Wednesday, August 29, 2018

የፓርቲ የንግድ ተቋማት የወደፊት ዕጣ ፈንታ - የግል ምልከታ



የዛሬ ፅሁፍ መነሻ አቶ በረከት ስምዖን ጥረትን ከሃያ ሚሊዮን ብር መነሻ ወደ 11 ቢሊዮን አድርሼ ነው የለቀቅሁት የሚለው ጉዳይ ነው፡፡ ይህ መግለጫ እነዚህን ተቋማት ምን ያህል የዘረፋ ድርጅቶች እንደሆኑ ከማሳየት ውጭ አንድም እነ በረከት እና ታደሰ ጥንቅሹን ታማኝ ናቸው የሚያስብል ቁምነገር አላየሁበትም፡፡ በዚህ አጋጣሚ ብአዴን እነዚህ ድርጅቶች ከፓርቲ እጅ ወጥተው ወደ መንግሰት ይዛወሩ የሚል ውሣኔ መወሰኑንም ሰምተናል፡፡ ይህ በጎ ጅምር ግን ወደ መጨረሻው ትክክለኛው መንገድ መሄድ ይኖርበታል፡፡
በእኔ እምነት በኢህአዴግ አባል ድርጅቶች ውስጥ የሚገኙት እነዚህ ድርጅቶች (በአራቱም አባል ድርጅቶች ማለቴ ነው) ወደ መንግሰት ይዞታነት ሳይሆን መዛወር ያለባቸው ወደ ግል ይዞታነት መዛወር ይኖርባቸዋል፡፡ ሰለዝውውሩ አማራጭ ከማቅረቤ በፊት ግን ለዚህ ዝውውር የሚሆን አንድ አንድ ሃሳቦችን ማቅረብ እፈልጋለሁ፡፡
ለምሣሌ ኤፈርት በእውነት የትግራይ ሕዝብ ድርጅት ነው? ይህ ከእውነት የራቀ ነው፡፡ በኢትየዮጵያ ፖለቲካ ውስጥ ሴራ የሚሰራው የንግድ ተቋም በኤፈርት የሚመራው ነው፡፡ ይህ ድርጅት የትግራይ ሕዝብ ንብረት ነው እያሉ ሕዝቡን ላም አለኝ በሰማይ ሲያጓጉት ኖረዋል፡፡ ተሰፋው ተሰፋ ሆኖ የሚቀር ቢሆንም፣ እርግጠኛ የሆነ ነገርም አለ፡፡ እነዚህ ድርጅቶች በተወሰኑ የትግራይ አካባቢዎች የስራ እድል ፈጥረዋል፡፡ የህወሓት ካድሬዎች በእነዚህ ድርጅቶች ውስጥ የሚሰሩ ሠራተኞ ይህን የሥራ እድል የሚቀርባቸው አድርገው የሚሰሩት ፕሮፓጋንዳ ማንኛውንም ወደ ሕጋዊነት የሚወስድ አማራጭ በሕዝብ ድምፅ ስም ማደናቀፋቸው የሚቀር አይደለም፡፡ ይህ ከግምት ውስጥ መግባት እና የሕዝብ ተጠቃሚነት ባለበት ሁኔታ ሁሉ የሕዝቡ ጥቅም ጉዳት ላይ እንደማይወድቅ ማስረዳት ያስፈልጋል፡፡ ይህ የተጠና የህዝብ ግንኙነት ሥራ ይፈልጋል፡፡ ምን ያመጣሉ በሚል እሣቢ ፈግጪው ፈግጠው ማለት አይገባም፡፡ ማስተዋል ያስፈልጋል፡፡ በተለይ በእኛ አገር ሁኔታ በብሔር ፖለቲካ በሚናጥ ሲሆን እና አናሶች ከስልጣን ተገፋን ሲሉ ችግሩ የከፋ ሊሆን ይችላል፡፡
ሌላው ጉዳይ በተለይ በኦሮሚያ የሚታየው ድባብ ነው፡፡ በኦህዴድ ካድሬዎች ሰፈር የሚታየው ሰሜት ኤፈርትን ወደ ሕጋዊ ሥርዓት ማስገባት ሳይሆን ኦሕዴድም እንደ ሕወሓት ሌላ የኢኮኖሚ ኢምፓየር እንዲገነባ መገፋፋት ነው፡፡ ይህ ትክክለኛ አቅጣጫ አይደለም፡፡ የዚህ ሕገወጥነት የሚጀምረው የፖለቲካ ሥልጣን የያዙ ሰዎች ኢኮኖሚ መዘወር ሲጀምሩ የማሻጠር ጉዳዩም አብሮ ይፈጠራል፡፡ በረከት ሰምዖን  በአደባባይ እንደነገረን ሃያ ሚሊዮን፤ አሰራ አንድ ቢሊዮን የሚሆንበት አስማት ይፈጠራል ማለት ነው፡፡ ከአስማቶቹ አንዱ በሕገ ወጥ መንገድ የመንግሰት ንብረት ወደ ፓርቲ ንብረት ማዛወር አንዱ ሲሆን፣ ያለብቃት ትርፍ የሚያስገኝ አሰራር መዘርጋት ሌላው ነው፡፡ ሰራተኛ እንዴት እንደሚቀጥሩ አቶ በረከት የነገሩን ሚስጥር አሳፋሪ መሆኑን የምንታዘብ ያለን አይመስላቸውም፡፡ ዜጎች በውድድር ሳይሆን በክልል መንግሰት ዝርዝራቸው ቀርቦ እንዲመደቡ ይላካል ነው ያሉን፡፡ ይህ አቶ ሙሉጌታ ጓዴ የኤፈርትን ቅሌት በኢሳት ቀርበው ካስረዱን እውነት ጋር መሳ ለመሳ የሚገጥም ነው፡፡
እነዚህ ተቋማት አሁን መንግሥት የሚሰጣቸው ድጋፍ ሲቋረጥ የደም ስር እንደተቆረጠ የሚቆጠር ነው፡፡ ይሞታሉ፡፡ ይህ ሁሉ ሀብት፣ ንብረት ከሁሉም በላይ በሺዎች የሚቆጠሩ ሰዎችን የስራ እድል ይዘው እንዳይሞቱ መንግሥት የተጠና እርምጃ መውሰድ ይኖርበታል፡፡ ሳይሞቱ አገርና ሕዝብ በሚጠቅም ሁኔታ ወደ ሕጋዊ መስመር ማስገባት ያስፈልጋል፡፡ በእኔ እምነት ሁለት አማራጮች አሉ፡፡ ሌሎችም ሊኖሩ ይችላሉ፤ ብቸና የሚባል ነገር አይደለም፡፡
አንደኛ አማራጭ፡ እነዚህ የሁሉም ፓርቲዎች ንብረቶች ከመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ በተዘረፉ ንብረቶች የተመሰረቱ እና ከምስረታ በኋላም በሕገ ወጥ መንገድ እንዲደልቡ የተደረጉ በመሆናቸው የፌዴራል መንግሰቱ ወደ ግል ይዞታ እንዲዛወሩ በማድረግ፤ ገንዘቡን ለክልሎች በቀመር መሰረት ማካፈል ሊሆን ይችላል፡፡ ይህ አማራጭ አስቸጋሪ የሚያደርገው ከፍተኛውን ንብረት የያዘው ኤፈርት/ሕወሓት ፈቃደኝነት ያለመኖር ብቻ ሳይሆን፤ በህዝብ ዘንድ ሲነዛ የነበረው የትግራይ ሕዝብ ንብረት ነው የሚለው መሰረተ ቢስ ፕሮፓጋንዳ ነው፡፡ የትግራይ ሕዝብ ከዚህ ከላይ በጠቀስኩት መልክ በተፈጠረ ሥራ ለፍቶ ከማግኘት በላይ የተጠቀመው ነገር የለም፡፡ ዋንኛዎቹ ተጠቃሚዎች የፖለቲካ ሹሞቹ መሆናቸው ግልፅ ነው፡፡ የፖለቲካ ስልጣን በማንኛውም ሁኔታ ለመያዝ የሞት የሸረት ትግል የሚያደርጉትም ለዚህ የግል ጥቅማቸው ነው፡፡
ሁለተኛው አማራጭ፡ የኢትዮጵያ ሕዝብ በዚህ ምክንያት ከትግራይ ሕዝብ ጋር መሰረት የሌለውም ቢሆን ቁርሾ የሚገባበት ሁኔታ ሳይኖር፤ እነዚህ ድርጅቶች በሙሉ በሸያጭ ወደ ግል ይዞታነት እንዲዛወሩ ተደርጎ፤ ከሽያጭ የሚገኘውን ገቢ ክልሎች ለበጀት ድጎማ እንዲጠቀሙበት እና ልዩ ልዩ ማህበራዊ አገልግሎቶች እንዲገነቡበት ሊፈቅድ ይችላል፡፡ ይህ ወደ ግል የማዛውር ሂደት በዋነኝነት የኢትዮጵያ ሕዝብ ችሮታ መሆኑ ታውቆ የተወሰኑ የፖለቲካ ልሂቃን እጅ እንዳይገባ የፌዴራል መንግሰቱ ከፍተኛ ጥንቃቄ ሊያደርግበት የሚገባ መሆን አለበት፡፡ ይህ አማራጭ ኢትዮጵያ አገራችን ትልቅና ከዚህ የላቀ ሀብት የማፍራት አቅም እንዳላት ማመን ብቻ ሳይሆን፤ ኢትዮጵያዊያን ከእጥረትና እጦት አስተሳሰብ መላቀቃችንን የሚያሳይ ነው፡፡ በእኔ እምነት የተሻለ አማራጭ አድርጌም እወስደዋለሁ፡፡
ይህ የሚደረገው አሁን በፖለቲካ ፓርቲዎች ስም በሕገወጥ መንገድ ያሉትን ማስወገድ ብቻ ሳይሆን፤ ከአሁን በኋላ በአገራችን የፖለቲካ ፓርቲዎች የሚመሩት የንግድ ተቋም በምንም መልኩ መፈቀድ እንዳይኖርበት መሰረት ለመጣል ነው፡፡ አሁን የተቋቋሙትም በአፋጣኝ ወደ ሕጋዊ ስርዓት መግባት የግድ ይላቸዋል፡፡ እነዚህ ተቋሞች አሁን ያለው ሕገወጥ አሰራር ሲቆም መሞታቸው የማይቀር ነው፡፡ ሲሞቱ ደግሞ እጅግ ብዙ ሀብትና ንብረት ይዘው እንደሚሆን ግልፅ ነው፡፡ ሰለዚህ ኢህአዴግ እንደ ድርጅት ለማደግም ሆነ ለመሞት በእነዚህ ድርጅቶች እጣ ፈንታ ላይ ቆራጥ ውሣኔ በመወሰን በቀጣይ ለሚመጣው የመድበለ ፓርቲ ስርዓት ስራ ሊያቀልለት ይገባል፡፡ ካልሆነ ቀጣዩ ጊዜ አገር ግንባታ ሳይሆን የጭቅጭቅ እና የንትርክ ከማድረግ አልፉ እናልፈዋለን የምንለውን የሰላም ማጣት አዙሪት በድጋሚ እንዳይገጥምን ያስፈራል፡፡


Saturday, June 2, 2018

አንዳርጋቸው ፅጌ - የገብርኤሉ መንገድ ካህን



ኢትዮጵያ አገራችን ወደ ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ለመግባት ብዙ ታሪካዊ አጋጣሚዎች፤ እንዲሁም ደግሞ ሁለት ሰር ነቀል የሚባሉ ለውጦች በዚህ አጭር ጊዜ ውስጥ አሰተናግዳለች፡፡ ከእነዚህ አንዱ የሆነው የዛሬ ሃያ ሰባት ዓመት ግንቦት 20 ቀን 1983 ዓ.ም የነበረው ለውጥ በብዙዎች ዘንድ ብሩዕ ተሰፋ አጭሩ ነበር፡፡ ይህ ተሰፋ ካጫረባቸው ሰዎች አንዱ በቅርቡ ከእስር የተፈታው ከየመን ታግቶ የመጣው የነፃነት ታጋዩ አንዳርጋቸው ፅጌ ነው፡፡በዚያ ክፉ ጊዜ ይህ ሰው እንደ ብዙዎቻችን ተሰፋ መሰነቅ እና ለበረኽኞቹ ዕድል እንስጣቸው ብሎ አልተቀመጠም፡፡ ይልቁንም ላግዛችሁ እችላለሁ፣ ከለውጥ ባቡሩ መሳፈር ብቻ ሳይሆን ልሾፍር ብሎ አዲስ አበባ በመግባት፣ የሽግግር መንግስቱን በአዲስ አበባ ዋና ፀኃፊነት በማገልገል ተሳትፏል፡፡ ይህን ጉዳይ ያነሳሁት አንዳርጋቸው በአሰገራሚ ሁኔታ ይህን ተሳትፎ በክብር ለመሞት እንደውለታ አንዲቆጠርለት፤ ለአሳሪዎቹ ጥያቄ ማቅረቡን ሰለነገረን ነው፡፡ ማሩኝ አትግደሉኝ፣ በክፉ ቀን አብሬያችሁ ነበርኩ፤ አይደለም ያላቸው፡፡ እየሳቁ በክብር ለሞሞት የሚዘጋጅ ጀግና ፊታቸው ሲቆም፤ አሳሪዎቹ ምን እንደተሰማቸው ወደፊት በዝርዝር የማወቅ ዕድሉ ይኖረናል ብዬ አምናለሁ፡፡ ከዚህ የምንማረው ትልቁ ነገር አምነን ለቆምንለት ዓላማ፣ በጠላት ዕጅ ውስጥ ብንሆንም ለክብር ሞት መዘጋጀት እንዳለብን ነው፡፡ ይስማል!!!
አንዳርጋቸው ፅጌ በመሰራችነት የተሰለፈበት ግንቦት ሰባት፣ የጠመንጃ ሱስ እና ወንድም ወንድሙን ገድሎ ጀግንነት የሚመዘገብበት አውድ ለመፍጠር ፍላጎት እንደሌለው ማንም ንፁህ ሕሊና ያለው ይረዳል፡፡ ነገር ግን በመሣሪያ ሀይል ሥልጣን የያዘ የሚመስለው በህወሓት ቁጥጥር ሥር የነበረው መንግሥት (አሁን ህወሓት በዚህ ደረጃ ያለች ስለማይመስለኝ ነው፡፡) ፉከረው ሁሉ መንገዱን ጨርቅ ያርግላችሁ በሚል ትዕቢት ውስጥ መግባቱ፣ ብረት ለማንሳት ዋንኛው ገፊው ምክንያት እንደነበር እንረዳለን፡፡ የማሪያም መንገድ ከተዘጋ፣ የገብሬሉ ይከፈታል ብለን ብንወተውትም የሚሰማን አላገኘንም ነበር፡፡
የገብሬሉ መንገድ ሲከፈት ደግሞ ከካህናቱ አንዱ ሆኖ ብቅ ያለው፣ ህወሓተች በሚያሳዩት ዕብሪት በንዴት በመጦዝ፣ እነርሱ ጫማ ስር ለማጎንበስ እና ለመጫን ፈቃደኛ ካልነበሩት አንዱ ውስጣቸው ሆኖ ገምግሟቸው “ነፃነት የማይውቅ፣ ነፃ አውጪ” ብሎ ስም ያወጣላቸው አንዳርጋቸው ፅጌ ነው፡፡ ይህ ሰው በአንዲት ክፉ ቀን እና አጋጣሚ ምንአልባትም ወደፊት ይፋ በሚወጣ ልዩ ደባ በህወሓት “ደህንነቶች” እጅ ስር ወድቆ ለአራት ዓመት በቁጥጥራቸው ሥር ሆኖ ነበር፡፡ ይህን የጭለማ ዘመን ለማሰብ ይከብዳል፡፡ ሕገ መንግሥታዊ ሥርዓት ብለው እየተመፃደቁ፤ አንድ መሰመር የሕገ መንግሥት ድንጋጌ ከማያከብሩ ሀይሎች ቁጥጥር ውስጥ ሲኮን ደግሞ ጨለማው ድቅድቅ ነው፡፡
ባለፉት አራት ዓመታት የኢትዮጵያ ሕዝብ ይህን የገብርኤል መንገድ ካህን ምን አደረጉት? ምንስ ያደርጉት ይሆን? የሚለው ስጋት ወጥሮት ነበር፡፡ አንዳርጋቸው በመረጠው የገብርኤል መንገድ ባንስማማ፣ ተገፍቶ የገባበት መሆኑን የምንረዳ ሁሉ በዚህ ጭንቅ ውስጥ እንደነበርን ለማንም ግልፅ ነው፡፡ በግሌ አገሩን እንደሚወድ ዜጋ አንዳርጋቸው ላይ በዚህ መንግሥት ሊደርስ የሚችለውን ግፍ በማስብ አገሬ በምን ደረጃ ልትዋረድ እንደምትችል ሳሰበው ይጨንቀኝ ነበር፡፡ መንግሥቱ ኃይለማሪያም ስልሣዎችን የንጉሡን ሹማምንት፣ አስከትሎም አገሪቱን አሉኝ የምትላቸውን ጄነራሎች ገድሎ በግሉ የፈጠረለትን ደስታ ባላውቅም ለአገሬ ኢትዮጵያ የፃፈላትን ጥቁር ታሪክ ሳስብ ያመኛል፡፡ የህወሓት ሰዎቸም ለአገር በማሰብ ሳይሆን በግል ቂምና በቀለኝነት አንዳርጋቸው ላይ ሊያደርሱ የሚችሉት ግፍ ለአገሬ ኢትዮጵያ አንድ ተጨማሪ ጥቁር ጠባሳ ያለበት ታሪክ እንደሚፃፍ በማስብ በስቃይ ውስጥ የከረመው ሕዝብ እንዲሁ ከአንዳርጋቸው መፈታት ጋር የሠላም አየር መተንፈስ ችሎዋል፡፡ በሕይወትና እና በጤና ማግኘታችን ደስ የሚያሰኝ ነው፡፡

አንዳርጋቸውን ሳገኘው የተሰማኝ ደስታ ከሁሉም በላይ ከፍ ያደረገው በሠላም፣ በጤና መገኘቱ ብቻ አይደለም፣ እንዲህ ዓይነቱ ልዩ እስር በሚፈጥረው የመረጃ ክፍተት ያልተወናበደ መሆኑ ጭምር ነው፡፡ አንዳርጋቸው ሰል ከሆነ ጭንቅላቱ ጋር በጤና ሰላገኘሁት ደስ ብሎኛል፡፡ በአገሬም ተጨማሪ ጥቁር ጠባሳ የሚፈጥር ታሪክ አለመፃፉ በተጨማሪ አስደስቶኛል፡፡
በዚህ አጋጣሚ የህወሓት/ኢህአዴግ መንግሰት በዓለም ልዩ የሆነ ቶርች ሲስተም በመፍጠሩ በታሪክ ሊመዘገብለት የሚገባ ይመስለኛል፡፡ በፖለቲካ ጉዳይ የሚያስራቸውን ሰዎች በተለይ ቀንደኞች ብሎ ለሚፈርጃቸው በሃያ አንደኛው  ክፍለ ዘመን መረጃ እንዳያገኙ ማድረጉ ነው፡፡ ብርቱካን ሚደቅሳ ከደካማ እናቷ እና ሕፃን ልጇ በስተቀር ማንም እንዳይጠይቃት በማድረግ ዕለት ከዕለት ፕሮፓጋንዳ የሚነዛበት የገዢውን ሥርዓት ቴሌቪዥን ፈቅዶ በትግል ላይ ናቸው ብላ የምታስባቸው የፓርተ አባላት ሲደባደቡ ማሳየት ዋና ተግባሩ ነበር፡፡ በተመሣሣይ አንዳርጋቸው ፅጌ ከዘጠና ዓመት አረጋዊ አባቱ በስተቀር ማንም አንዳይጎበኘው በማድረግ የፈፀሙት ግፍ፤ የፈለጉትን ወጤት አለመጣም፡፡ በፈለጉት መንገድ አንዳርጋቸውን ባለማስጎንበሱ ደስተኛ ነኝ፡፡ ባለፉት ጥቂት ሣምንታት አንዳርጋቸው ቴሌቪዥን አንዲገባለት መደረጉ ደግሞ ከመውጣቱ በፊት ተሰፋ እየዘሩብን ያሉትን አዲሱን ጠቀላይ ሚኒሰትር ዶክተር አብይ አህመድን ለመተዋወቅ እንደሚረዳው እና ተስፋም እንዲሰንቅ ረድቶታል የሚል እምነት አለኝ፡፡ ከተፈታ በኋላ ጠቅላይ ሚኒሰትር አብይ አንዳርጋቸውን ለማግኘት መወሰናቸው በራሱ አንድ ትልቅ እርምጃ ነው፡፡ ያለፈውን ትተን ወደፊት ለአገራችን ሠላምና ብልፅግና፤ ለሕዝቦች ክብር የምንቆምበት ቀን የተቃረበ ይመስለኛል፡፡
ግርማ ሠይፉ ማሩ

Saturday, May 12, 2018

ዘመኑን የዋጀ ጠንካራ የፖለቲካ ሀይል መቼ?



የኢትዮጵያ ፖለቲካ ኬሚስትሪው መቀየሩን ወይም በቀላሉ ሊቀየርበት የሚችልበት ደረጃ ላይ መገኘቱን ሰንቶቻችን ገብቶናል፡፡ ከዛሬ ሶስት ዓመት በፊት ምን አልባትም አንድነት ፓርቲ “ድንክ” ከመደረጉ እና ለምር ፖለቲካ ሳይሆን ለፌዝ ፖለቲካቸው እንዲመጥናቸው ለማድረግ በደህንነት ተቋም ውሣኔ ከመተላለፉ በፊት የኢትዮጵያ ፖለቲካ ፓርቲ ተበዬዎች በርዕዮተ ዓለም መስመር ለይተው ግብ ግብ ለመግጠም ሳይሆን ሁሉም ተባብሮ ህወሓት/ኢህአዴግ የሚባልን ሰይጣናዊ ሀይል በማሰወገድ ቀጥሎም የፖለቲካ ምእዳር ማስተካከል ቀጥሎ ደግሞ እርስ በእርስ መወዳደር የሚል ነበር፡፡ በአንድ አንዶች አገላለፅ ትግሉ “የነፃነት የፍትህና የዴሞክራሲ” ስለሆነ ከአብዮታዊ ዴሞክራሲ በተፃራሪ የቆመ ሁሉ ተባብሮ መስራት ይጠበቅበታል የሚል ነበር፡፡ ትክክልም ነበር፡፡
ተባብሮ መስራት እና ሕዝቡን ለነፃነቱ ቀናሂ በመሆን ጭቆና በቃኝ፣ ነፃነት ያስፈልገኛል፣ አማራጭ እፈልጋለሁ፣ ወዘተ እንዲል ማነሳሳተ ትክክለኛ የፖለቲካ ውሣኔ ነበር፡፡ ከዚህ አንፃር አንድነት ፓርቲ “የሚሊዮኖች ድምፅ ለነፃነት” በሚል “በፀረ ሸብር” ተብዬ ሕግ ላይ ያደረገው ዘመቻ ማስታወስ ያስፈልጋል፡፡ ሚሊዮኖች ለፖለቲካ ፕሮግራም ልዩነት እና ተመሳሳይነት ሳይሆን አፋኝ የሆነውን የህወሓት/ኢህአዴግን ሥርዓት እንቢኝ ያሉበት ነበር፡፡ በዚህ እንቅስቃሴ በብሔር የተደረጃው ብሔር ዘለል ከሆነው አደረጃጀት ጋር በጋራ ለመቆም ሙከራ አድርጓል፡፡ መድረክና አንድነት የነበራቸው ግንኙነት ዓይነት፡፡ የግንኙነቱ ወጤት አሳዛኝ የነበረ ቢሆንም፡፡
ዛሬ ላይ ሆነን ስንመለከተው በአኔ እምነት ፖለቲካው ተቀይሯል፡፡ ወይም ሊቀየር የሚችልበት ደረጃ የደረሰ ይመስለኛል፡፡ ዶክተር አብይ የሚመራው ኢህአዴግ የመለስ ዜናውን የአብየታዊ ዴሞክራሲ/ልማታዊ መንግሰት ተረኮች ወደ ጎን በማለት (በራሳቸው ቃል ለመጠቀም) ለተፉካካሪዎች ምቹ የፖለቲካ ምሕዳር የሚከፍቱ ከሆነ ጉዳዩ ኢህአዴግን በማንኛውም መንገድ ይወገድ ከሚለው መስመር መላቀቅ ግድ ይለናል ማለት ነው፡፡ ይህ ደግሞ መሣሪያ አንስተው ይዋጣልን ያሉትም ቢሆኑ የሚመለከት ስለሆነ መሣሪያውን አፈሙዝ አሰደፍቶ ወደ እስክሪብቶና ወረቀት ጫወታ ይቀየራል ማለት ነው፡፡ በዚህ ጊዜ የጫወታ ሕግ ለጋራ አገራችን በፉክክር ማመን፣ ለሕዝብ ዳኝነት መቅረብ፣ ጀግንነት ማሸነፍ ሳይሆን መሸነፍን መቀበል  የሚሆንበት ይሆናል ማለት ነው፡፡ ጫወታው ተሸንፎ ጭምር ጀግና የሚኮንበት መሆን ይኖርበታል፡፡
ይህ እድል አሁን በበር ላይ ቆሞ ያለ ይመስለኛል፡፡ ክፈት በለው በሩን …. ብለን እንገባ ወይስ በሩ ተከፍቷል ግቡ እንባል የሚለው እያነጋገረ ያለ ጉዳይ ነው፡፡ ዶክተር አብይ አና ቡድናቸው በአፋጣኝ መሳሪያ ያነሱትን ሀይሎች መሳረያቸውን አስቀምጠው በሕግ ወደሚመራ ጫወታ እንዲገቡ ጥሪ ማድረግ ይኖርባቸዋል፡፡ ከፖለቲካ አሻጥር ነፃ የሆነ ጥሪ ማድረግ ያስፈልጋል፡፡ ይህ ወሳኝ የሆነ የፖለቲካ ጅማሮ ነው በሩ መከፈቱን ማብሰርና ግቡ ማለት ያስፈልጋል፡፡ በአገር ቤት የምንገኝ አማራጭ አለን የምንል ደግሞ አማራጫችንን ይዘን ክፈት በለው በሩን ማለት ይኖርብናል፡፡ እንደ ከዚህ ቀደሙ “ትግሉ የነፃነት ነው” በሚል በርዕዮት ዓለም ይሁን በግብ ከማይመስለን ጋር ሁሉ መሞዳሞድ መቆም ይኖርበታል፡፡ ጫወታው በሃሣብ ብልጫ እና በምናቀርበው አማራጭ ልዕልና የሚወሰን መሆኑን ተረድተን ለዚሁ መትጋት ይኖርብናል፡፡ አደረጃጀታችን ይህን የሚመልስ እንጂ የኢህአዴግን አደረጃጀት የሚመጥን ቁጥር ፍለጋ አባላት በማግበስበስ ላይ የሚመሰረት መሆን የለበትም፡፡
የኢትዮጵያ ሕዝብ ከአሁን በኋላ መብት ተነክቷል ለነፃነትህ ተነስ ብሎ ቀስቃሽ አይፈልግም፡፡ በየሰፈሩ እና መንደሩ ይህ ጉዳይ በጎበዝ አለቆች፣ በቄሮና ዘርማ እየተመራ ያለ ጉዳይ ነው፡፡ ይህን ለማድረግ የፖለቲካ ፓርቲ አያስፈልግም፡፡ እደግመዋለሁ የፖለቲካ ፓርቲ አያስፈልግም፡፡ ለዚህ ጉዳይ ጠንካራ ሲቪል ማህበራት መኖር የግድ የሚልበት ሁኔታ ይታየኛል፡፡ ጥያቄዎች በስርዓት እንዲቀረርቡ፣ ዜጎች የተለያዩ አማራጭ ማቅረቢያ ዘዴዎችን በየደረጃው እንዲጠቀሙ የሚያስተምሩ ተቋማት ያስፈልጋሉ፡፡ ለሁሉም ጥያቄ መንገድ መዝጋት እሳት ማንደድ ተገቢ ሰላልሆነ ማለት ነው፡፡ ከዚህ አንፃር ማንሳት ያለብኝ በቅርቡ ወንድማችን በቀላ ገርባ በግፍ ከሚማቅቅበት እስርe ቤት ያስፈታው የመንግሰት ቸርነት ሳይሆን ቄሮ ያነደደው አሳት መሆኑ ግልፅ ሆኖ ሳላ ትልቁ ሰው በቀለ ገርባ ግን ዛሬም ይህ አማራጭ ብቸኛው አማራጭ ያለመሆኑን ይስብካል፡፡ የዚህ ዓይነት በመርዕ ላይ ያሉ ሰባኪዎች ያስፈልጉናል፡፡ እስክንድር ነጋ “ፕሮፌሽናል እንቢተኞች” በሚል የጠራቸው የእርሱ ዓይነቶቹን መብት ተሟጋቾች የአስቸኳያ ጊዜ አዋጅ ምናቸውም እንዳልሆነ ብቻ ሳይሆን የኢትዮጵያ ሕዝብ ለመብቱ፣ ለነፃነቱ፣ ወዘተ የጀመረውን እንቅስቃሴ እስከመጨረሻው መቀጠል ይኖርበታል እያለን ነው፡፡ ይህ ሁሉ ግን የሚሆነው በሠላማዊ እንቢተኝነት ብቻ መሆን አለበት ብሎ እየሰበከን ነው፡፡ በእኔ እምነትም እሳት ማንደድ የመጨረሻው አማራጭ መሆን ይኖርበታል፡፡ የህወሓት እጅ መስብሰብ ካቃተው እንቢታው ከበዛ፣ ዳተኝነት ካየለ ግን እሳት ማንደዱ፣ መንገድ መዝጋቱ የግድ መሆኑን አምናለሁ፡፡ ያስፈልጋልም፡፡
ባለፈው አጭር ክታቤ ኢትዮጵያ ስንት ፓርቲ ያስፈልጋታል ስል ጉዳዩን ወደ ቁጥር አውርደውተ የነበሩ ሰዎች ነበሩ፡፡ ጉዳዩ የቁጥር አልነበረም፡፡ ለሕዝብ ትከክለኛ አማራጭ ሊያቀርቡ የሚችሉ ምን ያህል የተደራጁ ሀይሎች ያስፈልጋሉ? የሚል ነበር፡፡ ለምሣሌ በግሌ በብሔር ለመደራጀት ፈቃደኛ አይደለሁም፡፡ ሰለዚህ በአገራችን ከሰማኒያ በላይ የብሔር ድርጅቶች ሊኖሩ ይችላሉ፡፡ መብታቸው ነው፡፡ በፌዴራል ደረጃ ሥልጣን ለመያዝ ግን አንድ ድርጅት በቂ ሊሆን የሚችልበት ሁኔታ በኢትዮጵያችን የለም፡፡ ሰለዚህ ግንባር መፍጠር የግድ ይላል ማለት ነው፡፡ ለዚህ ሁነኛው ምሣሌ በህወሓት የሚመራው ኢህአዴግ ሲሆን፤ ሌላው አማራጭ ደግሞ መድረክ ነው፡፡ ከዚህ ውጭ አሁን በውጭ የሚገኙ በብሔር የተደራጅ ሀይሎች ኢህአዴግን ወይም መድረክን መቀላቀል ወይም ደግሞ የራሳቸውን ግንባር ፈጥረው መምጣት ወይም ደግሞ በክልል ደረጃ ለመሳተፍ  ብቻ መወስን ይችላሉ፡፡ የዚህ ዓይነት ስንት ስብስብ ያስፈልጋል? ጥያቄው ይህ ብቻ ነው፡፡
በብሔር መደራጀት የማንፈልግ “የሃሣብ ሰብስብ” እንዲኖር የምንፈልግ ሰዎች ደግሞ አሁን በአገራችን ያሉትን ሰርተፊኬት ያላቸውን ፓርቲዎች ከቁም ነገር ወስደን ጫወታ ለመጀመር የሚቻልበት ሁኔታ እንደሌለ የረጀም ጊዜ ግምገማችን ያሣያል፡፡ ከዚህ ውጭ ያለው አማራጭ ደግሞ  በተዓምር ከላይ ዱብ ሊል አይችልም፡፡ ዶክተር አብይም ቢሆን ኢህአዴግን ከህወሓት የአይዲዎሎጂ ቅርቃር አውጥቶ ለውድድር የሚሆን ቁመና ያለው ፓርቲ ማድረግ ትልቁ ሃላፊነቱ ሲሆን ይህን በአግባቡ ሲወጣ ሌላ ሀይል የሚፈጠርበት ምዕዳር ይመቻቻል የሚል እምነት አለኝ፡፡ ዶክተር አብይ የአብዮታዊ ዴሞክራሲ አስተሳሰብ መርዝ ከኢህአዴግ ካላስተፋልን በዚህ አስተሳሰብ ውስጥ አማራጭ የሚባል ነገር የምር የለም፡፡ ሰለዚህ ሌላ ሀይል መፍጠር አይቻልም፡፡ አማራጩ እሳት ማንደድ እና ማስገደድ ብቻ ይሆናል፡፡ እሳት እንዳይነድ አማራጭ ሀይል እንዲፈጠር ደግሞ የዶክተር አብይ አመራር ከባድ ሃላፊነት አለበት፡፡ የእኛ ደግሞ ሃላፊነት አማራጭ ሀይል መፍጠሩ ላይ ነው፡፡ ይህን ሀይል መፍጠር ደገሞ አሁን በፓርቲ ጥላ ሥር የሚገኙም ሆነ ከዚያ ውጭ ሆነው በዚህች አገር የፖለቲካ ዕጣ ፋንታ ሃላፊነት አለብኝ የሚሉ ዜጎችን ሁሉ ይመለከታል፡፡ ያለበለዚያ ግን እንደ ከዚህ ቀደሙ ህወሓት/ኢሕአዴግን በማውግዝ፤ የሕዝብ ጥያቄ የሚመልስ አማራጭ ሳይኖረን ከቆየን፤ ዘመኑን አልዋጀንም እና ዋጋ አይኖረንም፡፡

ኢትዮጵያ ለዘላለም በክብር ትኑር!!!

ግርማ ሠይፉ ማሩ
ቅዳሜ ግንቦት 4/2010


Friday, April 13, 2018

ለክቡር ዶክተር አብይ አህመድ በኢትዮጵያ አገራችን መድበለ ፓርቲ ስርዓት ለመገንባት ከገዢው ፓርቲ/መንግስት ምን እንደሚጠበቅ ለመጠቆም የቀረበ የመነሻ ሃሣብ ከግርማ ሠይፉ ማሩ girmaseifu@gmail.com girmaseifu.blogspot.com



ከብር ጠቅላይ ሚኒሰትር ይህን ከባድ ሃላፊነተት በተረከቡ ዕለት ለኢትዮጵያ ሕዝብ ባደረጉት  አነቃቂ ንግግር “የሃሣብ ልዩነት መርገምት አይደለም፣ ይልቁንም በረከት ነው፡፡” ባሉት መነሻ፣ ከኢህአዴግ ጋር የሃሣብ ልዩነት ያለን ዜጎች በተናጥል ይሁን በተደራጀ መልክ ሃሣባችንን ለሕዝብ ማቅረብ እንደሚገባን መረዳቶን ተገንዝቢያለሁ፡፡ ከዚህ አንፃር ክቡር ጠቅላይ ሚንሰትር መወሰድ አለባቸው፤ ይገባልም ብዬ የማስባቸውን ነጥቦች በግሌ በዚህች አጭር ፅሁፍ የማቀርብ ሲሆን፤ ከዚያ ቀድሜ ግን አንድ ጠቃሚ እውነት ማሰጨበጥ ይኖርብኛል፤
በኢትዮጵያ አገራችን አብዛኞቹ ተቃዋሚዎች በሚያሳዝን ሁኔታ ምንም ለህዝብ የሚጠቅም የፖለቲካ ፍላጎት/ሃሣብ የላቸውም፡፡ አሁን ባለው ሁኔታ ለመኖር የሚያስፈልጋቸውን ምንዳ ከኢህአዴግ እንዴት እንደሚሰፈርላቸው መጠበቅ ዋንኛ ሥራቸው ነው፡፡ በዚህ መስመር ጉድለት ካለ ሊነጫነጩ ይችላሉ፡፡ ነገር ግን ምንም ለውጥ አያመጡም፡፡ ተገቢ የሆነ ጠበቅ ያለ የስርዓት ማስከበር እርማጃ ቢጀመር እና በህይወት እንዲቆዩ እንደ ኦክስጅን የሚደረግላቸው ምንዳ ቢቋረጥ ለመኖር እንደማይችሉ እርግጠኛ ነኝ፡፡ ጥቂቶቹ ተቃዋሚዎች፤ በተለያየ የውስጥና የውጭ ጫና ተጠልፈው፤ ከገዢው ፓርቲ ጋር በሚደረግ ምንም ዓይነት ግንኙነት፤ ምን ማግኘት እንዳለባቸው ሳይሆን፤ በግንኙነት ወቅት የህዝብ ግንኙነት ስራ በመስራት የውስጥና የውጭ ጫናውን ለማለዘብ እና ለህዝብ ቋሚ ተጠሪ መሆናቸውን ለማሳየት የሚውተረተሩ ናቸው፡፡ ሰለሆነም ተቃዋሚዎች ለመንግስት ቀላል እና ለመፈፀም የሚቻል፣ ፍላጎታቸውን ያማከለ ጥያቄ በማቅረብ ሊፈትኑት አልተዘጋጁም፡፡ የሚያቀርቡት ጥያቄ ለህዝቡ በሚገባው ቋንቋ፤ መንግሰት ይህን ማድረግ ከቻለ ሌላውን ስራ ለእኛ ተዉት በሚል ደረጃ ለማቅረብ አልተዘጋጁም፡፡ በዚህ አውድ ውስጥ ሆኜ ነው የግል ሃሣብ የምሰነዝረው፡፡
ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር እርሶ የሚመሩት መንግሰትና/ኢህአዴግ በግሌ ተግባራዊ እንዲያደርጉት የምፈልገው ቀላል ጥያቄ አንድ ብቻ ነው፡፡ ይህም ኢህአዴግ በመንግሰትነት በያዘው ሀይል ተጠቅሞ፤ የፖለቲካ ምህዳሩን አጥብቦታል እና ይህን ይክፈትልን የሚል ነው፡፡ ይህን ሲያደርግ አብዛኞቹ ከጫወታ ይወጣሉ፤ ጥቂቶቹ አማራጫቸውን ለህዝብ በተደራጀ መልክ የሚያቀርቡበት እድል ያገኛሉ፡፡ ይህ የፖለቲካ ምህዳር መጥበብና መስፋት ጉዳይ ለጥቂት ፖለቲከኞች የሚገባ ቢሆንም ለአብዛኛው ህዝብ ጥቅል ሃሣብ ነው፡፡ ይህ ለህዝቡ እንዲገባው ማድረግ በሚችል መልኩ በዝርዝር መቀመጥ ይኖርበታል፡፡ እርሶም ምን ምን ማድረግ እንደሚገባው መነሻ ሆኖ ያገለግለዎታል የሚል እምነት ሰላለኝ፡፡ በአጭሩ ለማቅረብ እሞክራለሁ፤
1.      የፖለቲካ ፓርቲዎች ለቢሮ የሚሆናቸውን ደረጃውን የጠበቀ ፅ/ቤት በኪራይ ማግኘት ይኖርባቸዋል፡፡ ቢያንስ አንድ የተሟላ ፅ/ቤት የሌለው ፓርቲ እንደ ፓርቲ ሊቆም የሚችልበት ሁኔታ የለም፡፡
2.      የፖለቲካ ፓርቲዎች ለሚያደርጉት የአዳራሽ ስብሰባ ማነኛውም አዳራሽ በኪራይ የሚያቀርብ ተቋም/ሆቴል ያለምንም የተለየ የዋጋ ጭማሪ አገልግሎቱን እንዲሰጥ፤
3.      የህትመት አገልግሎት የሚሰጡ ድርጅቶች ፓርቲዎች የሚያቀርቡትን ማንኛውንም የህትመት አገልግሎት ያለምንም ቅድመ ሁኔተታ መስጠት፣ እና
4.      ማንኛውም የፓርቲ አባላት የፓርቲውን ሰነዶች (የድምፅ፣ የምስል፣ የህትመት፣ ወዘተ) በሚያሰራጩበት ወቅት ምንም ዓይነት ጫና በፖሊስም ሆነ በሌላ አካል እንዳይደርስበት ማድረግ፤
ያስፈልጋል፡፡ እነዚዚ ከላይ የተዘረዘሩት ጉዳዮች ለአንድ ፓርቲ ወደ ሕዝብ ቀርቦ አማራጩን ለማቅረብ ወሳኝ ጉዳዮች ናቸው፡፡
ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር እነዚህ ተግባራት አሁንም የሚቻሉ በሕገ-መንሥት እውቅና ያገኙ ናቸው፤ የሚል የድርቅና ሙግት ሲቀርብልን ለረጅም ዓመተት መቆየታችን ይታወቃል፡፡ ትልቁ ችግር እነዚህን መብቶች፤ በውስጥ አስራር በመንግሰት መዋቅር እንዲታፈኑ መደረጋቸው ነው፡፡ የፖለቲካ ምዕዳሩ ጠፍቷል ያስባለው እና ይህን ሕገ መንግሰታዊ ድንጋጌ ለመተግበር የተንቀሳቀሱ ደግሞ ለእስርና እንግልተ የተዳረጉት በዚህ ኢ-ሕገመንግታዊ አሰራር ነው፡፡ ክቡርነትዎም በንግግሮ ሕገ መንግሰቱ ያሰቀመጣቸው ዴሞክራሲያዊና ስብዓዊi መብት የተመለከተቱ ድንጋጌዎች በተሟላ ሁኔታ መከበር እንዳለበተት አፅዕኖት ሰጥተውታል፡፡ መፍትሔውም፤
የቢሮ ችግር ለመፍታት ብዙ አማራጭ ሊታይ እንደሚችል ባስበውም ለዚህ ምላሽ ለመስጠት እንደመነሻ በየወረዳው የተገነቡ የወጣት ማዕከላት አሁን በተለያየ አግልግሎት በአብዛኛው ተከራይተው ምግብ ቤት እና ታይኳንዶ ማሰልጠኛ የሆኑት ሊታሰቡ ይችላሉ፡፡ ጠንከር ያለ መመዘኛ ወጥቶ ለፓርቲዎች ፅ/ቤት እንዲሆኑ ማሰብ ይቻላል፡፡
በሆቴሎች በሚደረጉ ስብሰባዎች የሚተላለፍ መልዕክት፤ ማተሚያ ቤቶች በሚያትሙት መልዕክት ወይም የፓርቲ አባላት በሚያደርጓቸው እንቅስቃሴዎች ውስጥ ህገወጥ ተግባር ተፈፅሞ ቢገኝ አግልግሎት ሰጪዎች ወይም ዝርዝር የፓርቲ ተግባር የሚፈፅሙ አባላት ምንም ዓይነት ተጠያቂነት የሌለባቸው መሆኑ ታውቆ በይፋ መነገር እና በዚህ ጉዳይ ሙሉ ሃላፊነቱን የሚወስደው የፓርቲ አመራር መሆኑን በህግ መደንገግ ይኖርበታል፡፡ በተጨማሪ አገልግሎት ሰጪዎች በማንኛውም ሁኔታ፤ የመንግሰት አካል ነኝ ብሎ በግንባር ቀርቦ፣ በቃል፣ በስልክ ወይም በሌላ ሁኔታ አገልግሎት አቋርጡ የሚል ትዕዛዝ ቢሰጥ፤ ይህን ትዕዛዝ መቀበል እንደሌለባቸው በህግ መደንገግ ይኖርበታል፡፡ ፓርቲዎች በተከራዩት አዳራሽ፣ በሚያሰራጩት ህትመት፣ ወይም ሌላ እንቅስቃሴ ጥፋት መፈፀማቻው በፍርድ ቤት ተረጋግጦ በህግ ሲታገዱ ብቻ አገልግሎት አለመስጠት እንደሚችሉ እንዲያውቁት ማድረግ ያስፈልጋል፡፡ ይህ በአገልግሎት ሰጪዎች እንዲሁም ዜጎች ላይ የተዘራውን ፍርሃት ለመግፈፍ መወሰድ ያለበት እርምጃ ነው፡፡
ክበር ጠቅላይ ሚኒስትር በቁጥጥር ስር የነበሩ ፖለቲከኞች፣ ጋዜጠኞች፣ በመፍታት በጎ ጅምር ታይቷል፡፡ በቀጣይም ሁሉም እስረኞች እንደሚፈቱ እምነታችን ነው፡፡ ይህም በአገር ውስጥ ለመንቀሳቀስ ምቹ ሁኔታ ይፈጥራል፡፡ በአገር ውስጥ በሚፈጠረው አዎንታዊ እርምጃ መሠረት ላይ፤ በማንኛውም መንገድ መንግሰትን መጣል አለብን ብለው ለተነሱት ሀይሎች ጥሪ ማቅረብ እና በሀገራቸው በሰላማዊ መንገድ ሊንቀሳቀሱ የሚችሉበት ምህዳር መፈጠሩን ማሳየትና ማስተማመኛ መስጠት ያስፈልጋል፡፡ እነዚህን ተግባራት ለመፈፀም ክቡርነትዎ አንድ ገለልተኛ ኮሚሽን ማቋቋም ያስፈልጎታል የሚል እምነት አለኝ፡፡ በተቋም ላይ ተቋም ማቋቋም አያስፈልግም፤ የሚል ጎንጭ አልፋ ክርክር ሲነሳ እንደነበር ይታወቃል፡፡ ይህ መንገድ ገዢው ፓርቲ ቁርጠኛ ያለመሆኑን ከማሳየት ውጭ ሌላ ነገር አላስተማረንም፡፡
የሚቋቋመው ኮሚሽን ዋናው ተግባሩ በጥርጣሬ የሚተያዩ ሀይሎች እንዲተማመኑ ምቹ ሁኔታ ከመፍጠር በተጨማሪ አሁን ያሉት ተቋማት በመፈተሸ በሚጠበቅባቸው ደረጃ ከወገንተኝነት ተላቀው እንዲሰሩ ማስቻል ነው፡፡ ይህ ኮሚሽን አፋኝ የምንላቸውንም ሕጎች መፈተሸ ይኖርበታል፡፡ ከዚህ ጎን ለጎን ደግሞ፤ ኮሚሽኑ ለዴሞክራሲው ስርዓት ግንባታ አዎንታዊ ሚና ያላቸው ሚዲያና ሲቪል ማህበራት ህዝቡን በማንቃትና በነፃነት እንዲንቀሳቀስ የሚሰሩበት ሁኔታ እንዲፈጠር መስራት ይጠበቅበታል፡፡ ይህ ሁሉ ግን ሊሆን የሚችለው እርሶዎ በሚመሩት መንግስት እና ግንባር በጎ ፈቃድ ብሎም ለአውነተኛ አገራዊ ለውጥ ባለው ፍላጎት ነው፡፡ ገዢው ግንባር እንዲህ እንዲያደርግ ሊያስገድድ የሚችል ተቃዋሚ ፓርቲ አደረጃጀት በሚያሳዝን ሁኔታ የለም፡፡ አማራጭ ሆኖ የቀረበው ሕዝባዊ እንቢተኝነት መሆኑ ቀጣዩን ተግባር ከባድ ያደርገዋል፡፡ እርሶ የሚመሩት ግንባርና መንግስት የተደራጀ ሀይል አማራጭ እንዲያቀርብ ካላደረጋችሁ፤ ይዋል ይደር እንጂ የተዳፈነው የህዝብ ቅሬታ ይፈነዳል፡፡ አሁን በተያዘው የኢህአዴግ ብቸኛ መስመር ወይም “ጥልቅ ተሃድሶ” ሊፈታ እንደማይችል መታወቅ ይኖርበታል፡፡ መደመር ይኖርበናል፣ ተባብረንም ረጅም ጊዜ ሊወስድብን ይችላል፡፡ ይህ የዜጎች ቅሬታ በተለይ የ30 ሚሊዮን ወጣት ብሶት፤ መንግሰት መደብኩት ባለው ብር 10 ቢሊዮን የሚለዝብ እንዳልሆነ እርግጠኛ ሆኜ መናገር እችላለሁ፡፡
ከብሩነትዎ እርሶም ሆኑ የሚመሩት ግንባር ኢህአዴግ በዚህች ሀገር ውስጥ አዎንታዊ ታሪክ እንዲኖርዎ ፍላጎቴ ነው፡፡ ይህ ከተፈለገ፣ ለዴሞክራሲ ስርዓት ግንባታ በሚል የተሰዉት ክብር እንዲያገኙ ከተፈለገ፤ እስከዛሬ የተከናወኑ በጎ ተግባራት ለቀጣይ የዴሞክራሲ ስርዓት ግንባት እርሾ እንዲሆን ከተፈለገ፣ ወዘተ….ድርጅቶ በፈቃደኝነት የቀረበለትን ቀላል የፖለቲካ ምህዳር ማሻሻያዎቹን ማድረግ ይጠበቅበታል፡፡ ድርጅቶ ቀላሉን ከመለስ ከባዱን አብረን ለመስራት እድል ይገኛል፡፡ ይቻላልም፡፡
አመሰግናለሁ!!!
የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ጊዜ ያለፈበት እና መነሳት እንዳለበት ሳልዘነጋ ነው፡፡

Saturday, March 31, 2018

ዶክተር አብይ አህመድ እንደ ጠቅላይ ሚኒሰትር እና የጦር ኃይሎች ጠቅላይ አዛዥ



ተሰፈኞች ተሰፋ የምናደርገው ሞኞች ስለሆንን አይደለም፡፡ ይልቁንም ጮሌዎች፣ በልጣ ብልጦች ሳንሆን አንቀርም፡፡ ይህም በሠላም የመኖራቸን የጤንነታችን መሠረት እንደሆነን እምነቴ ነው፡፡ ተስፋ ቢስነት ምን ያደርጋል? ተስፋ ቢስነት (Negative Energy) ኃይል ጨራሻ ነው፡፡ በሆነው ባልሆነው ተስፋ እየቆረጥን ኃይላችንን መጨረስ ያለብን አይመስለኝም፡፡ ተስፋ የምትቆርጡ ሁሉ የተሰፈኞችን ቡድን ብትቀላቀሉ ምክሬ ነው፡፡ መፅሃፉ እንደሚለው ለራስህ እንዲሆን የምትወደውን፤ ለባልንጀራህም አድርግ እንደሚለው ማለት ነው፡፡ ባለፈው አቶ ሀይለማሪያም ደሳለኝ በወንበር ገፍ ሥልጣን ሲይዙ “ማወከብ ሳይሆን ማገዝ አለብን” ብዬ ስሟገት ነበር፡፡ ይህን በማለቴ ከፓርቲዬ (ነብሱን ይማርና አንድነት ድንክ ሳይሆን) ጭምር ከፍተኛ ውግዘት ደርሶብኛል፡፡ አይቼ አይቼ ሲበቃኝ ደግሞ ከሁለት ዓመት በፊት መሆኑ ነው፤ እባኮትን ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር ሥልጣን ይልቀቁ ብዬ ፃፍኩ፡፡ ሁለቱም ጊዜ ልክ ነበርኩ፡፡ በእርግጥ ከእኔ በተቃራኒ የቆሙትም ቢሆኑ በራሳች መለኪያ ልክ ናቸው፡፡ ብለን ነበር፤ ይኽው ለውጥ የሚባል ነገር አላመጡም፣ ብለው ሊሟገቱ ይችላሉ፡፡ ልዩነቱ የእኔ ብጤዎች ለተወሰነ ጊዜም ቢሆን በተስፋ ዳቦ ኖረናል፡፡ በእኔ እምነት አቶ ሀይለማሪያም ደሣለኝ ላይ ተሰፋ እንድጥል ያደረጉኝ ነገሮች ሁሉ ተሰፋ ለማድረግ ከበቂ በላይ ነበሩ፡፡ እሳቸው ይህን ሊጠቀሙበት አልቻሉም፡፡ ይህ በወርቅ ሳሕን ታሪክ የሰጣቸውን እድል ባለመጠቀማቸው ጥፋቱ የእርሳቸው እንጂ የእኔ እና የእኔ ቢጤ ተስፈኞች ሊሆን አይችልም፡፡ ዶክተር አብይ አህመድ በአቶ ሀይለማረያም ደሣለኝ ላይ ተስፋ እንዳደርግ ያደረጉኝ ምክንያቶች በሙሉ ያሏቸው ሲሆን ሌሎች ተጨማሪ ችሎታዎችም አይቼባቸዋለሁ፡፡ ሰለዚህ ተሰፋ ማድረጌን እቀጥላለሁ፡፡ ተሰፋዬ እውን ባይሆን አሁንም ጥፈቱ የእኔ ሳይሆን የዶክተር አብይ አህመድ ብቻ ነው ሊሆን የሚችለው፡፡ ዶክተር አብይ አህመድ ለኢህአዴግ ሊቀመንበርነት ሲመረጡ በፌስ ቡክ ገፄ ላይ እንዲህ ብዬ ከትቤ ነበር፡፡ “ለታሪክ የተፃፈን ሰው ከታሪክ መዝገብ መፋቅ አይቻልም፡፡ ከአሁን በኋላ አብይ አህመድ በታሪክ መዝገብ ተፅፏል በደግ ይሁን በክፉ ወሳኙ እርሱና እርሱ ብቻ ናቸው፡፡”
በዚህ መነሻ ዶክተር አብይ በመጪው ለምክር ቤቱ ወይም ደግሞ ለመላው ኢትዮጵያ ሕዝብ በሚያደርጉት ንግግር በምንም መመዛኛ ዝም ብሎ ለሕዝብ ግንኙነት ፍጆታ ተብሎ የሚደረግ የፖለቲካ ቃላት ድረቶ መሆን የለበት፡፡ የጠቅላይ ሚኒስትሩ ንግግር ኢህአዴግን እንደ ፓርቲ ከዘመኑ ጋር ሊያቀራርቡት መስራት እንደሚፈልጉ ሊነግሩን ሙከራ ባያደርጉ እመክራለሁ፡፡ ይህ የድርጅት የቤት ሥራቸው ስለሚሆን የሚያደርጉት ንግግር በሙሉ መቃኘት የሚኖርበት በጠቅላይ ሚኒስትርነት እና የጦር ኃይሎች ጠቅላይ አዛዥ በመሆናቸው የሚያደርጉት ንግግር መሆን ይኖርበታል፡፡ ይህን ካልተረዱት የውድቀታቸው መጀመሪያ ይሆናል፡፡ ጠቅላይ ሚኒሰትር ሀይለማሪያም መውደቅ የጀመሩት “የመለስን ራዕይ አስቀጥላለሁ”፣ “ዘላለማዊ ክብርና ሞገስ ለታላቁ መሪ”፣ ወዘተ ማለት ሲጀምሩ ነው፡፡ ተሰፋ ሳንቆርጥ አሻራዎን ያኑሩ ክቡር ጠቅላይ ሚኒሰትር ብንልም አልሰሙን፡፡ መጨረሻቸው ይህ ሊሆን፡፡
ዶክተር አብይ ኢህአዴግን ለሃያ አንደኛው ክፍለ ዘመን የሚሆን ፓርቲ ማድረግ ለእኔ እና ለእኔ መሰል ዜጎች አንድም የሚፈይደው ነገር እንደሌለው መረዳት አለባቸው፡፡ ይህ ለፓርቲ አባሎቻቸው ማድረግ የሚገባቸው ንግግር ነው፡፡ በፓርቲያቸው ጠቅላላ ጉባዔ ላይ ይህን ንግግር ማቅረብ ተገቢ ቦታ ነው፡፡ እኛ ክቡር ጠቅላይ ሚኒሰትር በንግግራቸው ውስጥ እንዲያካትቱት የምንፈልጋቸው ነገሮች አሉ፡፡ ዋና ዋናዎቹን በመጠቆም ሃላፊነቴን ለመወጣት እሞክራሉ፡፡
ፖለቲካዊ ጉዳዮች፤ የኢትዮጵያ አገራችን ፖለቲካ በመንግሰት ሚዲያ ሠላም፣ሠላም፣ ሠላም በሚሉ ዘፈኖች፤ እንዲሁም በቴሌቪዥን በሚበሩ ነጫጭ ወፎች የሚገኝ አይደለም፡፡ የኢትዮጵያ ፖለቲካ ፈውስ የሚያገኘው፣ ሁሉም ዜጋ በአገሬ ጉዳይ ያገባኛል ብሎ በመረጠው መስመር መደራጀት እና ሃሣቡን በነፃነት ለህዝብ ማቅረብ ሲችል፡፡ ሃሣቡን የሚያቀርብበት መድረክ ደግሞ ክፍት እንዲሆን ማድረግ፤ የመንግስት ሃላፊነት ነው፡፡ ባለፉት ሃያ ሰባት ዓመታት ይህ ሊሆን ባለመቻሉ በነፍጥ ያሸነፉት ቤተ መንግሥት በገቡ ማግስት ሌሎች ደግሞ ጥራኝ ጫካው፣ ጥራኝ ዱሩ ብለው ነፍጥ አንስተዋል፡፡ ይህ ሁኔታ ለአንዴ እና ለመጨረሻ ጊዜ እንዲቀለበስ በማንኛውም ሁኔታ ነፍጥ አንስተው ሥርዓቱን ለመጣል የተሰለፉትን ቡድንኖች ወደ ሠላማዊ መድረኩ እንዲመጡ ከልብ የመነጨ ከፖለቲካ ብልጣብልጥነት የፀዳ ጥሪ መደረግ ይኖርበታል፡፡ የሂደቱን ታማኝነት ለማረጋገጠ ደግሞ ገለልተኛ የሆኑ አካላት እንዲሳተፉበት ማደረግ ክብር ያሰጣል እንጂ ውርደት ሊሆን የሚችልበት አንድም ምክንያት አይኖርም፡፡ ይህን ጉዳይ መምራት የክቡር ጠቅላይ ሚኒሰትሩ ኃላፊነት ነው፡፡ በሴራ የተካኑ የቀድሞ ፖለቲከኞች በፍፁም ከዚህ ተግባር ለአገር ፖለቲካ ድህነት ሲባል መራቅ ይኖርባቸዋል፡፡ ቢቻል በፈቃዳቸው ገለል በማለት ሥራቸውን እንዲያቀሉላቸው ጥሪዬን አቀርባለሁ፡፡
በአገር ውስጥ በመንቀሳቀስ ላይ የሚገኙ የፖለቲካ ኃይሎችም ሆኖ ሌሎች ለመንቀሳቀስ ፍላጎት ያላቸው ሁሉ በአገር ውስጥ መንቀሳቀስ እንዲችሉ የሚያስችል ምቹ ሁኔታ መፍጠር የግድ መሆኑን ያህል፤ በግል ጥቅም (ሥልጣን፣ ገንዘብ ወይም ሌላ ሊሆን ይችላል) ተነሳሰተው ሕዝብን አደጋ ላይ ሊጥል የሚችል እንቅስቃሴ ለማድረግ ፍላጎት ያላቸውን ሀይሎች ለመቆጣጠር እና ለማጋለጥ የሚያስችል ጠንካራ የሲቪል ማህበራትና የሚዲያ ተቋማት ሚናቸውን ማሳደግ ያስፈልጋል፡፡ ሲቨል ማህበራት ሕዝቡ አማራጮችን ገምግሞ እንዲወስን ውሣኔውን ደግሞ መቼና እንዴት እንደሚያደርግ ማሰተማር እንዲችሉ ድጋፍ ማድረግ የግድ ነው፡፡ ሚዲያዎች አሁን ካለቸው የአየር ሰዓት ሕዝቡ አማራጨን ለማድመጥ እና ለመመልከት እንዲችል ማድረግ እንዲችል መፈቀድ ይኖርበታል፡፡ ማለትም አሁን የተጫነባቸው የፍርሃት ቆፈን በጠቅላይ ሚኒሰትሩ ንግግር ተስፋ እንዲጫርባቸው ያስፈልጋል፡፡
ዜጎች የተሳሳተ አማራጭም ቢሆን የመምረጥ መብት አላቸው፡፡ ይህ መብታቸው ሊከበር ይገባል፡፡ በተጨማሪ፤ የክልል መንግሰታት ነፃነት ሊከበር እና ፌዴራል መንግሰቱ ደግሞ በጥብቅ የሰብዓዊ መብት አያያዛቸውን ሊከታተል እንደሚገባ ጠቅላይ ሚኒሰትሩ ማስገንዘብ ይኖርባቸዋል፡፡ የክልል መንግስታት የፖለቲካ ነፃነት ለአካባቢያቸው እድገት ብቻ ሳይሆን ለሠላማችን ጭምር ወሳኝ ግብዓት ነው፡፡ የፌዴራል መንግሰቱ ከማገዝ የዘለለ ሚና ሊኖረው አይችልም፡፡ የመድበለ ፓርቲ ሥርዓት የሚወለደው በክልሎች እንደሆነ በግሌ ይሰማኛል፡፡
ከላይ ከተገለፁት አጭር ፖለቲካዊ ጉዳዮች በተጨማሪ ክቡር ጠቅላይ ሚኒሰትሩ እንዲያነሷቸው የሚጠበቀው፤ ምን አልባት በተሻለ ያስቀምጡታል ብዬ የማስበው ኢትዮጵያዊያን ያለን ማህበራዊ ግንኙነት በዘርና ብሔር መከፋፈል እንደሌለበት ይህም ከከፍታችን ያወርደን እንደሆነ እንጂ የሚጨምርልን ነገር አለመኖሩን፣ ሁሉም ዜጋ አገሩ የጋራ መሆኑን አፅዕኖት ይሰጡታል ብዬ አምናለሁ፡፡ ኢትዮጵያዊነታችን የሚደምቀው በማህበራዊ ግንኙነታቸን ውስጥ እንጂ ባለን የፖለቲካ ልዮነት ወይም አስተሳሰብ ሊሆን አይገባም፡፡ ይህን ስፅፍ በፆም ወቅት ምርጥ ዶሮ ወጥ በህሊናዬ እየታየኝ ነው፡፡
ከሁሉም በላይ በአገራችን ኢትዮጵያ ከፍተኛ የኢኮኖሚ እድገት ተመዝግቧል እየተባለ፤ አንዱ በፎቅ ለይ ፎቅ ሲደርብ ሌላው ለምፅዋት እጁን የሚዘረጋበት የኤኮኖሚ ስርዓት መፍረሱን ማብሰር አለባቸው፡፡ ፍትሓዊ ተጠቃሚነት ሲባል፣ ዜጎች በኤኮኖሚ ደረጃ መለያየት መኖሩን ማስወገድ የማይቻል ቢሆንም ልዩነቱ ግን በጥረት የሚመጣ እንጂ ከባልሥልጣን ጋር በመሻረክ እና የእገሌ ዘር በመሆን እንደሌለበት መሰመር ያለበት እና ሁሉም ኢትዮጵያዊ ለሥራ ታጥቆ እንዲነሳ ሊያበረታቱት ይገባል፡፡ ፍትሓዊ ያልሆነ ተጠቃሚነት ምንጩ የፖለቲካ ሥርዓት በመሆኑ ይህ ደግሞ ቀድሞ ማህበራዊ ግንኙነታችንን ቀጥሎም ደግሞ ሥርዓቱን እንደሚገረስሰው ፍንትው ብሎ ታይቷል፡፡ መቼም ይህ ያልተገለፀለት የኢህአዴግ አባል ካለ ችግር ላይ መሆኑን ማስታወስ ያስፈልጋል፡፡
ባለፈው ሶሰት ዓመታት በአገራችን በፖለቲካው ውጥንቅጥ መንስዔ ማህበራዊ እሴቶቻችን እንዲሁም የኤኮኖሚ መሰረቶቻችን አደጋ ላይ ወድቀዋል፡፡ ሰለዚህ ፖለቲካውን በማከም አገራችንን ከውድቀት ልንጠብቃት የግድ ይለናል፡፡ ማንኛውም ዜጋ ደህንነቱ የሚረጋገጠው ኢትዮጵያዊ መንግሰት ሲኖር መሆኑን በማመን የእኔ ብሔር መከላከያ፣ የእኔ ብሔር ደህንነት ካልሆነ አደጋ ላይ እወድቃለሁ ከሚል ስጋት ነፃ እንዲሆን ማድረግ የመጪው ጠቅላይ ሚኒሰትር ትልቁ ሥራ ነው፡፡ የመከላከያ እና የደህንነት እንዲሁም የፖሊስ ተቋማት በሙሉ ለዜጎችና ለአገር ደህንነት እንጂ ለአንድ ቡድን ታዛዥ የሚሆኑበት ሥርዓት ማክተም ይኖርበታል፡፡ የዜጎችን ሃሣብ የሚሰልል ተቋም አያስፈልገንም፡፡ ዜጎችን ከውጭ ጠላት የሚጠብቀን ሠራዊት ያስፈልገናል፡፡ በአገልግሎታችሁ እንኮራለን የምንላቸው የሠራዊት አባላት ይናፍቁናል፡፡ በትምህርት ቤት የሠራዊት ቀን ተብሎ ዩኒፎርም ለብሰው ልጆቻችን ፎቶ ሲነሱ ለማየት ይናፍቀናል፡፡ የኢትዮዮጵ መለዮ ለባሾች ልብስ ዜጎችን ማስፈራሪያ መሆኑ ማብቃት ይኖርበታል፡፡
መልካም የሥራ ዘመን ክበር ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ
ከግርማ ሠይፉ ማሩ


Tuesday, March 27, 2018

ኢትዮጵያችን በመንታ መንገድ በገደል አፋፍ ትገኛለች ዜገች ምን እንወሰን?



የአገራችን ፖለቲካ መበላሸቱ ብቻ ሳይሆን፣ የአገር እልውናን አደጋ ላይ የሚጥል ሊሆን እንደሚችል ስጋት ያላቸው ብዙ ናቸው፡፡ እኔም የፈለገ ተሰፈኛ ብሆን ከዚህ ስጋት ነፃ ነኝ ልል አልችልም፡፡ አፍቃሪ ህወሓት/ኢህአዴግ የሆኑ የማህበራዊ ሚዲያም ይሆን ሌሎች መገናኛ ብዙዓን ይህን ስጋት አጉልተው ለማሳየት የማያደርጉት ጥረት የለም፡፡ ከጥረታቸው ሚዛን የሚደፋው በቅርቡ በመታመስ ላይ ያሉተን ሊቢያ፣ ሶሪያና የመንን እንደምሣሌ በማቅረብ ነው፡፡ ይህ በምሥልና ድምፅ እየተደገፈ የሚቀርበው ዘግናኝ ትዕይንት ለመማር ለሚፈልግ ጥሩ ማሣያ ነው፡፡ ነገሩ ግን ሌላ ነው፡፡ እንደ እነዚህ አገሮች እንዳንሆን አርፋችሁ ተቀመጡ የሚል መልዕክት ያዘለ፣ ሠላም፤ ሠላም፤ ሠላም በሚል መዝሙር አጅበው ማቅረባቸው ነው፡፡ ሊቢያ፣ ሶሪያ እና የመን ለዚህ ደረጃ ያበቋቸው አንባገነን መሪዎች ናቸው፡፡ ከዚህ መማር ያለባቸው አንባገንን መሪዎች እንጂ ህዝቡ ሊሆን አይችልም፡፡ መቼም በእነዚህ አገሮች ውድመት ህዝቡ ነው ተጠያቂ የሚል ሰምቼም አንብቤም አላውቅም፡፡ የእኛም አገር መሪዎች እባካችሁ አገራችን እንደነዚህ አገሮች እንዳተትሆን ከግል ሥልጣን መሻት እና ሌላ ማንኛውም ግላዊ ፍላጎት እራሳችሁ አፅድታችሁ ታሪክ ስሩ እያልነናችሁ ነው፡፡ ኢትዮጵያ ከላይ ከተጠቀሱት አገሮች እንደ አንዳቸው እንዳትሆን ኃላፊነቱ ያለው በፖለቲካ መሪዎች ይልቁንም በህወሓት/ኢህአዴግ እጅ ውስጥ ነው፡፡
አገራችን በመሰቀለኛ መንገድ ላይ እንደምትገኝ፡፡ ከመገዶቹ ዳር እና ዳር ደግሞ ጥልቅ ገደል መኖሩን እንገነዘባለን፡፡ ትክክለኛውን መንገድ መምረጥ እና ከገደሉ መራቅ የግድ ይላል፡፡ ይህ የአሰተዋይ ምርጫ ነው፡፡ የሰሞኑ ነገሮችን አያያዝ ለሚያስተውል ግን የብልዕ አያያዝ አይመስልም፡፡ እስረኞችን መፍታት መጀመሩ በጎ ጎኑ ሲሆን ሌሎችን ያለመፍታት ሲከፋም በተመሳሳይ ሁኔታ እስርን መጀመሩ አሳኙ ክስተት ነው፡፡ እስረኞች የተፈቱበት ምከንያት ለጋራ አገር በጋራ መፍትሔ ለመፈለግ የመሰለን ሰዎች ተሳስተናል ማለት ነው፡፡
የኢህአዴግ አባል ድርጅቶች ፖለቲካ ምህዳር ለማስፋት በቁርጠኝነት የተሻሉ እርምጃዎች ይወሰዳሉ የሚለው ቀርቶ ለቀጣይ ስድስት ወር በአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ስር እንድንሆን ያለፍላጎታችን ሲፈረድብን ደግሞ የበለጠ ግምታችን የተሳሳተ፣ ተሰፋችንም የዕልም እንጀራ እየሆነብን ይገኛል፡፡ ሌላው ተሰፋ የጣልንበት ወፌ ቆመች እያልነው የነበረው ፓርላማ መዋረዱ ተስፋችንን ያጨልምብናል፡፡ ፓርላማውን የሚያዋርዱት ደግሞ “የተከበሩ” ተብለው በምክር ቤት ውስጥ ያሉት ጭምር መሆናቸው ነው፡፡
እንዲህ እንድንል የሚያድርገን ደግሞ ግንባሩ ከዚህ በፊት በሚስጥር ሲያደረግ የነበረው ሁሉ አሁን በይፋ እያደረገው መሆኑ ነው፡፡ ግንባሩ ሸፍጥ እና የሸፍጥ ድርጅት እንደሆነ በግልፅ አውቀናል፡፡ በቅርቡ ኢህአዴግ እንደ ግንባር የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ያስፈልገኛል ብሎ ቆርጦ ተነስቷል፡፡ በግልፅ ቋንቋ ወታደራዊ አገዛዝ ያስፈልገኛል እያለ ነው፡፡ ይህን ደግሞ በኢህአዴግ ስራ አስፈፃሚ በተለመደው አካሄድ ከፀደቀ በኋላ ወደ ካቢኔ በመሄድ ለወጉ እንዲፀድቅ ተደርጓል፡፡ ፓርቲው ያፀደቀውን የመንግሰት አካል ተብዬው “ካቢኔ” የሚባለው የሚቃወምበት አቅም የለውም፡፡ ለዚህ ነበር ቴክኖክራት ካቢኔ ዋጋ የለውም ስንል የነበረው፡፡ ይህ ጉዳይ ወደ ፓርላማ መቅረብ ሰለነበረበት ደግሞ በተመሳሳይ በፓርላማ አባላትም ቀድመው ውይይት እንዲያደርጉ በየድርጅቶች የስራ አሰፈፃማዊ ውሳኔው ተነገራቸው፡፡ ውይይቱ ውሣኔ ለመቀየር ሳይሆን እንደተtለመደወ የስራ አሰፈፃሚውን ውሳኔ እንዲቀበሉ ነበር፡፡ ድርጅታዊ ማዕከላዊነት በሚባል አስራር፡፡ ይህ በተመሳሳይ አጋር ለሚባሉት ድርጅቶችም ተደርጓል፡፡ ሁለት ሶሰተኛ ድምፅ የሚያስፈልግ በመሆኑ 46 ድምፅ ያላቸውን አጋሮችንም ችላ ማለት ሳያስፈልግ፣ አፈ ጉባዔው ፈልገውት እንደነበረው በተባበረ ድምፅ ለማጽደቅ ታስቦ ነበር፡፡ በኢትዮጵያ ህዝብ ላይ ቲያትር ለመስራት፡፡
ድርጅቶቹ ውስጥ ለውስጥ ውሳኔ ካሳለፉ በኋላ ምክር ቤት ሰብሰባ ብለው ይቀመጡና ለቀለድ ጥያቄና መልስ ሲያደርጉ ቆይተው በሙሉ ድምፅ ፀደቀ ለማለት አፋቸው ደንቀፍ ሳይል ለማጠናቀቅ ወስነው ነበር፡፡ ይህን የድርጅታዊ አስራር በመተማመን ነበር አፈ ጉባዔ አባዱላ ገመዳ በተባበረ ድምፅ እንዲፀድቅ የሚል ደፋር ጥያቄ ለምክር ቤት ተብዬው ያቀረቡት፡፡ ለማንኛውም ይህ እንዲሆን ለጊዜውም ቢሆን ያልፈቀዱት እጅግ ብዙ አባላት በታሪክ ፊት በኩራት የሚያቀርባቸውን ውሳኔ ወስነዋል፡፡ በየድርጅቱ ሲደረገ ከነበረው ውትወታና ማገባባት ይልቅ ወደ ሕዝብ ድምፅ፤ የህሊና ፍርድ እና ሕገ መንግሰቱን ወደ ማክበር አድገዋል፡፡ ይህ የፈጣሪ ስራ ነው፡፡

ከህዝብ ጀርባ፤ ከህዝብ ፍላጎት ውጭ ይህ ሁሉ ሲደረግ በእኔ አሰተያየት አቶ ሀይለማሪያም ደሣላኝ ከስልጣን ለመልቀቅ ጥያቄ አቀረብኩ ከሚሉን፤ በእውነትም የለውጡ አካልና መሪ ሊሆኑ የሚችሉበትን እድል በሚያሳዝን ሁኔታ አሳልፈው ሰጥተዋል፡፡ ይህንን ምክር ቤት በህገ መንግሰቱ አንቀፅ 60 መሠረት በትነው በስድስት ወር ውስጥ ምርጫ በማድረግ ለአሸናፊ ስልጣን ማስረከብ ነበር፡፡ ይህ ታሪክ በወርቅ ሳህን ያቀረበላቸውን እደል ሳይጠቀሙበት አልፈዋል፡፡ እናዝናል፡፡ አሁን ደግሞ ማንም ይሁን የሚመጣው ጠቅላይ ሚኒስትር ታሪክ እንዳይስራ እንቅፋት የሚሆን አፈና በአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ስም ለምን እንዳሰፈለገ አልገባንም፡፡ ለለውጥ የተነሳን ህዝብ ማንኛውም የአፈና አካሄድ አያቆመው፡፡ በውሰጥ ለውስጥ ስምምነት ተደርጎ በመጣ ውሳኔ በምክር ቤት ስም ለማላገጥ የመጣን ቡድን አምላክ በኪነ ጥበቡ አጋለጠለን፡፡ አሁን የተፈጠረው የቁጥር ስህተት ለአንደኛ ደረጃ ተማሪም ቢሆን ከባድ አልነበረም፡፡ እንኳን ስማርት ፎን/ስልክ ይዞ ሂሣብ ለሚስራ የምክር ቤት አፈ ጉባዔ፡፡ ፈጣሪ ግን ከኢትዮጵያ ሕዝብ ጀርባ የተሰራን ሴራ በአደባባይ አጋልጦልናል፡፡ ይህን ሸፍጥ ለማጋለጥ ብርታት ላገኙት የምክር ቤት አባላት ምስጋና እና ክብር ይገባቸዋል፡፡ ይህን ስህተት ማረሚያ መንገድም ወደ ምክር ቤቱ መድረክ ተመልሶ በግልፅ በሚሰራ ማስተካከያ ብቻ ነው፡፡
በዚህ አጋጣሚ አቶ ሀይለማሪያም ደሣለኝ እድላቸውን ባይጠቀሙበትም ሌሎች ታሪክ እንዲሰሩ እድል ፈጥረዋል ለማለተም ይቻላል፡፡ አዲሱ ጠቅላይ ሚኒሰትር ማን ይሆናል? የሚል ጥያቄ እንዲነሳ በማድረግ፡፡ ነገር ግን ይህ አዲስ ጠቅላይ ሚኒስትር የመሰየም ጣጣ አሁንም በድርጅት ሴራና አሻጥር ውስጥ መውደቁ አሳዛኙ የህወሓት/ኢህአዴግ ቲያትር ሌላኛው ክፍል ነው፡፡ ሰሞኑን አዲሱ ጠቅላይ ሚኒሰትር ማን ይሁን? የሚለው ጥያቄ እያስነሳ ያለው ጭቅጭቅ የኢትዮጵያ ህዝብ በግልፅ መሪውን የመምረጥ ፍላጎት ብቻ ሳይሆን አቅም አንዳለውም የሚያመላክት ነው፡፡ ከዚህ ቀደም ህወሓት በተለይ አቶ መለስ ዜናው በህዝብ ዘንድ ያላቸውን ዝቅተኛ ተቀባይነት ከግምት በማስገባት “ፓርላሜንታዊ ሥርዓት” በሚል ሸፋን ዜጎች መሪያቸውን በቀጥታ እንዳይመርጡ ይልቁንም ድርጅቶች ከህዝብ ጀርባ መሪ ተብዬ የሚመርጡበት ሴራ ሰርተውብን አልፈዋል፡፡ ይህ አካሄድ ግን ማብቂያው ጊዜ ደርሷል፡፡ ራዕይ አለኝ፣ የኢትዮጵያን ህዝብ ለመምራት እችላለሁ የሚል ዜጋ በይፋ ወጥቶ ለህዝብ ቀርቦ ዳኝነቱን ከህዝብ መጠበቅ አለበት፡፡
ኢትዮጵያዊያን በመንታ መንገድ በገደል አፋፋ ላይ ብንገኝም መውጫውን መንገድ እናውቀዋለን፡፡ ደንቃራ የሆነብን አብዮታዊ ዴሞክራሲ የሚባለው መንፈስ እና የመንፈሱ ተሸካሚ የሆኑት የህወሓት/ኢህአዴግ አመራሮች ናቸው፡፡ ለዚህች አገር ትንሣዔ ሲባል አገራችን የጋራ መሆኗን ከግንዛቤ በማስገባት በጋራ መፍትሄ እንፈልግ፡፡ ቀጣዩ ጠቅላይ ሚኒሰትር ከዚህ የሚበልጥ ታሪካዊ አጋጣሚ አያገኝም፡፡ ይህን እድል ይህችን ትልቅና ታሪካዊ አገር ወደ ከፍታው ማማ ለማውጣት በጋራ አብረን እንቁም!!!!!
ግረማ ሠይፉ ማሩ
መጋቢት 2010

Wednesday, February 21, 2018

አገራችን ኢትዮጵያ ወደ ዲሞክራሲያዊ ስርዓት በሰላም እንድትሸጋገር ለማድረግ የቀረበ የመነሻ ኃሣብ



ግርማ ሠይፉ ማሩ
ሕዳር 2010
ኢትዮጵያ ሀገራችን አሁን የምትገኘው ዜጎች የሰብዓዊና ዲሞክራሲያዊ መብቶች በህገመንግሰት በተቀመጠው መሰረት የማይከበርበት፤ይህን ለማድረግ የሚያስችል የፖለቲካ ስርዓት መፍጠር የሚጠበቅባቸው የፖለቲካ ፓርቲዎች በፍፁም መንቀሳቀስ ያልቻሉበት እና የአንድ ፓርቲ ፍፁም አንባገነን ኢ-ዲሞክራሲያዊ አገዛዝ የሰፈነበት ሁኔታ ነው፡፡ አሁን በሀገራችን የሚታዩት ዘርፈ ብዙ ችግሮች በምንም መመዛኛ ኢህአዴግ እንደሚለው በኢህአዴግ መስመር ብቻ የሚፈቱ አይደሉም፡፡ ሰለ እውነት ለመናገርም በኢህአዴግ አገዛዝ ብቻ የተፈጠሩም አይደሉም፡፡ ሰለዚህ ሁሉንም ባለድርሻ ተሳታፊና ባለቤት ሊያደርግ የሚችል ሁሉን አቀፍ መፍትሔ መፈለግ ወቅቱ የሚጠየቀው ወሳኝ ጉዳይ ሆኖ ከፊታችን ቀርቧል፡፡
ችግር መኖሩን ተገንዝበው እጅግ ብዙ ባለሞያዎች እና ያገባናል የሚሉ ዜጎች በተደጋጋሚ አሰተያት ሲሰጡ የነበረ መሆኑ ይታወቃል፡፡ ባለፉት ሁለት ዓመታት ያለንበትን ሁኔታዎች በግልፅ የተገነዘቡ የተለያዩ አካላት ቀደም ሲል የህወሃት ታጋዮች የነበሩና ስርዓቱን ሲያገለግሉ የነበሩ ሰዎችን ጨምሮ ችግሩ መኖሩን እና ለውጥ እንደሚያስፈልግ ምክር እየለገሱ  ሲሆን፣ ችግር መኖሩን መንግሰትም ቢሆን የካደው ጉዳይ አይደለም፡፡ መንግሰት ችግሩን አምኖም የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ለማወጅ መገደዱ ይታወሳል፡፡ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ከተነሳም በኋላም ሁኔታዎች መሻሻል አለመታየቱ ብቻ ሳይሆን፤ መንግሰት ችግሮቹን በኢህአዴግ መስመር እፈታቸዋለሁ ከሚለው አቋሙ ፈቀቅ ማለቱን የሚያሳይ ፍንጭ ያለመታየቱ፣ ጉዳዩን በማባባስ ሌሎች ሀይሎችም ማንኛውንም አማራጭ ተጠቅመው ለውጥ ለማምጣት መወሰናቸው እና ህዝቡ በይፋ “በቃ” ብሎ አደባባይ መውጣቱን መቀጠሉ ነው፣ የምንወዳት አገራችን በጥፋት ጎደና ላይ እንደሆነች እንዲሰማን እያደረገ ያለ ያፈጠጠ ሀቅ ነው፡፡
የዚህ ምክር ሃሣብ ዓላማም መንግሰት ለዚህ ውስብስብ ችግር በተናጠል መፍትሔ ለማምጣት የማይችል መሆኑን በመገንዘብ አቋሙን እንዲያለሳልስ በመጠየቅ በመፍትሔ ፍለጋው ላይ ሌሎች ኃይሎችም እንዲሳተፉበት ለማድረግ ፖለቲካዊ እርምጃ እንዲወስድ ሲሆን፤ ሌሎች ተሳታፊ ኃይሎችም በተመሳሳይ አቋማቸውን እንዲያለዝቡ እና ወደ አማካይ መስመር እንዲመጡ ለማድረግ መንገዱ ተቀራርቦ መወያየት መሆኑን ለማሳየት ነው፡፡ ህዝቡም አሁን የጀመረውን የመብት ጥያቄ መስመር ወደ ከፋ ብጥብጥና ቀውስ ሳያድግ የሚፈልገውን ለውጥ በዲሞክራሲያዊ መስመር ማሳካት የሚችልበትን ምቹ ሁኔታ የሚፈጠርበት ሁኔታ መኖሩን በማመን ወደ መደበኛ ተግባሩ እንዲያተኩር ለማስቻል ነው፡፡  
በሀገራችን ኢትዮጵያ በዋነኝነት በፖለቲካ መድረክ ተሳትፎ አለን የምንል በግራም ሆነ በቀኝ መታዘብ የሚቻለው ሀቅ ቀደም ሲል በተከናወኑ ለታሪክ መተው ባለባቸው ኩነቶች ላይ ስንነታረክ እና በአንድ ወይም በሌላ አጋጣሚ አባል የሆንበትን ቡድን በመከላክል እና ሌላውን ጥፋተኛ በማድረግ/Self Defensing and Blaming Others/ ላይ ያተኮረ ነው፡፡ ይህ አካሄድ ከአርባ ዓመታት በላይ አብሮን በመኖሩ ተፍጥሮዋዊ እስኪመስለን ድረስ ተዋህዶን ለልጆቻችን እያስተላለፍን እንገኛለን፡፡ ከዚህ አዙሪት ለመውጣት የሚያስችል የመፍትሔ ሃሳቦች በተለያዩ አካላትና ግለሰቦች ቀርበዋል፤ ነገር ግን ሰሚ አግኝቶ ወደ ተግባር መግባት አልተቻለም፡፡ አሁንም ይህን የመፍትሔ ሃሣብ ትኩረት ሰጥቶ ወደ ተግባር መሸጋገር ከፊታችን የተደቀነ ወሳኝ የወቅቱ ፈተና ነው፡፡ ኳሱ በገዢው ፓርቲ ሜዳ ቢሆንም ሌሎችም ትኩረት ሰጥተው መንቀሳቀስ ይኖርባቸዋል፡፡
አሁን በሀገራችን ያለው ነባራዊ ሁኔታ ባጠቃላይ ሲታይ ገዢው ፓርቲ እና መንግስት ዜጎች የሚፈልጉትን ኢኮኖሚያዊ፣ ማህበራዊና ፖለቲካዊ ጥያቄዎች በአግባቡ እና በተገቢው መንገድ ለመመለስ ያለመቻላቸውን በግልፅ የሚያመላክት ነው፡፡ የዜጎች ሁለገብ ጥያቄዎች በተበራከቱበት እና መንግሰት ጥያቄዎቹን መመለስ ባልቻለበት ሁኔታ በተደረገ “ምርጫ” ገዢው ፓርቲ መቶ-በመቶ ምርጫ አሸንፊያለሁ ብሎ ስልጣን ላይ ለመቆየት በወሰነበት የመጀመረያ ዓመት ጀምሮ በመላው ሀገሪቱ ከፍተኛ ህዝባዊ ንቅናቄዎች ተፈጥረው ለብዙ ዜጎች በአሳዛኝ ሁኔታ ህይወት መጥፋት ምክንያት የሆነ ሲሆን፤ እጅግ በርካት ንብረቶችም ወድመዋል፡፡ ይህ ሁኔታ በዚሁ እንዲቀጥል ከተተው ሀገሪቱ ልትወጣው ወደማትችለው የቀውስ አዙሪት ውስጥ ልትገበ እንደምትችል የብዙዎች እምነት ነው፡፡
አሁን በሀገራችን ያለውን ቸግር ለመፍታት ዋነኛውና ወሳኝ ጉዳይ ሁሉም ያገባኛል ባይ “የእኔ መንገድ ብቻ ነው ልክ” ከሚል ግትር አስተሳሰብ ወጥቶ ለውይይት እራሱን በማዘጋጀት “በሰጥቶ-መቀበል” ስልጡን ፖለተካ አካሄድ መፍትሔ እንደሚገኝ በማመን፣ በሂደቱ ውስጥ ለመሳተፍ ሲወስን ነው፡፡ ሁሉም አሸናፊ ሆኖ የሚወጣበት/win-win/ መንገድ ለመፈለግ ተነሳሸነት መውሰድ የግድ የሚልበት ወቅት ላይ እንገኛለን፡፡ መንግሰት ከፓርቲዎች ጋር እየተወያየሁ ነው፣ በሚል የተለመደውን በድርድር ሰም በሕዝብና በአገር ላይ የሚደረግ ቀልድ መቆም እንዳለበት  በዚሁ አጋጣሚ አብክሮ መጠቆም አስፈላጊ ይመስለኛል፡፡ በአገራችን ያለው ችግር የምርጫ ስርዓት ሳይሆን የፖለቲካ ምዕዳሩ ሆን ተብሎ ለአንድ ገዢ ቡድን መተዉ ነው፡፡
ይህ ፅሁፍ ሁሉም አሸናፊ ይሁን ከሚል መንፈስ እና ማንም ተንበርካኪ ሆኖ በተሸናፊነት ሰሜት የሚቀርብበት መሆን የለበትም፤ የአገሬ ገዳይ ያገባኛል በሚል መነሻ የተዘጋጀ ነው፡፡ ይህ ኃሣብ መድረሻው ቢዘገይ በቀጣይ 2012 በሚደረግ ምርጫ ኢህአዴግን ጨምሮ ሁሉም የፖለቲካ ፓርቲዎች በነፃ በሚያደርጉት ውድድር ተጠያቂነት ያለበት መንግሰት እንዲመሰረት የሚያስችል ጥርጊያ መንገድ መክፈት ነው፡፡ ይህን ለማድረግ መንግሰት የሚጠበቅበት አሁን ከያዘው ብቻዬን መልስ እሰጣለሁ ማለቱን ማቆም ሲሆን፣ ሌሎች ተፉካካሪዎችም እኛ ከምንለው ውጭ ከሚል ግትር አቋም እራሳቸውን መግራት ይጠበቅባቸዋል፡፡ ይህን የመፍትሔ ኃሣብ ተግባራዊ ለማድረግ መነሻ የሰምምነት ነጥቦች/Point of Reference or Pillars/ የሚከተሉት ቢሆኑ ከተለመደው የቀድሞውን አጥፍቶ ከዜሮ ከመጀመር የዜሮ ድምር አስተሳሰብ የሚታደግ ይሆናል፡፡ ሰጥቶ የመቀበል አስተሳሰብም በተግባር እነዚህን ነጥቦች ከመቀበል ይጀምራል፡፡
1.  አሁን ተግባራው እንዲሆን የሚታሰበው የፖለቲካ ምዕዳር ማስፋት እንቅስቃሴ/Political Reform/ ህገ-መንግሰቱን መስረት አድርጎ ሲሆን፣ ህገ መንግሰቱ እንደ አስፈላጊነቱ በህዝብ ይሁንታ ሊሻሻሉ የሚችሉ ጉዳዮች እንዳሉት ከግንዛቤ በማስገባት ነው፡፡ ህገ መንግሰቱ እንዲሻሻል ፍላጎት ያላቸው ሀይሎች አማራጫቸውን በሚፈጠረው ነፃ የፖለቲካ ምዕዳር ማቅረብ ይችላሉ፡፡
2.  ነፃ፣ ፍትሃዊና ዲሞክራሲያዊ ምርጫ (በሁሉም ተወዳዳሪዎች በቂ ዝግጅት ለማድረግ የሚሰጠው ጊዜ እንደተጠበቀ ሆኖ ቀኑ በሂደት የሚወሰን ይሆናል ነገር ግን ከግንቦት 2012 ሊያልፍ አይችልም) ተደርጎ መንግሰት እስኪመሰረት ድረስ ኢህአዴግ እና አጋር ፓርቲዎች የመንግሰትን የዕለት ከእለት ተግባራትን በከፍተኛ የሃላፊነት ሰሜትና ተጠያቂነት እንዲወጡ መፍቀድ፡፡ ወሳኝ በሆኑ አገራዊ ጉዳዮች ላይ ምንም ዓይነት ውሳኔ ከመስጠት እንዲታቀቡ ማድረግ፡፡
3.  የፓርቲና የመንግሰት ስራ በግልፅ ተለይተው ይከናወናሉ፡፡ ኢህአዴግ እንደማንኛውም ፓርቲ በሂደቱ ውስጥ ተሳትፎ ያደርጋል የመንግሰት ሃላፊዎች ያለባቸውን የመንግሰትና የፓርቲ ኃላፊነት በሚመጥን ደረጃ እንዲንቀሳቀሱ ክትትልና ቁጥጥር ይደረጋል፡፡ በመንግሰት መዋቅር ውስጥ የተደራጁ የፓርቲ መዋቅሮች በሙሉ ይፈርሳሉ፣ ወደ ፓርቲያቸው መዋቅር ፓርቲው በሚያዘጋጀው መስመር ይጠቃለላሉ፡፡
4.  የመከላከያ፣ የፖሊስ ሠራዊት እና የደህንነት መስሪያ ቤቶች ከፖለቲካ ፓርቲዎች ጋር ምንም ዓይነት ግንኙነት የሌላቸው መሆኑ ተረጋግጦ ማንኛውም አሸናፊ ፓርቲ ለሚመሰርተው መንግሰት በሚሰጠው መመሪያ መሰረት ህዝብን ማገልገል በሚችል መልኩ ተከታታይ ስልጠና እና የማውቅር ማሻሻያ ይደረጋል፡፡ በሁሉም ጊዜ የሀገርን ሉዓላዊነት ለማስጠበቅ በሚያስችለው ቁማና ላይ እንዲሆን ይደረጋል፡፡ የፖለቲካ ተሳትፎ ፍላጎት ያላቸው የሠራዊት አባላት በፈቃዳቸው ከስራቸው መልቀቅና በፖለቲካ ቀጥታ መሳተፍ ይችላሉ፡፡
5.  ልዩ ሁኔታ ካልተፈጠረ በስተቀር በሀገር ውስጥ የሚከናወኑ የፀጥታ ስራዎች በሙሉ በፌዴራልና ክልል ፖሊሶች ብቻ ይከናወናል፡፡ በአገሪቱ ልዩ ሀይል የሚባል አደረጃጀት በሙሉ ወደ ፖሊስና መከላከያ ይጠቃለላል፡፡
6.  የፍትህ ስርዓቱ ከማነኛውም የስራ አስፈፃሚ ተፅዕኖ ነፃ ሆኖ እንዲሰራ ይጠበቅበታል፡፡ ይህን ለማድረግ የሚያስችል የአቅም ግንባታና ድጋፍ በተከታታይ ይስጣል፡፡
ከዚህ በላይ የተቀመጡት ሃሳቦች በዋነኝነት የመንግሰት ሥልጣን የሚያዘው በህዝብ ይሁንታ መሆኑን ለማረጋገጥ፣ እየቀረበ ያለው ጥያቄ የሥልጣን በአቋራጭ የማግኘት ያለመሆኑን፣ መንግሥትን ከፖለቲካ ፓርቲ በመለየት የስርዓት ቀጣይነትን ለማረጋገጥ፣ ገዢው ፓርቲ በተሸናፊነት ሰሜት ሳይሆን በሃላፊነት ሰሜት እንዲንቀሳቀስ የሚጠበቅበት መሆኑን ለማሳየት፣ ሌሎች ኃይሎችም በጭፍን ምክር ቤት ይፍረስ፣ የሸግግር መንግስት ይቋቋም የሚሉትን የሁለት ወገን አሸናፊነት የማያሳይ መሆኑን ለማስጨበጥ፣ ወዘተ የሚረዱ ሰለሆነ በአገር ውስጥም ሆነ በውጭ የሚገኙ ሀይሎች በቅንንት ተመልክተው ሊቀበሉት ይገባል፡፡
ከላይ በቀረቡት የመነሻ የሰምምነት ሃሳቦች መግባባት ከተደረሰ ይህን መሰረት ያደረገ ለውጥ እንዲደረግ የሚከተሉት ወሳኝ ተግባራት መከናወን ይኖርባቸዋል፡፡
1.  አገር አቀፍ ጉባዔ ሊጠራ የሚችል በመንግሰት፣ በአገር ውስጥና በውጭ ከሚገኙ ሀይሎች ይሁንታ ያገኙ የጉባዔ ጠሪ ኮሚቴ ማወቀር፤
2.  በሕዝብ ዘንድ አመኔታ ያላቸው ዜጎች የሚወከሉበት ሀገር አቀፍ ኮንፈረንስ በአጭር ጊዜ እንዲጠራ ተደርጎ የሸግግር ስራዎችን የሚሰራ ኮሚሸን እንዲቋቋም ማድረግ፤
3.  የኮሚሸኑ አባላት በመንግሰትና በውጭም ሆነ በአገር ውስጥ በሚገኙ አካላት ተቀባይነት ያላቸው መሆናቸውን ማረጋገጥ፡፡
ዋና ዋናዎቹ ናቸው፡፡ እነዚህ ተግባራት በአጭር ጊዜ በማከናወን ገዢው ፓርቲ አሁን ከገባበት ምን አልባትም አገርን ሊበትን ከሚችል አዙሪት ለመውጣት መወሰኑን ያረጋግጣል፡፡
ይህ ኮሚሸን በዋነኝነት በአገሪቱ ወሳኝ የሆነውን ምቹ የፖለቲካ ምዕዳር ለመፍጠር ነው፡፡ ይህ ኮሚሽን የሚከተሉትን ዋና ዋና ተግባራት ማከናወን እንዲችል በህግ ስልጣን ይሰጠዋል፤ (የሚቀነስ የሚጨመር መኖሩ የሚታይ ነው፡፡)
·         በቀጣይ በአዲሰ አበባና ሌሎች አካባቢዎች ሊደረግ የታሰበውን ምርጫ እንዲራዘምና ከቀጣይ አገር አቀፍ ምርጫዎች ጋር በጋራ እንዲከናወን ያደርጋል፡፡
·         ለሀገራዊ መግባባት አስፈላጊ ናቸው ተብለው የሚታመንባቸው እስረኞች እንዲፈቱ፣ በውጭ የሚገኙ ማንኛቸውም የፖለቲካ ዓይሎች በነፃነት በሀገር ውስጥ ሰላማዊ እንቅስቃሴ እንዲያደርጉ ሁኔታዎችን ያመቻቻል፤ መንግሰት አጠቃላይ የምዕረት አዋጅ እንዲያውጅ ሃሣብ ያቀርባል፤
·         የመንግሰት ሚዲያዎች ለሁሉም የፖለቲካ ፓርቲዎች በህገ መንግሰት ድንጋጌ መሰረት ክፍት ይሆናሉ፡፡ የመንግሰት ሚዲያ ቦርድ አባላት ይህን በሚያረጋግጥ ሁኔታ እንደገና ይደራጃል፡፡
·         የግል ሚዲያ ተቋማት በህግ መስረት እንዲንቀሳቀሱ ምቹ ሁኔታ ይፈጥራል (በዘርና ሀይማኖት መሰረት ወይም ደግሞ ለኢትዮጵያዊነት ባህል ውጭ የሆኑት ላይ ተገቢውን ቁጥጥር ማድረግ እንደተጠበቀ ሆኖ)፤ በተቻለ መጠን ጋዜጠኞች መረጃ ከመስጠት በተጨማሪ ተጠያቂነት እንዲሰፍን የመረጃ ማግኘት ነፃነታቸው ይከበራል፤
·         ለነፃ ፖለቲካዊ እንቅስቃሴ እንቅፋት የሆኑ ህጎች ተለይተው እንዲሻሻሉ ወይም ተግባራዊ እንዳይሆኑ ያደርጋል፤
·         በፖለቲካ አስተምህሮ ላይ መስራት የሚፈልጉ ነፃ ሲቪል ማህበራት በተጠያቂነት ሰሜት እንዲንቀሳቀሱ እና ህዝቡ ስብዓዊና ዲሞክራሲያዊ መብቱን ለመጠቀም እንዲችል ድጋፍ እንዲያደርጉ ይደረጋል፡፡
·         በህገ መንግሰት የተፈቀደውን የዜጎች የመደራጀት መብት ሳይጋፋ የፖለቲካ ስልጣን ለመያዝ የሚወዳደሩ ፓርቲዎች ይህን ለማድረግ የሚየስችል አቅም ያላቸው መሆኑ ለማረጋገጥ ህግ ይወጣል በዚሁ መሰረት ተረጋግጦ ምዝገባ ይደረጋል፡፡ (ዝርዝሩ በህግ የሚወሰን ይሆናል) ይህን መስረት አድርጎ የፓርቲዎች ምዝገባ አዋጅ እንዲሻሻል ይደረጋል፡፡ አሁን ተመዝግበው ያሉ ፓርቲዎች የሚቀመጠውን ዝቅተኛ መስፈርት ማሟላታቸው ሲረጋገጥ ድጋሚ ምዝገባ ያደርጋሉ፡፡
·         የምርጫ ቦርድን ጨምሮ ሌሎች ተጠሪነታቸው ለምክር ቤት የሆኑ አካላት (አሁን ምክር ቤቱ በአንድ ፓርቲ የተያዘ መሆኑ ከግንዛቤ በማስገባት) አወቃቀራቸው ተቀባይነት እንዲኖረው ከማድረግ በተጨማሪ ሪፖርታቸውን ለህዝብና ለሚዲያ በይፋ ያቀርባሉ፤ ያቀረቡት ሪፖርት በማነኛውም አካል ይፋ ሆኖ ተዓማኒነቱ ይረጋገጣል፡፡
ከላይ የቀረበው ሃሳብ በዋነኝነት መንግሰት የዚህችን አገር ለብቻዬ ልፍታ ከሚል የተለመደ መንገድ እንዲወጣ፤ ተቃዋሚ ወገኖችም በሚፈጠረው ምቹ የፖለቲካ ምዕዳር ለአገራቸው የሚያስቡትን በጎ ነገር ሁሉ ለህዝብ በይፋ እንዲያቀርቡ፤ ወሳኙ ሕዝብ መሆኑን ሁሉም አካል ተቀብሎት አገራችን ወደ ዴሞክራሲያዊ ስርዓት ሸግግር በሰላም እንድታደርግ ለማድረግ ነው፡፡ በዚህ መነሻ ኃሣብ መሰረት መንግሥት ሌሎች ሁኔታውን ሊያሻሽሉ የሚችሉ ተጨማሪ ጉዳዮችን በመጨመር ለተግባራዊነቱ በይፋ መነሳት ይኖርበታል፡፡ ይህ ሲሆን አሁን በስልጣን ላይ ያሉትም ግለሰቦችም ሆነ ቡድኖች አገር የግላቸው እንደሆነ አድርገው ብቻቸውን ከመጨነቅ የሚወጡበት መንገድ እንደሆነ ይሰማኛል፡፡
ይህች አገር በአፋጣኝ ወደ ወሳኝ የፖለቲካ ምዕዳር ለውጥ ማሸጋገር ሳይቻል ቀርቶ አሁን በተያዘው ሁኔታ በሚደረጉ ጥገናዊ ለውጦችና ሠራዊት በመጠቀም በሚደረግ አፈና ከቀጠለ ወደማንወጣው ቀውስ ከመውሰድ የዘለለ ምንም ለውጥ ሊሆን የሚችል ነገር መጠበቅ አይቻልም፡
ግርማ ሠይፉ ማሩ
girmaseifu@gmail.com