Sunday, January 11, 2015


የአንድነትን ፓርቲና የምርጫ ቦርድ
ደብዳቤ ልውውጦች ዝርዝር ሁኔታ በማሰረጃ የተመሰረተ
ታህሳስ 19-20፡
አንድነት ፓርቲ ታህሳስ 19-20/2006 ዓ.ም ልዩ ጠቅላላ ጉባዔ አካሄድ፡፡ ይህ ጠቅላላ ጉባዔ ልዩ የተባለበት ምክንያት የአንድነት አምስት ዓመት ስትራቴክ ዕቅድ ላይ በተቀመጠው መሰረት ፓርቲ ከ2007 ዓ.ም ምርጫ ቀደም ብሎ የአመራር ሽግሽግ በማድረግ ፓርቲውን በአዲሰ አመራር ወደ ምርጫ ይዞ ለመግባት በተቀመጠ ግብ መሰረት ነው፡፡ በዚህ ጠቅላላ ጉባዔ ኢ/ር ግዛቸው ሽፈራው የፓርቲው ፕሬዝዳንት ሆነው ተመረጠዋል፡፡ ይህ ጠቅላላ ጉበዔውም የተለያዩ ውሳኔዎች አሳልፎዋል ከዚህ ውስጥ መሰረታዊ ሊባል የሚችለው ጉባዔው በሌለበት ወቅት ፕሬዝዳንቱን ማንሳት የሚያስችል ስልጣን ለብሔራዊ ምክር ቤቱ መስጠቱ ሲሆን ሌሎችም ለምሳሌ የወጣቶች፣ የሴቶች ጉዳይ ኃላፊዎች በስራ አስፈፃሚ ውስጥ እንዲካተቱ ያደረገ ሲሆን የተቀደሚ ፕሬዝዳንት ቦታም እንዲኖረው አድርጎዋል፡፡
አንድነት ፓርቲ ጠቅላላ ጉባዔውን ባካሄደ በሶስት ወር ጊዜ ውስጥ አመራሩ በሚጠበቅበት ፍጥነት አልሄደም በሚል አለመስማማት የተፈጠረ ሲሆን በአጋጣሚ አንድነት ከመኢህአድ ጋር የሚያደርገው ውህደት ጉዳይ ውይይት በመጀመሩና ለመጠናቀቅ አፋፍ ላይ የደረሰ ሲሆን ይህንንም አጋጣሚ በመጠቀም የውህዱን ፓርቲ የሚመራ የአንድነት ተወካይ ዕጩ ፕሬዝዳንት በብሔራዊ ምክር ቤት ተሰይሞ ውሕደት ይጠናቀቃል ሲባል ውህደቱ እንደማይቻል በምርጫ ቦርድ በኩል ይፋ ተደረገ፡፡ ኢ/ር ግዛቸው ሸፈራው በዚህ አጋጣሚ ተጠቅመው ለወጣት አመራር ቦታ ይለቃሉ ሲባል ይህን ከማድረግ ይልቅ ለውህደት በሚጠራው ጉባዔ በዕጩነት ለመሳተፍ ዝግጁ መሆናቸውን ይፋ አደረጉ፡፡
ሐምሌ 14-30፡
በኢንጅነር ግዛቸው የሚመራው ስራ አስፈፃሚ በታህሳስ 19-20 የተካሄደውን ጠቅላላ ጉባዔ ሪፖርት ገቢ ያደረገው 7 ወር ዘግይቶ ሐምሌ 14 ቀን 2006 ዓ.ም ነበር፡፡ ብዙ ሰዎች ይህ ሪፖርት እንዲዘገይ የተደረገው በአዲሱ አመራር ስለሚመስላቸው ነው ይህን ነጥብ መግለፅ የፈለኩት፡፡ ይህን ሪፖርት መሰረት አድርጎ ምርጫ ቦርድ ሐምሌ 25 ቀን ዘጠኝ ነጥቦችን አንስቶ ማብራሪያ እንዲሰጠው ጠይቆዋል እነዚህም፤
  1. በጉባኤው ዕለት በቀረበው ሪፖርት የገቡት አላሰፈላጊ ቃላት እንዲወጡ፤
  2. የፓርቲው ባንዲራ እንዲቀርብ፤
  3. ፓርቲው አሻሽሎ ባቀረበው አንቀፅ 8 ንዑስ አንቀፅ 2 ሰር የተዘረዘረው ሃሳብ ግልፅ አለመሆኑ፤
  4. የጉባዔተኛው ቁጥር አለመገለፁ፤
  5. የፕሬዝዳንቱን በብሔራዊ ምክር ቤት መመረጥ ከህግ አንፃር ያለው ጉዳይ በሚመለከት፤
  6. የፓርቲው የገቢ ምንጭ በአዋጅ ቁጥር 573/2000 መሰረት ያለመቀመጡ፤
  7. የፓርቲ መፍረስ በተመለከተ በአዋጅ ቁጥር 573/2000 መሰረት ያለመቀመጡ
  8. የፓርቲው አባልነት በውርስ እንደማይተላለፍ አለመገለፁ፤ እና
  9. ፓርቲው ያቀረባቸው የፓርቲ አካላት ውስጥ የሚሳተፉ አባላት አድራሻና በኃላፊነት ለመስራ የተሰማሙበት ሰነድ ያለመቅረቡ፤
የሚሉት ናቸው፡፡ ለእነዚህ ለቀረቡት ጥያቄዎች ሐምሌ 30 ቀን  18 ገፅ ያለው ማብራሪያ ተሰጧዋል፡፡
ይህ በእንዲህ እንዳለ የመኢህአድና የአንድነት ውህደት አሰመልክቶ ከምርጫ ቦርድ ጋር በሚደረግ ውይይት በአንድነት በኩል ምንም ችግር እንደሌለ ነገር ግን ቦርዱ ሲሰበሰብ ውሰኔ እንደሚሰጥ በተደጋጋሚ ሲነገር ቆይቶ የመኢህአድ ጠቅላላ ጉባዔ ኮረም ሳይሞላ የተካሄደ ስለሆነ ተቀባይነት የለውም በሚል ሰበብ ውህደቱ እንደማይሳካ በምርጫ ቦርድ ተገለጠ፡፡ ይህንንም ተከትሎ የአንድነት ስራ አሰፈፃሚ ኮሚቴ አባላት የነበሩ አምሰት ከፍተኛ አመራሮች በሰራ አሰረፃሚነት ላለማገልገል መወሰናቸውን ገልፀው መልቀቂያ ደብደቤ አሰገቡ፡፡ ኢንጂነር ግዛቸውም በምትካቸው ሌሎች አመራሮቸን በመሰየም ስራቸውን ለመቀጠል ሞከሩ፡፡
ጥቅምት 3፤
ኢንጂነር ግዛቸው ሸፈራው የብሔራዊ ምክር ቤቱን ጠርተው በጥቅምት ሁለት ካቢኔያቸውን ማሰናበታቸውን በመግለፅ ከውስጥና ከውጭ በደረሰባቸው ጫና ለፓርቲው እልውና ሲሉ ጠቅላላ ጉባዔ የሰጣቸውን ኃላፊነታቸውን ለመልቀቅ እንደወሰኑ ለምክር ቤት አቀረቡ፡፡ ምክር ቤቱም ኃላፊነት ለመልቀቅ መወሰናቸው ተቀብሎ ፓርቲው አመራር በቀጣይ እንዴት መሆን አለበት በሚል ባደረገው ከፍተኛ ውይይት ፓርቲው ለአንድ ቀንም ያለ አመራር ማድር እንደማያስፈልግ ታምኖበት ከዚህ በፊት የመኢህአድና አንድነት ውሕደት አስመልክቶ ለዕጩነት ሲንቀሳቀሱ የነበሩትን ጨምሮ ሌሎች ተጨማሪ ዕጩዎች በፈቃደኝነት ቀርበው ውድድር ተደርጎ በሚስጥር ደምፅ አስጣጥ በተደረገ ምርጫ አቶ በላይ ፍቃዱን በፕሬዝዳንትነት ሰየመ፡፡ በሳምንቱ ጥቅምት 10 ደግሞ የስራ አስፈፃሚ ኮሚቴውን ሰይሞ ስራውን በይፋ ጀመረ፡፡
ጥቅምት 19-21፤ የምርጫ ቦርድ ፅ/ቤት ምክትል ኃለፊ ጥቅምት 19 በተፃፈ ደብዳቤ አንድነት ፓርቲ ያደረገው የፕሬዝዳንት ምርጫ በታሕሳስ 19-20 በተደረገው ጉባዔ የተሻሻላው ደንብ በቦርዱ ባለፀደቀበት ሁኔታ ስለሆነ ተቀባይነት የለውም የሚል ስሜት ያለው ደብዳቤ ሲፃፍልን፣ በዚህ ጉዳይ ላይ ለመነጋገር ጥቅምት 20 የቦርዱ ፅ/ቤት ኃላፊ ጋር ለመነጋገር የፓርቲ ወኪሎች ስንሄድ የቦርዱን ጥቅምት 19 ያደረገውን 2ኛ መደበኛ ስብሰባ ውሳኔ ደረሰን፡፡ ፓርቲያችን ሁለቱን ደብዳቤዎች መሰረት አድርገን ከቦርዱ ፅ/ቤት ኃላፊ ጋር ባደረግነው ውይይት ቦርዱ በጥቅምት 20 ላቀረባቸው ጥያቄዎች መልስ ስጡ ዋናውም የቦርዱ ጥያቄ ነው ተብለን በመግባባት መንፈስ ተለያየን፡፡ ቦርዱ ጥቅምት 19 ተሰብስቦ ለፓርቲያችን ያቀረበልን ጥያቄዎች፤
1.      ሪፖርቱ ለምን 7 ወር ዘገየ፤
2.     የጠቅላላ ጉበዔ አባላት ቁጥር በደንቡ ውስጥ የለም እና
3.     የፕሬዝዳንት መረጣ ለማድረግ ጠቅላላ ጉባዔ ለብሔራዊ ምክር ቤት ውክልና የሰጠበት አግባብ ከዲሞክራሲያዊነት እና ከአባላት ተሳትፎ አንፃር ማብራሪያ ይፈልጋል፤
የሚሉት ናቸው፡፡
ለእነዚህ የቦርዱ ጥየቄዎች እና ጥቅምት 19  በቦርዱ ምክትል ኃላፊ ለቀረቡት ህገወጥ ጥያቄዎች መልስ አዘጋጅተን ጥቅምት 21 2007 ዓ.ም ለቦርዱ ፅ/ቤት ገቢ አደረገን፡፡
ህዳር 10 -19/2007፤
የምርጫ ቦርድ በጥቅምት 20 ላቀረባቸው ጥያቄዎች በጥቅምት 21 ለሰጠነው መልስ ገምግሞ የሚከተሉትን ውሳኔዎች የያዘ ደብዳቤ ህዳር 10 2007 ዓ. ም ለፓርቲያችን እንዲደርስ አደረገ፡፡ እነርሱም
1.      ሪፖርት መዘግየቱ አግባብ ያለመሆኑን ጠቅሶ ለወደፊት ሪፖርቶች በወቅቱ ገቢ እንዲደረግ
2.     የጠቅላላ ጉባዔ አባላት ቁጥር ተወስኖ በደንብ ውስጥ መግባት እንደሚያስፈልግ እና
3.     የፕሬዝዳንቱን ምርጫ አስመልክቶ ጠቅላላ ጉባዔው ለብሔራዊ ምክር ቤት ውክልና የሰጠበትን አግባብ በቅንንት እንደሚያየው ገልፆ፤
በተራ ቁጥር 2 ለተጠየቀው ጥያቄ መልስ ሲቀርብ ውሳኔ እንደሚሰጥ የሚጠቅስ ነበር፡፡
ህዳር 11 ቀን 2007 ዓ.ም የጠቅላላ ጉባዔ አባላት ቁጥር 320 እንደሆነ እና ከዚህ ውስጥ 161 ሲገኝ (ሃምሳ ከመቶ በላይ)ምልዓተ ጉባዔ እንደሆነ ገልፀን ለቦርዱ አስገባን፡፡ በዚሁ መሰረት መልስ ይሰጡናል ብለን ስንጠብቅ፣ በቦርዱ በኩል ደግሞ ዝምተው ስበረታብን የቦርዱን ፅ/ቤት ኃላፊ እንዲሁም የቦርዱን ሰብሳቢ ሰናነጋግር ደንብ የሚሻሻላው በደብዳቤ ሳይሆን ይህን ማድረግ በሚችለው በጠቅላላ ጉባዔው መሆኑን በተዘዋዋሪ ገለፁልን፡፡ በዚህ ውይይት ዘወትር የሚሰጠን ምክር አርፋችሁ ለምርጫ ዝግጅት አድርጉ እኛ በቅንንት ነው የምናየው የሚሉ የማግባቢያ ንግግሮች ነበሩት፡፡ ይህንን ግን በፅሁፍ እንዲያደርጉት ባደረግነው ጉትጎታ ህዳር 19 ቀን ቦረዱ ያለውን የመጨረሻ ጥያቄ በፅሁፍ ሰጠን፡፡ ይኽውም የጠቅላላ ጉባዔ አባላትን ቁጥር በደንብ ውስጥ አካቱና አምጡ የሚል ነው፡፡ ቦርዱ ከዚህ በኋላ ባደረገው የደብደቤ ልውውጥ የህዳር 10 እና ህዳር 19 ደብዳቤ ሆን ተብሎ አይጠቅስም፡፡ የቦርዱን ቅንነትና ሆደ ሰፊነት የሚለውን አባባል ያልተመቻቸው አባላት ጠቅላላ ጉባዔ አባላት ተጠርተው ለጉዳዩ መቋጫ ለመስጠት በመወሰን ጉባዔ እንዲጠራ ተወሰነ፡፡
ታህሳስ 3-4፤
የአንድነት ፓርቲ በቦርዱ በቀረበለት ጥያቄ መሰረት የጠቅላላ ጉባዔ ኮረም በደንብ ውስጥ ለማስገባት ብቻ መጥራት ተገቢ አይደለም በሚል እምነት ከጉባዔ አባላት ቁጥር ከማካተት በተጨማሪ ያሉ የዞን አመራሮችን ጨምሮ በምርጫ ጉዳይ ላይ ሰፊ ውይይት የሚያደርግበት በፓርቲያችን ላይ በምርጫ ቦርድ በኩል በሚዲያ እየተፈጠረ ያለውን ብዥታ ለማጥራት የሚያሰችል ደማቅ ጉባዔ ተካሄደ፡፡ መፈክራችንም “ምርጫ 2007 ለለውጥ” የሚል ነበር፡፡ በኢትዮጵያ የተቃዋሚዎች ታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ ያሸበረቀ ጉበዔ አካሄደን የሚከተሉትን ውሳኔዎች ጉባዔ አሳለፈ፤
1.      የጠቅላላ ጉባዔ አባላት ቁጥር 320 እንዲሆን እና ኮረም 50 ከመቶ ሲደመር አንድ እንዲሆን፤
2.     የብሔራዊ ምክር ቤቱ የፓርቲውን ፕሬዝዳንት ለመምረጥ የሄደበት መንገድ ህገ ደንባዊ መሆኑን፤
3.     በቀጣይ ምርጫ ቦርድ በጠቅላላ ጉባዔው ውሳኔ ላይ ጥያቄ የሚያነሳ ቢሆን ብሔራዊ ምክር ቤቱ የጠቅላላ ገባዔውን ወክሎ ምላሽ እንዲሰጥ የሚሉት፤
ዋና ዋናዎቹ ናቸው፡፡
ታህሳስ 10፤
የጠቅላላ ጉበዔውን ሪፖርት ታህሳስ 10 ቀን 2007 ዓ.ም ለቦርዱ ፅ/ቤት ገቢ የተደረገ ሲሆን ቦርዱ ይህንን ችላ በማለት ፍፁም ኃላፊነት በጎደለው ሁኔታ በዕለቱ ምሽት የቦርዱ ኃላፊዎች በሚዲያ ቀርበው በአንድነት ፓርቲ ውስጥ ችግር እንዳለ የሚገልፅ መግለጫ ይሰጣሉ፡፡ በማግስቱ ቅዳሜ ደውለው ደብዳቤ እንድንወስድ ይነግሩናል፡፡ በታህሳስ 10 ቦርዱ ተሰብስቦ በወሰነው መሰረት የጠቅላላ ጉባዔ ሪፖርት በ7 ቀን ውስጥ እንድታስገቡ የሚል ነበር፡፡ ይህን ደብዳቤ አስመልክቶ እና በሚዲያ የሰጡትን መግለጫ አስመልክቶ ከቦርዱ ስብሳቢ ጋር ባደረግነው ውይይት ያቀረብነውን ሪፖርቱን በአጭር ጊዜ ተሰብሰበው ውሳኔ እንደሚሰጡት መግለጫ በክፋት ሳይሆን በቅንንት እንደሆነ ይገልፁልናል፡፡ ይህ እንደማይሆን ግን ምልክቶች እያየን ነበር፡፡ የቦርዱ ፅ/ቤት ኃላፊና ምክትላቸው በተለያየ መልኩ ከፓርቲያችን ውስጥ ቅሬታ ተሰምቶናል የሚሉ ህገወጦች ጋር በቢሮዋቸው እንደሚዶልቱ እየሰማን ነበር፡፡ በግንባርም በኃላፊው ቢሮ ከግለሰቦቹ ጋር ሲመክሩ አግኝተናቸዋል፡፡
ታህሳስ 27 -30፡
ቦርዱ ተሰብሰቦ ያቀረብነውን ሪፖርት መርምሮ መልስ ይሰጣል ብለን በቅንንት ስንጠብቅ ታህሳስ 26 እሁድ በስልክ ተደውሎ የቦርዱ ኃላፊዎች ለውይይት እንደሚፈልጉን ይነገረናል፡፡ የዚያኑ እለት እሁድ በፓርቲያችን ለሆዳቸው ያደሩ ባንዳዎች አራት ኪሎ በሚገኝ ካፍቴሪያ ተሰብሰበው ፊርማ ተፈራርመው ለቦርዱ ገቢ አድርገዋል፡፡ በእሁድ ቀን ማለት ነው፡፡ ታታሪው ምርጫ ቦርድ አንድነትን ለማናጋት እሁድን ጨምሮ ሌት ከቀን ይሰራል፡፡ ታህሳስ 27 ቀን 2007 ዓ.ም ቦርዱ ፅ/ቤት ስንገኝ ካሜራ ደቅነው ከአቶ የማነአብ አሰፋ እና ከአቶ አየለ ሰሜነህ ጋር “ውይይት” እንድናደርግ ግብዣ ያደርጉልናል፡፡ ዓላማው በምሽት ቦርዱ ሊሰጠው ላሰበው ውዥንብር መፍጠሪያ መግለጫ የቪዲዮ ግብዓት ለማግኘት የነበረ ሲሆን መኢህአዶች በየዋህነት በቪዲዮ ተቀርፀው ሲቀርቡ እኛ ከእነዚህ ሰዎች ጋር በምርጫ ቦርድ መድረክ የምናደርገው ውይይት እንደሌለ፤ ቦርዱ ያሰገባነውን ሪፖርትና ግለሰቦች ያቀረቡትን ሪፖርት መርምሮ ውሳኔውን እንዲያሳውቅ ብቻ መሆኑን ገልፀን ተመለስን፡፡ በምሽቱ የቦርዱ ምክትል ሰብሰቢ የውስጥ ችግራቸውን እንዲፈቱ ልናስማማቸው ሞክረን አልተሳካም፤ የታህሳስ 19-20 ሪፖርት 7 ወር አዘግይተው አስገብተዋል፤ የፕሬዝዳንቱ ምርጫ ህገወጥ ነው፤ የሚሉ መግለጫዎችን በመስጠት ህዝቡን ብዥታ ውስጥ ለመክተት ሞከሩ፡፡ ይህን ሲያደርጉ ቦርዱ ስብሰባ የተጠራው ለታህሳስ 28 ሲሆን ቦርዱ ከመሰብሰቡ በፊት በቅድሚያ በማን አለብኝነት የቦርዱ ምክትል ሰብሰቢ የግል ውሳኔያቸውን አስታውቀው ለቀሪዎቹ የቦርድ አባላት ዋጋ ቢስነት በህዝብ ፊት አረጋገጡ፡፡
በታህሳስ 28 በምሳ ሰዓት ተደውሎ የቦረዱን ውሳኔ ለመስማት በ9፡00 ሰዓት እንድንገኝ ጥሪ ተደርጎልን ስንሄድ ገዛኽኝ አዱኛ የሚባል የወረዳ ስድሰት አባል እና እራሱን የወረዳ ሰድስት ዕጩ አድርጎ ያቀረበ 10+1 ያጠናቀቀ እና ሰፊው የሚባል የወረዳ 7 አባልና አራሱን ለ2007 ምርጫ የወረዳ 7 ዕጩ አድርጎ አቅርቦ ያልተሳካለት አኩራፊ አኩራፊ የአንድነት አባላትን ወክለው እንዲገኙ በአኩራፊዎች ተወክለው ነበር፡፡ ይህ ቡድን ምርጫ ቦርድ ከመምጣቱ በፊት በአምባሳደር መናፈሻ ድራፍት ቢራ እየተጎነጩ በአቶ ትዕግሰቱ አውሎም መመሪያ ሲሰጣቸው ነበር፡፡
ቦርዱ ፅ/ቤት ያለውን ሁኔታ ስንረዳው አሁንም ለኢቲቪ የቪዲዮ ግብዓት ለማግኝት ካልሆነ ትርጉም እንደሌለው በመረዳታችን የቦርዱ ውሳኔ በፅሁፍ እንዲሰጠን ጠይቀን ወደ ቢሮዋችን ተመለስን፡፡ በምሽት ዜና እና በቅርቡ በከፍተኛ ወኔ ገዢውን ፓርቲ ለመከላከል የቆመው የኢህአዴግ ሚዲያ የሆነው ሬዲዮ ፋና የቦርዱ ውሳኔ ነው ያሉትን ነገር ግን ቦርዱ ከመሰብሰቡ በፊት በቦርዱ ምክትል ሰብሳቢ በሚዲያ የተነገረውን ውሳኔ በትንተና አቀረቡት፡፡ የቦርዱ ሰብሳቢ ፕሮፌሰር መርጊያም ከንፈራች እስኪደርቅ ድረስ አንድነት ላይ አለ የሚሉትን ክስ ሁሉ አዘነቡት፡፡ ታህሳስ 29 የገና በዓል በመሆኑ ታህሳስ 30/ 2007 ጠዋት ማልደን ምርጫ ቦርድ ተገኘተን በሚዲያ የነዙትን ክስ በፅሁፍ እንዲሰጡን ስንጠይቅ ደብዳቤ እየተዘጋጀ እንደሆነ ገልፀውልን በ5፡00 ሠዓት ደብዳቤ ሰጡን፡፡ አባላቶቻችን ቁጭ ብሎ ተረቆ የተፃፈ ደብዳቤ አስገራሚው በሆነ ሁኔታ በታህሳስ 28 ተደርጎ ወጭ እንዲሆን ተደርጎ ቀን ተፃፈበት፡፡ እዚህ ጋ የቦርድ ኃላፊዎች የበታች ሰራተኞችን ምን ያህል ከህግ ውጭ እንደሚያሰሩ ነው፡፡ የቦርዱ ፅ/ቤት ምን ያህል ለመዋረድ እንደተዘጋጀ የሚያሳይ ነው፡፡ ለማነኛውም ታህሳስ 30 የደረሰን ደብዳቤ አራት ነጥቦች ያሉት ለማስመስል ቢሞክርም ሁለት ጥያቄዎች ናቸው ያሉት፡፡ እነርሱም
1.      የታህሳስ 19-20 ሪፖርት ለምን ዘገየ የሚል እና
2.     የፕሬዝዳንቱ ምርጫ የፓርቲውን ህገ ደንብ የተከተለ አይደለም የሚል ነው፡፡
የሚያሳዝነው ነገር ቦርዱ የታህሳስ 3 ቀን 2007 ጠቅላላ ጉባዔ ሪፖርት ለመመርመር ተሰብሰቦ የታህሳስ 19-20/2006 ሪፖርት ለምን ዘገየ ማለቱ ብቻ ሳይሆን በቅንንት ተቀብዬዋለሁ ያለውን የፕሬዝደንት ምርጫ በድጋሚ ማንሳቱ ነው፡፡ በግልፅም ቦርዱ የአንድነትን ሪፖርት በጥልቀት ገመገምኩ ይበል እንጂ እንዳልገመገመው ማሳይ ነው፡፡ ይህ ደግሞ ቦርዱ ወሰነ የተባለው እና የቦርዱ ምክትል ሰብሰቢ ከቦርዱ ስብሰባ በፊት በሚዲያ የሰጡት መግለጫ መመሳሰል ብቻ ሳይሆን ቦርዱ ሊመረምረው ከተቀመጠው ሪፖርት ይዘት የወጣ ውሳኔ አሳለፈ መባሉ ነው፡፡
ስለዚህ የታህሳስ 19-20/2006 ሪፖርት ለምን ዘገየ ከአሁን በፊት በቂ መልስ ተሰጥቶታ ቦርዱ እንደተቀበለው ማስታወስ እና አንድነትም በተከታይ ባደረገው ጠቅላላ ጉበዔ በሰባት ቀን ሪፖርት ማስገባቱ ነው፡፡
ጥር 1-3፤
አንድነት ፓርቲ ለመጨረሻ የደረሰው ደብደቤ ጥር 1 ቀን 2007 ከሰዓት በኋላ  11፡45 (ከሰራ ሰዓት ውጭ) የደረስን ህገወጥ ደብዳቤ በጥር 3/ ለሚደረገው ጠቅላላ ጉባዔ የምርጫ ቦርድ ታዛቢ መላክ እንደማይችሉ ገልፀው ለዚህም የሰጡት ሰበብ በእነ አየለ ሰሜነህ የሚመሩ አባላት ሌላ ጠቅላላ ጉባዔ በሳሬም ሆቴል በመጠራቱ ሁለት ቦታ ጉባዔ ታዛቢ መላክ አልችልም የሚል ነው፡፡ በመሰረቱ የምርጫ ቦርድ በእጁ በሚገኝው የፓርቲያችን ደንብ  አባላት ጠቅላላ ጉባዔ ሊጠሩበት የሚችሉበት ስርዓት በግልፅ ተቀምጦ እያለ ከዚህ ውጭ የፓርቲውን ጉባዔ ለማደናቀፍ ምን ያህል እየተሰራ እንደሆነ ግልፅ ማሳያ ነው፡፡ አንድነት በማግስቱ መገኘት ባይፈልጉም ጉባዔው በተያዘለት ፕሮግራም መሰረት እንደሚቀጥል ጥር 2/2007 እንዲያውቀት ተደርጎዋል፡፡ በዚሁ መስረት አድነት ጥር 3/2007 በደማቅ ሁኔታ እየተካሄደ ይገኛል፡፡ ይህን መስመር የፃፍኩት ጉባዔዬው አሰመራጭ ኮሚቴ ሰይሞ ሲያጠናቅቅ ነው፡፡ ትግሉ ይቀጥላል……….. የደብዳቤው ልውውጥም ይቀጥላል፡፡ ይህ ታሪካዊ ዘገባ ይሆናል፡፡

ግርማ ሠይፉ ማሩ  (ጥር 3/ 2007)

Saturday, December 27, 2014

አንድነትና ምርጫ ቦርድ


ዛሬ በምርጫ ቦርድ ጉዳይ ለመፃፍ ያነሳሳኝ ነገር ማንም ይረዳዋል ብዬ አምናለሁ፡፡ ፀረ አንድነት ዘመቻ ከተጀመረ ቢቆይም እያለፈ እያለፈ ብቅ ማለቱ ብዥታ ስለፈጠረብኝ ነው፡፡ ምርጫ ቦርድ ከአንድነት ጋር የሚያድርግ ያለውን ዝርዝር ከማውራቴ በፊት ግን ለአንባቢ ማስጨበጥ ያለብኝ ነገር አለ፡፡ አንድነት ፓርቲ ምርጫ እሳተፋለሁ ሲል ምን ማለቱ ነው? የሚለውን ብዙዎች እነደፈለጉ ይልቁንም እነሱ ለመረጡት የሰነፍ መንገድ በሚመቻቸው መንገድ እየተረጎሙት ይገኛል፡፡
አንድነት ፓርቲ ምርጫ እገባለሁ ብሎ ሲወስን አንድነት በምንም መመዘኛ ከገዢው ፓርቲም ሆነ ከመንግሰት መዋቅሮች የተለየ ድጋፍ አገኛለሁ ብሎ በማሰብ አይደለም፡፡ ምርጫ ቦርድን ጨምሮ ማለት ነው፡፡ ይልቁንም አሁን ባለው ሁኔታ ማለትም ከዋና አዛዣቸው የቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትር እልፈት በኋላ ለመጀሚረያ ጊዜ የሚያካሂዱትን ሀገራዊ ምርጫ ከቀድሞ በተለየ ለመሸነፍ ዝግጁ ይሆናሉ ብሎ ማሰብ አይቻልም፡፡ ማለትም በ1997 እንዳደረጉት ለሙከራም ቢሆን የጫወታ ሜዳውን ሊከፍቱት አይችሉም፡፡ ባጠቃላይ የአንድነት ፓርቲ ግምገማ ገዢው ፓርቲ ከምን ጊዜውም በላይ ዘግቶ መጫወት እንደሚፈልግ ከግንዛቤ ያሰገባ ነው፡፡ ሰለዚህ መድረኮች በቅርቡ እንዳሉት እንዲሁም አንድ እንድ ፓርቲዎች ሲሉት እንደነበረው ኢህአዴግ በሩን ለውይይት የዘጋው እንደ አንድነት ፓርቲ ምርጫ እንገባለን ስለአልን አይደለም፡፡ ኢህአዴግ አሁን ካለበት ነባራዊ ሁኔታ ተነስቶ ምንም ክፍተት እንደማይሰጥ በመረዳት ከወዲሁ መላውን ህዝብ አንቀሳቅሰን ለማስከፍት የወሰንን መሆኑን ማውቅ ይኖርባቸዋል፡፡
አንድነት ምርጫ እሳተፋለሁ ሲል ደግሞ ለተሳትፎ እንዳልሆነ ደግሞ ሁሉም ያውቀዋል፡፡ የመጀመሪያው በር ማስከፈቻው ደግሞ ህዝቡ አማራጭ የለም ከሚል ፕሮፓጋንዳ እንዲላቀቅ በማድረግ አማራጭ ማሳየት ዋነኛው ሲሆን፣ አማራጭ መኖሩን ከተረዳ ደግሞ በነቂስ ወጥቶ ለመራጭነት እንዲመዘገበ፣ እንዲመርጥ እና ድምፁን እንዲያስከብር ማስተማር ነው፡፡ ይህ ደግሞ በሩን ክፈቱ ከሚል ጉንጭ አልፋ ጭቅጭቅ ተላቀን እንዴት እንክፈተው ላይ ማተኮር የሚል ስትራቴጂ ነው፡፡ ሚሊዮኖች በዚህ መስመር ከተሰለፉ ደግሞ ማንም ውሳኔያቸውን እንደማይቀለብስ እርግጠኞች ነን፡፡ ይህ ደግሞ በህዝብ ኃያልነት መተማመን ነው፡፡ ህዝቡ ከተባበረ ይህን በመንግሰት መዋቅሮች የሚደርሰውን አፈና ሊበጥሰው እንደሚችል ማመን ይኖርብናል፡፡ ከሌሎች ፓርቲዎች ጋር የምንለየው በዚህ ነው፡፡ ሌሎች ኢህአዴግ በሩን ይክፈትና እንግባ ሲሉ እኛ ደግሞ ከፍተን እንግባ ብለናል፡፡ ኢህአዴግ ልብ ቢገዛና ሜዳውን ለሁሉም እኩል እንዲሆን ቢያደርገው ምርጫው ፍጥጫ ሳይኖርበት ሊጠናቀቅ እንደሚችል የሁላችንም እምነት ነው፡፡ በነገራችን ላይ በሩን ከፍተን እንግባ ያልነው እኛ ብቻ አይደለንምን የሀይል አማራጭ የሚከተሉትም ይህን ከፍቶ መግባት ይስማሙበታል፡፡ ልዩነታችን እኛ በሰላማዊ መንገድ ህዝብን አስተባብሮ ማሰከፈት እና መግባት ይቻላል ማለታችን ነው፡፡
ወደ ምርጫ ቦርድ ጉዳይ ስንመለስ፣ ምርጫ ቦርድ አንድነትን ምን አድርግ እያለው እንደሆነ ለሁላችን ግልፅ አይደለም፡፡ ከምርጫ ቦርድ ሰዎች ጋር በግንባር ቀርበን ስንወያይ በአክብሮት እንደሚያስተናግዱን መካድ ተገቢ አይደለም፡፡ ይሁን እንጂ በተለያየ ጊዜ በሚዲያ ብቅ እያሉ የሚሰጡት መግለጫ ስንመለከት አንድነት ፓርቲን ለምን በዚህ ደረጃ እንደሚፈታተኑት ለመረዳት ይከብዳል፡፡ በቅርቡ በአንድነት ውስጥ በአመራር አሰያየም ችግር እንዳለ አስመስለው ያቀረቡት ነገር በጣሙን አሳኝ ብቻ ሳይሆን በተለይ አንድነት ፓርቲ የህዝብ ታዛቢዎች ምርጫን በንቃት ለመሳተፍ በቂ ዝግጅት አድርጎ መንቀሳቀስ በጀመረበት ወቅት መሆኑ ጋር ተራ ግጥምጥሞሽ ነው ለማለት አያስደፍርም፡፡ ከዚህ ጋር ተያይዞ የምርጫ ቦርድ ከዚህ ቀደም እንደሚያደርገው በሚዲያ ምንም ዓይነት ቅስቀሳ ሳያካሂድ፣ በየሰፈሩም የህዝብ ታዛቢ ምርጫ እንደሚካሄድ በይፋ ጥሪ ሳይደረግ፣ በሚስጥር በደብዳቤ በተጠሩ የቀበሌ ነዋሪዎች የህዝብ ታዛቢ ምርጫ ማድረጉን ስንታዘብ፣ ምርጫው ፕሮፌስር መርጊያ በቃና በተደጋጋሚ ምርጫን በተሻለ ሁኔታ ለማካሄድ አቅም ፈጥረናል ይበሉ እንጂ ሁሉንም እኩል ለማጫወት ዝግጁ ናቸው ብለን ለማለት አቅም እያነሰን፣ እነሱም እምነታችንን እየሸረሸሩት ይገኛል፡፡
ምርጫ ቦርድ አንድነት ፓርቲን ከሌሎች ፓርቲ በተለየ ሁኔታ የጠቅላላ ጉባዔ አባላትን ብዛት አሰገቡ ይህም በደንባችሁ ውስጥ ይካተት ብሎ ሲል በግልፅ ባይሆንም በገደምዳሜ ጠቅላላ ጉባዔ ካልጠራችሁ ይህን ማድረግ አትችሉም ማለቱ ነበር፡፡ አንድ ዓመት ባልሞላ ጊዜ ደግሞ አንድ ተቃዋሚ ፓርቲ ይህን ማድረግ አይችልም የሚል ታሳቢ ያደረጉ ይመስላል፡፡ አንድነት ግን ይህን ግምት መና ባስቀረ መልኩ ጠቅላላ ጉባዔ ጠርቶ በደመቀ ሁኔታ ለ2007 ምርጫ መሰረት ጥሎ ሲለያይ ምርጫ ቦርድ እሰይ ተፎካካሪ የሚሆን ፓርቲ መጣ ብሎ መደሰት ሲገባው በተራ የአስተዳድር ስራዎች መሰረት አድርጎ ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥቶ በሳምንት ጊዜ እንድታስታውቁ የሚል ማስጠንቀቂያ አዘል መልዕክት በማስተላለፍ ህዝቡን ግራ ማጋባት ተገቢ እንቅስቃሴ አይደለም፡፡ ይህን ጉልበታቸውን ለፓርቲዎች አቅም ግንባታ ቢያውሉት የሚጠቀሙ ይመስለኛል፡፡ ሀገርም ከዚህ ይጠቀማል፡፡
አንባቢ እንዲረዳ የምንፈልገው ዋና ቁምነገር አንድነት ፓርቲ እንደ ፓርቲ ሁሉንም ህጋዊ መስመሮች አሟልቶ በተደጋጋሚ በሆደ ሰፊነትና በቅንነት በህግ ከሚጠበቅብን በላይ በመሄድ ከግብግብ ግንኙነት ወደ ውይይት ለማምረት ሙካራ እያደረግን መሆኑን አውቆ አንድም የህግ ክፍተት ፈጥረን ከጫወታ ለመውጣት ሰበብ እንደማንሰጣቸው ነው፡፡ ይህ ማለት ግን እንዲያንበረክኩን እድል እንሰጣለን ማለት አይደለም፡፡ ለማነኛውም ምርጫ ቦርድ ህዳር 19 ቀን በፃፈልን ደብዳቤ መሰረት የሚጠበቅብን የጠቅላላ ጉባዔ ቁጥር በደንብ አካታችሁ አምጡ የሚል ሲሆን ይህን ደግሞ ታህሳስ 3 የተሰበሰበው ጠቅላላ ጉባዔ እንዲካተት አድርጎ ሪፖርቱ ታህሳስ 10 2007 ለቦርዱ ፅ/ቤት ገቢ ተደርጎዋል፡፡ ታህሳስ 10 ማለት ቦርድ ስብሰባ ያደረገበት ዕለት እና በሚዲያ የቀረበበት ቀን ስለሆነ ሪፖርቱን ከማየቱ በፊት ያሳለፈው ውሳኔ ነው ብለን በቅን ልቦና በመውሰድ በህዝቡ ዘንድ የፈጠሩት ብዥታ በሚያጠራ መልኩ የፈለጉት ሪፖርት በአንድነት በኩል የቀረበ መሆኑን በሚዲያ ይገልፃሉ ብለን አሁንም በቅንነት እንጠብቃልን፡፡
አንድነት ፓርቲ ላይ ምርጫ ቦርድ ከዚህም የከፋ ጫና ሊያደርስብን እንደሚችል መጠበቅ ትጥቃችንን ጠበቅ ለማድረግ እንደሚረዳን መገንዘብ አለብን፡፡ በቀጣይ በሚኖሩት ተደጋጋሚ ምርጫ ተኮር እንቅስቃሴዎች በቁጥር ብዙ የሚባሉ ለውጤት ሳይሆን ለተሳትፎ የሚገቡ ፓርቲዎች ይህን ጫና ለማድረግ አብረው መሰለፋቸውም የግድ ነው፡፡ ለለውጥ የተነሳው ህዝብ ግን ትኩረቱን ማን ላይ ማድረግ እንዳለበት ግን ጠንቅቶ ያውቃል፡፡ በቅርቡ በምርጫ ቦርድ በተሰጠው የሚዲያ መግለጫም አብዛኛው ሕዝብ ይህ ዘመቻ አንድነት ላይ ለምን በዛ? ብሎ ጠይቆዋል፡፡ መልሱም ግልፅ ነው፡፡ አንድነት ፓርቲ ቁርጥ አቋም ይዞዋል፣ በቀጣይ ምርጫ ሚሊዮኖች ተንቀሳቅሰው ድምፃቸውን ይስጣሉ፣ የሰጡትን ድምፅ ደግሞ ያስከብራሉ ብሎ ያምናል፡፡ አምሳ ሎሚ ለአንድ ሰው ሸክሙ ለአምሳ ሰው ጌጡ እንደሚባለው፣ አንድነት ፓርቲ እያንዳንዱ ዜጋ ነፃነቱን ለማስከበር ዘብ ከቆመ የሚሊዮኖች ድምፅ ይከበራል ብሎ በማመን የኢትዮጵያ ህዝብ ታሪክ እንዲሰራ ምቹ ሁኔታ እየፈጠረ ይገኛል፡፡
ቀኝ ኋላ ዙር ሊሉ የሚፈልጉትን በሙሉ ወደፊት በማለት ለማሸነፍ የስነ ልቦና ዝግጅት እናድርግ እላለሁ፡፡ ምርጫ የገባ ነው ምርጫ ቦርድን አምነን ሳይሆን የህዝብን ሀያልነት ተገንዝበን ስለሆነ ማሸነፋችን ሳይታልም የተፈታ ነው፡፡ መንገዱ ምንም ያህል ጎርባጣ ቢሆንም ለድል የተነሳን መንፈስ ማሸነፍ ይከብዳል፡፡ ይቻላል ብለን እንደጀመርነው ከግብ ለማድረስ ቀበቶዋችንን ጠበቅ ነው፡፡ ቀላል ነው፣ የመጀመሪያው ሰራ ለመራጭነት መመዝገብ ነው፡፡ ቀዳሚ ይሁኑ ካርዶን በእጆ ያስገቡ!!!
ቸር ይግጠመን!!!!


Saturday, December 20, 2014

ጀግኖቻችን እና የፍርድ ቤት ነፃነት!!!

ግርማ ሠይፉ ማሩ
girmaseifu32@yahoo.com; girmaseifu.blogspot,com
በቅርቡ የሚካሄደውን የ2007 ምርጫን  አስመልክቶ የፓርቲዎችን ዝግጅት ምን እንደሚመስል ለመረዳት ኢህአዴግ፣ አንድነት እና ኢዴፓ የወከሉ ሰዎች በፋና ሬዲዮ ባለፈው እሁድ ውይይት አድርገው ነበር፡፡ መኖሩ ትርጉም ስለአልነበረው ነው እንጂ ሌላም አንድ ፓርቲ ወክያለሁ ያለ ሰው እንደነበር ዘንግቼው አይደለም፡፡ የኢህአዴጉ ወኪል በመጨረሻ ላይ ያቀረቡትን ሃሳብ ሳደምጥ የኢህአዴግ ፓርቲ ወኪል ማንም ቢሆን ተመሳሳይ እንደሆነ መረዳት የምንችለው ነገር አንዳቸውም በተነገራቸው እንጂ በራሳቸው መርምረው ሊደርሱበት የሚፈልጉት ሀቅ ያለ አይመስለኝም፡፡ በፓርቲው ስብሰባ ከሚሰበካቸው ውጭ ዋነኛ የመረጃ ምንጫቸው የኢትዮጰያ ሬዲዮና ቴሌቪዥን ገፋ ሲል ደግሞ ፋና ናቸው፡፡ እንደዚህ ዓይነት መደምደሚያ ላይ እንድደርስ ያደረገኝ ነጥብ ደግሞ የአንድነት ምክትል ፕሬዝዳንት እና የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ ሆኖ ሲሰራ የነበረው አንዱዓም አራጌ እና ሌሎች የህሊና እሰረኞች ላይ የተፈረደውን የፍርድ ቤት ውሳኔ መቀበልና አለመቀበል ከፍርድ ቤት ነፃነትና ለፍርድ ቤት እውቅና ከመስጠት ጋር ማያያዛቸው ነው፡፡ በፍርድ ቤት ውሳኔ ባለመስማማት የምንይዘውን አቋም መረጃ የሌለው ነው ብለው የሚያቀርቡት ጉንጭ አልፋ  ክርክር እጅግ አስገራሚ ነው፡፡
ከዚህ ቀደም አንዱዓለም አራጌ ይፈታ በሚል አንድ ፅሁፍ ፅፌ ነበር አንዱዓለም የታሰረው በ “አሸባሪነት” ነው ለሚሉን መስሚያ የሌለን መሆኑን ብቻ አይደለም የታሰረው የኢህአዴግ ጉምቱ ባለስልጣናት ከእቅዳቸው በፊት ከስልጣን የሚነቀንቃቸው ሰላማዊ ታጋይ መሆኑን በመጠርጠራቸው ነው የሚል ነበር፡፡ ብዙዎች እንደሚስማሙት ደግሞ በምርጫ ሁለት ሺ ሁለት ክርክር ወቅት ተናዳፊ ተከራካሪ ሆኖ በመቅረቡ ነው፡፡ በብዙዎች ዘንድ አንዱዓለም ንቢቱን አስንቆ በስልጣን ሲናገሩ የነበሩትን በመረጃ አስደግፉ ሲያጋልጣቸው ቂም ይዘው እንደሆነ ይታመናል፡፡ ይህን እንድንገምት ያደረገን ደግሞ አንዱዓለም በተከሰሰበት ወንጀል ለዕድሜ ልክ እስር አይደለም ለምክር የሚገብዝ ጥፋት ማጥፋቱን የሚያስረዳ ማስረጃም አልቀረበበትም ምስክርም አልተሰማበትም፡፡ አዳፍኔ ምስክሮችም ቢሆኑ ከእስር ቤት ለመውጣት ቃል የሰጡ ቢሆንም በፍርድ ቤት ገብተው ግን አንዱዓለም ለሸብር ተግባር ወጣት ሲያደረጅ ነበር ብለው ሊመስክሩ አልቻሉም፡፡ የኢህአዴግ ሹሞች በቦታው አልነበሩም፤ እኛ ግን በቦታው ነበርን፡፡
ፍርድ ቤት ውሳኔ የሰጠበት መዝገብ በአሁኑ ወቅት ማንም ሰው ሊያገኘው እንደሚችል ግልፅ ነው፡፡ የኢህአዴግ አባላትና ሹማምንት ደግሞ ይህን መረጃ ለማግኘት ከማነኛችንም በላይ እድሉ አላቸው፡፡ እነዚህ የኢህአዴግ አባላትና ባለስልጣናት ይህን የምናቀርበውን ጩኽት ልክ መሆኑን ለማጣራት ለምን ይህን የፍርድ ቤት መዝገብ መርምረው አቋም አይዙም? የሚል ብርቱ ጥያቄ ማቅረብ እፈልጋለሁ፡፡ እነዚህ ሹሞች ከላይ እንደገለፅኩት በኢህአዴግ ስብሰባ ወቅት ከሚሰሙት ማብራሪያ እና በመንግሰት ሚዲያ ከሚሰሙት ውጭ ሌላ ነገር አንብበው ለመረዳት ዝግጁ አይደሉም፡፡ የኢህአዴግ ደጋፊዎች ቢሆኑም ከዚህ ጭፍን መስመር ውጭ አይደሉም፡፡ አንዱዓለም ይፈታ በሚል በፃፍኩት ፅሁፍ እንዲ ብዬ ነበር፤
“መደበቅ የሌለብኝ ዕውነት ግን ከአንዱዓለም ጋር ከምናደርገው የሠላማዊ ትግል ውይይት (አንዳንዴም ጭቅጭቅ የሚባል ቦታ ሊደርስ የሚችል) በተቃራኒ አንድ የሆነ ሠይጣን አሳስቶት - ይህ ሠይጣን ኢህአዴግ ሊሆን ይችላል፤ ማለትም የሠላማዊ መንገዱን ሁሉ እያጠበበ ያለ ከመሆኑ ጋር ተያይዞ - አንዱዓለም ተገዶ ሌላ አማራጭ ፍለጋ ሄዶ ይሆን በሚል የመረጃ ፍለጋ ጉጉቴ አልጨመረም ልላችሁ አልችልም፡፡”
ይህ የሚያሳየው አንዱዓለም ጓደኛ የትግል ጓዴ ቢሆንም ሊሳሳት ይችላል ብዬ መጠራጠሬ አልቀረም ነበር፡፡ ሟቹ ጠቅላይ ሚኒስትርም ክምር ማስረጃ አለ ብለውን ነበር፡፡ ፍርድ ቤት ከቀረበው ማስረጃ እና ከቀረቡት ምስክሮች ግን አንድም ውሃ የሚቋጥር ነገር ስናጣ፤ ክምር ቀርቶ አንድ ገፅ ወረቀት ሲጠፋ ፍርድ ቤት ወስኖዋል ብለን ከህሊናችን ጋር ተጋጭተን እንደ ኢህአዴጎቹ አንዱዓለም አሽባሪ ነው እንድንል መፈለጋቸው አስገራሚ ብቻ ሳይሆን እነዚህ የኢህአዴግ ሹሞች እንዴት አድርገው እንደሚሰሯቸው መረዳት አስቸጋሪ ነው፡፡
ይህን ሁሉ በድጋሚ እንድል ያስባለኝ ኢህአዴግን ወክሎ የቀረበው የውይየት ተሳታፊ “በእስር ቤት የሚገኙትን አመራሮችና አባሎች ጅግኖቻችን ማለታችሁ አሁንም በሁለት ሺ ሰባት ምርጫ ህጋዊና ህገወጥ መስመር እያጣቀሳችሁ ለመሄድ ያላችሁን ዝግጅት የሚያሳይ ነው፡፡” የሚል አስተያየት ሲሰጡ መስማቴ ነው፡፡ የሁለት ሺ ሰባት ምርጫ ሰላማዊ ሊሆን የሚችለው ሀቅን በመደፍጠጥ እና ፍርድ ገምድል ውሳኔን አሜን ብሎ በመቀበል ሳይሆን ኢህአዴግ በስልጣኑ የመጡበትን ያለምንም ይልኝታ እድሜ ልክም ቢሆን እስር ቤት ለመጎር ደንታ የሌለው መሆኑን በማጋለጥ ነው፡፡ ይህንን ሀቅ ለመመርመር ድፍረት ያገኙ የኢህአዴግ አባላትም ሆኖ ሹሞች በዚህ አይነት ስርዓት ማንም ተጠቃሚ እንደማይሆን ለመረዳት አይቸገሩም፡፡ ይህን ስርዓት በመለወጥ የሚገኘው ትንሳኤ ማንም በግፍና በፍርደ ገምድል ውሳኔ ሰጋት ላይ እንዳይወድቅ የሚያድርግ ነው፡፡ የዚህ ደግሞ ትሩፋት ለኢህአዴግ አባላትም የሚሆን ነው፡፡
የኢህአደግ ሹሞች በዚህ ዓይነት ውይይት ወቅት ከፓርቲያቸው በተቃራኒ መስመር ይቁሙ የምል የዋሃ አይደለሁም፡፡ ይልቁንም እነዚህን ነጥቦች መከራከሪያ ሆኖ ቢመጣ እንኳን ችላ ብለው በማለፍ ከትዝብት ሊተርፉ ይቻላሉ የሚል እምነት ስለ አለኝ ነው፡፡ በሀገራችን ያሉትን ተቋሞች የምናከብራቸው በህንፃቸው ግዝፈት ወይም በቀጠሩት የስው ሀይል ብዛት ሊሆን አይችልም፡፡ ፍርድ ቤቶች ሊከበሩ የሚችሉት በሚያሰፍኑት ፍትህ ነው፡፡ ዜጎች መብቴ ፍርድ ቤት ሄጁ አስከብራለሁ የሚል ደረጃ ሲደርሱ ነው፡፡ በሀገራችን ያለው የፍትህ ስርዓት ፖለቲካ ነክ በሆኑ ጉዳዮች ብቻ ሳይሆን በቤተስብ ውርስ ጉዳይ እንኳን አፋጣኝ ፍትህ የሚሰጥ አይደለም፡፡ በፍትሃብሔር ጉዳይም ቢሆን በዓለም አቀፍ ደረጃ የሚሰጠው ደረጃ የወረደ ነው፡፡ ይህ እንዲሻሻል ማሳሰብ እና መታገል ፍርድ ቤቶቸን እውቅና እንደመንፈግ መቁጠር ተገቢ ነው ለማለት አይቻለም፡፡ በተመሳሳይ ፍርድ ገምድል ውሳኔዎችን እንድንቀበል መገደድም የለብንም፤ ብንገደድም ሊሳካ የሚችል አይደለም፡፡ ለዚህ ነው የህሊና እስረኞችን ጅግኖቻችን የምንለው፡፡
እኔም እላለሁ የአንድነት ፓርቲ አባላት ላይ እየተለጠፈ ያለው “የአሸባሪነት” ታፔላ በፍጹም ተቀባይነት እንደሌለው ደግመን ደጋግመን ማሳሰብ እንፈልጋልን፤ መፍተሔውም ፖለቲካዊ ውሳኔ በመስጠት መፍታት እና ለሰላማዊ ትግል የፖለቲካ ምዕዳሩን ማስፋት ነው፡፡ የሰላማዊ ትግል መድረኩ በጠበበ ቁጥር ደግሞ ዜጎች አማራጭ የትግል ስልት መፈለጋቸው የግድ ነው፡፡ በጠረጴዛ ላይ ያለው ሌላኛው አማራጭ ሀገርን ህዝብን ከመጉዳት ውጭ ገዢዎችንም ሊጠቅማቸው የሚችልበት አንድም መንገድ አይታይም፡፡ ሁሉም አሽናፊ ሆኖ የሚወጣበት ስርዓት መዘርጋት ለፍትህ ስርዓቱም ትንሳኤ ስለሚሆን ጅግኖቻችንን በመፍታት ለፍትህ ስርዓቱ ትንሳኤ በጋራ እንድንቆም መንግሰት ኃላፊነት አለበት፡፡
ምርጫ ሁለት ሺ ሰባት ለለውጥ!!!
ቸር ይግጠመን



Sunday, December 14, 2014

ህገ መንግሰቱን የሚንደው ማን ነው?




ግርማ ሠይፉ ማሩ
girmaseifu32@yahoo.com; girmaseifu.blogspot.com
በአገባደድነው ሳምንት መጀመሪያ ህዳር 29 ቀን በከፍተኛ የገንዘብ ወጪ ብቻ ሳይሆን በከፍተኛ የፕሮፓጋንዳ ዘመቻ የ “ብሔር ፣ብሔረሰቦች እና ህዝቦች”  ቀን ተክብሮ ውሎዋል፡፡ “ብሔር፣ ብሔረሰቦች፣ ህዝቦች” የሚሉት ሶሰት ቃላቶች ቢሆኑም በህገ መንግስት ውስጥ አንድ ትርጉም የተሰጣቸው ቢሆንም ባለቤቶች ነን የሚሉትም ቢሆኑ በውል ያልተረዷቸው ተምኔታዊ ነገሮች ናቸው፡፡ ወጣም ወረደ ግን እነዚህ ቃላቶች በኢትዮጵያ ፖለቲካ ውስጥ ጉልዕ ቦታ ያላቸው እንዲሆኑ ተደርገዋል፡፡ እኛም እነዚህን ቃላቶች በኢትዮጵያ ፖለቲካ ጉልዕ ቦታ የያዞ መሆናቸውን አምነን ተቀብለናል፡፡ ይህ ማለት ግን ገብቶናል ማለት አይደለም፡፡ ይህ በየክልሉ በዙር የሚከበረው ባህል ታስቦበት ህገ መንግሰት ከጸደቀበት እለት ጋር የተገናኘ ስለሆነ እለቱን ከህገ መንግሰት ጋር የተያያዙ ጉዳዮች የሚነሱበት ብናደርገው ክፋት የለውም፡፡ ስለዚህ ባለፉት 20 ዓመታት ይህ ህገ መንግሰት ምን ሰጠን ምንስ ነፈገን ብለን መጠየቅ እና የተወሰኑ ማሳያዎች ማቅረብ ተገቢነት ያለው ይመስለኛል፡፡
ጠበቃ ተማም አባቡልጉ ባለፈው ሳምንት ዕትም በሰጠው ቃለ ምልልስ ላይ እንዳስቀመጠው ህገ መንግሰታችን ተገቢ ባልሆነ ሁኔታ የህግ ግዴታ ለማይጣልባቸው “ብሔር፣ ብሔረሰቦችና ህዝቦች” ለሚባል ሃሳባዊ ስብስብ ተሰጥቶ ህገ መንግሰቱ የናንተ ነው ተብለዋል፡፡ በዚህም የተነሳ ህገመንግሰቱ የማንም እንዳይሆን ተደርጎዋል ብሎናል፡፡ ይህ የሆነው ግን በስህተት የሚመስለው ካለ ተሳስቶዋል፡፡ የማንም ያልሆነን ማለትም ባለቤት የሌለወን ነገር በአደራ ለመጠበቅ በሚል ለረዥም ጊዜ በስልጣን ለመቆየት የተደረገ ደባ እንደሆነ መረዳት ተገቢ ይመስለኛል፡፡ የዚህን ሴራ ማሳያ የሚሆን ምሳሌ ከዚህ በታች ማቅረብ ጉዳዩን ግልፅ ያደርገዋል፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ በፕሬዝዳንትነት የጀመሩትን በታሪክ አጋጣሚ የተገኘ ሀገር የመምራት ተልዕኮ ወደ ጠቅላይ ሚኒስትርነት ሲያወርዱት በፕሬዘደንታዊ ስርዓት (በቀጥታ የህዝብ ምርጫ ስልጣን የሚይዝ) ፕሬዝዳንት መሆን ጠልተው አይደለም፡፡ በዛን ጊዜ በነበረው ነባራዊ ሁኔታ አቶ መለስ ዜናዊን ማንም ሀገር ወዳድ ተነስቶ ዕጩ ሆኖ ቢቀርብ ሊያሸንፋቻው እንደሚችል ስለሚያውቁ ከዚህ የተለየ አደረጃጀት መከተል ነበረባቸው፡፡ ይህም በድርጅታዊ አሰራር በሚስጥር ጠቅላይ ሚኒስትር መሆን የሚያሰችል ዘዴ መከተል ነው፡፡ ይህ ህውሃት እንደ ቡድን አቶ መለስ ዜናዊ በግል ያለባቸውን ያለመመረጥ ስጋት ካነሱት ነጥቦች አንዱ በ1987 አይደለም ዛሬ ከሃያ ዓመት በኋላ ኢትዮጵያዊያን የባህር በር አጥተው መታነቃቸውን ለመዘንጋት አልተቻላቸውም፡፡
ከዓለም የባህር በር ከሌላቸው ሀገሮች በህዝብ ብዛት አንደኛ መሆናችን ብቻ ሳይሆን በቅርብ ርቀት በባሕር በር ላይ ተገኝተን የበይ ተመልካች መሆናችን ታሪክ ይቅር የሚለው ስህተት አይደለም፡፡ የዚህ ታሪካዊ ስህተት መሃንዲስ ደግሞ ሟቹ ጠቅላይ ሚኒስትር ናቸው፡፡ ሌላው የቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትር የኢትዮ-ኤርትራ የወንድማማቾች ጦርነት ተከትሎ ህዝቡ ለባንዲራ ያሳየውን ፍቅር ተመልክተው የባንዲራ ቀን እንዲከበር አረንጓዴ መብራት ቢያሳዩም፤ እራሳቸው በስታዲየም ተገኝተው “ጨርቅ” ነው ብለው ያጣጣሉትን ባንዲራ በክብር ቢሰቅሉትም ህዝቡ ባንዲራ “ጨርቅ” ነው የሚለውን የአፍ ወለምታ ሊዘነጋው አልተቻለውም፡፡ በእነዚ እና ሌሎች ብዙ ምክንያቶች የኢትዮጵያ ህገ መንግሰት ዜጎች በቀጥታ የሚመራቸውን መሪ እንዳይመርጡ ያደረገ ህገ መንግስት ነው፡፡
ባንዲራን በሚመለከት የኢትዮጵያ ህገ መንግሰት በግልፅ የኢትዮጵያ ባንዲራ አረንጓዴ፣ ቢጫና ቀይ ነው ብሎ ደንግጓል፡፡ በተጨማሪም አርማ እንደሚኖረው ይደነግጋል፡፡ አርማው ላይ ካልተስማማን በሚያስማማን የባንዲራው ይዘት ላይ አብረን መቆም እንችላለን፡፡ በግሌ ከዚህ ቀደም ከነበሩት አርማዎች የአሁኑ የተሻለ ነው የሚል እምነት ቢኖረኝም ሁሉም ዜጋ ይህ አርማ የሌለበት ባንዲራ መያዝ አለበት የሚለውን ህገ ወጥ የህግ ድንጋጌ ግን ለመቀበል እቸገራለሁ፡፡ መንግሰት በኤምባሴዎች፣ በመንግሰት ተቋማት አርማዬ ያለውን የማድረግ ግዴታ ቢጥል ግድ የለኝም፡፡ በግል አርማ ካላደረጋችሁ የሚል አስገዳጅ ህግ ማውጣት ግን መንግሰት ጉልበተኛነቱን ለማሳየት ካልሆነ በስተቀር ይህ አርማ ከልብ የሚፃፍ እና በፍቅር ሊወደቅለት የሚችል ሊያደርገው አይችልም፡፡
በሌላ በኩል የኢትዮጵያ ህገ መንግሰት ከማነኛውም ጊዜ እና ምን አልባትም በፅሁፍ ደረጃ ከማንም ሀገር በተለየ የሰብዓዊ መብት ድንጋጌዎች ህገ መንግስታዊ ዕውቅና የሰጠ ነው ቢባል ማገነን አይሆንም፡፡ ምን ያደርጋል እነዚህ ድንጋጌዎች በወረቀት ላይ የቀሩ ናቸው፡፡ በደም የተፃፈ የሚባለው ህገ መንግሰት በቾክ እንደተፃፈ መቁጠር የተሳናቸው የመንግስት ሹሞች እንደ አፈተታቸው ሲደፈጥጡት ይታያሉ፡፡ ዜጎችን በአደባባይ ከመደብደብ ጀምሮ በዓለም ላይ የቀረ ቶርች የሚደረግባት ሀገር ኢትዮጵያ ነች፡፡ በህገ መንግሰት እውቅና ያገኘን የሰብዓዊ መብት ድንጋጌዎች በ “ፀረ ሽብር ህግ” ተደምስሶዋል፡፡ የሰው ልጅ ክቡርነት ዋጋ አጥቶ በህዝብ ስም ስልጣን ለማቆየት ምንም ዓይነት እርምጃ የሚወሰድባት ሀገር ሆናለች፡፡ ይህ ደግሞ ባለበቤት የሌለው ህገ መንግሰት ያመጣው ትሩፋት ነው፡፡ የህገ መንግሰት ባለቤት የተባሉት “ብሔር፣ ብሔረሰቦችና ህዝቦች” የህግ ተጠያቂነት የሌለባቸው ብቻ ሳይሆኑ ሰብዓዊነትም የሌላቸው ስለሆኑ መብታችን ተነካ ሊሉ አይችሉም፡፡ እስር ቤት አይገቡም፡፡ የሚታሰረው ሰው ነው፤ ሰብዓዊ መብቱ የሚጣሰውም ሰው ነው፡፡ ዜጋው የህገ መንግስት ባለቤት ለመሆን በቡድን ውስጥ መገኘት የግድ ይለዋል፡፡ እኔ ለምሳሌ እነዚህ ቡድኖች ውስጥ ለመገኘት ፍላጎትም ምኞትም ስለሌለኝ ይህ ህገ መንግሰት የእኔ ነው ብዬ በግድ የራሴ ለማድረግ ከመታገል ውጭ ሌላ አማራጭ የለኝም፡፡
ገዢው ፓርቲ በቡድናዊ አስተሳሰቡ በመወጠሩ የእኔ ዓይነት አመለካከት ያላቸውን ሰዎች ህገ መንግሰቱ የእኛ እንዲሆን የምናደርገውን ጥረት ህገ መንግሰት መናድ ነው ብሎ የቡድን ጠብ ለማስነሳት ይታትራል፡፡ በዚህ ዓይነት የቡድን አስተሳሰብ ውስጥ ለሚገኙ የኢህአዴግ አባላትም ሆነ አጋሮች ማረጋገጥ የምፈልገው አንድ ቁም ነገር አለ፡፡ ይህም ቁም ነገር፤
“ይህ ህገ መንግሰት ከነ እንከኑም ቢሆን እንዲከበር የምንፈልግ መሆኑን ብቻ ሳይሆን   ለማሻሻል የተቀመጡት ድንጋጌዎች ምንም ዓይነት አስቸጋሪ ቢሆኑም በዚሁ መስመር ብቻ እንዲሰተካከል እንደምንታገል ማወቅ አለባቸው፡፡”
ይህ ማለት ግን በህገ መንግሰቱ በተቀመጠው መሰረት እንዳይሻሻል ሊሆን የሚችልበት ሁኔታ የለም ማለት አይደለም፡፡ ለዚህም ዋነኛው ተጠያቂ ገዢው ፓርቲና መንግሰት ብቻ ናቸው የሚሆኑት፡፡ ገዢው ፓርቲ እና መንግሰት በዚህች ሀገር ሰላማዊ የስልጣን ሽግግር ሊኖር የሚችልበት እድል ዘግተው በነውጥ ወይም በጠመንጃ ለውጥ ከመጣ ይህ ህገ መንግሰት ከዚህ ቀደም እንደነበሩት ህገ መንግሰቶች ታሪክ ሊሆን ይቸላል፡፡ ይህ እንዲሆን ፍላጎት የሌለን ሰዎች ህገ መንግስቱ ያሉበትን ችግሮች በህግ ስርዓት ብቻ እንዲሻሻል እንፈልጋለን፡፡ ይህ ባልተሟለበት ሁኔታ አንድ ፊደል በፍሉድ ሳይጠፋ ህገ መንግሰቱ እንዲከበር እንፈልጋለን፡፡
ከዚህ በተቃራኒው ግን መንግሰት ህገ መንግሰቱ እንዲናድ እና ወደ መቃብር እንዲወርድ ተግቶ እየሰራ ነው፡፡ ይህን ስንታዘብ  ህገ መንግሰቱ እንዲናድ የሚሰሩት ተቃዋሚ ፓርቲዎች ናቸው ማለት አይቻልም፡፡ ተቃዋሚ ፓርቲዎች በአሁኑ ሰዓት እየጠየቁ ያሉት በህገ መንግስት በግልፅ የተቀመጡት ሰብዓዊና ዲሞክራሲ መብቶች ይከበሩ ነው፡፡ መብቱ የተከበረለት ዜጋ ለልማት ግብዓት እንጂ ዕዳ ሊሆን አይችልም፡፡ በቁስ በሚገለፁ እድገቶች መብታችንን አሳልፈን አንሰጥም ማለት ህገ መንግሰቱን ማስከበር እንጂ መናድ ሊሆን አይችልም፡፡ ዜጎች ህገ መንግሰታዊ መብታችንን ለማስከበር ነቅተን በምርጫ እንሳተፍ የመዝጊያ መልዕክቴ ነው፡፡
ቸር ይግጠመን




Saturday, December 6, 2014

የምርጫ ስትራቴጂ እንዴት ይሁን?



የምርጫ ስትራቴጂ እንዴት ይሁን?
ግርማ ሠይፉ ማሩ
girmaseifu32@yahoo.com; www.girmaseifu.blogspot.com
በስታራቴጂክ ዕቅድ ዝግጅት ወቅት ከተለመዱት የአካባቢ ሁኔታ ትንታና መሳሪያዎች አንዱ የውጭ እና የውስጥ ሁኔታን የምተነትንበት በእንግሊዘኛ ስዎት/ (SWOT/SLOT Analysis) የሚባለው ነው፡፡ ወደ ውስጣችን ስንመለከት አንዱ ጥንካሪያችን ምንድነው የሚለው ጥያቄ መመለስ ሲሆን ሌላኛው ደግሞ ያሉብን ድክመቶች ወይም ውስኑነቶች ምንድናቸው የሚለው ነው፡፡ ወደ ውጭ ስንመለከት ደግሞ ምን ምቹ ሁኔታ አለ አንዱ ሲሆን ሌላኛው ደግሞ ተግዳሮቶቹ ምንድናቸው ብለን በዝርዝር ማየት ይኖርብናል፡፡
አንድ ስትራቴጂክ ዕቅድ የውስጥና የውጭ ትንተና ሰርቶ የሚከተሉትን ማድረግ የግድ ይለዋል፤
·         በውስጣዊ ጥንካሬ ላይ ያተኮሩ እና በውጭ ያሉትን ምቹ ሁኔታዎችን ለመጠቀም ላይ ያተኮረ፤
·          በውጭ ያሉ መልካም አጋጣሚዎች ለመጠቀም  እና የውስጥ ድከመቶችን በማስወገድ ላይ ያተኮረ፤
·         በውስጥ ጥንካሬዎችን በመጠቀም የውጭ ተግዳሮቶችን በማሸነፍ ላይ ያተኮረ፤ አና
·         የውስጥ ድክመቶች እና የውጭ ተግዳሮቶች የሚያደርሱትን ጉዳቶች በመቀነስ ላይ ያተኮሩ
ስልቶችን መንደፍ የግድ ይላል፡፡ አነዚህን በዝርዝር ከሰለማዊና ህጋዊ ትግል በተለይም ከምርጫ ስትራቴጂ ዕቅድ ዝግጅት ጋር እንዴት ማየት እንዳለብን መረዳት ተገቢ ነው፡፡ እነዚህን ስልቶች አንድ አንድ ምሳሌ እያነሳን ማየት እስከ ዛሬ የሄድንበትን መንገድ ከመፈተሸ በዘለለ ወደፊት እንዴት መሄድ እንዳለብን የመወያያ ርዕስ ይከፍታል የሚል እምነት አለኝ፡፡ ከላይ የተቀመጡትን ስልቶች የተገኙት በዚህ መልክ ከተቀመጠ ሰንጠረዥ ውስጥ ነው፡፡
                                             
ውስጣዊ ሁኔታዎች
ውጫዊ

ሁኔታዎች

ጥንካሬ
ድክመት/ውሱንነት
መልካም አጋጣሚዎች/
ዕድሎች

በውስጣዊ ጥንካሬ ላይ ያተኮሩ እና በውጭ ያሉትን ምቹ ሁኔታዎችን ለመጠቀም ላይ ያተኮረ


በውጭ ያሉ መልካም አጋጣሚዎች ለመጠቀም  እና የውስጥ ድከመቶችን በማስወገድ ላይ ያተኮረ



ተግዳሮቶች

በውስጥ ጥንካሬዎችን በመጠቀም የውጭ ተግዳሮቶችን በማሸነፍ ላይ ያተኮረ

የውስጥ ድክመቶች እና የውጭ ተግዳሮቶች የሚያደርሱትን ጉዳቶች በመቀነስ ላይ ያተኮሩ

ከላይ የተዘረዘሩትን ስልቶች ከታች ወደ ላይ እንመልከታው፡፡
እሰከ አሁን ባለው ነባራዊ ሁኔታ በተቃዋሚ ጎራ የምንገኝ አካላት ትኩረት ሰጥተን ስንሰራ የነበረው የውስጥ ድክመቶቻችንን እና የውጭ ተግዳሮቶች የሚያደርሱብንን ጫናዎቸና ጉዳቶች በማጉላት ላይ ነበር፡፡ ከውስጥም ሆነ ከውጭ ያሉትን ችግሮች ማወቅ ተገቢ ቢሆንም እነርሱም ደጋግሞ ማንሳት መፍትሔ ሊያመጣ እንደማይችል አልተረዳንም፡፡ በስትራቴጅክ እቅድ ዝግጅት እነዚህ ጉዳታ የሚያደርሱ ውስጣዊና ውጫዊ ሁኔታዎች እንዳሉ ተረድቶ እነርሱን ለመቀነስ የምነወስዳቸው እርምጃዎች ቅድሚያ ማግኘት ይኖርባቸዋል፡፡ በተለይ ምንም ማድረግ የማንችላቸው ለውጫዊ ሁኔታዎች ትኩረት ስጥቶ እነርሱን ማግዘፍ ከጥቅሙ ጉዳቱ ነው የሚበልጠው፡፡ ከዚህ አንፃር ከምርጫ ጋር የተገናኙ ውስጣዊ ችግሮች ከምንላቸው አንዱ ለምርጫ ለመወዳደር ያለብን የፋይናንስ ችግር ሲሆን ይህን ችግር ማሰቀረት ባይቻል እንኳን ለመቀነስ ስልት ነድፈን ከመንቀሳቀስ ይልቅ የገዢው ፓርቲ ድጋፍን እንደ አማራጭ እንወስደዋለን፡፡ ገዢው ፓርቲ ከዚህ አኳይ ሊረዳን ሳይሆን እንዴት ችግራችን ተባብሶ እንድንወድቅ እንደሚሰራ አንረዳም፡፡ ገዢው ፓርቲ የሚያደርሰውን ጫና ከመቀነሻ መንገዶች አንዱ ከመንግሰት የሚጠበቅን የገንዘብ ድጋፍ መብትም ቢሆን ትኩረት አለመስጠት ነው፡፡
ይልቁንም ከመንግሰት የሚመጣን የዚህን ዓይነት ተግዳሮት ትንሸም ብትሆን ካለችን የውስጥ ጥንካሬ በመጠቀም እነዚህን ተግዳሮቶች ማሸነፍ ይኖርብናል፡፡ ከፋይናንስ አንፃር ባነሳነው ምሳሌ ብንቀጥል ተቃዋሚ ፓርቲ አባላትና ደጋፊዎች አምሰት መቶ አርባ ሰባት ምርጫ ክልል ለማሸነፍ የሚያስችል የፋይናንሲንግ ሰትራቴጂ ልንጠቀም እንችላለን፡፡ ይህም እያንዳንዱን ዕጩ ሰፖንሰር የሚያደርግ አንድ ደጋፊ መመልመል ሲሆን፤ ድጋፉ ለአንድ ሰው ይበዛል ከተባለ ለአስር ማካፈል ይቻላል፡፡ አንድ ዕጩ አሸናፊ ሆኖ እንዲወጣ አስር ደጋፊዎች ሰፖንሰር ሊያደርጉት ይችላሉ፡፡ አንድ ፓርቲ አምስት ሺ ደጋፊዎች ያስፈልጉታል ማለት ነው፡፡ ከዚህ በተጓዳኝ ተቃዋሚ ፓርቲዎች ካላቸው የውስጥ ጥንካሬ አንዱ ገንዘብን በቁጠባና መጠቀም፣ ይልቁንም በነፃ የሚያገለግሉ ሰፍር ቁጥር የሌላቸው ወጣቶች መኖራቸው ትልቅ ውስጣዊ ጥንካሬ ነው፡፡ ይህንን አጠንክሮ መሄድ ያለብንን የፋይናንስ ችግረ ለመፍታት ይረዳናል፡፡
በአሁኑ ሰዓት ከተቃዋሚ ፓርቲዎች ውጭ ያሉ አመቺ ሁኔታዎች እጅግ ብዙ ናቸው፡፡ ለምሳሌ መንግሰት በሚወስዳቸው የተለያዩ የተሳሳቱ ፖሊሲዎች እና አፈፃፀም ዙሪያ ያሉትን ችግሮች በመገንዘብ ህዝቡ ተቃዋሚ ፓርቲዎችን ለመደገፍ ዝግጅቱን እያሳየ ይገኛል፡፡ ይህንን የህዝብ ዝግጁነት ወደተግባር ለመለውጥ በውስጥ ያሉብንን ወደ ህዝብ የመቅረብ ችግር አሰወግደን ለውጤት ማብቃት ይኖርብናል፡፡ እኛ ወደ ህዝቡ በመቅረብ ያሉንን አማራጮች ካላቀረብን እና ከህዝቡ ምን እንደምንጠብቅ ካላስረዳነው ፓርቲዎች ከህዝቡ ጋር ሳይገናኙ ይቀራሉ፡፡ ገዢው ፓርቲ በአንድም በሌላም የሚሰራቸው ስህተቶች ለተቃዋሚዎች የተዘጋጁ ዕድሎች ሲሆኑ ተቃዋሚዎች ደግሞ ወደ ህዝቡ ለመቅረብ ያለባቸውን ችግር በማሰወገድ ለድል የሚያበቃ ሰልት መንደፍ የግድ ይላቸዋል፡፡ እዚህ ነጥብ ላይ ሊነሳ የሚችለው ወደ ህዝብ መቅረቢያውን መንገድ ኢህአዴግ ዘግቶታል የሚለው ነው፡፡ ትክክል ነው ተቃዋሚ ፓርቲ አባላት ህዝቡን ማግኘት ያለብን ሰብሰበን በአዳራሽና በአደባባይ ብቻ ነው ከሚለው አቋም ወጥትን የአንድ ለአንድ የሰው ለሰው ግንኙነት በየሰፈራችን መጀመር ይኖርብናል፡፡ ማህበራዊ ሚዲያዎች እንደተጠበቁ ሆነው ማለት ነው፡፡
ዋነኛውና አውራ/ግራንድ የሚባለው ስትራቴጅ ግን መሆን ያለበት ጥንካሬዎቻችን ላይ መሰረት ማድረግና በውጭ ያሉ ምቹ ሁኔታዎችን አሟጦ መጠቀሙ ላይ ነው፡፡ ላለፉት 23 ዓመታት ችግሮችን እና ተግዳሮቶችን ከበቂ በላይ ተናግረናል እነርሱ የሚያደርሱትን ጉዳት ለመቀነስ ከመስራት ይልቅ መኖራቸው እንዲታወቅ ጩኽናል፡፡ አሁን ጊዚው መለወጥ አለበት ያሉትን እድሎች ለመጠቀም ቆርጦ መነሳት መሆን ይኖርበታል፡፡ ምንም ትንሽ ቢሆኑ በውሰጣችን የሚገኙትን ጥንካሬዎች መፈተሸ እና ዕድሎችን የምንጠቀምበት እድል ማድረግ ይኖርብናል፡፡ ለምሳሌ አሁን በሀገራችን ያሉት ወጣቶች ከሞላ ጎደል ፊደል የቆጠሩ ናቸው እነዚህ ወጣቶች በእውቀት ላይ የተመሰረተ አማራጭ ከቀረበላቸው ያለምንም ፍርሃት በመራጭነት ለመሳተፍ አያቅማሙም፡፡ ይህ ትልቅ ዕድል ነው፡፡ በተቃዋሚ በኩል የበለጠ የሰራ እድል መፍጠር የሚያስችሉ የፖሊሲ አማራጮች ወጣቶችን ከመንግሰት ጥገኝነት የሚያላቅቅ የመኖሪያ ቤት ፖሊሲ፣ ወጣቶችን የመሬት ባለቤት ሊያድርግ የሚችል የመሬት ፖሊሲዎች እንዳሉን ግልፅ ነው፡፡ ይህ ወጣቱን ከፍተኛ የምርጫ ሀይል ሊያደርግ የሚችል በውጭ ያለ ዕድል እና በፓርቲዎች ውስጥ ያለ ጥንካሬ ነው፡፡
ሌላው ለምሳሌ በከተማ ውስጥ ያለው ከፍተኛ የመኖሪያ ቤት ችግር ለመፍታት የሚችል አማራጭ ፖሊሲ ብቻ ሳይሆን አሁን በተገነቡ ኮንዶሚኒየም ቤት አግኝተው የሚኖሩ ዜጎች የገጠሩን ህዝብ በመሬት እንደያዘው ሁሉ የከተሜውን የኮንዶሚኒየም ጠርንፎታል፡፡ የኮንዶሚንየትም ቤቱን ለአምስት ዓመት እንዳይሽጥ፤ እንዳይለውጥ፤ በባንክ እንዳያሲዝ የሚያደርግ ፖሊሲ አለው፡፡ ይህ በእርግጠኝነት የአንድነት ዓይነት ፓርቲ ስልጣን ቢይዝ በወራት ውስጥ ቀይሮ ሁሉንም የቤቱ ባለቤት የሚያደርግ ነው፡፡ የዚህ ዓይነት የሚታይና የሚጨበጥ እርምጃዎችን የሚያሳዩ እንቅስቃሴዎች ማድረግ ይኖርብናል፡፡ አንድነት ከዩኒቨርሲቲ ስትመረቁ ኮብል ሰቶን /ድንጋይ ፈለጣ/ ትገባላችሁ አይልም፡፡ ድንጋይ ለመፍለጥ አራት ዓመት ዩኒቨርሲቲ መቆየት አያስፈልግም፡፡ እንደ አማራጭ የስራ መስክ ሆኖ ለሌሎች ይቆያል፡፡ የተማሩ ዜጎች ስራ እንዲይዙ ምቹ ሁኔታ የሚፈጥሩ የግል ባለሀብቶች ግልፅ በሆነ አስራር እንዲሰፋፉ ድጋፍ ማድረግ ነው፡፡ ሀገር ማለት ህዝብ ነው ስንል ዜጎች ለዜጎች የስራ እድል የሚፈጥሩበት ማለታችን ጭምር ነው፡፡
ለዛሬ በዚሁ ይብቃኝ!!!!! ቸር ይግጠመን!!!!



Sunday, November 30, 2014

ምርጫ መሳተፍ በመርዕ ላይ የተመሰረተ ውሳኔ ወይስ ኢህአዴግን ማጀብ?

 ሰዎች በማንኛውም መንገድ ሸብረክ ሸብረክ የሚሉ ከሆነ መርህ አልባ መሆናቸውን ከማሳየት ውጭ ሌላ ምንም ሊሆን አይችልም፡፡ ባለፈው ሳምነት ፍኖተ ነፃነት ላይ ወጣቱ ፀሃፊ ኢዮኤል ፍስሃ ዳምጤ ለምን እንደምንፈራ ቁልጭ አድርጎ አሳይቶን ነበር፡፡ የገዢዎቻችን በትር የበረታብን በእነርሱ ጥንካሬ ሳይሆን ከፍርሃት በመጣ ዝምታችን እንደሆነ አስምሮበታል፡፡ መፍትሔውም ከፍርሃት መላቀቅና ዝምታውን ማፍረስ ነው፡፡ በዛሬው ፅሁፌ ማንሳት የፈለኩት ደግሞ ለምን ሸብረክ ሸብረክ እንደምንል ነው፡፡
ለምንድነው ኮሽ ሲል ደንግጠን ከቆምንበት “መርዕ” ከምንለው አስተሳሰብ የምንሸራተት? እንዲህ ከሆነ ቀድሞውንም መርዕ አልነበረንም ማለት ነው፡፡ መርዕ ብለን የምንይዘው አሰተሳሰብ በእኔ እምነት ለምናደርገው እንቅስቃሴ የማዕዘን ድንጋይ መሆን አለበት፡፡ ከዚህ መርዕ ሸርተት ስንል ቀጥሎ የምናገኝው ሌላ የተሻለ ማዕዘን የሚሆን ድንጋይ ሳይሆን ድጥ ወይመ ማጥ ነው የሚሆነው፡፡ ብዙዎች መርዕ የሚመስላቸው በአቋራጭ የሚፈልጉትን ግብ የሚያሳካ አጭር መንገድ አድርገው ይወስዱታል፡፡ ይህ አቋራጭ መንገድ ግን ብዙን ጊዜ ወደ ሌላ ውጥንቅጥ ከመውሰድ አልፎ ለስኬት ሲያበቃ አይታይም፡፡
ግልፅ ያልሆነ የህይወት ግብ ያለን ሰዎች የምንሄድበትን ስለማናውቅ ሌሎች በሄዱበት ተከትለን እንነጉዳለን፣ ሌሎች ግባቸውን ሲያሳኩ እኛ የበይ ተመልካች መሆናችን አይቀርም፡፡ ግባችን ግልፅ ያለመሆኑ መድረሻችንን ብቻ ሳይሆን መነሻችንንም ስሚያዛባው ከየት ተነስተን የት እንደምንደርስ፣ እንዴት እንደምንደርስ እንዳናውቅ ያደርገናል፡፡ መርዕ ማለት አሁን ካለንብት ቦታ ተነስተን ወደምንፈልገው ቦታ ለመድረስ የምንጓዝበት ፍኖተ ካርታ ነው፡፡ ይህ ደግሞ በአሰተሳሰብ ብቻ ሳይሆን በተግባርም ልክ መሆን ያለበት ነው፡፡ አንድ አንድ ሰዎች የምንፈልገውን ግብ ለማሳካት ማነኛውንም መንገድ መጠቀም ችግር የለውም ይላሉ፡፡ ይህ የትም ፍጪው ዱቄቱን አምጭው /the end justify the means/ የሚባለው ዓይነት መሆኑ ሲሆን፡፡ ከዚህ በተቃራኒው ደግሞ ሌሎች የምንሄድበት መንገድ እንደ ወጤቱ ሁሉ መርዕ ላይ መመስረት አለበት የሚሉ ናቸው /The means is equally important as the end/:: በግሌ የማምነውም የምከተለውም የኋለኛውን አማራጭ ነው፡፡ የትም ፍጪው ዱቄቱን አምጭው የስግብግቦች መንገድ ነው ብዬ በፅኑ ስለማምን፡፡
ሰሞነኛ ወደ ሆነው የምርጫ አጀንዳ እና በመርዕ ላይ የተመሰረተው የአንድነት ፓርቲ ምርጫ እሳተፋለሁ ውሳኔ እንዴት መታየት እንዳለበት በአጭሩ ይህን አቋም ለደገፉም ሆነ ለተቃወሙ ማሰረዳት ተገቢ ይመስለኛል፡፡ አንድነት ፓርቲ ስልጣን የሚገኘው በህዝብ ድምፅ ነው የሚል መርዕ አለው፡፡ የህዝብ ድምፅ የሚገኘው ደግሞ በምርጫ ወቅት መራጩ ህዝብ በሚሰጠው ካርድ ነው፡፡ ይህ ማለት ደግሞ በምርጫ የህዝብ ድምፅ ይገኛል ማለት ነው፡፡ ብዙዎች ምርጫ ለመሳተፍ እኩል ሜዳ ያሰፈልጋል ይላሉ፡፡ ትክክል ነው እኔም አምንበታለሁ፡፡ ሜዳውን ትክክል ከሚያደርገው አንዱ ጉዳይ የምርጫ ቦርድ ገለልተኝነት እንደሆነ ይታወቃል፡፡ የምርጫ ቦርድ ገለልተኛ ካልሆነ ማለትም ሜዳው ትክክል ካልሆነ ስልጣን በሌላም መንገድ መያዝ ተቀባይነት አለው የሚል መከራከሪያ ለማቅረብም ሰበብ ይሆናል፡፡
ስልጣን በተለያየ መንገድ ለመያዝ እንደሚቻል አማራጭ ማሳየት አንድ ጉዳይ ሆኖ እኛ የመረጥነው ብቻ ልክ ነው ማለትም ተገቢ አይደለም፡፡ በተገኘው መንገድ ለመያዝ መሞከር ግን መርዕ አልባ ያደርገናል፡፡ ሰላማዊ ትግል እከተላለሁ ብሎ በሰላማዊ ትግል መርዕዎች አምናለሁ የሚል ማታ-ማታ ወይም ቅዳሜና-እሁድ በሌላ መንገድ ልሞክር የሚል ከሆነ መርዕ አልባነት ነው፡፡ በእኔ እምነት ችግር ያለው የምርጫ ሜዳ ላይ ከሆነ የምርጫው ሜዳው ለማስተካከል ምን አድርገናል? ከሚለው መነሳት አለበት፡፡ ስልጣን የመያዣው መንግድ ኮሮኮንች በዝቶበታል ማለት ኮሮኮንቹን እንዴት እናሻሽል ወደሚል ሊገፋን ይገባል፡፡
ሁሉም ሰው መረዳት ያለበት ገዢው ፓርቲ የምርጫ ሜዳውን ያጠበበው ወይም ኮሮኮንች እንዲበዛበት ያደረገው አውቆ ነው፡፡ ሜዳው ደግሞ የጠበበን ደግሞ አማራጭ አለን የምንል ፓርቲዎች ነን፡፡ አማርጭ ለማቅረብ እድል ስንነፈግ መጠየቅ ያለብን አንድ መስረታዊ ጥያቄ አማራጭ የተከለከለው ህዝብ ምንም ማድረግ አለበት የሚለው ነው? አማራጭ የሚፈልግ ህዝብ ድንጋይ ወይም ጠብመንጃ ይዞ አማራጭ አትከልክሉን ቢል ነው የሚሻለው ወይስ የምርጫ ካርድ ይዞ? አንድነት የመረጠው መስመር የምርጫ ካርድ ይዞ ቢሆን ይሻላል የሚለውን ነው፡፡ ይህ በምንም ዓይነት ሌሎች የመረጡት መስመር አይሰራም ማለት አይደለም፡፡ የትም ፍጪው ዱቄቱን አምጭውን እንደ መርዕ የተቀበለ ብዙ ሌላ አማራጭ ሊያስብ፣ ሊተገብር ይችላል፡፡ ችግሩ የእኛ ካልሆነ ብሎ የሌሎችን ምርጫ ለማክበር አለመፈለጉ ላይ ነው፡፡
በሀገራችን ኢትዮጵያ በ1997 ከተደረገው ምርጫ ውጭ ህዝቡ በምርጫ እንዲሳተፍ የምርጫ ካርድ እንዲወስድ በተቃዋሚ ፓርቲዎች በተገቢው መልኩና ደረጃ ተቀስቅሶዋል የሚል እምነት የለኝ፡፡ ከ1997 በፊት ምርጫ መወዳድር ወያኔን ማጀብ ነው እያልን ምርጫ የሚወዳደሩትን ብቻ ሳይሆን መራጩንም ተሰፋ እያስቆረጥን ኖረናል፡፡ ይህን ምርጫ የማጣጣል ስትራቴጂያችንን በደንብ የተረዳው ገዢው ፓርቲ የራሱን መራጮችና ተመራጮች እያዘጋጀ ውድድር ሲያድርግ ነበር፡፡ እንደዚያም ሆኖ ህዝቡ በምርጫ ካርዱ ቅሬታውን ሲገልፅ እንደ ነበር የገዢው ፓርቲ የኮሚኒኬሽን ሚኒስትር ዴእታ የነበሩት አቶ ኤርሚያስ ለገሠ “የመለስ ትሩፋቶች” በሚለው መፅሃፍ አስነብቦናል፡፡ ስለዚህ የአንድነት ቤተሰቦች ምርጫ እንሳተፋለን ስንል መራጮቻችን እንዲመዘገቡ እናደርጋለን ማለት ነው፡፡ የእኛ መራጮች ሲመዘገቡ፣ ገዢው ፓርቲ የእኔ ብሎ ያስመዘገባቸውም ቢሆኑ እኛን ለመምረጥ እንዲችሉ መሸሸጊያ እንሰጣቸዋለን፡፡
ብዙ ሰው መረዳት ያለበት የምርጫ ቅስቀሳ የሚጀመርበት ወቅት መራጮች ምዝገባ ሊጠናቀቅ ሳምንት ሲቀረው ነው (በ1997 ቀድሞ የምርጫ ቅስቀሳ ተጀምሮ ነበር)፡፡ ለዚህ ነው ገዢው ፓርቲ ሁል ጊዜ የሚጮሁት ካርድ ያልያዙ ናቸው የሚለው፡፡ ያስመዘገባቸውን ስለሚያውቅ ነው፡፡ የእኛ መራጮች ካርድ ባልያዙበት ሁኔታ የፈለገ አማላይ የሆነ ለሀገር የሚጠቅም አማራጭ ብናቀርብ ለማሸነፍ ያለን እድል አነስተኛ ነው፡፡
ማስተላለፍ የፈለኩት ነጥብ ምርጫ እገባለሁ-አልገባም በሚል ዥዋዝዌ ስንጫወት ደጋፊዎቻችን በመራጭነት ሳይመዘገቡ እንዳይቀሩ በአንድነት በኩል የተወሰደው እርምጃ ትልቅ ፖለቲካ ውሳኔ ነው፡፡ የምርጫ ፓርቲ መሆናችን የሚታወቅ ቢሆንም እስከ አሁን በተቃዋሚ ፓርቲዎች መስመር ምርጫ መግባትና አለመግባት በቁርጥ ቀድሞ ስለማይወሰን መራጮች ሁለት ልብ እየሆኑ ከጫወታ ውጭ ሲደረጉ ከርመዋል፡፡ ይህ እንዳይደግም መራጮች እንዲመዘገቡ እና በምርጫው ሙሉ ሂደት በንቃት እንዲሳተፉ ይህን አቋም መያዝ እጅግ አስፈላጊ እና ጠቃሚ ነበር፡፡ ሁሉም እንደሚረዳው ያልተመዘገበ ደግሞ አይመርጥም፣ ያልመረጠ ደግሞ ድምፁ እንዲከበር ዘብ ሊቆም አይችለም፡፡ ድምፃችን ይከበር የሚለው እንቅስቃሴ የሚጀምረው ከህዝብ ታዛቢዎች ምርጫ እሰከ ድምፅ ቆጠራ ድረስ ይዘልቃል፡፡
ጎበዝ ሰላማዊና ህጋዊ ትግል እናደርጋልን ስንል የሰላማዊና ህጋዊ ትግል መርዖዎችን ጠንቅቀን መረዳት የግድ ይለናል፡፡ በስላማዊ ትግል ዋናው ግብ የህዝብን የስልጣን ባለቤትነት ማረጋገጥ ሲሆን፣ ስልጣን መያዝ የሚፈልግ ፓርቲ የህዝብ ይሁንታ ማግኘት የግድ ይለዋል፡፡ ይህ ደግሞ በምርጫ የሚገኝ ነው፡፡ ምርጫውን የህዝብ ፖለቲካ ተሳትፎ መለኪያ አድርገን ለመውስድ ቁርጠኞች መሆን የግድ ይለናል፡፡

ቸር ይግጠመን

Wednesday, November 26, 2014

ህዝቡ የሚለው …..


ዛሬ በርዕስነት የመረጥኩት ጉዳይ ለመፃፍ ካሰብኩ ቆይቻለሁ፡፡ መልዕክት ማስተላለፊያው መንገድ ሲዘጋ በጅምር ትቼው ነበር፡፡ ለዛሬ የ “ፍኖተ ነፃነት” ጋዜጣ እንዲሆን ብዬ ሳዘጋጀው የቱን አንስቼ የቱን እንደምጥል ግራ ገብቶኝ ለ “ህዝብ ጥቅም” ሲባል ከሚወሰዱት ህገ ወጥ እርምጃዎች የቅርብ የቅርቦቹን ብቻ ለማንሳት ወሰንኩ፡፡
የ “የፀረ ሽብር ህግ” ከምንጊዜውም በላይ ተግባራዊ እየተደረገ ያለበት ወቅት ላይ እንደምንገኝ ማንም ሰው ይረዳዋል ብለን እናምናለን፡፡ ሀገራት ሽብርን ለመከላከል የሚያስችላቸውን የህግ ማዕቀፍን ጨምሮ ሌሎች አወቃቀራቸውን በማደረጀት ህዝብን ከአደጋ ለመጠበቅ ዝግጁ መሆ እንዳለባቸው ዓለም አቀፍ ጥሪ ከቀረበላቸው ቆየት ቢልም ኢትዮጵያ ሀገራችን ዘግየት ብላም ቢሆን ከዓለም አቀፍ ማዕቀፉ ውጭ የዜጎችን ስብዓዊና ዲሞክራሲያዊ መብቶች ለማፈን የሚረዳ ህግ አውጥታ ተግባራዊ ማድረግ ጀምራለች፡፡ ለ “ህዝብ ጥቅም” ሲባል በሚል ማስመሰያ ብዙ ኢትዮጵያዊያን የ “ፀረ ሽብር” ህጉ ሰለባ እየሆኑ ይገኛሉ፡፡ በመላው ዓለም ፍተሻ ቢደረግ ዜጎቹን በሽብርተኝነት  በ“ፀረ ሽብር” ህግ የሚያንገላታ መንግሰት የሚገኘው እዚህ ኢትዮጵያ የምትባል ሀገር ብቻ ነው፡፡ የሌሎች ሀገሮች የፀረ ሽብር ህግ ትኩረቱና ግብ ሀገርን ከውጭ ሀገር ከሚመጣ የተደራጀ አሸባሪ ቡድን መጠበቅ ነው፡፡
በ “ፀረ ሽብር ህግ” ተከሰው ቅጣት ከተጣለባቸው ውስጥ ቅጣት የሚገባቸው ተከሳሾች የሉም የሚል ጭፍን ዕየታ የለኝም፡፡ እነዚህ ሰዎች በወንጀል ህጉ ሊቀጡ የሚችሉ እንደሆነ ግን መቶ በመቶ እርግጠኛ መሆን ይቻላል፡፡ ፖለቲከኞች እና ጋዜጠኞች እየታደኑ “በፀረ ሽብር” ህግ ስም የሚታጎሩት ግን ለህዝብ ደህንነትና ሰላም ሳይሆን በገዢዎች ወንበር ላይ በሚፈጥሩት ሽብር ነው፡፡ እነ አንዱዓም አረጌ፣ ናትናኤል መኮንን፣ እስክንድር ነጋ፣ ርዕዮት ዓለሙ፣ ሽብር የነዙት በአራት ኪሎ ወንበር ላይ ነው፡፡ የእነርሱ ድምፅ ለህዝቡ የነፃነት ድምፅ ነው፡፡ የተሰፋ ድምፅ ነው፡፡ አሁንም በብዞዎች የሚዘመር እና ወደፊትም ለክብር የሚበቃ የነፃነት ድምፅ፡፡

ሌላ የሰሞኑ ወሬ የግል ሚዲያዎች ህዝቡን ለብጥብጥ ህገመንግሰታዊ ሰርዓቱን በሀይል ለመናድ እየተንቀሳቀሱ እንዴት ዝም ተባሉ የሚለው ነው፡፡ የመንግሰት የፖሮፓጋንዳ ሚዲያዎች የህዝብ ጥያቄ እነዚህ ሚዲያዎች ለፍርድ ይቀረቡ የሚል ነው፡፡ ይህ በእውነት የህዝብ ጥያቄ ከሆነ ይህን ጥያቄ ያቀረበ ህዝብ ለምን አዲስ ዘመን ተሯሩጦ አይገዛም? ለኢቲቪም ያለምንም ውትወታ፣ ማስታወቂያና ማስፈራሪያ ዓመታዊ ኪራይ አይከፍልም? ለምን የግል ሚዲያ ህትመቶችን ተሻምቶ ይገዛል? ነገሩ ግን አንዲህ አይደለም፡፡ አንድ ቅምጥል የንጉስ ዘር የህዝብ ብዛት 20 ሚሊዮን ደርሶዋል ብትባል ምናምንቴውን ቆጥረው ይሆናል እንጂ እኛ ከአምሰት መቶ አንበልጥም ብላለች ተብሎ የሚበላ ወሬ አለ፡፡ ሕዝብ ለዚህች ቅምጥል ትርጉሙ የተለየ ነው፡፡ ለእኛዎቹ ቅምጥሎች ደግሞ ህዝብ የሚባለው ሌላ ትርጉም ካልተሰጠው እና አሁን በብዛት የግል ሚዲያ ሰርጭት ያለበት አዲስ አበባ ከሆነ እኛ ነን ህዝብ የምንባለው ካላሉን በስተቀር ነገሩ ለየቅል ነው፡፡ ህዝቡ እያለ ያለው ቅዳሜ ምን ልናደርግ እንውጣ? ነው፡፡ ቅዳሜ ተወዳጇ ፋክት መፅሔትን ጨምሮ ሌሎች ብዛት ያላቸው ህትመቶች ለገበያ ቀርበው የሚያነብበት ቀን ስለነበር ነው፡፡ በዚህ እለት አዲስ ዘመን በገበያ ላይ ብትውልም የሚመለከታት እንደሌለ እርግጠኛ ነኝ፡፡ ለጨረታ ማስታወቂያ ከሚፈልጉት ውጭ ማለቴ ነው፡፡
ሌላው የህዝብ ጥያቄ በእሰር ላይ የሚገኙትን ፍቱልን የሚል እንደሆነ ለመረዳት ፈላስፋ መሆን አያስፈልግም፡፡ በቅርቡ ቂሊንጡ እስር ቤት ሄጄ የታዘብኩት አንድ ነገር እጅግ ብዛት ያለው እስረኛ መኖሩን ነው፡፡ ተቃዋሚዎች እስር ቤት የሌለው መንግስት እንደማይመሰርቱ የታወቀ ቢሆንም በአሁኑ ሰርዓት ከህግ ውጭ ታስሮ መንገላታት ግን በግልፅ የሚታይ ሀቅ ሆኖዋል፡፡ ህዝቡ በግፍ የታሰሩትን ፍቱልን ሲል የቅምጥሎቹ ወገን የሆኑት ደግሞ እነዚህ ታሳሪዎች አሸባሪዎች ናቸው ይሉናል፡፡ እውነት እነዚህ ሰዎች አሸባሪ ከሆኑ ሰፍር ቁጥር የሌለው ህዝብ በየፍርድ አደባበዩ እና በየማጎሪያ ሰፍራ ለምን ይገኛል? እነዚህ በመንግሰት አሸባሪ የተባሉ ሰዎች ህዝቡ ለምን በፈቃዱ ይጎበኛቸዋል? እነዚህ ታሳሪዎች መጎብኘት የሚፈልግ ሁሉ በነፃነት እንዳይጎበኝ ለምን የተጠና እገዳ ይጣልባቸዋል? እዚህ ጋ ምፀት የሚሆነው ጉብኝት እግድ የሚጣለው “አሸባሪ” ብለው ያሰሯቸው እስረኞች ላይ ጉዳት እንዳይደርስ ነው የሚለው ነው፡፡ የሚያገላቱዋቸውም ለእነርሱ ደህንነት ብለው ነው፡፡
ከዚህ ጋር ተያይዞ ህዝቡ እያለ ያለው መሰረት የሌላቸው ሲከፋም ህገወጥ የሆነ የአቃቢ ህግ ክስና ይህን መሰረት አድርጎ የሚሰጥ የፍርድ ቤቶች ውሳኔ ይቁም ነው የሚለው፡፡ በመንግሰት በተጠና ጥናት እምነት የማይጣልባቸው ተቋማት የተባሉት እነዚህ ተቋማት በዚህ ድርጊት አሁን ባለው ጥልቀት መሳተፋቸው የተዓማኒነት ጉድለታቸውን ከማሳደግ ውጭ የህዝብ ጥያቄን አይመልስም የጊዜ ጉዳይ እንጂ የገዢዎችንም ወንበር አያፀናም፡፡
ሕዝቡ እያለ ያለው በየአምሰት ዓመት ምርጫ ቢመጣም አማራጭ አሳጣችሁን፡፡ አፈናውን አቁሙና ፍላጎት ያለው ተደራጅቶ አማራጭ ያምጣ ነው፡፡ የመደራጅት መብት ያለምንም ገደብ ይከበር!! ሕገመንግሰት ላይ በተቀመጠው መሰረት ተግባራዊ ይሁን!!! ነው፡፡ ከዚህ ቀደም ህዝቡ ያለው አሁንም የሚለው፡፡ እዚህ ላይ ገዢው ፓርቲም የመንግሰት መዋቅርን ተጠቅሞ የሚያደርገው አፈና አማራጭ አሳጣን እንጂ ደግ አደረጋችሁ የሚል ድምፅ አይሰማም፡፡ በቅርቡ በመንግሰት ድጋፍ በገዢው ፓርቲ አብዮታዊ ዲሞክራሲያዊ መስመርና ልማታዊ መንግሰት ፍልስፍና ዙሪያ የተደረጉት ከ-እሰከ የማይገልፃቸው ስብሰባዎች ያረጋገጡት ሀቅ ኢትዮጵያዊያን አማራጭ እንደሚፈልጉ እና የመንግሰት ህገወጥ አካሄድ እንዲቆም ነው፡፡ ኢትዮጵያዊያን እንደ ህዝብ ያቀረቡት ጥያቄ ከልማት እኩል ነፃነት ይገባናል ነው፡፡ ነፃነት ልማትን ያሳልጣል እንጂ የልማት ደንቃራ የሚሆንበት አንድም በቂ ምክንያት እንደሌለ ህዝቡ ተገንዝቦዋል፡፡ ህዝቡ የሚለው ነፃነታችንን አትንኩ ነው፡፡
ህዝቡ አሁንም እያለ ያለው የእምነት ነፃነት ይከበር የመንግሰት ጣልቃ ገብነት ይቁም ነው፡፡ ባለፈው ሰሞን ኢሳት የሚባል ለኢህአዴግ እሣት የሆነ ሚዲያ በቅርቡ ይፋ ያደረገው የሰብሰባ ውስጥ ውይይት መንግሰት በምን ያህል ጥልቀት በሙስሊሞች ጉዳይ ጣልቃ እንደሚገባ ብቻ ሳይሆን የሙስሊሙን ማህበረሰብ ለመምራት በሚል የአመራር ቦታ “የቀሙት” ሰዎች ግብ ምን እንደሆነ አጋልጧቸዋል፡፡ ህዝበ ሙስሊሙ እያለ ያለው እምነታችን በካድሬ አይመራም ነው፡፡ የኢሳትን ተደማጭነት ያጎላው የሀገር ውስጥ አፈና መሆኑን ለመረዳት ነብይ መሆን ያስፈልግ ይሆን? ህዝቡ እያለ ያለው አፈና ይቁም!!! ሀሳብ በነፃነት ማንሸራሸር የሚፈቅደው ህገመንግሰታዊ ድንጋጌ ይከበር ነው፡፡
ለማጠቃለል መንግሰት በህዝብ የመደራጀትና ሃሳብን በነፃነት የማንሸራሸር መብት ላይ በህዝብ ስም ገደብ እያደረገ ቢሆንም ህዝቡ ግን በተቃራኒ እየጠየቀ ያለው እነዚህ መብቶች ያለምንም ገደብ ይከበሩ ነው፡፡ እነዚህን መብቶች ተጠቅሞ በህዝብ ጥቅም ላይ ጉዳት የሚያድርስ ቡድንም ሆነ ግለሰብ ቢመጣ ህዝብ ለመቅጣት የሚያስችለው አቅም አለው እያለ ነው፡፡ የህዝብ ድምፅ ይሰማ፡፡
ቸር ይግጠመን!!!!