዴግ ውስጥ ያለው የኮታ ፖለቲካ በሁሉም ሰፈር አለ፡፡ በኦሮሚያም ቢሆን የዚህ እና የዚያ ዞን የሚል የጦዘ ፖለቲካ አለ፡፡ ይህ ሁሉ ሲሆን ግን የሁለት ሺ ሁለት ምርጫ ይዞት የሚመጣውን ማዕበል ገና ያወቀ የለም፡፡ ለማነኛውም የሰላም እንዲሆን ሁላችንም በመቻቻል መንፈስ መስራት ይኖርብናል፡፡
እንግዲህ ሁሉም ፓርቲዎች እኩል ናቸው ካልን እስከ አሁን ሶስት አራተኛ የሚሆነውን አይተናል ቀሪውን አንድ አራተኛ የያዘው የደቡብ ህዝቦች ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ/ደህዴን ሲሆን ይህ ሱሙ በአቅጣጫ የተሰየመ ፓርቲ መሪው አቶ ኃይለማሪያም ደሳለኝ የአሁኑ ጠቅላይ ሚኒሰትር ሲሆኑ ኢህአዴግን በመመስረት መጨረሻ ቢሆንም በትረ ስልጣን ለመያዝ ግን እድለኛ የሆነ ንቅናቄ ነው፡፡ ኢትዮጵያዊያኖች በጋራ አንድ ቤት ሊኖራቸው ይገባል ይቻላልም ብለን ስንሞግት አይችልም በብሔር መደራጀት ነው ለዚህች ሀገር መፍትሔው የሚለን ኢህአዴግ ከአምሳ ሰድስት በላይ የሆኑ ብሔሮችን በአንድ ላይ በደቡብ ንቅናቄ ሲያደራጅ እና በዚህ ምክንያት የሚታየውን የአሰተሳሰብ ተቃርኖ የሚረዳ ኢትዮጵያዊ አለ ብሎ አያምንም፡፡ ሲዳማዎች በሰማችን ጥሩን ደቡብ አቅጣጫ ነው ያሉት እንደተጠበቀ ሆኖ ማለቴ ነው፡፡
በነገራችን ላይ የብሔራቸው ተወላጅ ስልጣን ላይ ሲወጣ የሚደሰቱ ሰዎች እንዳሉ ይታወቃል፡፡ ትግሬ ሲሾም ደስ የሚለው ትግሬ ይኖራል፤ ኦሮሞ ሲሾም ደስ የሚለው ኦሮሞ ሊኖር ይችላል፤ ሌሎችም እንዲሁ፡፡ በዚህ ስሌት ከሄድን በአቶ ኃይለማሪም ደሳለኝ ጠቅላይ ሚኒስትር መሆን ደስ የሚለው ወላይታ ሊኖር እንደሚችል ባውቅም በምንም መመዛኛ ግን ይህ ሌሎችን የደቡብ ክልል በሚባለው የታቀፉትን ብሔሮች የሚያስደስት እንዳልሆነ እርግጠኛ መሆን አለብን፡፡ ስልጣን የሚያዘው በብቃት ሳይሆን  እንደ ኢህአዴግ ሰሌት በዙር ከሆነ በደቡብ ውስጥ ያሉት ብሔሮች በተለይ እንደ ሲዳማ፣ጉራጌ ከምባታ ኮታቸውን ጨርሰዋል ማለት ነው፡፡ ይህ በምንም ስሌት ተቀባይነት ያለው አይደለም፡፡ ደህዴን ኢህአዴግ ወደ ህብረብሔራዊ ፓርቲ መቀየር ከፈለገ እንዴት ማድረግ እንዳለበት ለሙከራ የተሰራ ድርጅት መሆኑ ይታወቃል፡፡ ለዚህ ስልጣንም የበቃው በውስጡ ባለው ተቃርኖ ምክንያት የያዘውን ስልጣን በማነኛውም ወቅት ቁጭ አድርግ ሲባል ቁጭ ያደርጋል በሚል ስሌት መስረት እንደሆነ እንጠረጥራለን፡፡
የእነዚህ አራት ፓርቲዎች ሰብሰብ ኢህአዴግ የሚባለውን ግንባር እንደፈጠረልን ይታወቃል፡፡ የዚህ ሁሉ መሃንዲስ የነበሩት  ከኋላ ሆነው መሪውን ለመያዝ ሲለፉ ሲተጉ የነበሩት “ባለራዕዩ” መሪ አሁን የለሙ፡፡ መሪያቻው በቀየሱላቸው መስመር ይሂዱ አይሂዱ እንደሆነ ጊዜ የሚነግረን ቢሆንም፡፡ አሁን የምንሰማቸው አንድ አንድ ነገሮች ግን ይህን የሚያሳዩ አይዳሉም፡፡ ሁሉም የኢህአዴግ አባል ድርጅቶች በፈለጉት እና በታያቸው መንገድ እየሄዱ እንደሆነ ይታያል፡፡ ፓርቲዎቹ ከኢህአዴግ ምክር ቤት በወረዳ አጀንዳ መሰረት ተወያየተው መወሰን ትተዋል፡፡ በማዕከላዊ መንግሰት ደረጃም ሟቹን ጥላ ከለላ አድርገው እንደልባቸው ሲሆኑ የነበሩትም ቢሆን ጣሪያው እንደተቀደደበት ሰው ፍሳሹ አስቸገረን እያሉ ሁሁ ሲሉ እየሰማን ነው፡፡ ከዚህ በፊት ተቃዋሚውን ጎራ ምንም ሳይደግፉት ይልቁንም ሲገፉት ቆይተው አሁን ግን ምን እየሰራችሁ ነው ማለት ጀምረዋል፡፡
ሊነጋ የሚመሰል ድቅድቅ ጨለማ ሀሉም ጋ ይታያል ….. ተሰፋ መቁረጥ እንዳይመጣ መጠንከር አለብን፡፡ ኢህአዴግ ግን እንደ ግንባር አንድ ቃል የሚናገር አይመስልም አጣባቂ ሙጫ የነበሩትን “ባለራዕይ” መሪውን አጥቶ ጎዳና ተዳዳሪ የሆነ ይመስለኛል፡፡
ቸር ይግጠመን፡፡

Friday, March 7, 2014

የትራፊክ አደጋን ለመቀነስ በምሽት አትንዱ!! ዘመኑን መረዳት ያቃተው የሰነፍ ውሳኔ!!



በጥር አጋማሽ አካባቢ ምክር ቤቱ ለዕረፍተ ከመበተኑ በፊት አስቸኳይ ያላቸውን ጉዳዮች ለመጨረስ በሚል ከስዓት በኋላ በሰምንት ሰዓት ለመገናኘት ቀጠሮ ይዞ ምክር ቤቱ ሲበተን ወደ ቢሮዬ ተጠግቼ ምሳ ለመብላትና እግረ መንገዴንም በቢሮ አንድ አንድ ነገር አድርጌ ለመመለስ ሳዘግም ፒያሳ ላይ ያለው የትራፊክ ጭንቅንቅ መላወሻ ሲያሳጣኝ ፌቴን አዙሬ ወደ ጣይቱ ሆቴል አመራው፡፡ ብቻዬን ምግብ ቤት መመገብ ባልወድም የግዴን አንድ ጥግ ይዤ ቁጭ እንዳልኩ አንድ ሰው መጥቶ ቅር ካላለህ አብሬህ ብቀመጥ ብሎኝ ፈቃድ ሲጠይቀኝ በደስታ ብዬው አብረን ምሳ በላን፡፡ ጋበዘኝም! ግብዣውን ላለመቀበል  ስግደረደር አይዞህ አንተ ባለስልጣን አይደለህም ካንተ ምንም አልፈልግም ብሎ ካሰፈገገኝ በኋላ ወግ ጀመርን፡፡ እዚህም እዚያም እያልን ብዙ ጠቃሚ ውይይቶች ለማድረግ ዕድል አገኘሁ፡፡ እንዲህ ዓይነት አጋጣሚዎች ለእንደኔ ዓይነቱ መረጃ ቃራሚ ጠቃሚ ነው ብዬ ነው የምወስደው፡፡
ካነሳናቸው ጉዳዮች አንዱ በምሽት አገልግሎት እንዳይሰጡ የታገዱትን ሚኒባስ እና መስል መኪኖችን የሚመለከት ሲሆን፤ በዛሬ ፅሁፍ ይህን ርዕስ እንዳደርግ ጫና ያደረገብኝ ደግሞ ከዚሁ ጉዳይ ጋር ተዛማጅ የሆነ ዘግናኝ ዜና በጠዋት በመስማቴ ነው፡፡ ይህውም በምሽት የሚደረግ ትራንስፖርት አሁንም ባለመቆሙ፣ ይልቁንም በድብቅ በህገወጥ መንገድ የሚደረግ መሆኑ ያስከተለው አደጋ ነው፡፡ በጥር 27  ሊነጋ ሲል ከጎንደር አዲሰ አበባ ሰዎች ጭኖ ሊገባ ሲል ነጋ አልነጋ ብሎ ሲከንፍ ለጉዳያችን በፍጥነት እንደርሳለን ያሉ ሰድስት ሰዎች ወዲያውኑ ህይወታቸው ያለፈ ሲሆን፣ ብዙዎች ለከባድና ቀላል ጉዳት ተዳርገዋል፡፡ በሀገራችን በትራፊክ አደጋ ህይወታቸው የሚያልፈው ቁጥሩ አሁን እየቀረበ ካለው እንደሚልቅ ደግሞ አንድ ባለሞያ በማግስቱ በሚዲያ ሲናገሩ ሰማሁ፡፡ ከባድ ጉዳት ደርሶባቸው ከጥቂት ቀናት በኋላ ህይወታቸው የሚያልፍ ሰዎች በመረጃው ውስጥ እንደማይካተቱ ነው ያስረዱን፡፡ በሀገራቸን የሚከሰተው የትራፊክ አደጋ ዝቅ ብሎ የሚቀርበውም መረጃ ቢሆን በምንም መመዘኛ ተቀባይነት እንደሌለው ማንም ይስማማል፡፡ ዛሬ የትኩረት አቅጣጫ ማድረግ የፈለኩት ግን የምሽት ትራንስፖርት የተከለከለው በእርግጥ አደጋ ለመቀነስ ነው? ወይስ ሌላ ውስጠ ወይራ አለው?
በምሳ ላይ ያጫወቱኝ ግለሰብ እንደሚያምኑት ከሆነ በምሽት በሚኒባስ የሚደረግ ጉዞ የተከለከለው አንድም የቴክኒክም ሆነ የህግ መስረት ኖሮት ሳይሆን ይልቁንም በዋነኝነት ሚኒባሶች በሚሰሩበት መስመር የሚንቀሳቀሰው የትራንስፖርት አገልግሎት ሰጪ  “ሰላም ባስ” በመባል የሚታወቀው ድርጅት ባለቤትነቱ የኤፈርት ድርጅት ገቢ በመቀነሱ ነው የሚል ነው፡፡
ይህ ምንም እውነት የሌለው ግምት ወይም አሉባልታ ነገር ነው ተብሎ የማይተው ቢሆንም ግን ሚኒባስ ከ150 ኪሎ ሜትር በላይ መሄድ አይችልም ብሎ ብቃቱ ላይ ምስክርነት የሰጠው ማን ነው? አንድ ሚኒባስ ከአዲስ አበባ ናዝሬት ሶስት ጊዜ ደርሶ መልስ ሄደ ወይም ቀጥ ብሎ ባህርዳር፣ጎንደር ወይም ድሬዳዋ ሄደ ለውጡ ምን እንደሆነ የሚያስረዳኝ ሰው ፈልጌ ማግኘት አልቻልኩም፡፡ ሌላው አስገራሚ ጉዳይ ተመሳሳይ የሆኑ መኪኖች ነገር ግን ባለቤታቸው ግን መንግሰት ወይም የቱሪስት ድርጅት ከሆነ በፈለጉት መንገድንና ጊዜ መጓዝ የሚከለክላቸው የለም፡፡ ተመሳሳይ መኪና ባለቤቱ ብቻ ስለተለያየ እንዴትና ወዴት መሄድ እንዳለበት ገደብ ይጣልበታል፡፡ የቴክኒክ ብቃት ከሆነ ምክንያቱ በማንም ባለቤትነት ይያዝ እገዳው መፅናት ይኖርበታል፡፡
ብዙ ሰዎች በተለይ በኤፍ.አም ሬዲዮ ስልክ ተደውሎላቸው (ደውለው ማለት ስለሚከብደኝ ነው) በዚህ ጉዳይ የምሽት ጉዞ መከልከል እንዳለበት አበክረው የሚገልፁበት ምክንያታቸው በምሽት በሚደረግ ጉዞ በሚፈጠር አደጋ የተማረሩ የሚመስሉ ናቸው፡፡ እንደው ለነገሩ በቀን አደጋ ቢበዛ በቀንም ይከለከል ይሆን? ሀገራችንን ቀን ከሌሊት ሰርተንም ቢሆን ለውጥ ለማምጣት መድከም ሲኖርብን በቀጭን ትዕዛዝ በምሽት መስራት አይቻልም የሚባልበት ሀገር መሆኗ አስገራሚ ብቻ ሳይሆን አሳኝም ነው፡፡ በሚኒባስ ሳይሆን በአውቶሞቢል ሀገር እያቋረጡ መሄድ በሚቻልበት የቴክኖሎጂ እና የተሻለ የሚባል መንገድ ባለበት ዘመን የዚህ ዓይነት መመሪያ አስገራሚነቱን ያጎላዋል፡፡ ሚኒባሶች መብራት የተሰራላቸው በምሽት መጓዝ ስለሚችሉና ስለአለባቸው ጭምር ነው፡፡ የምሽት ጉዞ በተለይ በጥሩ የአየር ሁኔታ ላይ ለመኪናም ሆነ ለተጓዥ እጅግ ምቹ እንደሆነ የሚታመን ነው፡፡ የየምሽት ጉዞ የሚፈልጋቸውን ጥንቃቄዎች መደረጋቸውን ማረጋገጥ ብቻ ነው የሚያስፈልገው፡፡ በምሽት ተጉዞ፣ በቀጣዩ ቀን ጉዳዩን አጠናቆ በቀጣዩ ምሽት ወደ ቤቱ ተመልሶ ወደ ስራ ለመግባት የሚተጋን ሰው ከዚህ ትጋት የሚያደናቅፉ የኤፍ.ኤም ጀግኖች ተዉ የሚላቸው መኖር አለበት፡፡ ያለበለዚያ ግን እንደሚባለውም የገዢዎች ንብረት እና ተጠቃሚነትን የሚነኩ ድርጅቶች እጅ አለበት የሚባለውን ለማመን እንገደዳለን፡፡
ይህንን ሀሳብ ሳቀርብ በምሽት ጉዞ የሚደርስ አደጋን መከላከያው መንገድ ጉዞውን ማስቀረት አይደለም ከሚል መነሻ እንጂ በምሽት ጉዞ ላይ ምንም ዓይነት ቁጥጥር መደረግ የለበትም ከሚል መነሻ አይደለም፡፡ በምሽት መስራትም ሆነ መጓዝ የሚፈልጉ ዜጎች መብታቸው ሊከበርላቸው ይገባል፡፡ ይህ መብት ፀኃይ ስለ አለችና ስለሌለች መሆን የለበትም፡፡ ጉዞው በህግ የሚገዛና ስርዓት ያለው ይልቁንም የዜጎችን ደህንነት በሚያረጋግጥ ደረጃ ላይ መሆኑን መቆጣጠር በሚያስችል መስመር ላይ መሆን ይኖርበታል፡፡ ለምሳሌ አንድ ሚኒባስ 12 ሰው መጫን ካለበት ከ12 ስው በላይ ጭኖ ቢገኝ የሚቀጣው ባለመኪናው ብቻ ሳይሆን በትርፍ ለመጫን ፈቃደኛ የሆነው 13ኛ ሰው ሲከፋም ይህን በመመልከት ምን ይደረግ ብለው ዝም ያሉት ሌሎቹ ተሳፋሪዎች ጭምር መሆን ይኖርባቸዋል፡፡ ይህን ማድረግ ስንችል ሰርዓት ያላው አገልግሎት ሰጪ ብቻ ሳይሆን ሰርዓት ያለው ተገልጋይም ማፍራት ይቻላል፡፡ ሌላው የፍጥነት ገደብ መቆጣጠሪያ ቴክኖሎጂ የመኪና ባለንብረቶች እንዲያስገጥሙ ማድረግ አሁን ባይቻልም፣ መንግሰት በየመቶ ኪሎሜትር ቲኬት መቁረጫ ማሽኖችን በማስቀመጥ አሽከርካረዎች የደረሱበትን ሰዓት በመመልከት ከፍጥነት ገደብ ውጭ የተጓዙት ላይ ተገቢው ህጋዊ እርምጃ እንዲወሰድ ማድረግ ይቻላል፡፡ ይህ ቴክኖሎጂ በየባንኮችና ቢሮዎች ወረፋ ለመያዣነት አገልግሎት እየሰጠ የሚገኝ ማሽን ዓይነት ሊሆን ይችላል፡፡ ሌላው አሽከርሪዎች በጉዞ ላይ የሚጠቀሙተን ጫትና ሌሎች ደባል ሱሶች እንዲያቆሙ በፍፁም ቁርጠኝነት መመሪያውን ለመተግበር በመወሰን እንጂ፤ ሰራ የምትሰሩት ፀኃይ ስትኖር ብቻ ነው የሚለውን የሰነፍ መንገድ ተገቢ ነው ለማለት ያስቸግራል፡፡ ችግር ብልዓትን ይፈጥራል የሚለውን ብሂል ከመተግበር እና ዜጎችን ቴክኖሎጂ ለመጠቀምና ለፈጠራ ከማንቃት ወደ ቁጥጥር ማድለት የመንግሰትን ደካማነት እንጂ ለዜጎች ሃሳቢነትን አያሳይም፡፡

አሁን በማን አለብኝነት ወይም ደግሞ ከአንድ ሰፈር በተፈጠረ የጥቅም ግጭት ምክንያት በተሰጠ ጥቅሻ ብዙ መቶ ሺ ብር አውጥተው ሰርተን እናድጋለን ቤተሰቦቻችንን እናስተዳድራለን ብለው ወደ ትራንስፖርት ዘርፍ የገቡተን ዜጎች እጅግ አሳዝኖዋል፡፡ ይህ ብቻም አይደለም መንግሰት ሊወስዳቸው የሚችላቸው ቁጥጥሮች እና የሚያወጣቸው መመሪያዎች ተገማችነት የሌላቸው በመሆናቸው በማነኛውም የስራ ዘርፍ ተሰማርቶ መስራት አደገኛ ነው ወደሚል መደምደሚያ የሚወስድ ነው፡፡ ብዙ ወጣቶች ይህን ተማምነው ከውጭ መጥተው ሰራ የጀመሩ ቢሆንም አሁን ደግሞ በኪሳራ ሸጠው ወደ ውጭ ለስደት ተሰጋጅተዋል፡፡ በዚህ ገንዘብ ትልቁ ልጄን ውጪ ልኬ መኪናው የሚያመጣውን ያህል እርሱ ይልክልኛል ብለው ያጫወቱኝ ጎልማሳ አሉ፡፡ የመንግሰታችን መልስ ይሞክሩት እንደሚሆን አለመጠርጠር ነው፡፡
በዚህ አጋጣሚ ባለንብረቶች የምሽት ጉዞ ንብረታቸውን ሲያሰማሩ የሾፌሮችን ብቃትና የመኪናቸውን ደህንነት እያረጋገጠ ሰምሪት የሚሰጥ አንድ ማህበር በማቋቋም ንብረታቸውን በህገወጥ መንገድ ለአደጋ እና እንዲሁም ዜጎችን አደጋ ላይ የሚጥል አገልግሎት እንዲቆም ለመተባበር ዝግጁ መሆናቸውን ማሳየት እና በህገወጥ መንገድ የተጣለባቸውን የምሽት አገልግሎት የመስጠት መብት ለማስከበር መንቀሳቀስ ይኖርባቸዋል፡፡ መንግሰትም ከፍተኛ ንብረት ወጥቶበት የተገነቡት መንገዶች 24 ሰዓት አገልግሎት የሚሰጡበትን መንገድ ለማመቻቸት ከክልከላ የተሻለ ዘዴ ለመቀየስ መስራት ይኖርበታል፡፡ ክልከላው የሰነፍ መንገድ ነው፡፡ 
ይህን ፅሁፍ እንድከትብ ያነሳሳኝ የጥር 27/2006 አደጋ መሆኑን በመግቢያዬ ገልጫለሁ፡፡ ስለዚህም ይህ መኪና ከጎንደር ተነስቶ አዲስ አበባ ሊገባ 20 ኪሎሜትር ሲቀረው ነው የተገለበጠው፤ የተገለበጠውም ሳይነጋ ትራፊክ ሳይዘው ለመግባት በሚያደርገው ጥረት እና በነበረው ፍጥነት ምክንያት ነው፡፡ ይህን ሁሉ ኪሎ ሜትር አቋርጦ የተጣለውን ክልከላ ጥሶ ሲመጣ መቆጣጠር ማሰቆም ያልተቻለው ለምንድነው? በዚህ ሁሉ መንገድ የነበሩ ይህን መመሪያ እንዲያስከብሩ ኃላፊነት የተሰጣቸው ክፍሎች ሁሉ በህግ መጠየቅ ይኖርባቸዋል፡፡ በሹፌር ላይ ጥፋቱን አላኮ መቆም የለበትም፡፡ ይህ በጥቅሻ እንቅስቃሴን ማስቆምና ማሰቀጠል ተጠያቂነት ሊኖርበት ይገባል፡፡ የዜጎች ህይወት በከንቱ እንዲጠፋ ምክንያት የሆኑት ሁሉ ለህግ እንዲቀርቡ ሁሉም ይጩኽ፡፡
በመጨረሻም እንደነገሩ የምንፅፋቸው ፅሁፎች አንባቢ እንዳላቸው እርግጠኛ ብሆንም የሚመለከታቸው አካላትም እንደሚያነቡት የሚያሳይ ሁለት የእግረመንገድ ነጥብ ላንሳ፡፡  በአንድ ወቅት ቃሊቲ ሄጄ ባነበብኩት ማሰታወቂያ መሰረት በመንግሰት ሀብት የብአዴን በዓል እንደሚከበር ገልጬ ነበር፡፡ የካቲት 2/2006 አንዱዓለም አረጌን ለመጠየቅ ሲሄድ ምንም ዓይነት ማስታወቂያ በሩ ላይ መለጠፍ ክልክል መሆኑን አንብቤ መጥቻላው፡፡ ይህ የሚያሳየው ፅሁፉን እንዳነበቡት ሲሆን የወሰዱት እርምጃ ግን የመንግሰትን ንብረት ለፓርቲ መጠቀሚያ እንዳይውል ማድረግ ሳይሆን አሁንም የመከልከል ዜዴያቸውን ነው የተጠቀሙት፡፡ የሰነፉን መንገድ፡፡
ሌላው ለፅሁፋችን ተነባቢነት ማሳያው አቶ አሰራት ጣሴ በአዲስ ጉዳይ ላይ ባሰፈሩት ሀሳብ ምክንያት ፍርድ ቤት ደፍረዋል ተብለው ለእስር መዳረጋቸውን ነው፡፡ ፍርድ ቤቶች ሊማሩ የሚገባ የነበረው፤ የዘገየ ፍትህ እንደተነፈገ ይቆጠራል የሚለውን ወርቃማ አባባል ሲሆን በተቃራኒው ከመንግሰታቸው ባልተለየ የማስፈራሪያ ዘዴያቸውን ተግባራዊ አድርገዋል፡፡ በዚህ ጉዳይ ትላንት የተሰጠውን ውሳኔ መሰረት አድርጌ ሳምንት እመለስበታለሁ፡፡
ለማነኛውም የዚህ ፅሁፍ አንባቢ የሆናችሁ የትራንስፖርት ዘርፍ ሹሞች ሀገራችን ኢትዮጵያ ሃያ አራት ሰዓት ሰርተን ዓለም ከደረሰበት ለመድረስ ብዙ እንደሚቀረን ተገንዝባችሁ ለሰራ የሚያነሳሳ ዘዴ እንድታሰቡ አደራ እላለሁ፡፡ ያለበለዚያ የትራፊክ አደጋን ለመቀነስ የቀኑንም ትራንሰፖርት አስቁሙና የትራፊክ አደጋ በመቀነስ ከዓለም አንደኛ ለመሆን ሞክሩ፡፡ በትራንስፖርት ኤኮኖሚክስ ከአደጋ ነፃ የሚባለው ዜሮ ርቀት ነው፡፡
ቸር ይግጠመን

ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማሪያም ደሰላኝ ከእውቀት እና እውነት ጋር የሚጋጭ ትንተና ለምን?



ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማሪያም ደሳለኝ በቅረቡ ወደ ሚዲያ የመጡት የኤርትራው ወዲ ኢሳያስ አፈወርቂ በሚዲያ ቀርበው አንድ አንድ ነገር በማለታቸው፤ ከማን እናንሳለን በሚል ነው የሚሉ ሰዎች ጋር መስማማት የለብንም፡፡ አጋጣሚ ነው ብለን ማለፍ ካልፈለግን አጋጣሚ ባይሆንም አጋጣሚውን ለእኛም እንድ አንድ “እውቀት” የሚጨምር ነገር ልናገኝበት የምንችል አጋጣሚ አድርጎ መውስድ ግድ ይለናል፡፡ እውቀት የሚለውን ነገር ግን ልብ ልንለው የሚገባ ነው፡፡ የጠቅላይ ሚኒስትሩን ምላሽ ተከትሎ ብዙ አስተያየት የተሰጠ ቢሆንም፣ የግል ዕይታዬን ማካፈል የተደጋገመ ቢሆን ጥሩ ነው ብዬ አመንኩ፡፡ ምክንያቱም በመሬት ላይ ካለና ከምናየው እውነትና እውቀት ጋር የተጋጨ ስለመሰለኝ፡፡
የቡድን አመራርን በተመለከተ
የቡድን አመራር ነው ለሃያ ዓመት በፓርቲያችን ያለው ማለት አቶ መለስ እያሉም አመራር ላይ ነበርን ሊሉን ከሆነ ተሳስተዋል፡፡ ከህወሃት ክፍፍል በፊት (እነ ሰዬ፣ ገብሩ፣ ተወልድ፣ ወዘተ) በሚመክሩበት አጀንዳ እኛም ነበርን ሊሉን አይችሉም፡፡ በዚያን ጊዜ የቡድን አመራር በህወሃት ውስጥ እንደ ነበር እናውቃለን፣ ይህ በኢህዴግ ውስጥም ዘልቆ ገብቶ ነበር ማለት አይቻልም፡፡ ይልቁንም አንድ አንድ የህወሃት ሰዎች በየክልሉ ተቀምጠው የህወሃት ውሳኔ ያስፈፅሙ ነበር፡፡ ከህወሃት ክፍፍል በኋላ ነገሮች እንደተቀየሩ እሙን ነው፡፡ ከህወሃት የቡድን አገዛዝነት ወደ አቶ መለስ ዜናው እጅ ስልጣን ተጠቃሎ ነው የገባው፡፡ ለዚህም ነው አቶ መለስ ዜናዊን “ጠቅላይ” የሚባሉት፡፡ አቶ ኃይለማሪያም ደሳለኝ ቦታውን ከያዙት በኋላ በጠቅላይነት የሚያማቸው የለም፡፡ እንደ እኔ ዓይነቱ ወደ ቡድን አሰራር ገብተዋል የሚል ግምት የያዝን አለን፡፡ ሌሎች ደግሞ ወደቀድሞ ቦታ ተመልስው ህወሃት ነው ከጀርባ ሆኖ ማርሽ የሚቀይረው ብለው ይጠራጠራሉ፡፡ እንዲህ ያለህ የተምታታ ግምት ስለአለ ነው በዘዴ በእርግጥ ጠቅላይ ሚኒስትር ነዎት?የሚል ሽንቋጭ ጥያቄ ያስነሳው፡፡
ኢህአዴግ በግልፅ እንደሚናገረው ተግባራዊ ነገር አድርጊያለሁ ብሎ የሚያምነው ከተሃድሶ በኋላ እንደሆነ የሚታወቅ ነው፡፡ ከተሃድሶ በኋላ ደግሞ አቶ መለስ ጠቅላይ የነበሩበት ወቅት ነው፡፡ በዚህ ወቅት አቶ ኃይለማሪያምም ሆኑ ሌሎች ሰዎች ሹመት እንጂ ስልጣን አልነበራችሁም፡፡ ለምሳሌ አቶ ኃይለማሪያም ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ነበሩ፡፡ በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ደረጃ ጠቅላዩ የነበራቸው መረጃ በሙሉ ነበረኝ ምክንያቱም የቡድን አመራር ስለምንከትል ብለው አይዋሹኑም፡፡ ቢሉም በፍፁም አናምኖትም፡፡ በዚያ ደረጃ ተተኪ ልሆን እችላለሁ ብለው ዝግጅት እንዳልነበሮት የሚያሳብቀው እውነት በጠቅላይ ሚኒስትሩ ድንገተኛ ሞት ቦታውን ሲይዙ ከሚሰጡት መግለጫ ለመረዳት የሚቻል ነበር፡፡ ለማነኛውም በቅጡ የኢህአዴግ የቡድን አመራር እንዲኖር ማድረግ ተገቢ ቢሆንም ወሳኝ ስብዕና ደግሞ ከጠቅላይ ሚኒስትር የሚጠበቅ መሆኑን ተረድተው የቡድንም የግለሰብም ወሳኝነት ተመጣጥነው የሚሄዱበት መስመር የግድ እንደሚል ማስታወስ ተገቢ ነው፡፡ በነገራችን ላይ የአሜሪካው ፕሬዝደንት በግላቸው እንደፈለጋቸው አይወስኑም፡፡ ይህን ለመረዳት ቢንላደንን ለመያዝ የተደረገውን ዘመቻ እንዴት በቡድን እና እንዴት በግል ኃላፊነት ወስደው እንደወሰኑ የሚያሳየውን ፊልም ይመልከቱት፡፡
ቴሌ እና የሚታለብ ላም
ይህን በተመለከት ዶክትር ካሱ ኢላላ ብለውት እስከ ዛሬ ድረስ ካደረጉት ስህተት እንደ አንዱ የሚቆጠር የነበረ ነው፡፡ ኢህአዴግ አፍ እንጂ ጆሮ የለውም የሚለውን በሚያጠናክር ሁኔታ ቃል በቃል ሲደግሙት በግሌ አዝኛለሁ፡፡ ምንም ጥርጥር የሌለው ነገር ቴሌ “በመንግሰት እጅም” ሆኖ አትራፊ ነው፡፡ ቴሌ አሁን ጠቅላይ ሚኒስትሩ በነገሩን መረጃ መሰረት በመንግሰት እጅ ሆኖ 6 ቢሊዮን ብር ትርፍ ለልማት ያውላል ብለውናል፡፡ ያልገባቸው ነገር ግን ቴሌ በግል ይዞታ ቢሆንም ከዚህ ሶሰት እጥፍ የሚሆን ትርፍ ሊያተርፍ እንደሚችል ነው፡፡ ከዚህ ትርፍም መንግሰት ድርሻውን ያገኛል፡፡ በኢህአዴግ ሰፈር ያለው ችግር የልማት ባለቤት ህዝብ ይሁን ወይስ መንግሰት የሚለው ነው፡፡ የግል ባለይዞታዎች ከቴሌ ትርፍ ካተረፉ የብር ኖት አይበሉም መልሰው አዋጭ ነው ብለው ባሉት መስመር ኢንቨስት ያደርጉታል፡፡ ምን አልባትም ከመንግሰት በተሻለ አዋጭ መስመር ነው ስራ ላይ የሚያውሉት፡፡ ለዚህ ጉልዕ ምሰሌ በመንግሰት እጅ የሚገኙ የነበሩትን የቢራ ፋብሪካዎች አሁን ለመንግሰት እየከፈሉ ያሉትን ታክስና በኢኮኖሚ ውስጥ እየፈጠሩ ያሉትን መነቃቃት ነው፡፡ እነዚህ ተቋሞች በመንግሰት እጅም እያሉ አትራፊ ነበሩ፤ አሁን ግን የበለጠ አትራፊ ናቸው፡፡
በዋነኝነት የቴሌ በመንግሰት እጅ መቆየት የሚፈለገው ለልማት ካለው ፋይዳ እንዳልሆነ ይገባናል፡፡ በስልጣን ለመቆየት ግን እንዲህ ያለን ህዝቦችን የሚያስተሳሰር ቴክኖሎጂ በግለሰብ እጅ አስገብቶ የነፃነት በር ሆኖ እንዲያገለግል አይፈለግም፡፡ ለሃምሳ ዓመት መግዛት የሚፈልግ ፓርቲ በዚህ ደረጃ ወርዶ ለማፈን ቢሞክር ባህሪው ነው ብሎ መውሰድ ነው፡፡ በልማት ስም በተለይ ለገጠሩ ህዝብ ለማስፋፋት ብለው ሰበብ ከሰጡ በኋላ ግን የቴሌ ገንዘብ ለባቡር መስመር ዝርጋታ እየዋለ ነው ብለው የገጠሩን ህዝብ ለመጠቀሚያ ብቻ እንደሆነ ይፋ አድርገዋል፡፡ የቴሌው የህዝብ ግንኙነት በቅርቡ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ አሁን በተያዘው ማስፋፊያ  85 ከመቶ የሚሆነው የሀገሪቱ ክፍል በኔትወርክ ይሸፈናል ብለዋል፡፡ ይህ ማለት ጠቅላላ ሀገሪቱን ለመሸፈን የቀረው ጥቂት ነው ማለት ነው፡፡ ስለዚህ አገልግሎቱን ከመንግሰት በተሸለ ጥራት ለሚሰጡ የግል ድርጅት አስተላልፉ፣ መንግሰት የመሰረተ ልማት ማስፋፊያና ቁጥጥር ላይ ለምን አይገባም የሚለው መከራከሪያ አሁንም ለፊት ለፊት ጉንጭ አልፋ ጭቅጭቅ እንጂ ይህ ሊሆን የሚችለው በአብዮታዊ ዲሞክራሲያዊ አስተሳሰብ መቃብር ላይ መሆኑን መዘንጋት የለብንም፡፡ ይዘገይ ይሆናል እንጂ ይህ እንደሚሆን ግን ጥርጥር የለውም፡፡ ማለትም አብዮታዊ ዲሞክራሲ አስተሳሰብ ወደ መቃብር ይወርዳል፡፡
እዚህ ጋ ሊሰመርበት የሚገባው ነገር የግል ባለሀብቱን ስብሰባ እየጠሩ የግሉ ዘርፍ ምትክ የሌለው እንደሆነ እናምናለን፤ ከግል ዘርፉ ጋር ጠብ የለንም የሚል መንግሰት ጠቅላይ ሚኒስትር “መንግሰት ብቻ ነው ይህን ትርፍ ለልማት የሚያውለው” ማለት እንዴት ያለ ተቃርኖ እንደሆነ ነው፡፡ በግለሰቦች (ሲደመሩ ህዝብ የሚሆኑት) እምነት የሌለው መንግሰት፤ የህዝብ ወኪል የሚሆን አይደለም፡፡ በህዝብ ስም ግን ይነግዳል፡፡ መንግሰት ብቻ ነው የሚያለማው የሚለውን ከወሰድን የአሜሪካ መንግሰት ከመከላከያ እና ከተወሰኑ ፓርኮች በስተቀር የመንግሰት የሚባል ነገር የለውም፡፡ በአሜሪካ ልማት የለም በቻይና ነው ያለው እንደማይሉ ተሰፋ አደርጋለሁ፡፡ ብዙ ሰው ቻይና ከአሜሪካ ቀጥሎ ግዙፉ ኢኮኖሚ እያሉ ሲሳሳቱ አሜሪካ ቻይናን 10 ዕጥፍ እንደምትበልጣት የምናውቅ አይመስላቸውም፡፡ ቻይና ከጃፓን በለጠች እንጂ አሜሪካ ጋር አልደረሰችም፡፡ ይህችን እንደ እግረ መንገድ ያዙልኝ፡፡ እርግጥ ነው የቻይና መንግሰት ሀብታም ነው፣ ህዝቡ ግን ድሃ፡፡ ምክንያቱም ፍልስፍናው መንግሰት ብቻ ነው የሚያለማው የሚል እና የኛዎቹም ቅጂያቸው እንደዚያ ስለሆነ ነው፡፡ ሰትራቴጂው ገጠሩን እዚያው ገጠር ለማሰቀረት እቅድ ከሌለ በስተቀር የገጠሩ ህዝብ አሁን የሚፈልገው ስልክ እና መብራት ይዛችሁለት በጫካ ስር መኖር ሳይሆን ከተሜነት ነው፡፡ ወደ ስልኩ እና መሰረተ ልማቱ መምጣት ይኖርበታል፡፡
የታክስ ምጣኔ እና የታክስ መሰረት ማሰፋት
ግብር በማይከፈልበት የቦርድ ክፍያ እና ሌሎች ገቢዎች ለሚደጎም ባለስልጣን ብዙ ግልፅ ያልሆነ ግን ደሞዝተኛውን በከፍተኛ ደረጃ እየጎዳ ያለው ከፍተኛ ታክስ የሚከፈልበት የደሞዝ ጣሪያ አሁን ያለውን ነባራዊ ሁኔታ ያገናዘበ አለመሆኑ ነው፡፡ በጋዜጠኞች የቀረበውም ጥያቄ ይህን የሚመለከት እንጂ አጠቃላይ የታክስ ሪፎርም እየተባለ ለረዥም ጊዜ የተያዘ የተሰፋ ፕሮጀክት ምንደረሰ የሚል አይደለም፡፡ ደሞዝተኛውን ደሞዝ ጨመርንልህ ብሎ በግብር ከመቀማት በተግባር የታክስ ምጣኔውን ማስተካከል የዘገየ ብቻ ሳይሆን የዜጎችን የስራ ተነሳሸነት እየገደለ ያለ በምድር ላይ ያለ ሀቅ ነው፡፡ የነዳጅ ዋጋ በዓለም አቀፍ ገበያ ጨመረ ብሎ በየጊዜው የነዳጅ ዋጋ የሚጨምር ፣ ይህንንም ተከትሎ የትራንስፖርት ዋጋ ላይ ጭማሪ የሚያደርግ መንግስት በቀጥታ ከደሞዝተኛ ላይ የደሞዝ መቀነስ እንደሆነ መረዳት አዳጋች አይደለም፡፡ ለኢትዮጵያ ሲቪል ሰራተኞች የመነሻ ደሞዝ ከፍ ማድረግ (ዝቅተኛ የደሞዝ መጠን መወሰን) እና የግብር ማሰከፈያውን የገቢ መጠን ከፍ ማድረግ አፋጣኝ ምላሽ የሚሻ ነው፡፡ በነገራችን ላይ ዜጎች የሚያገኙትን ገቢ እየተከታተለ የሚቀማቸውን አይፈልጉም፡፡ መንግሰትም ቢሆን፡፡ በታክሰና ግብር ስም እየቀሙ እኔ ለልማት አውለዋለሁ ማለት ከስድብ አይተናነሰም፤ ዜጎችም ሰርተው የሚያገኙትን ገንዘብ ለልማት ለዚያውም ለዘላቂ ልማት ነው የሚያውልቱ፡፡ ከዜጎቹ እየቀማ ዜጎችን በማደኽየት የሚበለፅግ መንግሰት ልማታዊ ነኝ ሊል አይችልም፡፡

ሊስትሮም ሁን ብባል ወረዳም ሂድ ከተባልኩ አደርጋዋለሁ፤
ሊስትሮም ሁን ብባል ወረዳም ሂድ ከተባልኩ የምሄድ ወታደር ነኝ፡፡ ይህ አባባል በኢህአዴግ ሰፈር የግል ነፃነት ስለሌለ ምን ያህል እውቀት እንደሚባክን ነው የሚያሳየው፡፡ ልክ ነው በሚቀጥለው ዙር ወደ ክልል ቢባሉ ሊሄዱ ይችላሉ፡፡ አሁኑ በምክትል ጠቅላይ ሚኒሰትር ማዕረግ የሚያገለግሉት ቱባ ባለስልጣን ወደ ክልል ብሎም ወደ ዞን ሲላኩ እሺ ብለው መሄዳቸው የዚሁ ማሳያ ነው፡፡ ከክልል ፕሬዝደንትነት ወደ ጠቅላይ ሚኒሰትረ አማካሪነት ተመሳሳይ የምደባ ዝውውር ነው፡፡ ይህ ግን በምንም ምክንያት ተገቢ ነው ብሎ መውሰድ አይቻልም፡፡ ቅዱስ መፅሐፍ ምሳሌ 4፡18 “የጻድቃን መንገድ እንደ ንጋት ብርሃን ነው፤ ሙሉ ቀን እሲከሆን ድረሰም እየጨመረ ይበራል” ይላል፡፡ ምን ነው የኛ መሪዎች ቁልቁል ማየት ፈለጋችሁ፡፡  የሌሎች ሀገር መሪዎች ከመሪነት ሲለቁ ተከታይ ቦታቸው ሊሰትሮ መሆን ወይም የእርሱ ተመጣጣኝ አይደለም፡፡ በዓለም አቀፍ ደረጃ አማካሪነት ነው፡፡ ዛሬ ክሊንተን አንድ ሰዓት ንግግር አድርገው የሚያገኙት ገንዘብ ከወረዳ በጀት በስንት እጥፍ እንደሚልቅ ነጋሪ የሚፈልግ አይመስለኝም፡፡ ይህን ብቃት አረጋግጫለሁ ያለ ሰው ወረዳ ለመሄድ አያስብም፡፡ በምደባ የተገኘ ስልጣን ግን በምደባ ሊነሳ ይሚችል ነው፡፡ በምደባ ከሚገኝ ስልጣን ያድነን፡፡ እኔ ግን ከዚህም በላይ የገባኝ፣ የጋራ አመራር አለ ብሎ ከግል ተጠያቂነት ለመሽሽ እንዳይሆን የሚል ፍርሃትም አለኝ፡፡ ሌላው ግን አብዛኛው ሹመኛ ነገ ወረዳ ልወረወር እቻላለሁ በሚል ስጋት ተግቶ በዘረፋ ይሰማራል፡፡ የብቃት ከግምት መውጣትና የምደባ ሹመት የሚያመጣው ጣጣ እጅግ ብዙ ነው፡፡ ለዛሬ ይብቃን ቸር ይግጠመን፡፡

የፍርድ ቤት ያለህ ……



በታሕሳስ ወር አጋማሽ አንድ የፌዴራል ፖሊስ መኮንን ችሎት በመድፈር ተከሰው አሁንም ጉዳይ በፍርድ ሂደት ላይ እንደሆነ እናውቃለን፡፡ ፖሊሶቹ አድመው አሁንም ማን እንደሆነ አላወቅንም ብለው አለቃቸው ፍርድ ቤት እንዲቀርቡ አስደርገዋል፡፡ አሁን አላውቅም ድሮ የመኮንን ማዕረግ የሚሰጣቸው ሰዎች ከፖሊስነቱ በተጓዳኝ የህግ ትምህር እውቀት እንዳላቸው ለማንም ግልፅ ነው፡፡ የዚህ ዓይነት ድፍረት መዳፈር አይቻልም፡፡ ይህን ጉዳይ ያነሳሁት በመፅሔት ላይ በተሰጠ አስተያየት ተደፍርኩ ያለ ችሎት አቶ አስራት ጣሴን የአምስት ወር የእስር ቅጣት በሁለት ዓመት ገደብ መወሰኑን ታዝቤ ነው፡፡ ከአምሰት ወሩ ይታሰብ አይታሰብ ባይታወቅም ለአስር ቀን በወህኒ ቤት እንዲቆዩም ተደርጎዋል፡፡ ለህግ ልዕልና ሲባል ፍርድ ቤት እንዲከበር ከዚህ የበለጠ መሰዋዕትነት ለመክፈል የተዘጋጀን ሰው ችሎት ደፍረሃል ማለት ግን ጠብ ያለሽ በዳቦ ነው፡፡
ለማነኛውም መኮንኑ ይግባኝ ሰለጠየቁ በሚል በገንዘብ ዋስትና ከእስር ያሰፈቱት የፌዴራል የመመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤቶች ፕሬዝዳንት አቶ አስራትን ግን ሊያስፈቱ አልቻሉም፡፡ ከሲቪል ሰርቪስ የሚሰበሰቡት ዳኞች የፖለቲካ ታማኝነት እንጂ የህግ እውቀታቸው ዝቅተኛ ነው የሚል እምነት አለን፡፡ ስለዚህ ለገዢው ፓርቲ ያዳላሉ ማለት እንዴት ሆኖ ነው ችሎት መድፈር የሚሆነው፡፡ በቅርቡ የፍትህ ሰርዓቱን የመልካም አስተዳደር መርዓ ግብር በቀረበበት ወቅት አቅመ ቢስ ያለውን ፍርድ ቤት እኛስ ብንለው ምን ይለዋል፡፡ አቅም የሌላቸው ዳኞች ተገቢውን ፍትህ ይሰጣሉ ብለን አለማመን መብታችን ነው፡፡
የፖለቲካ ትግል ውስጥ የገባነው ትክክለኛ የፍትህ ሰርዓት እንዲዘረጋ ጭምር ነው፡፡ መንግሰትን ፍርድ ቤት ገትረን መብታችንን የሚጠብቅልን ፍርድ ቤት ቢኖር በእውነት ወደ ፍርድ ቤት እንጂ የፖለቲካ ትግል ምን አመጣው፡፡ የዚህ ጊዜ ፖለቲካ የሚሆነው መሪ ለመሆን ዕጩ ሆኖ መወዳደር ብቻ ነው፡፡ ትግል የታባቱ፡፡
የፀረ ሙስና እና ሰነምግባር ኮሚሽን ባስጠናው ጥናት ተዓማኒነት ከጎደላቸው ተቋማት አንዱና ዋነኛው ፍርድ ቤቶች እንደሆኑ ገልፆዋል ይህን ተቋም ትክክለኛ ፍትህ ሊሰጠኝ አይችልም ብዬ ማመን በምን መንገድ ነው ችሎት መድፈር የሚሆነው፡፡ በግሌ በፍርድ ቤት ላይ እምነት ቢኖረኝ ኖሮ ያለ ስሜ የአሸባሪነት ዶክመንተሪ መስሪያ ስሆን በማግሰቱ ነበር ፍርድ ቤት የምገትራቸው፡፡ ነገር ግን ፍርድ ቤቱ ከፖለቲካ ጥቅሻ ነፃ ነው ብዬ ስለማላምን አላደረኩትም፡፡ አንድ ቀን እንዳውም በዚሁ ዶክመንተሪ እኔው ልከሰስ እችላለሁ፡፡ ፍርድ ቤትም ጥፋተኛ ነህ ተከላከል ብሎ ዕድሜ ልክ ሊፈርድ ይችላል፡፡
በአቶ አሰራት ጣሴ ክስ መነሻ ዳኛዋ በሌላ ክስ የማይፈለጉ ከሆነ ልቀቋቸው ብለው ለፖሊስ ሲያዙ፤ ፖሊሱ ያለምንም ማንገራገር አለቅም ሲል ደነገጥኩ፡፡ ፖሊሱ ይዞት የመጣውን እሰረኛ የሚለቅበት ሰርዓት ቢኖርም ክብርት ዳኛ ማዘዣው በፅሁፍ ሲደርሰን በህጉ መሰረት እንፈፅማለን የሚል ለፍርድ ቤት የሚገባን ክብር የማይስጥ ፖሊስ ይህን እንዲያደርጉ የሚያስገድድ ፍርድ ቤት ነፃ ነኝ ቢለኝ መብቱ ቢሆንም፤ እኔ ደግሞ አይመስለኝም ነፃ አለመሆናችሁን ብዙ ምልክት አለ ማለት መብቴ ነው፡፡

የፌዴራል የሥነ ምግባርና ጸረ ሙስና ኮሚሽነር አሊ ሱሌይማን እንደተናገሩት “በአሁኑ ወቅት ጠበቃ የሚመረጠው በሙያ ብቃትና በምስጉን ስነ ምግባሩ  ተከራክሮ እውነት ያወጣል በሚል ሳይሆን ምን ያህል ደላላ አለው? ዳኛና ባለስልጣናትን ያውቃልን? በሚሉ መስፈርት ነው” ብለዋል (አዲሰ ዘመን ጋዜጣ የካቲት 2/2006)፡፡ ይህ አሰተያየት ጠበቆችን ለመዝለፍ ቢመስልም ትክክለኛው ግን ደላሎች የሚያገናኙት ዳኞች፣ በባለስልጣን ጥቅሻ የሚሰሩ ዳኞች መኖራቸውን ነው፡፡ የጠበቃ፣ የዳኛ እና የባለስልጣናት ህገወጥ ግንኙነት የሰፈነበት የፍትህ ሰርዓት ትክክለኛ ፍትህ አይሰጠንም ብሎ ማመን እንዴት አድርጎ ነው ችሎት/ፍርድ ቤትን መድፈር የሚሆነው፡፡

“ፍትህ ከኢህአዴግ ፍርድ ቤቶች ይገኛል ተብሎ ሳይሆን ለታሪክ ምስክርነት ነው” ብሎ ጥርጣሬን መግለፅ ነው ወይስ “በደላላና በባለሥልጣን ጥቅሻ ይስራል” ማለት፡፡ ሁለቱም እውነት ከሆነ እውነት ነው፡፡
ሌባ ዳኞች ብለው ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ በምክር ቤት ሲሳደቡ እረ በህግ ማለት ያልቻለ ፍርድ ቤት ዛሬ ደግሞ ችሎት በአንድ መጣጥፍ ውስጥ በተሰጠ አሰተያየት ተደፈረ ማለት እንዴት እነዴት ነው ነገሩ፡፡